ሪፖርተር – Ethiopian Reporter – #1 reliable news source in Ethiopia

[የዴሞክራሲ ጉዳዮች ኃላፊው ክቡር ሚኒስትሩ ጋር ደውለው መንግሥትን እያስቸገረ ነው ተብሎ ስለተፈረጀ አንድ ዝነኛ ባለሀብት ጉዳይ እየመከሩ ነው]
- ጤና ይስጥልኝ ክቡር ሚኒስትር
- ሰላም
- የተጣበበ ጊዜ እንዳልዎት ስለተነገረኝ ነው በስልክ ላነጋግርዎና ምክርዎን ለመጠየቅ የወሰንኩት።
- እሺ… ቀጥል… ምን ገጥሟችሁ ነው?
- ክቡር ሚኒስትር ከዚህ ቀደም በመንግሥት ላይ ትችቶችን በተደጋጋሚ እየሰነዘረ ስለሚገኝ አንድ ዝነኛ ባለሀብት መረጃ አቅርቤልዎት ነበር። ያስታውሳሉ?
- አዎ… አስታውሳለሁ።
- እንዲያውም በወቅቱ ባለማወቅ ይሆናል እንታገሰው ብለውን ነበር።
- አዎ ልክ ነው። አስታውሳለሁ።
- ምንም ሊሻሻል አልቻለም።
- እንዴት?
- ክቡር ሚኒስትር፣ በሚቀርቡት ሰዎች ጥንቃቄ እንዲያደርግ ብናስመክረውም አደብ ሊገዛ አልቻለም። እንዲያውም ብሶበት ቀጥሏል።
- ምንድነው እያለ ያለው?
- ሚዲያዎችን በመጠቀም በመንግሥት ላይ እያነሳሳ ነው።
- ምን ብሎ?
- ሕዝቡ በኑሮ ውድነት እየተሰቃየ ነው እያለ በተደጋጋሚ ለሚዲያ መግለጫ ይሰጣል።
- በቃ ይኼ ነው?
- አይደለም ክቡር ሚኒስትር።
- ሌላ ምን ብሏል?
- ሕዝቡ የሚናገርለት አጥቶ እንጂ መሮታል እያለ ነው።
- በቃ?
- ይኼ ብቻ አይደለም ክቡር ሚኒስትር።
- ሌላ ምን አድርጓል?
- እነዚህን ትችቶች እያቀረበ ያለው ብቻውን አልመሰለኝም።
- እ… ከማን ጋር ሆኖ ነው?
- ከውጭ ባላንጣችን ጋር በመናበብ ይመስላል።
- ቆይ ይኼ ሰው ማነው?
- እስካሁን አላወቁትም እንዴ?
- አላወቅኩትም።
- የቀድሞ ወዳጃችን የነበረው እኮ ነው?
- የቱ?
- የማይፀፀተው።
[በተለያዩ ድርጅቶቻቸው ስም ያገኙ የነበረው የኢንቨስትመንት ማበረታቻ የተቋረጠባቸው አንድ ባለሀብት የኢንቨስትመንትና የታክስ ማበረታቻውን ዳግም ለማስፈቀድ በክቡር ሚኒስትሩ ቢሮ ተገኝተው ከሚኒስትሩ ጋር ስለሁኔታው እየተነጋገሩ ነው]
- ክቡር ሚኒስትር በርካታ ኩባንያዎችን አቋቁሜ አገሬ ላይ ኢንቨስት እያደረግኩኝ መሆኑን ያውቃሉ ብዬ አስባለሁ።
- በሚገባ። አውቃለሁ።
- በዚህም በበርካታ ሺዎች ለሚቆጠሩ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር ከመቻላችን በተጨማሪ ለመንግሥትም ግብር እየከፈልን ነው።
- አውቃለሁ።
- መንግሥትም የምናደርገውን ጥረት ተገንዝቦ ላለፉት በርካታ ዓመታት የኢንቨስትመንት ማበረታቻ ሲሰጠን ቆይቷል።
- ታዲያ አሁን ምን ገጠመህ?
- መንግሥት ይሰጠን የነበረው የታክስና የኢንቨስትመንት ማበረታቻው ለምን እንደሆነ ሳይነገረን በድንገት ተቋረጠ።
- ሙሉ በሙሉ ነው የተቋረጠው?
- ካሉኝ ኩባንያዎች መካከል ለዋነኞቹ ይሰጥ የነበረው ማበረታቻ ተቋርጧል።
- እስኪ ስኩባንያዎቹንና ስለተሰማሩበት መስክ ዘርዝርልኝ?
- አንደኛው የወተት ፋብሪካ ነው።
- ወተት ማለት?
- ለምግብነት የሚለውን ወተት ማለቴ ነው።
- እንዴት? ከምንድነው የምታመርቱት?
- የተለያዩ ግብዓቶችን ተጠቅመን ነው የምናመርተው።
- ለምሳሌ?
- በዋናነት ከውጭ አገር ያስመጣናቸው የሚታለቡ ላሞች አሉን።
- እሺ…?
- የተወሰነውን ግብዓት የምናገኘው ከዚያ ነው።
- የቀረውንስ?
- የቀረውን የወተት ላም ከሚያረቡ የማኅበረሰብ ከፍሎች እንገዛለን።
- ምንድነው ከእነዚህ የማኅበረሰብ ክፍሎች የምትገዙት?
- ወተቱን።
- ነው?
- አዎ። ከእነዚህ የማኅበረሰብ ክፍሎች ወተቱን እየገዛን እንሰበስባለን።
- ከዚያስ።
- ከዚያ ፓስቸራይዝድ በማድረግ አሽገን ለገበያ እናቀርባለን።
- ወተት እናመርታለን ያልከው ይኼንን ነው።
- አዎ። ይገርምዎታል በዚህ ሥራ ለብዙ የማኅበረሰብ ክፍሎች የሥራ ዕድል ፈጥረናል።
- እሺ፣ ሌላኛው ኩባንያህስ በምን መስክ ነው የተሰማራው?
- ሌላኛው ኩባንያ እርጎ የሚያመርት ነው።
- እርጎ ነው ያልከው?
- አዎ ክቡር ሚኒስትር።
- እንዴት?
- ከመጀመሪያው ኩባንያ የተረፈውን ወተት እንደ ግብዓት በመጠቀም ወደ እርጎ ይቀይርና…
- እ…?
- ፓስቸራይዝድ በማድረግ በጥሩ ፓኬጅ አሽጎ ለገበያ የሚያቀርብ ነው።
- ጥሩ። ሌላኛውስ ኩባንያህስ?
- እሱ ደግሞ የገበታ ቅቤ ነው የሚያመርተው።
- ሌላኛውስ?
- እሱ ድግሞ የሚያመርከት…
- እ…?
- አይቤ ነው።
- አይቤ ማለት?
- አይብ። ለምግብነት የሚውለው።
- ገባኝ፣ ድንቅ ነው። እነዚህ ሁሉ ድርጅቶች ራሳቸውን የቻሉ ናቸው?
- አዎ። ራሳቸውን የቻሉ ሆነው በአንድ ጥላ ድርጅት ሥር የሚመሩ ናቸው።
- የጥላ ድጅቱ ስም ማን ይባላል?
- ሚልክ ዌይ።
- ሚልክ ዌይ ምን?
- ሚልክ ዌይ ኢንቨስትመንት ግሩፕ።
- ይገርማል።
- ምኑ ክቡር ሚኒስትር?
- ለእነዚህ ኩባንያዎች ለሁሉም በተናጠል የኢንቨስትመንት ማበረታቻ ስታገኝ መቆየትህ ይገርማል።
- ለምን ይገርማል ክቡር ሚኒስትር? ሁሉም ኩባንያዎች እኮ ለዜጎች የሥራ ዕድል ፈጥረዋል?
- አሁን ግን ለሁሉም ድርጅቶች የኢንቨስትመንትና የታክስ ማበረታቻ መስጠት አንችልም።
- እንዴት ክቡር ሚኒስትር?
- ይሄንን ማድረግ የመንግሥትን ገቢ ያሳጣል። በውጤቱም አገር ይጎዳል።
- ስለዚህ ምንም ዓይነት ማበረታቻ ማግኘት አልችልም ማለት ነው ክቡር ሚኒስትር?
- አይደለም። ማግኘት የምትችልበት መንገድ አለ።
- ምንድነው እሱ?
- ለብቻቸው የተቋቋሙትን ኩባንያዎች አንድ ላይ ሰብስበህ…
- እ…?
- በአንድ ኩባንያ ሥር እንዲቋቋሙ ካደረግክ ማበረታቻውን ማግኘት ትችላለህ፡፡
- እንዴት አድርጌ በአንድ ኩባንያ ሥር እንዲቋቋሙ አደርጋለሁ?
- ለምን አትችልም?
- ራሳቸውን የቻሉ ኩባንያዎች ናቸዋ ክቡር ሚኒስትር። በዚያ ላይ ደግሞ…
- እ… በዚያ ላይ ምን?
- እያንዳንዳቸው የተለያዩ ፕሮዳክቶችን የሚያመርቱ ናቸው።
- እሱን ተወው። ይልቅ ልምከርህና ምክሬን ተቀብለህ የምልህን ብታደርግ ጥሩ ነው?
- እሺ ይንገሩኝ።
- ድርጅቶቹን አንድ ላይ አዋህደህ በሌላ ስያሜ ብትመጣ ማበረታቻውን ታገኛለህ።
- በሌላ ስያሜ ማለት?
- ድርጅቶቹን በአንድ ጥላ የሚያስተዳድረው ኩባንያህ ስያሜው ማን ነበር ያልከው?
- ሚልክ ዌይ ኢንቨስትመንት ግሩፕ።
- ኢንቨስትመንት ግሩፕ የሚለውን ተወውና…
- እ… ?
- ሌላ ነገር በለው።
- ሌላ ነገር ማለት?
- እኔ ልንገርህ?
- አዎ ይንገሩኝ።
- ሚልክ ዌይ…
- እ…?
- የወተት ተዋጽኦ ማምረቻ።
The post [የዴሞክራሲ ጉዳዮች ኃላፊው ክቡር ሚኒስትሩ ጋር ደውለው መንግሥትን እያስቸገረ ነው ተብሎ ስለተፈረጀ አንድ ዝነኛ ባለሀብት ጉዳይ እየመከሩ ነው] first appear on ሪፖርተር – Ethiopian Reporter – #1 reliable news source in Ethiopia and is written by በጋዜጣው ሪፓርተር