ሰኞ ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም. በተካሄደው በ7ተኛው ጠቅላላ አገራዊ ምርጫ በአዲስ አበባ ከሚገኙ 23 ምርጫ ክልሎች በተወሰኑት ሪፖርተር በመዘዋወር ቅኝት አድርጓል፡፡ በኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ ምርጫ ክልል 24 ወረዳ አምስት በሚገኘው ሠፈረ ሕይወት ዕድር ቤት ምርጫ ጣቢያ አምስት፣ ዘንባባ ዕድር ቤት ምርጫ ጣቢያ ስድስት፣ ራዕይ ሸማቾች ምርጫ ጣቢያ ሁለት፣ መጢ ዕድር ቤት ምርጫ ጣቢያ ሦስት በተደረገ ቅኝት በአብዛኛው ተመሳሳይ የሆኑ ክስተቶችን ለመታዘብ ተችሏል፡፡
በሠፈረ ሕይወት ዕድር ቤት ምርጫ ጣቢያ አምስት ከጠዋቱ 12 ሰዓት ቀድመው በብዛት የተገኙት በዕድሜ የገፉ እናቶችና አባቶች ነበሩ፡፡ በግቢውና ከግቢው ውጪ ባሉ ሁለት ድንኳኖች ውስጥ ሞልተው ከሚታዩት በተጨማሪ፣ ከውጭ አግዳሚ ወንበር ላይ ተቀምጠው ወረፋ የሚጠባበቁም ነበሩ፡፡


በማለዳው በርካታ መራጮች ወረፋ ሲጠብቁበት በነበረው በዚሁ ጣቢያ፣ የድምፅ መስጠት ሥነ ሥርዓቱ ከጠዋቱ 12 ሰዓት ላይ ነበር የጀመረው፡፡ በሰው ተደግፈው ለሚመጡ፣ ከዘራ ለያዙ እናቶችና አባቶች ቅድሚያ በመስጠት ሲካሄድ በነበረው የምርጫ ሒደት ካርዳቸው የጠፋባቸው፣ በኦንላይን ተመዝግበው መረጃ ያልተገኘላቸው መፍትሔ ለማግኘት ሲጠይቁና ካርድ የጠፋባቸው ሲመለሱ ታይተዋል፡፡
በዚህ ጣቢያ ማልደው የተገኙት አዛውንቶች ቢሆኑም፣ ረፋድና ምሽት ላይ በርካታ ወጣቶች ወረፋ ሲጠባበቁና መርጠው ሲወጡ አይተናል፡፡ የዩኒቨርሲቲ ተማሪ እንደሆነ የነገረን የ20 ዓመቱ ወጣት፣ ‹‹ዕድሜዬ ለምርጫ ከደረሰ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ በአገራዊ ምርጫ የመረጥኩበት ስለሆነ ደስ ብሎኛል፡፡ በምርጫው አሸንፎ የሚመጣ ፓርቲ ከሁሉም ነገር አስቀድሞ ሰላም ላይ ቢሠራ ደስ ይለኛል›› ብሏል፡፡
የምርጫ ሰዓት በ12 ሰዓት ይጠናቀቃል በመባሉ በዚሁ ጣቢያ ከድንኳን ውጪ የነበሩት እንዲመለሱ መደረጉን፣ በኋላም ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የድምፅ መስጫ ሰዓትን እስከ ሌሊቱ ስድስት ሰዓት ማራዘሙን በማሳወቁ ከምሽቱ አንድ ሰዓት አካባቢ ያልመረጡ ተመልሰው እንዲመርጡ እዚያው የሚተዋወቁ ሰዎች መልዕክተኛ ሲልኩና ሲጠራሩ ተሰምተዋል፡፡
በጣቢያው ከምሽቱ 3፡30 ላይ ያገኘናቸው አንድ መራጭ ከነጋ ለአራተኛ ጊዜ ተመላልሰው ወረፋ መያዛቸውን፣ ጠዋት አንድ ሰዓት ላይ ቢመጡም ወረፋው የሚቀመስ ስላልነበር በየመሀሉ ከቀነሰ በማለት ሲመላለሱ እንደነበር ነግረውናል፡፡
From The Reporter Magazine
እኛ በጣቢያው በዚሁ ሰዓት በተገኘንበት ወቅት ለመምረጥ ወረፋ የሚጠብቁ የነበሩ ሰዎች ቁጥር በድንኳኖቹ በነበሩ ወንበሮች ያልሞላ እንደነበር አይተናል፡፡ በኋላ ባገኘነው መረጃ ምርጫው ከሌሊቱ ከአምስት ሰዓት ቀድሞ ተጠናቋል፡፡
በምርጫ ክልል 24 በዘንባባ ዕድር ምርጫ ጣቢያ ስድስት እንዲሁ ተመሳሳይ ወረፋ ታዝበናል፡፡ በዚህም ከዕድር ቤቱ ውጪና ውስጥ ድንኳኖች የተጣሉ ቢሆንም፣ ሊመርጥ የመጣውን ሰው በሙሉ ማስተናገድ የሚችሉ አልነበሩም፡፡ በመሆኑም በርካቶች ፀሐይ ላይ ቆመው ወረፋ ለመጠበቅ ተገደው ነበር፡፡ ቀድሞ እንዳየነው ሁሉ ከካርድና ከኦንላይን ምዝገባ ጋር የነበሩ ክፍተቶች በዚህ ጣቢያም ታይተዋል፡፡ በምርጫ ጣቢያው በምርጫ ጣቢያ አምስት ካየነው የበለጠ በርካታ ሰዎች ምሽት ላይ ለመምረጥ ወረፋ ሲጠብቁ ነበር፡፡ አንዳንዶች ‹‹ጋቢ ደርበን እንምጣ›› እያሉ ሲመለሱ አይተናል፡፡ በምርጫ ጣቢያ 24 ወረዳ አምስት ላይ በሚገኙ የተወሰኑ ጣቢያዎች ባደረግነው ምልከታ ለነፍሰጡር እናቶች፣ ልጅ ላዘሉ፣ ለአዛውንቶችና በድጋፍ ለሚመጡ ቅድሚያ ሲሰጥ ነበር፡፡
በምርጫ ክልል 24 ወረዳ አምስት ውስጥ 15 ምርጫ ጣቢያ ማለትም 11 ዋናና አራት ንዑስ ጣቢያዎች ሲኖሩ፣ በእነዚህ 19‚020 መራጮች መመዝገባቸውን ሰምተናል፡፡
From The Reporter Magazine
በቃኘናቸው ጣቢያዎች የመራጮች የምርጫ ሒደት መጓተትን አስመልክተን ላነሳነው ጥያቄ አንድ ስሜ አይጠቀስ ያሉ አስተባባሪ፣ የምርጫ አስፈጻሚዎች በአብዛኛው አዲስ ከመሆናቸው አንፃር የተፈጠረ ክፍተት መሆኑን፣ በኋላ ላይ ግን ፈጥነው እንዲሠሩ በመነጋገር በተራዘመው የድምፅ መሽጫ ሰዓት ውስጥ በወረዳው ባሉ 15 ጣቢያዎች ለመምረጥ የመጡ መራጮችን አስተናግደው መጨረሳቸውን ተናግረዋል፡፡
በተለይ ራዕይ ሸማቾች ምርጫ ጣቢያ ሁለት የነበረው ሠልፍ ረዥም እንደነበርና ሰውም መንገድ ላይ ለረዥም ሰዓታት መቆሙን አስመልክቶም፣ ይህ ጣቢያ መንገድ ዳር በመሆኑና በርካታ ሰው በመመዝገቡ ሠልፉ ሊበዛ እንደቻለ፣ ሆኖም ከሌሊቱ ስድስት ሰዓት ቀድሞ ምርጫ ማጠናቀቁን አክለዋል፡፡
ሕዝቡ በማለዳ በነቂስ በመውጣቱና አንዳንዱም ‹12 ሰዓት ሊሆን ሲል ሄጄ እመርጣለሁ› በማለት አርፍዶ በመምጣቱ ሊዘገይ መቻሉን አስረድተዋል፡፡
በምርጫ ሕጉ መሠረት ውጤት ከማለዳው 12 ሰዓት ጀምሮ አለመለጠፉን አስመልክቶም፣ ምርጫ ከሌሊቱ ስድስት ሰዓት መጠናቀቁና በአንዳንድ ጣቢያዎች በርካታ ሰዎች በመመዝገባቸው መዘግየቱን ገልጸዋል፡፡
በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ወረዳ 8 ጄኔራል ጃጋማ ኬሎ ጤና ጣቢያ ምርጫ ክልል 23 በመገኘት በተደረገ ቅኝት፣ በርካቶች የእግረኛ መንገድ ላይ ተሠልፈው ወረፋ ሲጠብቁ ነበር፡፡
በዚህ ጣቢያ ከነበርንበት ከንጋቱ 12፡50 ሰዓት ጀምሮ በብዛት ያየነው ጎልማሶች፣ ልጅ እግር ወጣት ሴትና ወንዶችን ነው፡፡ በጣቢያው ከጠዋቱ ሁለት ሰዓት አስቀድሞ የአፍሪካ ኅብረት ታዛቢዎች ቅኝት ያደረጉ ሲሆን፣ ሁለት ሰዓት ላይ ደግሞ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ ተገኝተዋል፡፡ ለጥቂት ደቂቃዎች ያህል ወረፋ ጠብቀው ድምፅ የሰጡት ከንቲባዋ፣ አጠር ያለ ገለጻም ለጋዜጠኞች ሰጥተው ነበር፡፡
‹‹ሁላችንንም ለሰባተኛው ዙር የኢትዮጵያ አገራዊ ምርጫ አደረሰን ለማለት እወዳለሁ፤›› ያሉት ከንቲባ አዳነች፣ ‹‹የምርጫ ሒደቱን ሁላችንም እንዳየነው፣ እንደተመለከትነውና መገናኛ ብዙኃን እየዘገቡ እንዳሉትም ዴሞክራሲያዊ፣ ነፃና ፍትሐዊ በሆነ ሁኔታና በግልጽነት እየተካሄደ ነው፤›› ብለዋል፡፡
መገናኛ ብዙኃን እየዘገቡ ሕዝቡ ምርጫ ጣቢያ ከመከፈቱ በፊት ማልዶ ተነስቶ መብቱን በተግባር እያዋለ መሆኑን በመጠቆም፣ ‹‹ሕዝቡ ይጠቅመኛል፣ ይመራኛል ብሎ የሚፈልገውን መሪ፣ ያለማንም ተፅዕኖ፣ በምርጫ ላይ ተፅዕኖ ሊያሳድር የሚችል ምንም ዓይነት እንቅስቃሴ ሳይኖር፣ በሚገባ ደስ ብሎት እየመረጠ ነው፡፡ እኛ በምንገኝበት ምርጫ ጣቢያ ብቻ ሳይሆን፣ በአዲስ አበባ ሁሉም ምርጫ ጣቢያዎች እንደ መንግሥት ባለን ክትትል በጥሩ ሁኔታ የምርጫው ሒደት እየተከናወነና ሕዝቡ መብቱን እየተጠቀመ ነው፤›› ሲሉም ተናግረዋል፡፡
‹‹መንግሥትን ለማቋቋም ዋናው የሥልጣን ምንጭ በእርግጥም ሕዝብ እንዲሆን የኢትዮጵያ ሕዝብ አምኖ እዚህ ሽግግር ደረጃ ላይ መድረሱ፣ ኢትዮጵያ መሪዋን የምትመርጠው ዴሞክራሲያዊ በሆነ ሥርዓት፣ ፍትሐዊና ገለልተኛ ሕዝብን ሉዓላዊ ባደረገ የምርጫ ሒደት በመሆኑ፣ ለአገራችን ዘላቂ ሰላምና ልማት፣ የኢትዮጵያን ታላላቅ ራዕይ ለማሳካት ወሳኝ ምዕራፍ ነው፡፡ ሕዝቡም ይህንን እያደረገ ይገኛል፤›› በማለት አስረድተዋል፡፡
ከረፋዱ 5፡30 ሰዓት አካባቢ የተገኘንበት የቂርቆስ ክፍለ ከተማ ወረዳ 7 ትምህርት ጽሕፈት ቤት የዕድገት በኅብረት ቅድመ አንደኛ፣ አንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ምርጫ ክልል 21/22 ነበር፡፡ በድንኳን ወስጥና ከድንኳን ውጪ ሆነው ወረፋ እየተጠባበቁ ከሚገኙት መራጮች ውስጥ አብዛኞቹ ወጣት ወንዶች እንደነበሩ አይተናል፡፡ በዚህ ምርጫ ጣቢያ የግቢው የመኪና መግቢያ በር ሙሉ ለሙሉ ተዘግቶ የሰው መግቢያው ብቻ በጥበቃ ቁጥጥር ሥር ሆኖ የተከፈተ ቢሆንም፣ ብዙዎች በሩ ላይ ሆነው ለመግባት ይጨቃጨቁ ነበር፡፡ ከግቢው ውስጥ ካለው ድንኳን በብዛት የነበሩት ሴቶች ናቸው፡፡
በጣቢያው ለአካል ጉዳተኞች ቅድሚያ እየተሰጠ ሲገቡ የተመለከትን ሲሆን፣ ኦንላይን ተመዝግበው መረጃ ያልተገኘላቸው መራጮች በንዑስ ጣቢያ ሄደው መምረጥ እንደሚችሉ ሲገለጽላቸው ሰምተናል፡፡
በምርጫ ክልል 24 እንደታዘብነው ሁሉ፣ በምርጫ ክልል 21/22ም መራጮች ‹‹ወረፋው ሲቀል ወደ 11 ሰዓት እንመጣለን›› እያሉ ሲመለሱ አይተናል፡፡ በተዘዋወርንባቸው ምርጫ ጣቢያዎች የፀጥታ አካላት ከምርጫ ጣቢያዎች ርቀው ወደ የምርጫ ጣቢያ በሚያስገቡ መንገዶች ላይ የሚያልፉትን ሲፈትሹ አይተናል፡፡ በዕለቱ ባደረግነው ቅኝት በየምርጫ ጣቢያዎቹ በማለዳ የደረሱት አዛውንት፣ እናትና አባቶች ቢሆኑም፣ ከረፋድ ጀምሮ ግን በርካታ ወጣቶችን ለመመልከት ተችሏል፡፡
በዕለቱ ከአየር ጤና በዘነብ ወርቅ እስከ መሐንዲስና ወይራ፣ ከዘነበወርቅ ቶታል፣ ብሥራተ ገብርኤል ሜክሲኮ፣ ብሔራዊ አካባቢ እስከ ቀኑ ሰባት ሰዓት በነበረ ቅኝት የሰውም ሆነ የተሽከርካሪ እንቅስቃሴ አልነበረም ማለት ይቻላል፡፡ በአንዳንድ ሥፍራዎች ታክሲ የሚጠብቁ ቢታዩም፣ አልፎ አልፎ ከሚመጣ ታክሲ ውጪ አልነበረም፡፡ አንዳንድ የቤትና የንግድ መኪናዎች ውር ውር ሲሉም ነበር፡፡
ከሰባት ሰዓት በኋላ ከዕኩለ ቀን በፊት ከነበረው በተለየ የተሽከርካሪና የሰው እንቅስቃሴ ጨምሮ ታይቷል፡፡ በምርጫ ማግሥት ግንቦት 25 ቀን 2018 ዓ.ም. ትምህርት ባለመኖሩ የተማሪ እንቅስቃሴ ባይኖርም፣ የትራንስፖርት አገልግሎት ማልዶ መጀመሩን፣ የታክሲና የአውቶቡስ ተርሚናሎችም በተሽከርካሪዎች እንቅስቃሴ ተሞልተው ተመልክተናል፡፡
እኛ በተዘዋወርንባቸው ቦታዎች ምርጫው በሰላማዊ መንገድ መጠናቀቁን ታዝበናል፡፡ በአዲስ አበባ ፖሊስ ዋና ጠቅላይ መምሪያ የተደራጀው የምርጫ ኮማንድ ፖስት በሰጠው መግለጫም፣ በመዲናዋ የ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የድምፅ አሰጣጥ ሒደት በምርጫው ዕለት፣ ቀንም ሆነ ሌሊት ምንም ዓይነት ወንጀል አለመፈጸሙንና የምርጫ ሒደቱ በስኬት መጠናቀቁን ገልጿል።
