
የጌዴኦ ብሔር ዘመን መለወጫ የ‹ዳራሮ› በዓል ፋጬኤ (የይቅርታ ሥርዓት) አካሂዶ፣ ሁሉቃ ሠርቶ በመሿለክ፣ ጉማታ (አርሶ አደሮች ካመረቱት ምርት ለአባ ገዳ ስጦታ የሚሰጡበት)፣ ላባ (የአባገዳ አዋጅ) እና ዳራሮን በውስጡ ያቀፈ በበርካታ እሴቶች የበለፀገ ሕዝባዊ መሠረት ያለው በዓል ነው፡፡ ደን፣ ቡናና እንሰት ሕይወቱ የሆነው የጌዴኦ ብሔር የበርካታ ባህላዊና ታሪካዊ እሴቶች ባለቤትም ነው፡፡


የሥራና ክህሎት ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪሃት ካሚልም የጌዴኦ ሕዝብ ደን ውስጥ እየኖሩ ደንንም ማኖር እንደሚቻል ያሳየ፣ ባህላዊ ሥርዓቱን ተንከባክቦ ይዞት የመጣውን ባህላዊ መልክዓ ምድር ለዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ለውጥ መፍትሔነት ያበረከተ ሲሉም ይገልጹታል፡፡
መልክዓ ምድሩን በመጠበቅ፣ ዓለም እንዲማርበትና የባህል ቅርስ ሆኖ በዓለም አቀፍ የሳይንስና ትምህርት ድርጅት ያስመዘገበ ነው ሲሉም የሕዝቡን ተፈጥሮን ተንከባክቦ የመኖር ጥበብ ያጎሉታል፡፡
ሚኒስትሯ፣ የዳራሮ በዓል ጥር 30 ቀን 2018 ዓ.ም. በዲላ ከተማ በተከበረበት ወቅት እንደተናገሩት፣ ባህላዊ እሴቶቹ ከፍ ያለ ኢኮኖሚያዊ አስተዋፅኦ እንዲኖራቸውና በሥራ ዕድል ፈጠራ ዘርፍ አበርክቷቸው የላቀ ሆኖ የሀብት ምንጭ እንዲሆኑ እየተሠራ ነው።


ኢትዮጵያ የቱባ ባህሎች ባለቤትና በኅብረ ብሔራዊ አንድነት የደመቀች አገር ስትሆን፣ ከእነዚህም ከሚዳሰሱና ከማይዳሰሱ ሀብቶቿ መካከል ጥቂት የማይባሉትን በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የትምህርትና ሳይንስ ተቋም (ዩኔስኮ) ለማስመዝገብ ችላለች። ከእነዚህም መካከል የጌዴኦ መልክዓ ምድር አንዱ ነው።
እንደ ሚኒስትሯ፣ አገር በቀል ዕውቀትን በመጠቀም ደን ውስጥ እየኖሩ ደንን ማኖርና ለተቀረው የዓለም ማኅበረሰብ ምሳሌ መሆን ለቻሉ የጌዴኦ አባቶች ልዩ ክብርና ምሥጋና ይገባቸዋል፡፡ ትውልዱም ይህንን ባህል ማስቀጠልና የአባቶቹን ፈለግ መከተል ይኖርበታል።
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጥላሁን ከበደ እንደተናገሩት፣ የጌዴኦ ሕዝብ የማንነት መገለጫ የሆነው ዳራሮ፣ ሕዝቡ የምርት መሰብሰብን ተከትሎ በራሱ የጊዜ ቀመር የሚያከብረው የምሥጋናና የአዲስ ዓመት ማብሰሪያ ነው።
From The Reporter Magazine
የዳራሮ በዓል ሰላም፣ ፍቅር፣ አብሮነትና አንድነት የሚደምቅበት ከመሆኑ በተጨማሪ፣ ለአዝመራ ዝግጅት በሚደረግበት ወቅት የሚከበር መሆኑ ለምርት ዘመኑ የእርሻ ሥራ፣ ማኅበረሰቡ በአዲስ መንፈስና ተስፋ የሚነሳበት ነው ብለዋል።
‹‹የጌዴኦ ሕዝብ ተፈጥሮን በመጠበቅና በመንከባከብ በኩል ዓለም የመሰከረለት ነው›› ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ፣ ይህንንም አጠናክሮ ማስቀጠል እንደሚገባ አክለዋል።
ዳራሮ በውስጡ የያዛቸው እሴቶች ማኅበረሰብን በመገንባት በኩል ያላቸው ሚና ከፍ ያለ ነው። በተለይ ቂምና ቁርሾን በዕርቅና ይቅርታ በመቋጨት ትውልድን የማነፅና አገርን በፅኑ መሠረት ላይ ለማኖር ትልቅ አቅም እንዳለውም ተናግረዋል።
From The Reporter Magazine
እንደ አቶ ጥላሁን፣ ዳራሮ ከጌዴኦ ሕዝብ ወግና ባህል የሚቀዱ የሰላም፣ የአንድነትና የትብብር እሴቶች ያሉት በመሆኑ፣ ይህ እሴት የክልሉንም ሆነ የአገርን ሰላም በማፅናት በኩል ያለው ድርሻ የላቀ በመሆኑ ልምድ ሊወሰድበት ይገባል።
‹‹የዳራሮ በዓልን ስናከብር ለባህላዊ ትውፊቶች መጎልበትና መጠናከር ትኩረት በመስጠት፣ ይበልጥ እንዲለሙና እንዲተዋወቁ በማድረግ ነው፤›› ያሉት የጌዴኦ ዞን አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) ናቸው።
በዓሉ በውስጡ የያዛቸውን እሴቶች የቱሪስት መስህብ ለማድረግ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ እንደሚገኝና ዳራሮን በዩኔስኮ ለማስመዝገብ ካለፉት ዓመታት ጀምሮ ጥረት በመደረግ ላይ መሆኑን ጠቅሰዋል።
በዓሉ በዩኔስኮ ቢመዘገብ ዞኑን የቱሪዝም መዳረሻ በማድረግ በኩል ትልቅ አስተዋፅኦ እንደሚያበረክት ጠቅሰው፣ ዳራሮ በውስጡ በያዛቸው ትውፊቶች ዓለም አቀፋዊ ትርጉም እንዲይዝ በማድረግ የባህል እሴቱን ማጉላትና ሕዝባዊነቱን ማረጋገጥ ይገባል ሲሉ ገልጸዋል።
ከበዓሉ ታዳሚዎች መካከል አቶ ዘሪሁን በሻህ እንደተናገሩት፣ ዳራሮ ለጌዴኦ ማኅበረሰብ የዘመን መለወጫውና አርሶ አደሩ አፈር አለስልሶ ለዘራው ዘር፣ ፍሬና ምርት ለሰጠው ፈጣሪ ምሥጋናን የሚያቀርብበት ነው።
በዓሉ ሰላም፣ ፍቅርና አንድነትን የሚያጠናክርና በፀበኞች መካከል ዕርቅና ይቅርታ እንዲኖር በማድረግ በኩል ያለው ሚና ከፍተኛ በመሆኑ፣ ይህ እሴት ሳይበረዝና ሳይከለስ ተጠብቆ እንዲቀጥል ትውልዱ ኃላፊነቱን ሊወጣ ይገባል ብለዋል።
በዲላ ስታዲየም በተከበረው የጌዴኦ ሕዝብ የዘመን መለወጫ የዳራሮ በዓል፣ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች፣ አባገዳዎች፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች፣ በሺዎች የሚቆጠሩ ከዲላ ከተማና ከዞኑ የተለያዩ ወረዳዎች የመጡ ተሳታፊዎች የታደሙበት ነበር።