‹‹እስካሁን በነበረው ሒደት 14 ሺሕ ነጋዴዎች ተሳትፈዋል››
አምባየ ኡጋቶ (ዶ/ር)፣ የኢትዮጵያ አገራዊ ምክክር ኮሚሽነር
ሐምሌ 8 ቀን 2018 ዓ.ም. በአዲስ አበባ እንደሚጀመር በኢትዮጵያ አገራዊ ምክክር ኮሚሽን በተገለጸው አገራዊ ምክክር ጉባዔ ላይ ሁሉንም የንግድ ማኅበረሰብ አላካተተም የሚል ከንግዱ ማኅበረሰብ የአካታችነት ጥያቄ ቀረበበት፡፡
የኢትዮጵያ የንግድና ዘርፍ ማኀበራት ምክር ቤት ከአገራዊ ምክክር ኮሚሽን ጋር በመተባበር ‹‹የግሉ ዘርፍ ሚና በአገራዊ ምክክር ሒደት›› በሚል መሪ ሐሳብ ሰኔ 10 ቀን 2018 ዓ.ም. ባዘጋጀው መድረክ፣ ከተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች የተውጣጡ የንግዱ ማኅበረሰብ አባላት፣ የኮሚሽኑ አመራሮችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በተገኙበት ነው ጥያቄው የተነሳው፡፡
ለውይይቱ መነሻ የሚሆኑ ጽሑፎች በፖለቲካ ሳይንስ ተመራማሪዎች የቀረቡ ሲሆን፣ በኮሚሽኑ በኩል ደግሞ እስካሁን ያከናወናቸው ተግባራት ተዘርዝረዋል፡፡
የትግራይ ክልል የንግድ ማኅበረሰብን መወከላቸውን የገለጹ አንድ ተሳታፊ በኮሚሽኑ አካታችነት ላይ ያላቸውን ጥያቄ ሲያቀርቡ፣ አብዛኛው የኢትዮጵያ ክፍል አገራዊ ምክክርን በሚመለከት ተሳትፎ ማድረጉን መመልከታቸውን፣ ነገር ግን በትግራይ የመገለልና የመገፋት ሁኔታ መኖሩ እንደሚታይ ገልጸዋል፡፡
‹‹እኔ የምወክለው የንግዱን ማኅበረሰብ ነው፣ ፖለቲከኛ አይደለሁም፤›› ያሉት ተሳታፊው፣ እንደ ንግድ ማኅበረሰብ ደግሞ ሠርቶ የመለወጥና ለአገሪቱም ዕድገት አስተዋጽኦ የማበርከት ፍላጎት መኖሩን ጠቁመዋል፡፡ በክልሉ የነበረው ጦርነት ጥሎት ያለፈው ጠባሳ አሁንም መኖሩን፣ ማኅበረሰቡ እንደ ኢትዮጵያዊ መታየት እንዳለበት፣ ነገር ግን አሁን ያለው ሁኔታ ይህንን የሚገልጽ አለመሆኑን ተናግረዋል፡፡
From The Reporter Magazine
በጦርነት ምክንያት እንደ ማኅበረሰብ ከደረሰው ጉዳት በተጨማሪ፣ የንግድ ማኅበረሰቡ ከሙሉ በሙሉ ውድመት እስከ ኪሳራ ደርሶበታል ሲሉ ገልጸዋል፡፡ የነጋዴውን ችግር በሚመለከት እስካሁንም ምንም ዓይነት መፍትሔ አላገኘም ያሉት ተሳታፊው፣ ‹‹አሁን ላለው ችግር መፍትሔ ካላገኘን ለዘመናት ለተጠራቀሙ ችግሮች መፍትሔ ይገኛል የሚለው ነገር ተስፋ የሚያስቆርጥ ነው፤›› ብለዋል፡፡
ከሲዳማ ክልል ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት የተወከሉ ሌላው ተሳታፊ፣ ‹‹ከዚህ ቀደም የወል እንጂ የጋራ አገር አልነበረንም፤›› ብለው፣ አገራዊ ምክክር ኮሚሽን መንግሥታት በየጊዜው እየወዘፉት የመጡት ችግር መጨረሻ ላይ አገር እንዳይኖር ወደ ማድረግ ሲቃረብ የተቋቋመ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የአገሪቱ የሰላም ሁኔታ የንግዱን ማኅበረሰብም በከፍተኛ ሁኔታ የሚመለከተው መሆኑንና የራሱን አስተዋጽኦ ማበርከት እንደሚኖርበትም ጠቁመዋል፡፡
ነገር ግን ነጋዴውን ወክለው በአገራዊ ምክክር ጉባዔው ስለሚቀርቡ ተወካዮች ያላቸውን ጥያቄ ሰንዝረዋል፡፡ ‹‹ነጋዴውን ወክለው የሚቀርቡትና የንግዱን ማኅበረሰብ ድምፅ የሚያሰሙት እነማን ናቸው? የሚለው መታወቅ አለበት፤›› ያሉት ተሳታፊው፣ ‹‹እኔ የምጠይቀው ስለሲዳማ ነው፣ ውክልናችን እንዴት ነው የመጣው?›› በማለት ጠይቀዋል፡፡
From The Reporter Magazine
የተሰበሰቡት አጀንዳዎች በሒደት መፍትሔ ይሰጣቸዋል ከተባለ እስከ መቼ የሚለው መመለስ ይገባዋል በማለት ሐሳባቸውን ያቀረቡት ደግሞ፣ ከደቡብ ኢትዮጵያ የንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት መምጣታቸውን የገለጹ የውይይቱ ተሳታፊ ናቸው፡፡
መንግሥት ኃላፊነቱን በመውሰድ አገሪቱ ውስጥ ችግር አለ ካለና ይህም ከበፊት ጀምሮ የመጣ ነው ብሎ የሚያስብ ከሆነ፣ ከራሱ ከመንግሥት የሚመነጩ አዳዲስ ችግሮች ወይም ዝም እያለ የሚመለከታቸውን ችግሮች ኮሚሽኑ እንዴት ነው የሚመለከታቸው በማለት ጥያቄያቸውን አቅርበዋል፡፡
‹‹እዚህ ሰላም ፈልገን ለሰላም እየሠራን በሌላ ወገን ደግሞ ሰላምን የሚያደፈርሱ ወይም እንዲደፈርስ የሚያደርጉ አካላት፣ ሐሳብ ከመስጠት ጀምሮ የሚያደርጉትን ድርጊት ሲመለከት ኮሚሽኑ ምን ይሠራል?›› ብለዋል፡፡
በሐምሌ ከሚጀመረው ጉባዔ በኋላ ሁሉም ችግሮች በአንዴ ይፈታሉ ብሎ ማኅበረሰቡ እየጠበቀ መሆኑን፣ ነገር ግን በአንዴ መፍትሔ ሊመጣ እንደማይችል ለማኅበረሰቡ ማስገንዘብ እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል፡፡
‹‹በኢትዮጵያ በተለያዩ ቦታዎች ግጭቶች ነበሩ፤›› በማለት ምላሽ መስጠት የጀመሩት የኢትዮጵያ አገራዊ ምክክር ኮሚሽነር አምባየ ኡጋቶ (ዶ/ር) በትግራይና በኦሮሚያ፣ በተለይም በምዕራብ ኦሮሚያ ግጭቶች እንደነበሩና በዚህም ለረዥም ጊዜ ሲነሱ የነበሩ ጥያቄዎች ምላሽ እንዳላገኙ ተናግረዋል፡፡
አገራዊ ምክክር የተጀመረውም አገሪቱ በዚህ ሁኔታ ውስጥ እያለች በመሆኑ ኮሚሽኑ የተሰጠውን ኃላፊነት ለመወጣት የአሠራር ሒደቶች መፍጠሩን፣ ነገር ግን ከዚህ ጀምሩ የሚል የተሰጠ አቅጣጫ እንዳልነበር ገልጸዋል፡፡
ከአካታችነት አኳያም ኮሚሽኑ በሕግ ጭምር ስለሚገደድ ከወረዳ መጀመሩን፣ ለረዥም ጊዜ በፖለቲካ የተገለሉ ዜጎች ስለነበሩ ይህንንም ከግምት ውስጥ ያስገባ ሥራ ሲከናወን እንደቆየ ጠቁመዋል፡፡ ዜጎች በሒደቱ እንዲሳተፉ ሲደረግም የተደራጁባቸውን መንገድ ለመጠቀም መሞከሩን አስረድተዋል፡፡
የሲዳማ ክልልን ጨምሮ በሁሉም አካባቢዎች ነጋዴ ነን ያሉ አካላት መሳተፋቸውን፣ በአጠቃላይ በሒደቱ 14 ሺሕ ነጋዴዎች መሳተፋቸውን ገልጸዋል፡፡
የትግራይ ክልልን በሚመለከት በወቅቱ በክልሉ ጦርነት ስለነበረ ኮሚሽኑ ማድረግ የሚችለው ነገር እንዳልነበረና ከስምምነቱ በኋላ ግን ሚዲያዎችን፣ ምሁራንን፣ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶችንና ጊዜያዊ አስተዳደሩን አግኝተው ማነጋገራቸውን አብራርተዋል፡፡ ኮሚሽኑ በማኅበረሰቡ ዘንድ የሚነሱ ጥያቄዎችን ለመፍታት ኃላፊነት ባይኖረውም ለሚመለከታቸው አካላት ማድረሱን አስታውሰዋል፡፡ ‹‹ጥያቄው መሆን ያለበት ሒደቱ ወደፊት እንዲሄድ ያልተፈለገው ለምን እንደሆነ ነው፤›› ብለዋል፡፡
ነገር ግን የትግራይ ክልል በሒደቱ መካተት አለበት ተብሎ 300 ከትግራይ ክልል የመጡና በአጠቃላይ 701 የሚሆኑ ተሳታፊዎች ተገኝተው አጀንዳዎቻቸውን ማስረከባቸውን፣ ሆኖም የሚነሱ አንዳንድ ጥያቄዎች በኮሚሽኑ በኩል የሚፈቱ እንዳልሆኑና ኮሚሽኑ በመንግሥት የሚከናወኑ ሥራዎችን ተክቶ መሥራት እንደማይችል በማስታወስ፣ በተሰጠው ኃላፊነት ብቻ መሥራት እንደሚችል ጠቁመዋል፡፡
ለውይይቱ መነሻ የሚሆን ሐሳብ ያቀረቡት የፖለቲካ ሳይንስ ተመራማሪና መምህር ሰሚር የሱፍ (ዶ/ር)፣ ለዘመናት በአገሪቱ የተከማቸውን ችግር በሦስት ወራትና በአንድ ዓመት ውይይት መፍታት እንደማይቻል መገንዘብ እንደሚያስፈልግና አገራዊ ምክክር ችግሮችን ለመፍታት መደላድል የሚፈጠርበት አጋጣሚ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በአገር አቀፍ ደረጃ እያንዳንዱ ችግር ብያኔ ስምምነት ላይ አለመደረሱን የሚያነሱት ሰሚር (ዶ/ር)፣ ዴሞክራሲ፣ የቡድን መብት፣ የብሔር መብትና አገራዊ አንድነት ሲባል ምን ማለት እንደሆነ የሚለው ላይ የጋራ ትርጓሜ ባለመኖሩ፣ ምክክሩ የጋራ ብያኔ የሚገኝበት መድረክ መሆን እንደሚገባው አሳስበዋል፡፡
በመሠረታዊነት የሚቀርቡ እንደ ግለሰብ መብት፣ የቡድን ጥያቄ፣ ልማትና አገራዊ ስሜት ያሉ ጉዳዮች አንድ በአንድ እየፈቱ የመሄድ ዕድል እንደማይኖርና ከዚያ ይልቅ በጋራ ሊፈቱ የሚገቡ ጉዳዮች መሆናቸውን አብራርተዋል፡፡
አገራዊ ምክክር የሚያመጣው አገራዊ መግባባት፣ በሚያከራክሩ መሠረታዊ ጉዳዮች ላይ መስማማት እንደሚኖር መውሰድ እንደማይገባ፣ ነገር ግን ሒደታዊ መግባባት ላይ ማተኮር እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል፡፡ ምክክሩ ውጤታማና አመርቂ በሆነ መንገድ ቢከናወን እንኳን መሠረት መጣያ እንጂ ችግሮችን መፍቻ መሣሪያ ስለማይሆን፣ ከጉባዔው በኋላ ባሉ ሒደቶች ተመሳሳይ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ አስረድተዋል፡፡
የሰላም ዕጦት በአገር ኢኮኖሚ ላይ የሚያደርሰውን ተፅዕኖ ያብራሩት የኢትዮጵያ የንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ዋና ጸሐፊ ቀነኒሳ ለሚ (ዶ/ር)፣ ሰላም ሲጠፋ የመጀመሪያ ተጎጅ የሚሆነው የግል ዘርፉ በመሆኑ፣ በሰላም ግንባታ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማድረግ እንደሚኖርበት አሳስበዋል፡፡
በሰላም ዕጦት ምክንያት የዓለም ኢኮኖሚ ከፍተኛ ቀውስ ውስጥ መግባቱንና ለአብነትም አፍሪካ በዓመት አንድ ትሪሊዮን ዶላር እንደምታጣ ጠቁመዋል፡፡ የዓለም ባንክን ግምት በመግለጽም ኢትዮጵያ በሰሜኑ ጦርነት ከ20 ቢሊዮን ዶላር በላይ ማጣቷን ገልጸዋል፡፡
እነዚህን ችግሮች ለመከላከል አገራዊ ምክክርን እንደ አንድ መፍትሔ መጠቀም እንደሚገባ፣ በተለይም ዜጎች ቅሬታቸውንና የፖለቲካ አመለካከታቸውን በግልጽ እንዲወያዩ ማድረግ ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
አክለውም በዜጎች መካከል መተማመን እንዲኖር በማድረግና አካታችነትን በማስፈን፣ ብሔራዊ አንድነት እንዲመጣ አገራዊ ምክክር ትልቅ መንገድ የሚከፍት መሆኑን አስረድተዋል፡፡
