ስድስተኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የአምስት ዓመታት የሥራ ጊዜውን አጠናቆ ማክሰኞ ሰኔ 30 ቀን 2018 ዓ.ም. ተሰናብቷል፡፡ የሰባተኛው ምክር ቤት ተመራጮች በመስከረም 2018 ዓ.ም. የመጨረሻ ሳምንት መጀመሪያ እስከሚተኩ ድረስ አስቸኳይ ጉዳዮች ካላጋጠሙ በስተቀር፣ በሥራ ላይ የቆዩት የምክር ቤት አባላት ስንብት ተደርጎላቸዋል፡፡ የመረጣቸውን ሕዝብ ወክለው በምክር ቤት አባልነት የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት የተወጡ እንዳሉ ሁሉ፣ አምስት ዓመታት በሙሉ ድምፃቸው ሳይሰማ ወይም መኖራቸው ሳይታወቅ እንደ አመጣጣቸው ሹልክ ብለው የሄዱ እንዳሉ ዕሙን ነው፡፡ አንድ የምክር ቤት አባል ለሕገ መንግሥቱ፣ ለወከለው ሕዝብና ለህሊናው ታማኝ ሆኖ የሕግ አውጪውን አካል ሚና ማጎልበት ይጠበቅበታል፡፡ ሕጎች ተረቀው ወደ ምክር ቤቱ ሲላኩ ለአገር ያላቸው ፋይዳ ላይ መከራከር፣ መጨመር ወይም መቀነስ ያለባቸው ድንጋጌዎችን በጥንቃቄ መርምሮ አቋም መያዝና የመንግሥት አስፈጻሚውን አካል መቆጣጠር ተጠቃሽ ናቸው፡፡
የፓርቲ ወገናዊነት እንዳለ ሆኖ በአስፈጻሚው አካል የሚቀርቡ ሪፖርቶችንና ማብራሪያዎችን በጥንቃቄ መፈተሸ፣ በአገር ላይ ጉዳት ሊያደርሱ የሚችሉ ድርጊቶችን ማመላከት፣ ከብልሹ አሠራርና ሙስና ጋር የተያያዙ አፈጻጸሞችን ተከታትሎ ሕጋዊ ዕርምጃዎች እንዲወሰዱ ማድረግ፣ በፌዴራል ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት የሚቀርቡ የፋይናንስና የክዋኔ ሪፖርት ግኝቶችን ከማዳመጥ በዘለለ በአጥፊዎች ላይ ሕጋዊ ዕርምጃ እንዲወሰድ ጫና መፍጠር፣ የመንግሥታዊ ተቋማትን ሐሰተኛ ሪፖርቶች ማጋለጥ፣ የአስፈጻሚው አካል ጡንቻ እየፈረጠመ ሕግ አውጪውንና ተርጓሚውን እንዳይገዳደር የቁጥጥርና ሚዛናዊነት አሠራር መከበሩን ማረጋገጥ፣ የዜጎች ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች እንዳይጣሱ ብርቱ ጠበቃ መሆን፣ ለሕግ የበላይነት መከበር በፅናት መታገል፣ የአገር ብሔራዊ ደኅንነትና ጥቅሞች በአግባቡ እንዲከበሩ ማድረግ፣ ሰላም የሁሉም ነገር መሠረት ስለሆነ ለጠብና ለግጭት የሚያነሳሱ ማናቸውም ዓይነት ልዩነቶች ወደ ክብ ጠረጴዛ እንዲመጡ የምክር ቤት አባላት ትልቅ ኃላፊነት አለባቸው፡፡
ከላይ ከብዙ በጥቂቱ ለማሳየት እንደ ተሞከረው ምን ያህሉ የምክር ቤት አባላት ኃላፊነታቸውን በሚገባ ተወጥተዋል ለሚለው ለሕዝብ የህሊና ዳኝነት መተው አለበት፡፡ መራጩ ሕዝብ ‹ተቀመጥ በወንበሬ ተናገር በከንፈሬ› ብሎ በድምፁ ወክሎኛል የሚል የምክር ቤት አባል፣ ከምንም ነገር በፊት ማክበር ያለበት ሕዝብን ነው፡፡ በፖለቲካ ፓርቲም ሆነ በግል ዕጩ ሆኖ ለምርጫ ቀርቦ ተወዳድሮ ምክር ቤት የገባ ተመራጭ፣ በድምፁ መርጦኛል የሚለውን ሕዝብ የሚክሰው ለምክር ቤቱ በቀረቡ ጉዳዮች ላይ ለአገር የሚጠቅሙ ሐሳቦችን ሲሰነዝርና ውጤታቸው ያማረ እንዲሆን ጥረት ሲያደርግ ነው፡፡ በፖለቲካ፣ በኢኮኖሚ፣ በማኅበራዊና በሌሎች ጉዳዮች የኢትዮጵያ ሕዝብ እንዲጠቀምና ኢትዮጵያም አትራፊ እንድትሆን የመታገል ኃላፊነት እንዳለበት የተገነዘ የምክር ቤት አባል ከማንም በላይ የሚመሰክርለት ሕዝብ እንደሆነ መረዳት ይኖርበታል፡፡ ከዚህ ውጪ ያለው ፋይዳው እምብዛም ነው፡፡
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በአገር ዘርፈ ብዙ ጉዳዮች ላይ ክርክር ወይም ሙግት የሚደረግበት ሥፍራ ነው፡፡ የሕዝብ ተወካይ የሆኑ ተመራጮች ከፓርቲም ሆነ ከግላዊ ፍላጎት በላይ አገርን በማስቀደም መከራከር ይጠበቅባቸዋል፡፡ ለምክር ቤት በሚቀርቡ የተለያዩ ረቂቅ ሕጎች፣ ሪፖርቶች፣ በጀቶች፣ አስቸኳይ ውሳኔ የሚፈልጉ ጉዳዮችና ሌሎች ላይም ጥልቅና ሰፊ ውይይቶች መኖር አለባቸው፡፡ በሚቀርቡት ጉዳዮች ላይ ከድጋፍ በተጨማሪ ተቃውሞዎች ሲኖሩ ወይም የተለዩ ሐሳቦች ሲነሱ በአንክሮ መደማመጥ ተገቢ ነው፡፡ በዴሞክራሲያዊ ምርጫ ተመርጫለሁ የሚል ማንኛውም የምክር ቤት አባል ተቃውሞን ወይም የሐሳብ ልዩነትን ማጣጣል የለበትም፡፡ በገዥው ፓርቲም ሆነ በሚመራው መንግሥት ላይ ትችት ሲሰነዘርም እንደ ጠላት ከመፈረጅ ይልቅ፣ የሐሳቡ ይዘት ላይ ትኩረት በማድረግ በሰከነ መንገድ መነጋገር የዴሞክራሲ ባህል መሆኑ አይዘንጋ፡፡
የተለየ ሐሳብ ያላቸውን የሕዝብ ተመራጮች በፓርቲ ፖለቲካ ቅኝት ላይ ተመሥርቶ መመዘን ተገቢ አይደለም፡፡ ምክር ቤቱ የአገሪቱ ከፍተኛው የሥልጣን አካል በመሆኑ የሚመራበትን የአባላት ሥነ ምግባር ደንብ መሠረት በማድረግ፣ ሁሉም ድምፆች እኩል ተከብረው እንዲደመጡ ከማድረግ ባለፈ የክርክር ሒደቱን ዴሞክራሲያዊ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ የምክር ቤት አባላትም አስፈላጊ ነው የሚሉትን ሐሳብ ሲያቀርቡ ለይስሙላ ወይም ለማስመሰል ሳይሆን፣ የሚወክሉትን ሕዝብ ፍላጎት በትክክል የሚያንፀባርቅ መሆኑን ማረጋገጥ ይጠበቅባቸዋል፡፡ እያንዳንዱ አስተያየታቸውም ሆነ ክርክራቸው ወይም ጥያቄያቸው ምን ያህል ሚዛን የደፋ እንደሆነ አረጋጋጩ ሕዝብ እንደሆነ መረዳት አለባቸው፡፡ በሕዝብ ስም ማጭበርበርም ሆነ መቆመር ነውር ስለሆነ ውይይቱ ወይም ክርክሩ ደረጃውን መጠበቅ ይገባዋል፡፡ በዚህ መሠረት ምክር ቤቱ ሥራውን ማከናወን ሲችል የግልጽነት፣ የተጠያቂነትና የኃላፊነት መርህ መከበሩ ይረጋገጣል፡፡
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባልነት ለአገር ልማት፣ ዕድገት፣ ሰላም፣ መረጋጋትና ለሕዝቡ አንድነት ትልቅ ሥራ የሚከናወንበት ኃላፊነት ነው፡፡ የሕዝብ ተወካይነት በአደራ የተሰጠ ከባድ ኃላፊነት ስለሆነ ሸክሙን የሚመጥን ተግባር ይፈልጋል፡፡ ሕዝብ በድምፁ የሰጠውን አደራ ተቀብሎ በሁሉም አገራዊ ጉዳዮች ለመልካም ተግባራት መትጋት የተወካዩ ግዴታ ሲሆን፣ ይህንን አደራውን ሳይወጣ ሲቀር በሕዝብ የህሊና ዳኝነት እንደሚመዘን ማስታወስ ይኖርበታል፡፡ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት በዚህ መሠረት የተሰጣቸውን አደራ ሲወጡ ሙስናም ሆነ ብልሹ አሠራሮች አይንሰራፉም፡፡ ግልጽነትና ተጠያቂነት በተግባር ስለሚረጋገጥ የሕዝብን ፍላጎት የሚፃረሩ ውሳኔዎች አይተላለፉም፡፡ በመንግሥት አስፈጻሚ አካላት ላይ የሚደረገው ክትትልና ቁጥጥር ይጠናከራል፡፡ ሰሞኑን በተሸኙት ምትክ የሰባተኛው ምክር ቤት አባላት ሲተኩ ይህንን ጉዳይ አፅንኦት ይስጡት፡፡ የሕዝብ ውክልናን በአደራ የተቀበላችሁ ኃላፊነት ይሰማችሁ!