ሪፖርተር – Ethiopian Reporter – #1 Best and reliable news source in Ethiopia
የብሔርተኝነት ፖለቲካ ጡዘትና በአገር ላይ የሚደቅነው አደጋ
በነገደ ዓብይ
ከአንድ ዓመት በፊት በሪፖርተር ዕትም “እኔ እምለው” ዓምድ ላይ፣ “ብሔር ተኮር ፌዴራሊዝሙ ረጅም ርቀት ይወስደናልን?” በሚል ርዕስ በአንድ ጸሐፊ የተሰናዳ አንድ ወቅታዊ ጽሑፍ ማንበቤን አስታውሳለሁ፡፡ ይህንን ጽሑፍ ያስታወስኩት ዛሬ ርዕስ የማላደርገውን ነገር ግን፣ አሁን ላለንበት ምስቅልቅል የዳረገን ሕወሓት የገባበትን ቀውስ ስታዘብ ነው፡፡ እውነት ለመናገር አለመታደል ሆኖብን እንጂ፣ በአገራችን ወቅታዊ ሁኔታ ላይ ሙግትና ምክክር ማድረግ የሚያስፈልገው በእንዲህ ያለው መሠረታዊ ዕሳቤ ላይ መሆን ነበረበት፡፡ በጠቀስኩት ጽሑፍ የጸሐፊውን ሥጋትና አገራዊ ችግር እኔም የምጋራ በመሆኑ፣ የብሔር ፖለቲካው መለጠጥና መክረር ከፓርቲ ሽኩቻ አልፎ የእርስ በርስ ጦርነቱን እንዳያባብሰው፣ እንዲሁም አገርን የማያባራ ቀውስ ውስጥ እንዳይከት ያለኝን ግላዊ ሥጋት ለመሰንዘር እፈልጋለሁ፡፡
ሕወሓት መራሹ የኢሕአዴግ አገዛዝ በአገራችን አስከፊ ውጤት እያስከተለ ያለው የዘውግ ፖለቲካ ጠንሳሽ መሆኑን ታሪክ መዝግቦት ይኖራል፡፡ በእርግጥ የሥርዓቱ መገንባት መነሻዎች የቀደሙት አሀዳዊና አምባገነናዊ ሥርዓቶች መሆናቸውም አይካድም፡፡ ምንም ተባለ ምን ግን ኅብረ ብሔራዊ አንድነትና መከባበር ከሌለ፣ በእርስ በርስ ሽኩቻ በሚታመስ አገር ሉዓላዊነትን ማስከበርና የሕዝባችንን አንድነት ማስጠበቅ የሚችል ፀረ ዴሞክራሲያዊ አገዛዝ መሻሉ አይቀርም፡፡ ቢያንስ የህልውና ሥጋት አይጋረጥበትምና፡፡
አሁን እንደ አገር ለምንገኝበት አለመደማመጥ፣ በብሔርና በሃይማኖት ፅንፈኝነት መራኮት፣ ወይም በግጭትና በእርስ በርስ ጦርነት መፈጃጀት ዋነኛ መንስዔ ድህነታችን ቢመስልም፣ የሥርዓት ብልሽትና የዴሞክራሲ ምኅዳር መጥበብ መሆናቸውን ነው የፖለቲካ ሳይንስ ምሁራን የሚናገሩት፡፡ ለዚህም በዘውግ ፖለቲካ መስተጋብር ውስጥ የቆየው የማንነት፣ የእምነት፣ የታሪክ፣ የቋንቋና መሰል መገለጫዎች መፈላቀቅ ብሎም የጋራ እሴት የሌለን ሕዝቦች አስመስሎ በዕውር ድንብር መንጎድ ክፉኛ ጎድቶናል፡፡
ትናንት በትግራይ፣ አሁን በአማራ፣ ቀደም ሲል በኦሮሚያና በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልሎች ከሞላ ጎደል ሙሉ ጦርነት የተነሳባቸው ግጭቶች እየተካሄዱ ነበር፣ አሁንም ነው፡፡ በጋምቤላ፣ በደቡብና በሶማሌ ክልሎችም በተለያዩ ወቅቶች መለስ ቀለስ ያሉ የእርስ በርስ ግጭቶች የበርካቶችን ሕይወት ቀጥፈዋል፣ ንብረት አወድመዋል፡፡ እነዚህ ሁሉ አደጋዎች በአገር ላይ ያጠሉት ደግሞ የጋራ እሴትና አገራዊ መተማመንን መፍጠር በማይችሉ የብሔር ፓርቲዎችና ፖለቲከኞች መሆኑ ነው የሚያስቆጨው፡፡ ለምን ቢባል አሁን አሁን ኢትዮጵያ ውስጥ የብሔር ፓርቲ ማቋቋም ማዕድን የማውጣት ያህል የሚቆጠር አዋጭ የትርፍ ማግኛ ቢዝነስ ሆኗልና፡፡
በምንገኝበት ሁኔታ ሕወሓት ይባልም ኦነግ ሸኔ፣ አብንም ይባል ኦብነግ፣ ወይም ሌላ ነፃ አውጭና መሰል ኃይሎች በሙሉ የብሔር ካባ ውስጥ የተወሸቁ ፓርቲዎችና የፖለቲካ ስብስቦች ናቸው፡፡ ገዥው ፓርቲ ብልፅግናም ቢሆን በስያሜው አንድ አገራዊ ፓርቲ ይምሰል እንጂ፣ ከብሔር ኮርቻ ላይ መውረድ ያልቻለ በብሔር ቅርንጫፍ ፓርቲዎች ድስት እየተንተከተከ ያለ አልጫ ወጥ ነው የሚሉ ተቺዎች ትንሽ አይደሉም፡፡ እንዲህ ያለ የብሔርና የሃይማኖት ጥላ ይዞ የሚያባላ ፖለቲካ ማራመድ የሚቻለው ደግሞ እኛው መከረኞቹ ኢትዮጵያውያን ላይ መሆኑ ነው የሚያስቆጨው፡፡
በዘውግ ፖለቲካ መዘዝ እየተካረረ ቀስ በቀስ እየፈረጠመ የመጣው ዕሳቤ እየተባባሰ ለመሄዱ ምርጫ ሲመጣ የሚታየው የብሔርተኛው ካምፕ ሽርጉድ ነው፡፡ ቀደም ብዬ የዋና ዋናዎቹን ምሳሌ አነሳሁ እንጂ በአንድ ወቅት በደቡብ ክልል እንደ ወብን (ወላይታ ብሔራዊ ንቅናቄ)፣ ሲብን (ሲዳማ ብሔራዊ ንቅናቄ)፣ ጉብን (ጉራጌ ብሔራዊ ንቅናቄ)፣ ወዘተ የመሳሰሉ ከኅብረ ብሔራዊነት ይልቅ የጎሳ መንገድ ቀያሾች እየተቀፈቀፉ የነበሩት ሥርዓቱ የሚያበረታታው ይህንን ወልጋዳ መንገድ በመሆኑ ነው፡፡
በእርግጥም ባለፉት 34 ዓመታት በአገሪቱ በዘውጌ ፖለቲካ ከመንሳፈፍ ባሻገር፣ ስለአንድነት ማውራትም ሆነ መሥራት የሚያስፈራ (የሚያስወነጅል) ሆኖ መቆየቱ ለችግሩ መባባስ በር አልከፈተም ማለት አይቻልም፡፡ ኢሕአዴግም ሆነ ብልፅግና በብሔር ፖለቲካ ጉዳይ “ስልቻ ቀልቀሎ፣ ቀልቀሎ ስልቻ” መሆናቸው ዳፋው እየገረፈን ይገኛል፡፡
በመላው ዓለም በተግባር ላይ የዋለው የዜግነት ፖለቲካ ወይም በሐሳብ ትግል የሚያምነው ርዕዮተ ዓለማዊ ፖለቲካ በእኛ ሁኔታ አለ ሊባል አለመቻሉ ግን እንደ እርግማን የሚቆጠር ነው፡፡ ሌላው ይቅርና ኅብረ ብሔራዊ መልክ የነበራቸው የፖለቲካ ስብስቦች (ቅንጅት፣ የኢትዮጵያ አንድነት ኃይሎች፣ ኅብረት፣ ኢዴፓ፣ ሰማያዊ ፓርቲ፣ አርበኞች ግንቦት ሰባት፣ ኢዜማ) ጥንጣን እንደ በላው ግንድ እንክትክታቸው የወጣው ለምንድን ነው ብሎ ጥናት ማካሄድ አልተቻለም፡፡ ቁጭት መፈጠሩንም ማወቅ አይቻልም፡፡ የመከኑ መምሰላቸውም ነው የሚያሳዝነው፡፡
ይልቁንም ከዓመት ዓመት የብሔር ውዝግብና ትርክቱ እየፋፋ፣ መገፋፋትና መገዳደሉ እየደለበ በመቀጠሉ የብሔር ፅንፈኛው (ለዘብተኛ የነበረው የአማራ ብሔርተኝነትን ጨምሮ) ከዴሞክራሲያዊ ትግልና መደማመጥ ይልቅ ወደ አመፃ ወርዷል፡፡ እናም የለውጥ ተስፋ በተጣለባቸው ያለፉት አምስት ዓመታት ገደማ በከፍተኛ መጠን የንፁኃን ሞት፣ እንግልትና መፈናቀል ተባብሶ እንደቀጠለ ነው፡፡ አገራችንም በማይገመት ሁኔታ ወደ አስከፊ የእርስ በርስ ጦርነት ተረማምዳለች፡፡ ስለሆነም የችግሩን ምንጭ ከሥር መሠረቱ ከመመርመር የተሻለ መፍትሔ ማማተር የማይቻል ሆኗል፡፡
በእርግጥ ባለፉት ዓመታት የብሔርተኝነት ፌዴራሊዝሙና ፖለቲካው መዘዝ የከፋ ጉዳት ሳያስከትል፣ በሠለጠነ መንገድ የሚስተካከልበት የፖለቲካ ትግል መደረግ ሊጀምር ነው የሚል ተስፋ ብልጭ ብሎ መልሶ ተዳፍኗል፡፡ በተለይ ባለፉት ሦስት ዓመታት ገደማ በተለይ ከትግራይ ኃይሎች በኩል በተጀመረው ጦርነት ነገሩ ሁሉ የባሰ ከድጡ ወደ ማጡ ወርዷል፡፡ ያ ክስረት የመቶ ሺዎችን ሕይወት ቀጥፎ ሳያስተምረን እነሆ አሁንም በርከት ባሉ አካባቢዎች የብሔር ገጽታ ያላቸው አመፆችና ፍጅቶች እየታዩ ነው፡፡ መቼ ነው የሚያቆመው የሚለው ዋናው ጥያቄ ነው፡፡
ከላይ በመግቢያዬ የጠቀስኳቸው ጸሐፊ እንዳሉት የብሔር ፖለቲካው መካረር መዳረሻው መበታተን እንዳይሆን መጠንቀቅ አለብን፡፡ በነገራችን ላይ በብሔር ፅንፈኝነት የተላለቁት ሩዋንዳዊያን እንኳን በዘር ፖለቲካ መዘዝ የከፋ ዋጋ ከከፈሉ በኋላ መደራጀት አይደለም፣ ስለብሔር መነጋገርን ጭምር በሕግ ከልክለዋል፡፡ ኬንያና ታንዛኒያ የዜግነት ፖለቲካ እንጂ በብሔር የመደራጀትን ስም ሊያነሱት አይፈልጉም፡፡ እኛ ግን እየተዳማንበትና እየተላለቅንበት እስከ የት ድረስ እንቀጥላለን ነው ተብሎ ነው በአፅንኦት መጠየቅ ያለበት፡፡
ሌላው ቀርቶ የቀደመ ፌዴራሊዝም ተሞክሮ አላት የምትባለው ናይጄሪያ በማንነት ላይ የተመሠረተ አከላለል ውድ ዋጋ ካስከፈላት በኋላ፣ የሥርዓቱን ቅርፅና ይዘት ቀይራ ነው ዕፎይ ያለችው የሚሉ ጥናቶች አሉ፡፡ እነ ደቡብ ሱዳን፣ ኮንጎ፣ መካከለኛው አፍሪካም ይባሉ ሌሎች የአፍሪካ አገሮች ወደ ወደቁ አገርነት ተርታ እየወረዱ ያሉት በዋናነት በዘርና በማንነት ላይ ያተኮረ የሥልጣንና የሀብት ማጋበስ ፍላጎት እያራኮታቸው መሆኑም አይታበልም፡፡ እንዲሁም ዴሞክራሲውን በመድፈቃቸውና አገራዊ አንድነታቸውም እየተሸረሸረ በመሄዱ ነው፡፡ ታዲያ ምን ለማግኘት ነው የኢትዮጵያ ፖለቲከኞች ብሔር ላይ መንገታገት፡፡
በእኔ እምነትና ቀደም ሲል ከጠቃቀስኳቸው ዕይታዎች አንፃር፣ በአገራችን አሁን እያጋጠመ ላለው አገራዊ ፈተና በዋናነት በሕዝቦች መካከል አለመተማመን እየፈጠረ ያለው የዘውግ ትርክትና የብሔረሰብ ፍጥጫ ነው ማለት ስህተት የለውም፡፡ በግልጽ እንደምንመለከተው ንፁኃንን የሚገድሉና የሚያፈናቅሉ ታጣቂዎች፣ ሙሰኞች ወይም ወንጀል ፈጻሚዎች በድርጊታቸውም ሆነ ባጠፉት ወንጀል ሊጠየቁ ሲገባ፣ ግጭቱን ሕዝባዊ ካባ በማላበስ ወይም ማንነት ውስጥ በመደበቅ ለማምለጥ የሚፈልጉት መደበኛ ሥራ ያደረጉት የብሔር ፖለቲካን ስለሆነ ነው፡፡
እዚህ ላይ ላነሳው የምፈልገው ብዙዎቹ ብሔርተኞች በሕግ የሚያስጠይቃቸው ነገር ሲኖር፣ ሮጠው የመጡበት ብሔር ወይም ብሔረሰብ ጉያ ለመግባት ማንም አይቀድማቸውም፡፡ እንወክለዋለን ወይም እንታገልለታለን የሚሉትን ብሔር ወይም ብሔረሰብ፣ ከሚያጋብሱት ጥቅም አንዲት ስባሪ ሳንቲም አያቀምሱትም፡፡ ትምህርት ቤት፣ ክሊኒክ፣ መንገድና ሌሎች መሠረተ ልማቶች እንዲዳረሱት ከመታገል ይልቅ በየቀኑ ስሙን እያነሱ ይነግዱበታል፡፡ ልክ የካርታ ቁማርተኛ ለክፉ ጊዜ መጠባበቂያ “ጆከር ካርታ” እንደሚይዘው፣ እነሱም አንድ ችግር ወይም የሕግ ተጠያቂነት ሲገጥማቸው ለኑሮ ዕድገቱ የማያስቡለትን ብሔር ወይም ብሔረሰብ ይመዛሉ፡፡
ለዚህ ተልዕኮአቸው ስኬት ደግሞ ከብሔሩ ወይም ከብሔረሰቡ ውስጥ የሚመለመሉ ግብረ በላዎች ከኋላቸው ይሠለፋሉ፡፡ እነ ጃዋር መሐመድ እንዲህ ዓይነቱን ቁማር እንዴት ተጫውተው አላዋጣ ሲላቸው ሸብለል እንዳሉ ማስታወስ ጠቃሚ ይመስለኛል፡፡ በርካታ ሚሊዮን ብሮችን የሚያስገኝ ብሔር ወይም ብሔረሰብ የሚባል የመቆመሪያ ማሽን ለባለቤቶቹ የክፉ ጊዜ መሸሸጊያ ሲሆን፣ የማይፈልጉትን ብሔር ወይም ብሔረሰብ ለማጥቂያ ሁነኛ መጠቀሚያቸው ነው፡፡
አሁን በተጨባጭ እየታየ እንዳለው አገር ወዳዶችን በአብዛኛው ወደ ጠንካራ ኅብረ ብሔራዊ አንድነት መምጣት አለብን በሚሉ ኃይሎችና የዘውግ ፌዴራሊዝሙና የብሔር አከላለሉ እንዲቀጥል በሚፈልጉ ኃይሎች መካከል የተፈጠረው ተቃርኖ፣ አገርን ወደ ጦርነት ከትቶ ምስቅልቅል እየፈጠረ ነው፡፡ ለውጥ አመጣ የተባለው መንግሥትም የጀመረውን አገራዊ ብሔርተኝነት ሽሮ በመጣበት የትርክት ማዕበል ውስጥ ይላጋ ይዟል፡፡
ተደጋግሞ እየተባለ እንዳለው የብሔር ብሔረሰቦች መብትም ሆነ ፍትሐዊ ተጠቃሚነት መከበር አለበት፡፡ ኢትዮጵያ ለስድስት ሺሕ፣ ለሦስት ሺሕም ይባል ለ150 ዓመታት ያላትን የአገረ መንግሥትነት ተሞክሮ በመሸርሸር አጥፊ ፖለቲካ ለማራመድ መሞከር ግን ሥርዓተ መንግሥቱን ከመፍረስ አያድነውም፡፡ ለዘመናት ተሳስረው፣ ተዋልደውና ተዋህደው የኖሩ ሕዝቦችን ሁለንተናዊ መስተጋብር በዘውጌ ፖለቲካ መበጣጠስም ከወንጀልም በላይ የከፋ ወንጀል ነው፡፡ ከወዲሁ ስለመፍትሔው ካልታሰበም አገር ማፍረሱ አይቀሬ ነው፡፡
ኢሕአዴግ መራሹ ሥርዓት (ብልፅግናም የደገመው) ለከፋፍለህ ግዛው ሥልት (Divdid and Rule) ይጠቅመኛል ብሎም ይሁን፣ ብዙኃኑን ሕዝብና ከፍተኛ ውህደት የፈጠረውን ወገን በማለያየት የሥልጣን ጊዜውን ለማራዘም የተጠቀመበት መንገድ አገርን ወደ ውድቀት ሲወስድ ነበር የቆየው፡፡ አሁን በተጨባጭ አሉታዊ ጉዳቱ የመከራ ሰብል እያሳጨደን ይገኛል፡፡
እውነት ለመናገር በአገሪቱ ለተዘራው አብሮ የማያኗኑር የዘረኝነት ችግርና ነጣጣይ ፖለቲካ ዋናው ግብዓት በጎሳ ላይ የተመሠረተው ፌዴራሊዝምና ዘውጌ ተኮሩ ሕገ መንግሥት ናቸው የሚሉ ሰዎች መደመጥ አለባቸው፡፡ ተስፋ ያላት አገር ወደ ውድቀት ችግሩ ላይ በማተኮር መነጋገር የግድ መሆን አለበት፡፡ ምንም ተባለ ምን ኢትዮጵያውያን ከመቼውም ጊዜ በላይ በሚባል ደረጃ የመለያየት አባዜ ውስጥ ገብተን መባዘናችንን ማስተባበል አስቸጋሪ የሆነው ከቆምንበት እውነታ በመነሳት ነው፡፡
ቀደም ባሉት ዓመታት አገራዊ አብሮነትና ዴሞክራሲያዊ አገራዊ ብሔርተኝነትን ከመገንባት ይልቅ በመንግሥት ደረጃ፣ ‹‹ዓላማችን የአማራን ብሔርተኝነት ማፋፋም ነው›› ሲባል በመቆየቱ፣ አሁን የአማራ ብሔርተኞች አካሄድ እንደ ፍም እሳት ቢጨብጡት የማይያዝና አደገኛ ሊሆን ችሏል፡፡ ሌላውም ቢሆን ከሥጋትም ሆነ ከጥገኝነት ዕሳቤ በብሔር አጥር ገብቶ መተራመስን እንደመረጠ ነው፡፡ አካሄዱ ግን በፍፁም አገር ሊያቆም አይችልም፣ ይበታትነን እንደሆን እንጂ፡፡
በመነሻዬ የጠቀስኳቸው ጸሐፊ እንዳሉት አሁን በየክልሉ ብቻ ሳይሆን፣ በየዞንና በየወረዳው የብሔር ፖለቲከኛ፣ ተንታኝም ይባል አክቲቪስት የማንነት አጀንዳን እንደ አልፋና ኦሜጋ ተጣብቶ እንደ ጉድ እየተቀፈቀፈ ነው፡፡ በገዥው ፓርቲ ደረጃ ሳይቀር “የእኔ… የእኔ…” ባይነቱም ጣሪያ ነክቷል (ይህ አገራዊ መንሸራተት የሰነበተ ቢሆንም አገራዊ ለውጥ እየመጣ ነው በሚባልበት ዘመንም ተባብሶ መቀጠሉ ሲታይ፣ እንደ አገር ሥርዓታዊ ማሻሻያ ሳይሆን መሠረታዊ ለውጥ በሁሉ አቀፍ ሽግግርና ዕርቅ መምጣት እንዳለበት አመላካች ነው)፡፡
አሁን ኢትዮጵያውያን በአንድ የጋራ መድረክና የመተማመን መንፈስ የሚያቆሙን የወል አገራዊ እሴቶቻችን ሸርሽረናል፡፡ እምነት፣ ኅብረትና መረዳዳት የመሳሰሉትን ግዙፍ የኢትዮጵያዊነት የሞራል እሴቶች በብሔር መፈላለግ ብቻ ለመመንዘር ይዳዳን ከጀመረም ከራርመናል (ለዚህ ደግሞ ትልቁ ችግር ከኢትዮጵያዊነት ይልቅ ለብሔር ሙሉ ዕውቅና የሰጠው ከፋፋይ ሕገ መንግሥት፣ ለተዛባ ግንኙነትና ለጥላቻ ፖለቲካ ዕውቅና ያልነፈገው የቃል ኪዳን ሰነድ አለመታረሙ የአንበሳውን ድርሻ ይወስዳሉ የሚሉ ወገኖች ብዙ ናቸው)፡፡
እውነት ለመናገር ልጡን በምናላቸው ወይም በዕድገት ግስጋሴ ምህዋር ውስጥ ባሉ አገሮች ግን ይህ ብሂል ጭራውም የለም ለማለት ይቻላል፡፡ ለአብነት ያህል የሁሉ አርዓያ የምትባለው አሜሪካ ሕዝብን ልማድ ብንወስድ የመጀመሪያ መርህ፣ “አንድ ከሆንን እንቆማለን፣ ከተከፋፈልን እንወድቃለን” (United We Stand, Divided We Fall) የሚል ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ አሁን እኛ የምንርመጠመጥበትን የታሪክ ምዕራፍ አሜሪካኖቹ አላለፉበትም ባይባልም፣ በፍጥነትና ላይመለሱበት ነው የተሻገሩት ማለት ግን ይቻላል፡፡
በአንድነታቸውና በሕገ መንግሥታቸው ጉዳይ የማይደራደሩ መሆናቸውም የሚታወቅ ነው፡፡ ሌላው ይቅር ብዝኃነት ያለው ሕዝብ በአንድ ሉዓላዊ ምድር ውስጥ እንደመገኘቱ የአሜሪካ “ሕዝቦች” ሳይሆን “ሕዝብ” የሚል የአንድነት ስያሜ እንዲኖር ሆን ተብሎ የተደረገ ነው፡፡
እነሱ በታሪክ እንደሚታወቀው ከዚያና ከእዚህ ተቀላቅለው (ስፓኒሽ አሜሪካ፣ ፖርቱጊዝ አሜሪካ፣ አፍሪካን አሜሪካ…) የገነቧትን አገር በአንድነት ገመድ እያስተሳሰሩ ለእኛ ግን ነጣጣይና ዘረኛ ፖለቲካ ሲረጩብንና ሲያፋጁን ነው የኖሩት፡፡ አሳዛኙ ጉዳይ ደግሞ ለዘመናት በአንድነት እየኖርን የተዛቡ ችግሮችን በጋራ ብናልፍም፣ አሁን እንኳን በዴሞክራሲያዊና በአንድነት መንፈስ መቀጠል ሲገባን በብሔር ፖለቲካና በአክራሪ ብሔርተኝነት ውስጥ መዋኘታችንን ቀጥለናል (ፈጥኖ ከችግሩ መውጣት ካልተቻለም የብሔር ፅንፈኝነት የሚበታትነን ተግዳሮት ነው)፡፡
እንደ አገር የነበረንን ጠንካራ ፀጋ በብሔር ፍጥጫ ለውጠን ቀስ በቀስ መተማመንና መከባበርን እንደ በረዶ ስንንድ፣ መንግሥትን ጨምሮ ሌሎች ተቆጪዎች አለመኖራቸው ያስደንቃል፡፡ አሁን የብልፅግና መንግሥት ችግሩን ተገንዝቦ “ተው!” ማለት የጀመረ ቢመስልም፣ ከጥፋቱ የቀደመ የእርምት ዕርምጃ መታየት አለመቻሉ ጥፋቱን ለማረም አላስቻለም፡፡ ችግር በለውጥ ውስጥ አይቀሬ ቢሆንም የከፋ መስዋዕትነት እያስከፈለ የሚገኘው፣ መንግሥት ከልብ መሠረታዊ ለውጥና ዕርቅ ለማካሄድ ዳተኛ በመሆኑ ነው የሚሉት በርካቶች ናቸው፡፡
በአጠቃላይ በተጀመረው ሰላም የማፈላላግ ሙከራም ሆነ በአገራዊ የምክክር ኮሚሽን ጥረት መግባባትና ዕርቅ የማምጣት ዕርምጃ ሊታሰብበት የሚገባ ቀዳሚ ዕርምጃ ነው፡፡ የብሔር ፖለቲካ መካረርን የሚያረግብና ኅብረ ብሔራዊ አንድነትን የሚያመጣ የሥርዓት ማሻሻያ መፍጠር ሊሆን ይገባል፣ የግድም ነው፡፡ ካልሆነ ግን መተላለቁን ማስቀረት እንደሚታሰበው ቀላል አይሆንም፡፡ ለዚህ ደግሞ ሕወሓት ለሌሎች ደግሶ ራሱ የገባበትን አጣብቂኝ ማየት በቂ ነው፡፡
ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡
The post የብሔርተኝነት ፖለቲካ ጡዘትና በአገር ላይ የሚደቅነው አደጋ first appear on ሪፖርተር – Ethiopian Reporter – #1 Best and reliable news source in Ethiopia and is written by አንባቢ