– “የዘመሙ አካሄዶች ሲታዩ በጊዜውና በወቅቱ ዕርምት ይደረግባቸዋል”
የኢትዮጵያ አገራዊ ምክክር ኮሚሽን
– 250ው ስልታዊ ቡድን አዲስ አበባና ድሬዳዋ የፌዴራል አካል ሆነው እንዲቀጥሉ መግባባት ላይ መደረሱ ተገልጿል
የአገራዊ የምክክር ጉባዔ በአጀንዳ ጭብጦች ላይ ገለጻና ማብራሪያ እንዲሰጡ የተመደቡ አመካካሪዎች፣ምሁራንና ቃለ ጉባዔ ያዦች፣ ተመካካሪዎች የሚያነሱትን ሃሳብ ባለመቀበልና በተለይ የመጡበትን ተቋም መሠረት ያደረገ አቋም በመያዝ፣ ተመካካሪዎች ሐሳብ እንዲቀይሩና የምክክር ሒደቱ እንዲዘገይ ተፅዕኖ እያሳደሩ መሆኑን ስማቸው እንዲገለጽ ያልፈለጉ ተመካካሪዎች ገለጹ
በተለይ መንግሥትን ወክለው የመጡ አመካካሪዎች እንደ የመንግሥት አደረጃጀትና አገር ግንባታ ያሉ አጀንዳዎችን በተመለከተ ከምክክሩ ሒደት ባፈነገጠ መልኩ የራሳቸውን ሐሳብ ማንፀባረቃቸውን ምንጮች ተናግረዋል።
የመንግሥት አደረጃደት አጀንዳን በተመለከተ እንዲያወያዩ በኮሚሽኑ የተመደቡ አመካካሪዎች በዚህ የተነሳ ለቀናቶች ውይይት እንዳይመሩና ማይክ ብቻ እንዲያቀብሉ በማድረግ፣ በእነርሱ ምትክ ደግሞ ከቡድን መሪዎች ተመርጠው ውይይት እንዲመሩ መደረጉን ገልጸዋል።
ከዚህ አልፎ የኮሚሽኑ አመካካሪዎች ውይይት እንዲመሩ የተደረገበት ሁኔታ መኖሩን ጨምረው ተናግረዋል። በዚህ የአጀንዳ ሐሳብ በተለይ የተለያዩ የፓርቲዎችን ወክለው የተገኙ ተመካካሪዎች የአመካካሪዎች አካሄድ በተመለከተ ቅሬታ አቅርበው ሁኔታው ከላይ በተገለጸው መንገድ እንዲመራ መደረጉን ተመካካሪዎቹ ተናግረዋል።
From The Reporter Magazine


በተለይ የተቋማት ግንባታን በተመለከተ፣ “ስለ ተቋም ግንባታ ለእኛ አትነግሩንም፣ የተቋም ግንባታ ምን መሆን እንዳለበት እናውቃለን፣ ተቋሙን የምንመራው እኛ ነን፣ ሪፎርም አድርገናል” ተቋማትን ወክለው የተገኙ ተመካካሪዎች መኖራቸውንም ገልጸዋል። በዚህ ምክንያት ተቆጥተው ውይይት ጥለው የወጡ ተመካካሪዎች እንደነበሩም አክለዋል።
አመካካሪዎች በሙስናና መልካም አስተዳደር አጀንዳ ሥር፣ ንዑስ አጀንዳ በሆነው የሙስና ጉዳዮች፣ በአንዳንድ ቡድኖች ከስምምነት እንዳይደረስና ለውይይት በተያዘለት ጊዜ እንዳይጠናቀቅ ማድረጋቸውንም ጠቁመዋል። በዚህ ምክንያት ሐሳብ ተንዛዝቶ ከመግባባት ለመድረስ እስከ ረቡዕ ሐምሌ 29 ቀን ድረስ ውይይት እንዲቀጥል ማስገደዱን አስረድተዋል።
From The Reporter Magazine
የፌዴራል ከተሞች አዲስ አበባና ድሬዳዋ ከተማን በተመለከተ የፅንሰ ሐሳብ ገለጻና ማብራሪያ እንዲሰጡ በኮሚሽኑ የተመደቡ ምሁራን (Panel of Experts)፣ በተለይ አዲስ አበባ የኦሮሚያ ክልል አካል ትሁን በሚለው የአጀንዳ ሐሳብ ፅንፍ በያዘ ሁኔታ መከራከራቸውን ጨምረው ገልጸዋል።
ሆኖም ይህን አካሄድ የተከተሉ ምሁራን ሰፊ ክርክር ከተደረገ በኋላ ይቅርታ መጠየቀታቸውን ተመካካሪዎቹ ጨምረው ተናግረዋል።
በቃለ ጉባዔ ያዥነት የተመደቡ አንዳንድ ባለሙያዎችም የቀረቡ ሐሳቦችን በሙሉ ያለማጠናከርና በፈለጉት መንገድ ብቻ የመሰነድ ችግር እንደተስተዋለባቸው ተናግረዋል። እነዚህ ቃለ ጉባዔ ያዦች የአንዱን ሐሳብ ይዘው የሌላውን የመተው አካሄድ መከተላቸው ተነግሯል።
በመሆኑም እንዲህ ያሉ ድርጊቶች አስፈላጊ እንዳልሆኑ፣ የምክክሩም ዓላማ ይህ እንዳልሆነ የገለጹት የመረጃ ምንጮቹ አሁን ያሉ ተቋማት ብቁ፣ ነፃና ገለልተኛ ሆነው የማይሰሩና የሚቀርቡ ጥያቄዎችን የመፍታት ከፍተኛ ችግሮች ስላሉባቸው፣ ውሃው እንዳይደርቅና አሳውም እንዳይሞት መታረምና መስተካከል እንዳለባቸው በአፅንኦት አሳስበዋል።
ኮሚሽኑም እንደዚህ አይነት ጉዳዮችን ጣልቃ ገብቶ በጊዜ እንዲታረሙ ማድረግ እንዳለበትም አስገንዝበዋል።
ይህን አጋጣሚ መጠቀም ካልተቻለ እንደ አገር የከፋ ችግር ሊመጣ እንደሚችል ከግምት ማስገባት ይገባል ሲሉም ጠቁመዋል።
የ250 ሥልታዊ ውይይትን በተመለከተ ለሪፖርተር አስተያየታቸውን የሰጡት የቁጫ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ፓርቲን ወክለው በምክክሩ እየተሳተፉ የሚገኙት አቶ ገነነ ገደቡ፣ እሳቸው እየተመካከሩ በሚገኙበት አጀንዳ ሥር በአሥር፣ በ50ና በ250 ውይይት የተደረገባቸው ሐሳቦች ወደ መግባባት የሚያመጡ ሁኔታ ላይ እንደተደረሰባቸው ተናግረዋል።


እሳቸው ባሉበት የአጀንዳ ቡድን ውስጥ ማንነትና ራስን ማስተዳደር በተመለከተ የሚቀርቡ የሕዝብ ጥያቄዎች፣ የፖለቲካ ገለልተኝነት በሌለውና ነፃ ሆኖ ወደፊት በሚቋቋም ኮሚሽን መልስ እንዲሰጣቸው ከመግባባት መደረሱን ጠቁመዋል።
በዚህ አጀንዳ ሥር የሥራ ቋንቋን በተመለከተ በተደረጉ ውይይቶች ምልክትን ጨምሮ እስከ አሥር የሚደርሱ ሌሎች ቋንቋዎች መቅረባቸውን፣ በዚህም አማርኛ፣ ኦሮሚኛ፣ ትግርኛ፣ አፋርኛ፣ ሶማሊኛ ቋንቋዎች የሥራ ቋንቋ እንዲሆኑ ከመግባባት መደረሱን ተናግረዋል።
“ቋንቋ የመግባቢያ መሳሪያ ብቻ ነው” የሚለው አገላለጽ ቀርቶ፣ የማንነት ጉዳዮች በስፋት ተሸካሚ ስለሆነ ማስተካከተያ እንዲረግበት ዕርምት መወሰዱን ገልጸዋል።
የብሔራዊ ቋንቋ ጉዳዩ በውይይት ወቅት አጨቃጫቂ እንደነበር፣ የፌዴራል የሥራ ቋንቋ ከሆነው አማርኛ በተጨማሪ ኦሮሚኛ ቋንቋም ብሔራዊ ቋንቋ ይሁን የሚል ሐሳብ ቀርቦ እንደነበር፣ ካለው አገራዊ ተጨባጭ ነባራዊ ሁኔታ አንፃር አማርኛ የሥራ ቋንቋ ሆኖ እንዲቀጥል፣ እንዲሁም ብሔራዊ ቋንቋ እንዲሆን በሥልታዊ ቡድን ውይይት በአብዛኛው ከመግባባት መደረሱን ጠቅሰዋል።
ሆኖም ብሔራዊ ቋንቋ የሚለው ብሔር የሚል ቋል ያለበት ስለሆነ፣ ወደፊት አጨቃጫቂ ሊሆን ስለሚችል ብሔራዊ ቋንቋ አይኑር የሚል ሐሳብ ቀርቦ እንደነበርም ጨምረው ገልጸዋል።
አጨቃጫቂ ታሪኮች፣ ባሕሎች፣ ቅርሶችና ሐውልቶች ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ሁሉም ባለድርሻ አካል ባሉበት በገለልተኛ አካል በልዩ ሁኔታ እንዲጠኑና እንዲመለሱ ሙሉ ለሙሉ ከመግባባት መደረሱን አመላክተዋል።
ለአብነት ሰፊና አጨቃጫቂ ውይይት ከደተረገባቸው ታሪካዊ ጉዳዮች መካከል የካራማራ ድል አንዱ መሆኑን፣ በዚህም ትኩረት ተሰጥቶት እንዲከበር እንዲደረግ ከሶማሌ ክልል ተወካዮች ሰፊ ሐሳብ መቅረቡን ተናግረዋል።
የሰንደቅ ዓላማ ጉዳይን በተመለከተ አሁን ያለው ይቀጥል፣ አረንጓዴ፣ ቢጫ ቀይ የሆነው፣ ቀይ፣ ቢጫና አረንጓዴ ሆኖ ይስተካከል፣ አሁን ያለው ሆኖ ከመኃል ያለው ዓርማ ይቀየር፣ እንዲሁም አሁን ያለው ዓርማው በሌላ ይተካ የሚሉ ሐሳቦች መቅረባቸውን፣ ሆኖም አሁን ያለው እንዲቀጥልና ዓርማው እንዲቀየር የሚሉ ሁለት ሐሳቦች በአብዛኛው ተመካካሪ ከመግባባት የተደረሰባቸው መሆኑን አስረድተዋል።
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባሉና የፌዴራል ተቋማትን ወክለው በምክክሩ እየተሳተፉ እንደሆነ የገለጹልን አብርሃም በርታ (ዶ/ር) ፣እሳቸው በነበሩት የአጀንዳ ቡድን ሥር በአሥር፣ በ50 አባላት በተደረጉ ውይይት የተለያዩ የልዩነት ሐሳቦች ሲቀርቡ መቆየታቸውና በሥልታዊ ቡድን ደረጃ ከመግባባት ለመድረስ የተደራጀ ሐሳብ ላይ መደረሱን ገልጸዋል።
በዚሁ ረገድ የአዲስ አበባ ከተማ የባለቤትነት ጉዳይ ትልቁ ትኩረት የተሰጠው ጉዳይ እንደነበር፣ በዚህም አዲስ አበባ የፌዴራል መንግሥት አካልና ዋና መቀመጫ ከተማ እንድትሆን ከመግባባት መደረሱን ተናግረዋል።
ከአዲስ አበባ በተጨማሪ ሌሎች የፌዴራል ከተሞች እንዲኖሩ ሰፊ ምክረሐሳብ መቅረቡን፣ ለዚህም ደቡብ አፍሪካ እንደ ምሳሌ መቅረቧን ተናግረዋል።
አዲስ አበባ ከተማ የራሷ የሆነ ጠቅላይ ፍርድ ቤት፣ የተጠናከረ የፖሊስ ኮሚሽን እንዲኖራትና በከተማዋ ውስጥ የሚሰየሙ የሰፈር ስሞች የአገር አንድነትንና የሁሉንም ማኅበረሰብ ውክልና እንዲኖራቸው ከመግባባት መደረሱን ተናግረዋል።
የፌዴራል የሥራ ቋንቋ የሆነው አማርኛ ቋንቋ የአዲስ አበባ የሥራ ቋንቋ ሆኖ እንዲቀጥል ከመግባባት መደረሱን ተናግረዋል። ሆኖም አማርኛ፣ ኦሮሚኛና፣ ትግርኛ፣ አፋርኛና ሶማሊያ የፌዴራል የሥራ ቋንቋዎች ከሆኑ የአዲስ አበባም እንዲሆኑ ሐሳብ መኖሩን ጠቁመዋል።
ዜጎችን ከዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ጋር ለማገናኘት በተለይ የእንግሊዝኛ ቋንቋን በተመለከተ በሰፊው መሠራት እንዳለበት ምክረሐሳብ መቅረቡን አስረድተዋል።
ከድሬዳዋ ጋር በተገናኘ አሁን ያለው የ40/40/20 የአስተዳደር ሥርዓት ቀርቶ የፌዴራል አካል የሆነች ከተማ እንድትሆን በአብዛኛው ተመካካሪ ከመግባባት መደረሱን ገልጸዋል።
ድሬዳዋ የኦሮሚያና የሶማሌ ክልሎች ተጠሪ ትሁን የሚሉ ሐሳቦች እንደነበሩ፣ ሆኖም በውስጧ የሚገኘውን ብዙኃነት ለማስጠበቅና ለማስቀጠል የፌዴራል ተጠሪ ብትሆን የበለጠ አዋጭ ይሆናል የሚለው ሐሳብ ገዢ ሆኖ በሥልታዊ ቡድን ደረጃ ከመግባባት እንደተደረሰበት አመላክተዋል።
አገር የሚገነባው እየተደረገ ባለው ምክክር መልኩ መሆኑን የገለጹት አብርሃም (ዶ/ር)፣ የምክክር ኮሚሽን የተወሰኑ ችግሮችን ይፈታል ብለው እንደሚጠብቁ ገልጸዋል። ቀሪ ጉዳዮችን ደግሞ በቀጣይ ትውልድ እንዲስተካከሉ ያደርጋል ብለው እንደሚያስቡ ገልጸዋል።
እነዚህ ሐሳቦች በሥልታዊ ቡድን በተደረጉ ውይይት ከመግባባት የተደረሰባቸው መሆኑን የገለጹት ተመካካሪዎቹ፣ ለ500 ዎቹ ቡድኖች እንደሚቀርቡ፣ ውሳኔም ያን ጊዜ እንደሚሰጥባቸው ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ አገራዊ ምክክር ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር መስፍን አርዓያ (ፕሮፌሰር)
ሐምሌ 8 ቀን 2018 የተጀመረውን አገራዊ ምክክር ጉባዔ ወቅታዊ ሁኔታ በመለከት ሐምሌ 29 ቀን 2018 ዓ.ም በሰጡት መግለጫ፣ አንዳንድ ሐሳቦችን በተመለከተ ምላሽ ሰጥተዋል።
በምክክሩ ጉባዔ 160 አመካካሪዎች መኖራቸውንና የታሰበውን ሚና በአግባቡ እየተወጡ ነው ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።
ሆኖም እሳቸውንም ጨምሮ በሌሎች አመካካሪዎች ዘንድ አልፎ አልፎ ማጋደል ከታየ እንደማይፈረድባቸው ተናግረዋል።
በአመካካሪዎች፣ በምሁራን፣ በኮሚሸነሮችና በሌሎች ባለሙያዎች በዚህ መንገድ ሒዱ የሚል ሐሳብ ተሰጥቶ ከሆነ ልክ አለመሆኑን፣ ሁኔታውም በትክልል እየተጣራ መሆኑንና አልፎ አልፎ የዘመሙአካሄዶች ሲታዩ በጊዜውና በወቅቱ ዕርምት እንዲደረግባቸው እንደሚደረግ አስረድተዋል። ኮሚሽኑ ከአመካካሪዎችና ገለፃ ከሚሰጡ ምሁራን ጋር በየጊዜው ግምገማ እንደሚያደርጉም ተናግረዋል።
በተመሳሳይ 160 ያህል ቃለ ጉባዔ ያዦች በፍርድ ቤቶች፣ ዩኒቨርስቲዎች፣ በትምህርት ቤቶች የሰሩ ልምድ ያላቸው በመሆናቸው የሚሰሩትን በሚገባ እንደሚያውቁ ገልጸዋል።
እነዚህ ተመካካሪዎች ንግግር የሚደረግባቸውን እያንዳንዷን ነጥብ እንደሚይዙና ለወደፊት በሚገባ ተሰንዶ ለተመራማሪዎች፣ ለምሁራን፣ ለተማሪዎች፣ ለፖሊሲ አውጪዎች፣ ለየክልልና ፌዴራል መንግሥታት የሚጠቅሙ ሰነዶችን እንደሚያዘጋጁ ገልጸዋል።
ቃለ ጉባዔ ያዦች የራሳቸውን ወይም ሌሎች የሰጧቸውን ሐሳብ ጨምረው ያቀርባሉ የሚል ዕምነት እንደሌላቸው፣ ምናልባት ግን ይህን ያደረጉ አንድ ወይም ሁለት ተከስተው ከሆነ፣ በምክክሩ እየተሳተፉ ያሉ 160ዎቹ ሁሉ ሊወቀሱ እንደማይገባ ተናግረዋል። ሆኖም ኮሚሽኑ ስህተቶችን ከስር ከስር እየተከታተለ ዕርምት እንሚወስድ ጠቁመዋል።
ኢትዮጵያን ማዕከል ያደረገ ውይይት እየተደገ መሆኑን፣ በዚህም ማንም በማንም ዘንድ ጫና ማሳደር እንደሌለበት ዋና ኮሚሽነሩ ገልጸዋል።
ተመካካሪዎች የሚያነሷቸውን ሐሳቦች የሚያሳንሱ አንዳንድ የስነምግባር ጥሰቶች መስተዋላቸውን የገለጹት ዋና ኮሚሽነሩ፣ ለወደፊት በስብሰባ ስነምግባር መመርያ መሠረት የዕርምት ዕርምጃ እንደሚወሰድ ጠቁመዋል።
በሥልታዊ ቡድን ደረጃ እየተደረገ ባለው ውይይት ወደ መግባባት የሚወስዱ ምክረሐሳቦች የታዩ ይመስላሉ ሲሉም በመግለጫቸው ገልጸዋል።
ሌሎቹ ሐሳቦች ደግሞ ማጥራት እንደሚፈልጉ፣ ለዚያም የፈጀውን ጊዜ ፈጅቶ ወደ ዋናው የቡድን ውይይት መገባት እንዳለበት ተናግረዋል።
አንዱ በአንዱ ላይ ጫና ሳያሳድር ሁሉምን ወደ አንድ ማዕከል በሚያመጣ ምክረሐባ ከመግባባት እንዲደረስ የሚመለከተው ሁሉ የበኩሉን እንዲወጣ መስፍን (ፕሮፌሰር) ጥሪ አቅርበዋል።