- ትክክለኛ ማስረጃ ለሚያቀርቡ ሃምሳ በመቶ ይቀነስላቸዋል›› ዩኒቨርሲቲው
የኮተቤ ትምህርት ዩኒቨርሲቲ ከ30 ዓመት በላይ በዘለቀው በማኅበረሰባዊ አገልግሎት አሠራሩ መሠረት፣ በተለያዩ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ባልሆኑ ተቋማት ያገለገሉ ባለውለተኞችና የአካባቢው ነዋሪዎች የስፖርት ማዘውተሪያ ጂምናዚየሙን በዝቅተኛ ዋጋ ሲጠቀሙበት ነበር፡፡
በቅርቡ ዩኒቨርሲቲው በተከተለው አዲስ አሠራር ቀደም ሲል በአንድ ሰው ይጠየቅ የነበረውን የ100 ብር ክፍያ ወደ 2,000 ብር ማሳደጉን አስታውቋል፡፡ በዩኒቨርሲቲው አካባቢ የሚገኘው ተጠቃሚ ማኅበረሰብ ግን በሃያ እጥፍ የተደረገውን ጭማሪ ላይ ቅሬታውን አሰምቷል፡፡
የተደረገውን የዋጋ ጭማሪ በተመለከተ ቅሬታቸውን በጽሑፍ ለሪፖርተር ያቀረቡ የአካባቢው ማኅበረሰብ ነዋሪዎችና ባለውለተኞች፣ የኮተቤ ትምህርት ዩኒቨርሲቲ ያደረገው ጭማሪ የመክፈል አቅማቸውን ያላገናዘበ ነው ብለዋል፡፡
የሪፖርተር ዝግጅት ክፍል የተመለከተውና 80 የአካባቢው ነዋሪዎችና ባለውለተኛ ሠራተኞች ተፈራርመው ለዩኒቨርሲቲው ያስገቡት ጽሑፍ እንደሚያመለክተው፣ ዩኒቨርሲቲው ከ1988 ዓ.ም. ጀምሮ ለሦስት አሠርታት ከሰጣቸው የማኅበረሰብ አገልግሎቶች ውስጥ፣ ለአካባቢው ማኅበረሰብ በተለይም ተላላፊ ባልሆኑ ሕመሞች ተጋላጭ ለሆኑ ባለውለታ የዕድሜ ባለፀጋ እናቶችና አባቶች እንደ መድኃኒት የሚጠቀሙበት የጤና ስፖርት መሥሪያ አዳራሽ በመፍቀድ ለተገልጋይ የአካባቢው ነዋሪዎች ባለውለታነቱን ሲያረጋግጥ ቆይቷል፡፡
ቀደም ሲል ይህንን አገልግሎት ወደ ግል የገቢ ምንጭ መለወጥ የሚፈልጉ ግለሰቦች እንደነበሩ የሚገልጸው የቅሬታ አቅራቢዎቹ ጽሑፍ፣ በወቅቱ የነበሩ የዩኒቨርሲቲው ማኔጅመንት አባላት ማኅበረሰባዊ አገልግሎት መስጠት ታላቅ ተግባር መሆኑን ከግምት በማስገባት፣ ለብዙ ዓመታት ለተሳትፎ ያህል እያንዳንዱ ተገልጋይ በወር 100 ብር ሲከፍል የነበረ መሆኑ፣ ይህ ወደ ኋላ ላይ ለዩኒቨርሲቲው የሚኖረው ድጋፍ ብዙም የሚጠቅም ባለመሆኑና ይህንኑ መክፈል የሚቸገሩ ተገልጋዮች መኖራቸውን በማገናዘብ ያለ ምንም ክፍያ በአዳራሹ ለአሠሪዎች አነስተኛ ክፍያ በመክፈል ገንዘቡም በየጊዜው በሚመረጡ የሒሳብ ባለሙያዎች ኦዲት እየተሠራ ማኅበረሰባዊ አገልግሎቱን ላለፉት 30 ዓመታት ሲያገኙ መቆየታቸው ያስረዳል፡፡
‹‹መንግሥት የከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የገቢ ምንጭ እንዲፈጥሩ አቅጣጫ አስቀምጧል፡፡ ቢሆንም የአካባቢው ማኅበረሰብ ሊሸከመው የማይችለውን ክፍያ መጠበቅ ግን ከንቱ ምኞት ነው፤›› ሲል የሚቀጥለው የቅሬታ አቅራቢዎቹ ደብዳቤ፣ ‹‹ከ30 ዓመታት በላይ ያለ ማቋረጥ የጂም ቤቱ ለማኅበራዊ አገልግሎት እየዋለ፣ አልፎ አልፎ በግለሰቦች መካከል አለመግባባቶች መፈጠራቸው የነበረ ቢሆንም፣ የተፈጠረውን ክፍተት ለግል ፍላጎት ሲሉ የሚያባብሱ ክፍሎች የነበሩና በተገልጋዩና አልፎ አልፎም በዩኒቨርሲቲው አመራሮች መፍትሔ እየተቀመጠለት የጂም አገልግሎቱ ሳይቋረጥ ቆይቷል፤›› ሲል ያስረዳል፡፡
ግለሰቦች ጂምናዚየሙ ሲሰጠው የቆየው ማኅበረሰባዊ አገልግሎት እንዲቋረጥ ለዩኒቨርሲቲው ያቀረቡበት ሁኔታ የነበረ ቢሆንም፣ በጂምናዚየሙ የሚጠቀሙ የማኅበረሰብ አባላት በተወካዮቻቸው አማካይነት እውነታውን ለዩኒቨርሲቲው አስተዳደር እንዲገነዘብና የጂም አገልግሎት እንዲጀመር በ24/04/2018 ዓ.ም. ጠይቀው የነበረ ቢሆንም፣ ይህ ጉዳይ የሚመለከተው የዩኒቨርሲቲው የስፖርት ሳይንስ ፋካልቲ በሚያቀርበው ፕሮፖዛል እንዲመሠረት ተደርጎ መቆየቱን ጭምር ያትታል፡፡
From The Reporter Magazine
በጂምናዚየሙ ተጠቃሚዎች የነበሩት የአካባቢው ማኅበረሰብ አባላት ብዙዎቹ በጡረታ ላይ ያሉ፣ የቤት እመቤቶች፣ የዕድሜ ባለፀጋዎችና ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች የተያዙ፣ እንዲሁም በወር ገቢ የሚተዳደሩ የመንግሥት ሠራተኞች በመሆናቸው የገቢ ምንጫቸው በዚያው ልክ አነስተኛ ስለመሆኑ ጭምር በጽሑፍ ተካቷል፡፡
ጭማሪውን የሚመለከተው መመርያ ከመፅደቁ በፊት የማኅበረሰቡ ተወካዮችና በዩኒቨርሲቲው ማኔጅመንት መካከል ተደጋጋሚ ውይይቶች ተደርገው፣ በአቤቱታው መሠረት የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ጉዳዩ እንደሚታይ ቃል ቢገቡም አልተተገበረም፡፡ በዩኒቨርሲቲው ስፖርት ፋካልቲ አማካይነት በከፍተኛ አመራሮች የፀደቀው የጂሙ ክፍያ እያንዳንዱ ተገልጋይ በወር ከ100 ብር፣ በአንድ ጊዜ ወደ 2,000 ብር ከፍ ተደርጎ መክፈል እንደሚጠበቅበት ደንግጓል፡፡ ይህም አባላቱን ቅር ከማሰኘቱም ባሻገር የማኅበረሰብ አባላቱ መበተን ብቸኛው አማራጭ እንደሆነባቸው ጭምር ጽሑፍ ያብራራል፡፡
‹‹መንግሥት ባስቀመጠው አቅጣጫ ዩኒቨርሲቲው የራሱን የገቢ ምንጭ ማሳደግ እንዳለበት እንገነዘባለን፤›› የሚለው የቅሬታ አቅራቢዎቹ ደብዳቤ፣ ‹‹ከ30 ዓመታት በላይ ሲያገለግለው የነበረን የማኅበረሰብ ክፍል የመክፈል አቅሙ ባለመፍቀዱ ብቻ ‹መበተን› ከገንዘብ ባሻገር የሞራል ጥያቄም ነውና ዩኒቨርሲቲው ችግሩን በማጤን የመኖር ያለመኖር ጉዳይ የሆነውን የጤና ስፖርት ፕሮግራም መዝጋት አግባብነት የለውም፤›› ይላል፡፡
From The Reporter Magazine
የቅሬታ አቅራቢዎቹን ደብዳቤ መነሻ በማድረግ ሪፖርተር ያነጋገራቸው በኮተቤ ትምህርት ዩኒቨርሲቲ የሰውነት ማጎልመሻና ስፖርት ኢንስትቲዩት ዲን ጥላሁን በረደድ (ዶ/ር)፣ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ ጂምናዚየሙ ለአካባቢው የማኅበረሰብ ክፍሎች አገልግሎት ሲሰጥ የቆየ ቢሆንም፣ ዩኒቨርሲቲው አሁን ላይ አዳዲስ አሠራሮች ለመተግበር ደንቦችንና መመርያዎችን ማዘጋጀት በማስፈለጉ የዩኒቨርሲቲው የማዘውተሪያ ሥፍራ (ጂምናዚየም) ክፍያን በተመለከተ አዲስ አሠራር መዘርጋቱን ገልጸዋል፡፡ ጂምናዚየሙን ጨምሮ የዩኒቨርሲቲው ማዘውተሪያ ሥፍራዎች ከዚህ በፊት የማዘውተሪያ ሥፍራ አስተዳደርና አጠቃቀም መመርያ እንዳልነበራቸው የሚናገሩት ጥላሁን በረደድ (ዶ/ር)፣ ‹‹ቀደም ሲል የነበረውን ክፍያ ያለው መረጃ የሚያሳየው የፋይናንስ ሥርዓትን ያልተከተለ፣ ገንዘቡ አንዳንዴ በዩኒቨርሲቲው ሌላ ጊዜ ደግሞ በግለሰቦች የሚሰበሰብ ሆኖ ነው የተገኘው፤›› ይላሉ፡፡
ከዩኒቨርሲቲው የፋይናንስ ሥርዓት ጋር ተያይዞ መመርያ መዘጋጀት እንዳለበት ያስፈለገበት አንዱና ዋነኛው መነሻ ደግሞ፣ የክፍያ መጠን ለማሻሻል እንደሆነ የሚናገሩት ኃላፊው፣ ይህም የዩኒቨርሲቲው ጂምናዚየም በአዲስ አደረጃጀት ራሱን እንዲችል በሚል መነሻ የቀረበ ነው፡፡ ይህ ማለት ግን በጂምናዚየሙ ቅሬታ አቅራቢዎቹ እንዳሉት ‹‹ንግድን ታሳቢ ያደረገ ሳይሆን፣ በጂምናዚየሙ የሚገኘው የክፍያ መጠንም የፋይንናስ አሠራር ሥርዓትን የተከተለ መሆን ይችል ዘንድ በማሰብ ነው፤›› ብለዋል፡፡
የኢንስትቲዩቱ ዲን ‹‹ቀደም ሲል የነበረውን ክፍያ መጠን ዩኒቨርሲቲው በውል አያውቀውም፡፡ ምክንያቱ ደግሞ በወቅቱና በጊዜው ዩኒቨርሲቲው የጂምናዚየሙን ገቢ በተመለከተ ግልጽ የሆነ የፋይናንስ ሥርዓት መመርያ ስላልነበረው ነው፡፡ አሁን ግን መመርያ ተዘጋጅቶ ተፈጻሚ እንዲደረግ የተፈለገው የነበረውን ክፍተት ወደ ሥርዓት ለማስገባትና ጂምናዚየሙም ለትርፍ ሳይሆን፣ በተመጣጣኝ ዋጋ የሚጠበቅበትን አገልግሎት እንዲሰጥ ለማድረግ ነው፤›› ቢሉም፣ የጂምናዚየሙ ተጠቃሚ የአካባቢው ነዋሪዎች ቅሬታቸውን ለሪፖርተር ያቀረቡት ደብዳቤ እንደሚያመለክተው ከሆነ፣ ‹‹የተጠቃሚዎቹ ጥያቄ ክፍያው ሥርዓት ባለው መልኩ መፈጸም የለበትም ሳይሆን፣ የክፍያ መጠኑ በዝቶብናልና የመክፈል አቅማችንን ያገናዘበ አይደለም፤›› የሚል ነው፡፡
የኢንስትቲዩቱ ዲን ለዚህ የሰጡት መልስ፣ ‹‹እውነት ነው፡፡ ስለዚሁ ጉዳይ ቅሬታ አቅራቢዎቹ በተወካዮቻቸው በኩል ከእኔ ጋር ተደጋጋሚ ውይይቶችን አድርገናል፡፡ ገቢው የፋይናንስ ሥርዓት በተከተለ መልኩ መሄድ እንዳለበትና ትክክለኛም እንደሆነ ያምናሉ፡፡ ይህ በተገናኘንባቸው መድረኮች ላይ በተደጋጋሚ ያረጋገጡልኝ ጉዳይ ነው፡፡ ጥያቄያቸውም ግልጽ ነው፡፡ የክፍያው መጠን ከአቅማቸው ጋር የሚጣጣም ስላልሆነ ታሳቢ እንዲደረግላቸው ነው፡፡ ነገር ግን የዩኒቨርሲቲው ማኔጅመንትና አመራሮች ደግሞ በሌሎች ተቋማት ካለው የጂምናዚየም ክፍያ አንፃር፣ ጭማሪው በጣም አነስተኛና ተመጣጣኝ ነው በሚል የተገልጋዮችን አቅም ከግምት ያስገባ መሆኑ ታምኖበት የክፍያ መመርያው ተግባራዊ እንዲደረግ በዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ፊርማና ማኅተም ውሳኔ ያገኘ ጉዳይ ነው፤›› ብለው፣ ይህ ማለት ግን የሁሉም ተገልጋዮች ቅሬታና አቤቱታ ዝግ ሆኗል ማለት እንዳልሆነ አልሸሸጉም፡፡
ጂምናዚየሙ ለትርፍ እንኳ ባይሆን ራሱን እንዲችል ለማድረግ ክፍያው ተመጣጣኝና የመክፈል አቅምን ያገናዘበ መሆኑ ቢታመንበትም፣ ነገር ግን ደግሞ ለዚህ አቅማቸው የማይፈቅድላቸው ተገልጋዮች ካሉ ትክክለኛ ማስረጃ ለሚያቀርቡ ተገልጋዮች ሃምሳ በመቶ ቅናሽ የሚደረግላቸው ስለመሆኑ ጭምር የኢንስትቲዩቱ ዲን ጥላሁን በረደድ (ዶ/ር) ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
