
ለሰባተኛው አገራዊ ምርጫ በመራጮች ትምህርትና በምርጫ ታዛቢነት ለመሳተፍ ከ180 በላይ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ፈቃድ ማግኘታቸውን የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን አስታወቀ።
ከየካቲት 26 እስከ 28 ቀን 2018 ዓ.ም የሚካሄደውን የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ሳምንት ምክንያት በማድረግ ዛሬ የካቲት 4 ቀን 2018 ዓ.ም ጋዜጣዊ መግለጫ የተሰጠ ሲሆን፣ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ፋሲካው ሞላ ፣ለሰባተኛው አገራዊ ምርጫ ለመሳተፍ ከ180 በላይ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ፈቃድ ማግነታቸውንገልጸዋል፡፡ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች በምርጫው ትልቅ አስተዋጽኦ ከሚያደርጉ አካላት መካከል መሆናቸውንና በዚህም የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ሳምንት ላይ የፓናል ውይይትማዘጋጀታቸውን ተናግረዋል፡፡
ከአንድ ወር ገደማ በፊት ምርጫው ሰላማዊ፣ ዲሞክራሲያው ነጻና ታዓማኒነት ያለው እንዲሆን ድርጅቶቹ የሚጠበቅባቸው ሀላፊነት እንዲወጡ ዕቅድ ማዘጋጀቱን የሚገልጹት ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ፣ ዕቅዱን በክልል አብረዋቸው ከሚሰሩ አካላት ጋር በ14ኛው የባለስልጣኑ ጉባኤ ላይ በማቅረብ ውይይት ማድረጋቸውን ገልጸዋል፡፡ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች በምርጫው ሂደት በንቃት መሳተፍ እንደሚጠበቅባቸው፣ ነገር ግን በምርጫ ዙሪያ መሥራት የሚፈቀድላቸው አገር በቀል ድርጅቶች ብቻ እንደሚሆኑና የብሄራዊ ምርጫ ቦርድ በመራጮች ትምህርት ምዝገባና በምርጫ መታዘብ ሂደት እንዲሳተፉ ፈቃድ ሊያገኙ እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡
ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ይፋ ባደረገው የሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ የጊዜ ሰሌዳ መሰረት፣ የመራጮች ትምህርት ለሚሰጡ ሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ዕውቅና የመስጠት ሥራ ጥቅምት 15 ቀን 2018 ዓ.ም ማካሄዱን ማስታወቁ ይታወሳል፡፡ በቦርዱ የጊዜ ሰሌዳ መሰረት ጠቅላላ ምርጫው ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል መባሉ ይታወሳል፡፡