የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም በተካሄደው ሰባተኛ አገራዊ ምርጫ፣ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምርጫ ከተደረገባቸው 501 የምርጫ ክልሎች ውስጥ 438 መቀመጫዎችን ብልፅግና ፓርቲ ማሸነፋን ተነገረ።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ዛሬ ሰኔ 14 ቀን 2018 ዓ.ም የጠቅላላ ምርጫ ውጤት ማሳወቂያ መርሀ ግብ በስካይ ላይት ሆቴል አካሂዷል።
ቦርዱ ምርጫ ካልተካሄደበት የትግራይ ክልልና ከአማራ ክልል 8 የምርጫ ክልሎች ውጭ ፣ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምርጫ ከተካሄደባቸው 501 የምርጫ መቀመጫዎች ውስጥ ብልፅግና ፓርቲ 438 መቀመጫዎችን ማሸነፋ የተገለፀ ሲሆን፣ ከፍተኛውን ማለትም 167 መቀመጫ በኦሮሚያ ክልል በማግኘት ማሸነፋ ተገልዿል።
በሀረሪ ክልል ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ካሉት ሁለት መቀመጫዎች ወስጥ ሁለቱንም መቀመጫዎች ብልፅግና ፓርቲ አሸንፏል ተብሏል።
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ካሉት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫዎች ውስጥ ሁለቱ ድጋሚ ምርጫ የሚደረግባቸው ሲሆን፣ ከቀሪዎቹ 33 መቀመጫዎች መካከል 26ቱን ብልፅግና፣ ኢዜማ 2፣ ትብብር ለኢትዮጵያ አንድነት 1፣ ነፃነትና እኩልነት 1 እና በረከት ማርቆስ የተባሉ የግል ተወዳዳሪ 1 መቀመጫዎችን ማግኘታቸው ተገልዿል።
በሲዳማ ክልል ሁለት የምርጫ ክልሎች የድጋሚ ምርጫ እንደሚደረግባቸውና አንድ የምርጫ ክልል ደግሞ ድጋሚ ቆጠራ የሚደረግበት ሲሆን፣ ከሶስቱ የምርጫ ክልሎች ውጭ በሆኑ 16 የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫዎች ውስጥ ብልፅግና 13ንና የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ 3 መቀመጫዎችን ማሸነፋቸውን ቦርዱ አስታውቋል።
በሶማሌ ክልል ምርጫ ከተካሄደባቸው 22 የምርጫ ክልሎች 16 መቀመጫዎችን ብልፅግና ፓርቲ ያገኘ ሲሆን፣ በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ካሉት 9 መቀመጫዎች ውስጥ 8ቱን ብልፅግና ፓርቲ አሸንፏል ተብሏል።
ከአማራ 130 የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫዎች ወስጥ 117፣ ከአዲስ አበባ 23 መቀመጫዎች 20፣ ከአፋር 8 መቀመጫዎች 7፣ ከ ኦሮሚያ 173 መቀመጫዎች 167፣ ከደቡብ ምዕራብ 20 መቀመጫዎች ወስጥ 17 ብልፅግና ፓርቲ ማሸነፋ በቦርዱ ተገልዿል።
ደቡብ ኢትዮጵያ ካሉት 45 መቀመጫዎች 35፣ ድሬደዋ ካሉት ሁለት መቀመጫዎች ሁለቱንም ፣ እንዲሁም የጋምቤላ ክልል ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ካሉት 3 መቀመጫዎች ሶስቱንም ብልፅግና እንዳሸነፈ ቦርዱ አስታውቋል።
