
ለዓለም ገበያ ከሚቀርበው ምርት ውስጥ 90 በመቶው በመርከብ ይጓጓዛል፡፡ የባህር ትራንስፖርት ከቆመ ወይም ለጥቂት ጊዜ ከተስተጓጎለ ገበያው ብቻ ሳይሆን፣ መላው የዓለም ኢኮኖሚ በእጅጉ ይንኮታኮታል፡፡ ወደ 40 ቀናት ባስቆጠረውና ማክሰኞ መጋቢት 29 ቀን 2018 ዓ.ም. ሌሊት ለሁለት ሳምንታት በሚቆይ የተኩስ አቁም ስምምነት ጋብ ያለው የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት የዓለምን ንግድ እንቅስቃሴ በከባዱ አስተጓጉሎታል፡፡


የፋርስ ባህረ ሰላጤው አገሮች በየቀኑ ለዓለም የሚቀርበውን 20 በመቶ ወይም 20 ሚሊዮን በርሜል ነዳጅ ዘይት የሚያቀርቡ አገሮች ናቸው፡፡ ከእነዚህ አገሮች የሚገኘው ነዳጅ በኢራንና በኦማን ጫፍ መካከል በሚገኘው፣ በጠባቡ ሆርሙዝ የባህር መተላለፊያ ሰርጥ አልፎ ነው ለገበያ የሚቀርበው፡፡ እስራኤልና አሜሪካ በጋራ ሆነው በኢራን ላይ ጦርነቱን በጀመሩ በጥቂት ቀናት ልዩነትም፣ ኢራን ይህን ከ38 ኪሎ ሜትር የማይሰፋ ጠባብ የባህር መስመር ዘግታዋለች፡፡ የባህር መተላለፊያውን በፈንጂ ጭምር ያጠረችው ሲሆን፣ ለመረጠቻቸው አገሮች መርከቦች ብቻ ስትከፍት ቆይታ ወዲያው ደግሞ በመርከብ ሁለት ሚሊዮን ዶላር ቀረጥ በማስከፈል መርከቦችን ስታሳልፍ ሰንብታለች፡፡
የጦርነቱን መቀስቀስ ተከትሎ የሆርሙዝ ሠርጥ በመዘጋቱ ወደ 20 በመቶ የዓለም ፈሳሽ ጋዝ አቅርቦትም ተቋርጧል፡፡ ኢራንና ኳታር የዓለማችን ግንባር ቀደም የፈሳሽ ጋዝ አቅራቢ አገሮች ሲሆኑ፣ ሌሎቹ የአካባቢው አገሮች የሚያቀርቡት ተዳምሮ ለዓለም ገበያ በየቀኑ ከሚቀርበው ውስጥ 20 በመቶው ተቋርጧል፡፡ ይህን ተከትሎ የዓለም የነዳጅና ጋዝ ገበያ ዋጋ በከፍተኛ ደረጃ አሻቅቧል፡፡
የዓለም አቀፉ የኢነርጂ ኤጀንሲ ዋና ኃላፊ ፋቲህ ቢሮል ሲናገሩ፣ ‹‹ዓለም ካጋጠሟት የኢነርጂ ገበያ ውድቀቶች የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት አመጣሹ የገበያ መናጋት ታይቶ የማይታወቅና ከባዱ ነው፤›› ይላሉ፡፡ ኃላፊው እንደሚናገሩት እ.ኤ.አ. በ1973 ወይም በ1979 ያጋጠሙት የዓለም ነዳጅ ገበያ ቀውሶች፣ ለዓለም ገበያ ይቀርብ ከነበረው የነዳጅ ምርት አምስት ሚሊዮን በርሜል እንዲቋረጥ ነው ያደረጉት፡፡
‹‹ሩሲያ ዩክሬንን ስትወር ለዓለም ገበያ ይቀርብ ከነበረው 75 ቢሊዮን ሜትር ኪዩብ ነዳጅ ነው የተቋረጠው፡፡ የቀደሙት ሁለት ክስተቶችና የሩሲያና የዩክሬን ጦርነት የገበያ ቀውሶች ተደምረው፣ አሁን ያጋጠመውን ያህል የኢነርጂ ቀውስ አልፈጠሩም፡፡ በአሁኑ ቀውስ ለዓለም ገበያ ከሚቀርበው ነዳጅ 140 ቢሊዮን ሜትር ኪዩብ ነው የተቋረጠው፤›› ሲሉ የተናገሩት ፋቲህ፣ ይህ ጦርነት ታይቶ የማይታወቅ የኢነርጂ ገበያ ቀውስ መፍጠሩን ጠቁመዋል፡፡ ይህ የሆነው በሆርሙዝ ባህር መተላለፊያ መዘጋት ብቻ እንዳልሆነ የጠቆሙት ኃላፊው፣ በጦርነቱ ምክንያት በባህረ ሰላጤው አገሮች ወደ 40 የነዳጅና ተፈጥሮ ጋዝ ኢንዱስትሪዎች ላይ በከፊል ወይም ሙሉ ለሙሉ ጉዳት መድረሱ ችግሩን እንዳከፋው ገልጸዋል፡፡
የሆርሙዝ ባህር መተላለፊያ የዓለም የኢነርጂ ገበያን አዛብቶታል፡፡ የነዳጅ ዘይትና የተፈጥሮ ጋዝ ዋጋ በከፍተኛ ደረጃ አሻቅቧል፡፡ ከጦርነቱ በፊት በበርሜል ከ70 ዶላር በታች ይሸጥ የነበረው ነዳጅ ጦርነቱ እየተጠናከረ ሲመጣ ግን በአንዴ ከመቶ ዶላር በላይ አሻቅቧል፡፡ የነዳጅ ዋጋ ሲጨምር በመላው ዓለም የሸቀጦች ገበያ አለመረጋጋትና የዋጋ ንረትን የሚያስከትል በመሆኑ፣ ከአፍሪካ እስከ አሜሪካ፣ ከእስያ እስከ አውሮፓ በሁሉም የዓለም ክፍል የገበያ አለመረጋጋት ሲስተዋል ነበር፡፡
From The Reporter Magazine
ይሁን እንጂ የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት ያስከተለው የሆርሙዝ ሰርጥ መዘጋት፣ የኢነርጂ ምርቶች ገበያን ብቻ አይደለም ያናጋው፡፡ ዓለም አቀፉ የምግብ ፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት (International Food Policy Research Institute-IFPRI) የባህረ ሰላጤው ቀጣና ከፍተኛ የማዳበሪያ ምርት ለዓለም ገበያ የሚያቀርብ መሆኑን ያስረዳል፡፡ በተለይ የናይትሮጂን ማዳበሪያ የሚባለው ወይም በተለምዶ ዩሪያ የማዳበሪያ ዓይነት 36 በመቶው ከዚህ ቀጣና ነው ለዓለም ገበያ የሚቀርበው ይላል፡፡
ኳታርና ሳዑዲ ዓረቢያ ደግሞ ዩሪያ ለዓለም ገበያ በማቅረብ በቀጣናው ግንባር ቀደም ናቸው፡፡ የፋርስ ባህረ ሰላጤው አገሮች በተለምዶ ዳፕ የሚባለው (Diammonium Phosphate-DAP) የማዳበሪያ ዓይነት 26 በመቶ ለዓለም ገበያ የሚያቀርቡ ናቸው፡፡ ማፕ ወይም (Monoammonium Phosphate-MAP) የሚባለው የማዳበሪያ ዓይነት ደግሞ 13 በመቶውን ለዓለም ገበያ የሚሸፍኑ ናቸው፡፡
እ.ኤ.አ. በ2024 ከእነዚህ አገሮች ወደ 16 ሚሊዮን ቶን ማዳበሪያ በባህር ትራንስፖርት ለዓለም ገበያ መቅረቡ ይነገራል፡፡ ከዚህ ውስጥ ደግሞ 67 በመቶ ዩሪያ ሲሆን፣ 20 በመቶው ዳፕ፣ ቀሪው ዘጠኝ በመቶ ደግሞ ማፕ ነው፡፡ ሰልፈር የሚባለው በመላው ዓለም ለማዳበሪያና ለሌሎች ምርቶች ግብዓት በመሆን የሚያገለግል ማዕድን ዋና ምንጩ የባህረ ሰላጤው ቀጣና ነው፡፡ ለዓለም ገበያ 45 በመቶ ሰልፈር አቅራቢዎች እነዚህ አገሮች ናቸው፡፡
From The Reporter Magazine
ጦርነቱ ከተቀሰቀሰ በኋላ በባህረ ሰላጤው አገሮች የደረሰው ቀውስ የዓለም የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪንም ክፉኛ የጎዳ ነው ይባላል፡፡ ለምሳሌ የዓለም አልሙኒየም ምርት ዘጠኝ በመቶ የሚሸፍኑት የዚህ ቀጣና አገሮች ናቸው፡፡ በአጠቃላይ በጦርነቱ መዘዝ የቀጣናው አገሮች የኮንስትራክሽን ግብዓቶች ኢንዱስትሪ ክፉኛ መናጋቱ ተነግሯል፡፡
ኢራንና ሳዑዲ ዓረቢያ ከዓለም አምስት ቀዳሚ የቅርጣን አምራች አገሮች መካከል የሚገኙ መሆናቸው ይነገራል፡፡ ድፍድፍ ነዳጅ ከተጣራ በኋላ የሚገኘው ተረፈ ምርት ወይም ቅርጣን የአስፋልት ኮንክሪት መንገድ ግንባታ ዋና ግብዓት ሆኖ የሚያገለግል ከፍተኛ ተፈላጊነት ያለው ምርት ሲሆን፣ የፋርስ ባህረ ሰላጤ አገሮችም የቅርጣንና የአስፋልት ምርት ለዓለም በማቅረብ ከቀዳሚዎቹ መካከል ይገኛሉ፡፡ ከቻይና፣ ከአሜሪካና ከካናዳ ቀጥሎ ኢራንና ሳዑዲ የዓለም ቅርጣን ገበያን የሚመሩ ሲሆን የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ ደግሞ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች፡፡
በዓለም አቀፍ የቅርጣን ገበያ (Global Bitumen Market) መረጃ መሠረት እ.ኤ.አ. በ2023 ኢትዮጵያ ከውጭ ካስገባችው ቅርጣን ውስጥ 33 በመቶ ከኦማን፣ 30 በመቶ ከባህሬን፣ 19 በመቶ ከኢራቅ፣ 11 በመቶ ከዓረብ ኤምሬትስ፣ እንዲሁም 3.4 በመቶ ከቻይና ተገዝቶ የገባ ነው፡፡ ኢትዮጵያ በቅርጣንና አስፋልት ምርት በአፍሪካ ደረጃ ሰፊ ያልተነካ ገበያ እንዳላትም ይነገራል፡፡ እ.ኤ.አ. በ2023 ብቻ ለአስፋልት ምርቶች ግዥ ከ19 ሚሊዮን ዶላር በላይ እንዳፈሰሰችና ቀዳሚ አቅራቢዎቿም ባህሬን፣ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ፣ ኢራቅና ኦማን እንደሆኑ ሪፖርቶች ያመለክታሉ፡፡
ኢትዮጵያ ወደ 97 በመቶ የነዳጅ ምርት የምታስገባው ከፋርስ ባህረ ሰላጤ አገሮች እንደሆነ ደግሞ ዘ ኢኮኖሚስት ከሰሞኑ ዘግቦታል፡፡ በዓመት ከአራት ቢሊዮን ዶላር በላይ ለነዳጅ ግዥ ፈሰስ የምታደርገው ኢትዮጵያ እንደ ኩዌት፣ ሳዑዲና ዓረቢያና የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ የመሳሰሉ አገሮች ዋና አቅራቢዎቿ መሆናቸው ይነገራል፡፡
በመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት ሳቢያ ከባድ ኢኮኖሚያዊ ቀውስ የሚገጥማቸው 15 አገሮችን በተለያዩ መሥፈርቶች የሚፈትሸው የዘ ኢኮኖሚስት ሰሞነኛ ሪፖርት፣ እንደ ፓኪስታን ያሉ አገሮች ነዳጅ በራሽን ወደ ማከፋፈል መግባታቸውን ይጠቅሳል፡፡ አንዳንዶች ሠራተኞቻቸውን ከቤት ሆናችሁ ሥሩ እስከ ማለት መድረሳቸውን፣ እንዲሁም ትምህርትና ሌሎች አገልግሎቶችን ማቋረጣቸውን ይገልጻል፡፡
ህንድ፣ ፊሊፒንስ፣ ቱርኪዬ፣ ኢንዶኔዢያ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ቬትናም፣ ባንግላዴሽ፣ ኬንያ፣ ስሪላንካ፣ ታይላንድ፣ ኔፓል፣ ዮርዳኖስ፣ ግብፅ፣ ኢትዮጵያ፣ ፓኪስታን በማለት በኢራን ጦርነት መዘዝ የከፋ ጉዳት የሚገጥማቸው አገሮችን ስም ዝርዝር ያስቀምጣል፡፡
ይህንን በአኃዝ አስደግፎ ሲያቀርብም ለአብነት ዮርዳኖስ 90.6 በመቶ፣ ኢትዮጵያ 97 በመቶ፣ ፓኪስታን 88.8 በመቶ የነዳጅ ፍጆታቸውን ከባህረ ሰላጤው አገሮች ነው የሚያገኙት ይላል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ዮርዳኖስ 7.5 በመቶ፣ ግብፅ 5.5 በመቶ፣ ፓኪስታን 5.6 በመቶ፣ ኔፓል 8.1 በመቶ የጥቅል ምርታቸውን (ጂዲፒያቸውን) የሚያገኙት በባህረ ሰላጤው አገሮች ካሰማሩት ሠራተኛ ሕዝብ ከሚላክ የሐዋላ ገንዘብ (ሬሚታንስ) ነው ይላል፡፡ እንደ ኢትዮጵያ ያሉ አገሮችም ቀላል የማይባል መጠን ያለው የሬሚታንስ ገቢ በዚሁ አካባቢ ከተሰማሩ ዜጎቻቸው እንደሚያገኙ አያይዞ ያስረዳል፡፡
የዘ ኢኮኖሚስት ሪፖርት አገሮቹ በኢራን ጦርነት ከደረሰባቸው ኢኮኖሚያዊ መቃወስ በተጨማሪ ነባርና ውዝፍ ሸክም አለባቸው፡፡ ለአብነት ግብፅ 29 ቢሊዮን ዶላር ብድር ዘንድሮ መክፈል ይጠበቅባታል የሚለው ሪፖርቱ፣ ይህ ደግሞ የአገሪቱን ከግማሽ በላይ የመጠባበቂያ የውጭ ምንዛሪ ክምችት የሚሸፍን ማለት ነው ይላል፡፡
ፓኪስታን ከሦስት ወራት ሸቀጥ ማስገቢያ በታች ነው የውጭ ምንዛሪ ክምችቷ የሚለው ሪፖርቱ፣ ይህ ደግሞ የዓለም የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) ካስቀመጠው ጣሪያ በታች ነው ይላል፡፡ ዮርዳኖስም ከፍተኛ ብድርና የምንዛሪ እጥረት አለባት የሚለው ሪፖርቱ፣ ኢትዮጵያና የሌሎቹ አገሮች ሁኔታም ከዚህ የከፋ እንጂ የተሻለ አይደለም ሲል ይደመድማል፡፡
በኢራን ጦርነት መዘዝ ከአሜሪካ እስከ ቻይና በሁሉም አገሮች የገበያ አለመረጋጋት፣ የዋጋ ግሽበትና የኢኮኖሚ መቃወስ ችግር መፈጠሩ ይነገራል፡፡ ይሁን እንጂ እንደ ኢትዮጵያ ያሉ አገሮች ጉዳት ግን እንደሚያመዝን በርካታ ዓለም አቀፍ ሪፖርቶች እየጠቆሙ ነው፡፡ በተለይም እንደ ነዳጅና ማዳበሪያ ያሉ ስትራቴጂካዊ ምርቶችን ከውጭ በማስገባት ኢኮኖሚያቸው ጥገኛ የሆኑ አገሮች ጉዳት እንደሚያጋድል፣ በርካታ ተቋማትና ምሁራን በማሳሰብ ላይ ናቸው፡፡
ኢትዮጵያን ጨምሮ ሴኔጋል፣ ግብፅ፣ ኬንያና ሌሎች የአፍሪካ አገሮች የነዳጅ እጥረት እንደገጠማቸውና ለዚህም በቁጠባ የመጠቀም አማራጭን እየተከተሉ መሆኑን አልጄዚራ ዘግቧል፡፡ አልጄዚራ በዚህ ጉዳይ ለውይይት የጋበዛቸው በለንደን የክሪቲካል ሚነራልስ አፍሪካ ግሩፕ ተቋም ኃላፊ ቬሮኒካ ቦልተን ስሚዝ እንደተናገሩት፣ አፍሪካ የተትረፈረፈ የኢነርጂ ምንጭ ኖሯትም ነገር ግን በመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት ምን ያህል ተጋላጭ ናት፡፡
‹‹ደቡብ አፍሪካ የነዳጅ ታክስን አስወግዳለች፣ ግብፅ ከሦስት ሰዓት በላይ ማምሸት እንዲከለከል አድርጋለች፣ ሌሎች አገሮችም የአጭር ጊዜ ያሉትን መፍትሔ እየወሰዱ ነውና እርስዎ በአኅጉሩ ያጋጠመውን የነዳጅ እጥረት ለመቅረፍ በአጣዳፊነት ምን ቢደረግ ይበጃል ይላሉ?›› ተብለው የተጠየቁት ቬሮኒካ፣ የረዥም ጊዜ እንጂ ለዚህ የሚሆን የተለየ የአጭር ጊዜ መፍትሔ እንደሌላቸው ተናግረዋል፡፡
በአፍሪካ የመንገድና ሌሎች መሠረተ ልማት አቅርቦቶች አለመሟላት፣ የኃይል ማስተላለፊያና ማሠራጫ መስመሮች አለመዘርጋት፣ ከዋና ዋና የኃይል መስመሮች ጋር ያልተገናኙ የኃይል አማራጮችን አለመጠቀም፣ የዕውቀትና የገንዘብ ችግር ሳይቀር የኢነርጂ ዘርፉን እንደጎዱት አመልክተዋል፡፡
‹‹ከሁሉ በላይ ግን በአፍሪካ የእርስ በርስ የኢነርጂ ገበያን ማጠናከር አስፈላጊ ነው፡፡ አፍሪካ ውስጥ ነዳጅ ያላቸው አገሮች እያሉ ብዙ የአፍሪካ አገሮች ከሌሎች አገሮች ነው የሚያስመጡት፡፡ ስለዚህ አፍሪካን ያስተሳሰረ የነዳጅ ግብይት ያስፈልጋል፡፡ አሁን የገጠማቸውን ችግር በአጣዳፊነት ለማቃለል ለምሳሌ ነዳጅ ያላቸው የጎረቤት አገሮችን ለመርዳት መፍቀድ አለባቸው፤›› በማለት ምክር ለግሰዋል፡፡
ሌላዋ ተወያይ ሌና ስኒ በበኩላቸው በመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት የአፍሪካ አገሮች የገጠማቸውን ቀውስ ሲናገሩ፣ ‹‹ግብርናን እንውሰድ፣ የአፕሪል 2026 የማዳበሪያ ዋጋ ከቀደመው ወር በከፍተኛ ደረጃ አሻቅቧል፡፡ በዓለም ባንክ መረጃ መሠረት የዩሪያ ዋጋ 46 በመቶ ሆኗል፡፡ ቀውሱ ከቀጠለ ደግሞ ወደ 45 ሚሊዮን ሕዝብ በዓለም ምግብ ፕሮግራም መረጃ መሠረት ለአስከፊ የምግብ እጥረት ችግር ሊጋለጥ ይችላል፤›› በማለት፣ ኢትዮጵያን ጨምሮ የአፍሪካ አገሮች ህልውና በመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት መዘዝ በቀውስ አፋፍ ላይ እንደሚገኝ አብራርተዋል፡፡
የዘ አፍሪካ ሪፖርት መጽሔት ዘገባ እንደጠቆመው ከሆነ ደግሞ፣ የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት ከዚህ ሁሉ በተጨማሪ የባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዘርፍን፣ እንዲሁም የአቪዬሽን ኢንዱስትሪን አሽመድምዷል፡፡ እንደ ኢትዮጵያ ያሉ የአፍሪካ አገሮችም በነዳጅና በማዳበሪያ ችግር ብቻ ሳይሆን፣ በአቪዬሽንና በሎጂስቲክስ ዘርፍ መቃወስም ራሱን የቻለ ጉዳት እንደሚያገኛቸው አመልክቷል፡፡ አልጄዚራ በበኩሉ 90 በመቶ የዓለም ንግድ በባህር ትራንስፖርት እንደሚንቀሳቀስ በመጥቀስ፣ አሁን የዓለም መርከቦች የሚንቀሳቀሱበት ‹‹በንከር ፊውል›› የተባለው ዝቃጭ ወፍራም ነዳጅ እጥረት እንደገጠማቸው ይጠቅሳል፡፡ ይህ የዕቃ ጫኝ መርከቦች ዋና የኢነርጂ ምንጭ የሆነ ነዳጅ ዋና መገኛው የባህረ ሰላጤው አገሮች መሆናቸውን፣ ነገር ግን በጦርነቱ ሆርሙዝ ሰርጥ ስለተዘጋ በዓለም ገበያ ከፍተኛ እጥረት መከሰቱን ይጠቁማል፡፡ ቀውሱ ከቀጠለ የዓለም መርከቦች መንቀሳቀሻ እንደሚያጡ፣ የዓለም ንግድም እንደሚቆም የጠቀሰው ዘገባው ይህ ደግሞ የዓለም ፍፃሜ እንደማለት መሆኑን ያትታል፡፡
አማኒ አፍሪካ የተባለው የምርምር ተቋም በመጪው ሐሙስ የአፍሪካ ኅብረት ሰላምና ፀጥታ ምክር ቤት ኢመደበኛ ስብሰባ በዚህ ጉዳይ እንደሚያደርግ አመልክቷል፡፡ ስብሰባውን እንዲካሄድ የጠየቀችው ደግሞ የወቅቱ የምክር ቤቱ ተረኛ ሊቀመንበር ኢትዮጵያ እንደሆነች ገልጿል፡፡ የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ከዚህ ቀደም ሁለት ጊዜ በኢራን ጉዳይ መግለጫ አውጥቷል፡፡ ኅብረቱ ብቻ ሳይሆን የአኅጉሩ ቀጣናዊ ድርጅቶች እንዲህ ባለው አኅጉሩን ባደቀቀ አሳሳቢ ዓለም አቀፍ ቀውስ ጉዳይ ከመግለጫ ባለፈ፣ የተለያዩ መፍትሔዎች ማቅረብ አልቻሉም የሚለው ወቀሳ ከአንዳንድ ወገኖች በኩል ይሰማል፡፡
የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት በኢትዮጵያ በሁሉም የኢኮኖሚ መስክ ታይቶ የማይታወቅ የዋጋ ንረትና የአቅርቦት መስተጓጎል ሲፈጥር እየታየ ነው፡፡ ከትራንስፖርት እስከ አስቤዛ ዕቃዎች፣ ከኮንስትራክሽን እስከ መሠረታዊ ፍጆታዎች በብዙ መንገድ የሚታይ ተፅዕኖ ፈጥሯል፡፡
የኢራን ጦርነትን ዓለም አቀፍና በኢትዮጵያ ላይ የሚያሳድረውን ተፅዕኖ በተመለከተ ከሪፖርተር ጋር ሰፊ ቆይታ ያደረጉት በኳታር የኢንሹራንስ ባለሙያ የሆኑት አቶ አሚኑ ኑሩ፣ በብዙ መንገዶች ጉዳቱ እንደሚገለጽ ይናገራሉ፡፡ ‹‹ይህ ጦርነት ወደ ኢትዮጵያ ምን ተፅዕኖ ይዞ እንደሚመጣ ስናይ ደግሞ፣ ዩሪያ የሚባለው የማዳበሪያ ዓይነት ወደ 50 በመቶ አቅርቦቱ የተመሠረተው ከባህረ ሰላጤው አገሮች እንደ መሆኑ ይህ ሲቋረጥ እንደ ኢትዮጵያ ያሉ አገሮች ግብርና መጎዳቱ የሚቀር አይደለም፡፡ በሌላ በኩል የኢነርጂው መቋረጥ ጉዳትም ቀላል አይደለም፡፡ ነዳጅ ሲጠፋና ሲወደድ በሁሉም ምርቶች ላይ የዋጋ ለውጥ እንደሚኖረው የሚታወቅ ነው፡፡ የእኛ ኢኮኖሚ ከፍተኛ የንግድ ሚዛን ጉድለት የሚታይበት ነው፡፡ ለምሳሌ ከውጭ የምናስገባው ወይም የኢምፖርት መጠን ወደ 19 ቢሊዮን ዶላር ሲገመት፣ የወጪ ንግድ ገቢ ግኝታችን ግን ወደ አምስት ቢሊዮን ዶላር ነው፡፡ የንግድ ሚዛኑ ጥቂት መሻሻል በቅርብ ዓመታት ቢያሳይም፣ ነገር ግን አሁንም ከውጭ የምናስገባው ብዙ በመሆኑ ጦርነቱ በዚህ በኩል ተፅዕኖ ይኖረዋል፡፡ ከነዳጅ ምርትና ከሸቀጦች መተላለፊያ መቋረጥ ጋር ተያይዞ የዓለም ገበያ ዋጋ ሲንር፣ በእኛ ላይም ቀጥተኛ ተፅዕኖ ያመጣል፡፡ ብዙዎቹ የወጪና የገቢ ንግድ አጋሮቻችን ደግሞ በዚሁ በባህረ ሰላጤው ቀጣና ያሉ እንደ መሆናቸው የአቅርቦት ሰንሰለቱ ሊቆራረጥ ይችላል፡፡ ኢምፖርት ብቻ ሳይሆን ኤክስፖርት የምናደርግበት ሰንሰለትም ይጎዳል፡፡ ለምሳሌ አምና በመንግሥት በወጣ መረጃ መሠረት ኢትዮጵያ ወደ ውጭ ከላከችው ምርትና አገልግሎት ወደ 15 በመቶ ወደ ሳዑዲ ገበያ የምንልክ ሲሆን፣ ወደ 9.1 በመቶ አካባቢ ደግሞ ወደ ተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ እንልካለን፡፡ ይህ ጦርነት ቢያንስ ሁለቱን ወሳኝ የንግድ አጋሮቻችንን ያሳጣናል እንደ ማለት ነው፡፡ በአጠቃላይ ጦርነቱ የአቅርቦት እጥረት ስለሚፈጥር ከዋጋ ንረት ጋር ተያይዞ በቀጥታ ኢትዮጵያን የሚጎዳ ውጤት ይኖረዋል፡፡ የትራንስፖርት መስተጓጎል ከዚህ በተጨማሪም ለአምራች ድርጅቶች የጥሬ ዕቃ አቅርቦትና ዋጋ ላይ ተፅዕኖ ይኖረዋል፤›› በማለት ገልጸዋል፡፡
ጦርነቱ ከዚህ በተጨማሪም በሬሚታንስ ገቢ መቀነስ፣ እንዲሁም በአቪዬሽንና በሎጂስቲክስ አለመረጋጋት ረገድ የራሱን ጉዳት ይዞ እንደሚመጣም ጠቁመዋል፡፡