በመሶብ የአንድ ማዕከል ከመደበኛ የሥራ ሰዓት በኋላና ቅዳሜ ቀን ለሚሠሩ ሠራተኞች፣ የትራንስፖርት አበል ክፍያ መፈጸም የሚያስችል መመርያ መፅደቁ ታወቀ።
በመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ከመደበኛ የሥራ ሰዓት ውጪና ቅዳሜ ለሚሠሩ ሠራተኞች የትራንስፖርት አበል አፈጻጸም መመርያ ቁጥር 1145/2018 በሚል ስያሜ፣ በሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽነር መኩሪያ ኃይሌ (ዶ/ር) በተጠናቀቀው ሰኔ ወር ተፈርሞ መውጣቱም ታውቋል።
ሪፖርተር የተመለከተው ሰነድ እንደሚያስረዳው፣ ኮሚሽኑ መመርያውን እንዲያወጣ አስፈላጊ ካደረጉት ምክንያቶች መካከል፣ በመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የሚሳተፉ የፌዴራል መንግሥት ተቋማት ሠራተኞች ከመደበኛ የሥራ ሰዓት በኋላና ቅዳሜ አገልግሎት በመስጠታቸው ምክንያት ተጨማሪ የመጓጓዣ ወጪ ስለሚገጥማቸው ነው።
ከዚህ ባለፈም የአገልግሎት ቀጣይነትን፣ የሠራተኞችን ደኅንነትንና የሥራ ተነሳሽነት ለማጠናከር ፍትሐዊ፣ ግልጽና ተግባራዊ የትራንስፖርት አበል አፈጻጸም ሥርዓት እንዲዘረጋ ለማድረግ አስፈላጊ በመሆኑ በሚል፣ ኮሚሽኑ በአዋጅ 1353/2017 በተሰጠው ሥልጣን መሠረት መመርያው እንዲወጣ ማድረጉም ተገልጿል።
በሰኔ ወር 2018 ዓ.ም. የፀደቀው መመርያው መሟላት ያለባቸውን ሒደቶች ለሚያሟሉ ሠራተኞች የትራንስፖርት መጓጓዣ አበል መጠን በወር ለአራት ቅዳሜ ቀናት 800 ብር፣ እንዲሁም ለ22 ቀናት የምሽት ሥራ 2,200 ብር በአጠቃላይ ወርኃዊ የሦስት ሺሕ ብር ተከፋይ እንደሚደረግ ያስረዳል።
መመርያው ተፈጻሚ የሚሆነው በመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት ዋና መሥሪያ ቤትና ቅርንጫፍ ማዕከላት ውስጥ ከመደበኛ የሥራ ሰዓት በኋላና ቅዳሜ አገልግሎት በሚሰጡ፣ ሁሉም የፌዴራል ተቋማት ሠራተኞች ላይ እንደሆነም ተደንግጓል።
ይሁንና መመርያው የትራንስፖርት አበል የማይከፈልባቸው ሁኔታዎችንም በዝርዝር አመላክቷል።
From The Reporter Magazine
በዚህም መሠረት በረጅም ጊዜ ሥልጠና ወይም ትምህርት ላይ ለሚገኝ ሠራተኛ፣ በተፈቀደው የሥራ መርሐ ግብር መሠረት በሥራ ላይ ላልተገኘ ሠራተኛ፣ ተቋሙ የጋራ ወይም በተናጠል ትራንስፖርት አገልግሎት ላቀረበለት ሠራተኛ፣ እንዲሁም በተመሳሳይ ዓላማ ከሌላ ምንጭ የመጓጓዣ ድጋፍ ለሚያገኝ ሠራተኛ ክፍያ አይፈጸምም።