
ከሰሞኑ የኢትዮጵያ መንግሥት ከዚህ ቀደሞቹ ሁሉ ጠንከር ያለ አቋም በኤርትራ ላይ አንፀባርቋል፡፡ እሑድ ዕለት በውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ በጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) ተፈርሞ በቀጥታ ለኤርትራ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኦስማን ሳለህ የተላከው ደብዳቤ፣ ኤርትራን በሚመለከት ጠንከር ያሉ ክሶች ተዘርዝረውበታል፡፡ ኤርትራ የኢትዮጵያን ሉዓላዊ መሬት በቀጥታ ከመውረር ባለፈ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ የተለያዩ የትጥቅ ቡድኖችን እንደምትደግፍ ጭምር በመጠቆም፣ የኢትዮጵያን ሉዓላዊነትና የግዛት አንድነት እየተዳፈረች መሆኑን በመግለጽ ነው የሚንደረደረው፡፡ የቅርብ ጊዜ ሁነቶችን ጭምር ዋቢ በማድረግ ይህን ክስ የሚያጠናክረው ደብዳቤው፣ የኢትዮጵያ መንግሥት የኤርትራን ጥፋቶች የሚታገስበት ትዕግሥት እየተሟጠጠ መምጣቱንና ወደ ድርድር እንዲገባ በቀጥታ ለኤርትራ አቻው መልዕክቱን ያስተላልፋል፡፡


‹‹ባለፉት ጥቂት ቀናት የኤርትራ መንግሥት ጉዳዩን የሚያባብሱ ዕርምጃዎችን እየወሰደ ነው፡፡ በሰሜን ምሥራቃዊ የኢትዮጵያ ክፍል የኤርትራ ወታደሮች ድንበር ጥሰው ገብተዋል፡፡ በሰሜን ምዕራባዊ የኢትዮጵያ ድንበር ክፍል ደግሞ ከኢትዮጵያ አማፂያን ጋር ወታደራዊ ልምምድ አድርገዋል፡፡ እነዚህ እንቅስቃሴዎች ደግሞ ትንኮሳ ብቻ ሳይሆኑ ቀጥተኛ ወረራዎች ጭምር ናቸው፡፡ ይህን ተቀባይነት የሌለው ድርጊት ለማስቆም ሲባልም፣ የኤርትራ መንግሥት ከወረራቸው የኢትዮጵያ መሬቶች በአስቸኳይ ለቆ እንዲወጣና ከአማፂያን ጋር የሚያደርገውን መተባበር በአስቸኳይ እንዲያቆም በይፋ እንጠይቃለን፤›› በማለት ነው ደብዳቤው የኤርትራ መንግሥትን በግልጽ ያሳሰበው፡፡
ደብዳቤው ሲቀጥልም፣ ‹‹ለረዥም ጊዜ በግጭትና በአለመተማመን ሽክርክሪት ውስጥ ወድቆ የዘለቀውን የኢትዮጵያንና የኤርትራን ግንኙነት በንግግርና በዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትን በማጠናከር መቀየር ይቻላል ብለን እናምናለን፡፡ የኤርትራ መንግሥት የኢትዮጵያን ሉዓላዊነትና ግዛታዊ አንድነት ለማክበር አዎንታዊ ምላሽ እስከሰጠ ድረስ፣ የኢትዮጵያ መንግሥት በቀናነት ሁለንም የጋራ ጉዳዮቻችንን በንግግር ለመፍታት ዝግጁ ነው፡፡ ሁሉንም የጋራ ጉዳዮቻችንን ሲባልም በአሰብ ወደብ በኩል የባህር በር ማግኘትን ጨምሮ፣ ሌሎች የባህር ነክ አጀንዳዎችን ያካተተ ይሆናል፤›› በማለት ነው ለኤርትራ ማሳሰቢያ ብቻ ሳይሆን የመደራደሪያ ጥሪም የሚያቀርበው፡፡
ይህ የኢትዮጵያ ግልጽ ደብዳቤ በወጣ በማግሥቱ ማለትም ሰኞ ዕለት የኤርትራ ማስታወቂያ ሚኒስቴር የምላሽ መግለጫ በአጭሩ ሰጥቶበታል፡፡ በዚህ መግለጫ ላይም የኢትዮጵያ መንግሥት ደብዳቤ በኤርትራ ላይ ያሰማው ክስና ውንጀላ የሐሰት መሆኑን ኤርትራ አንፀባርቃለች፡፡ እንዲህ ያሉ ነገሮችን ለማባባስም ሆነ ለማጋጋል ኤርትራ ፍላጎት የሌላት መሆኑን የጠቀሰው መግለጫው፣ ስለመሬት ወረራውም ሆነ ከአማፂያን ጋር ስለሚደረገው ትብብር በዝርዝር ምላሽ ሳይሰጥ ዘግቶታል፡፡
የሁለቱ መንግሥታት የደብዳቤና የመግለጫ ልውውጥ ዲፕሎማሲያዊ አግባብነትና ቅቡልነት በአንዳንድ ወገኖች ዘንድ መነጋገሪያ መሆኑ ባይቀርም፣ ነገር ግን ከሁሉ በላይ ጉዳዩ የሚኖረው አንድምታ በሰፊው እያነጋገረ ነው የሚገኘው፡፡ በሁለቱ ቀናት የተደረጉት የመግለጫ ልውውጦች ምናልባትም ኢትዮጵያና ኤርትራ ወደ ጦርነት ለመግባት ከመቼውም ጊዜ በላይ ተቃርበዋል የሚል ሥጋት እያጫረ ነው፡፡
ይህ ሁኔታ ሥጋት ካሳደረባቸው አንዱ የሆኑት በኢትዮጵያ የቀድሞ የአሜሪካ አምባሳደርና የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ የአፍሪካ ጉዳዮች ረዳት ጸሐፊ የነበሩት ቲቦር ናዥ (አምባሳደር)፣ አሜሪካ በጉዳዩ ጣልቃ እንድትገባ እስከ መጠየቅ ደርሰዋል፡፡ ‹‹አሜሪካ ሁልጊዜ በሁሉም ጉዳይ ጣልቃ እንድትገባ አይጠበቅባትም፡፡ ነገር ግን ጣልቃ መግባት ካለባት አሁን ከመቼውም ጊዜ በላይ የተጋጋለውን የኢትዮጵያና የኤርትራ ግንኙነት መሻከር ትኩረት ልትሰጠው ይገባል፡፡ ኢትዮጵያ በብዙ ወሳኝ ጉዳዮች ላይ የእንደራደር ጥያቄ አቅርባለች፡፡ ይህ የንግግር ፍላጎት ደግሞ ሊደገፍ የሚገባው ነው፤›› በማለት ነው አንጋፋው ዲፕሎማት በኤክስ (ትዊተር) ገጻቸው የገለጹት፡፡
የተመድ የሰብዓዊ መብቶች ከፍተኛ ኮሚሽን ጽሕፈት ቤት (UN OHCHR) ከጄኔቫ ባወጣው መግለጫም፣ በሰሜን ኢትዮጵያ ከሰሞኑ የተፈጠረውን ግጭት ጨምሮ አሁን ያለው የኢትዮጵያና ኤርትራ ውጥረት በእጅጉ ያሳሰበው መሆኑን ጠቁሟል፡፡ የኮሚሽነሩ ቮከር ቱርክ ትናንት ማክሰኞ ይፋ ባደረጉት መግለጫቸው፣ በትግራይ ክልል ከሰሞኑ የተከሰተው እስከ ድሮን ጥቃት የደረሰው በመከላከያና በትግራይ ኃይሎች መካከል በጸለምት አካባቢ የተካሄደው ግጭት፣ በትግራይ ብቻ ሳይሆን ቀጣናዊ ቀውስ ሊፈጥር የሚችል ነው ብለዋል፡፡ የትግራይ ሠራዊት (ቲዲኤፍ) የሚባለው ኃይል ከመከላከያ ጋር ብቻ ሳይሆን የትግራይ ሰላም ሠራዊት (ቲፒኤፍ) ከሚባለው ኃይል ጋር ጭምር በራያ አካባቢ ግጭት ማካሄዱን ኮሚሽነሩ፣ ጠቅሰዋል፡፡ ይህን መሰሉ ግጭት ሊወገድ የሚገባው መሆኑን ያሳሰቡት ኮሚሽነሩ በትግራይ ካለፈው ጦርነት የመጣ የተከማቸ የሰብዓዊ ቀውስ አሁንም ድረስ መኖሩን በማስታወስ፣ በዚህ ሁኔታ ላይ ወደ አዲስ ጦርነት ቢገባ ቀውሱ ከባድ ሊሆን እንደሚችል አስምረውበታል፡፡
From The Reporter Magazine
ኮሚሽነር ቮልከር አያይዘውም በኢትዮጵያና በኤርትራ መካከል ያለው ውጥረት ያሳሰባቸው መሆኑን በመግለጫቸው አመላክተዋል፡፡ የሁለቱ አገሮች ውጥረት መባባሱ ከቀጠለ ወደ ጦርነት ማምራቱ እንደማይቀር የጠቆሙት ኮሚሽነሩ፣ ይህ ደግሞ መልሶ በሁለቱ አገሮች በውስጥ ያለውን ሰብዓዊ ቀውስ እንደሚያባብስና ለአጠቃላዩ የአፍሪካ ቀንድም ጭምር ሥጋት እንደሚሆን አሳስበዋል፡፡
የኢትዮጵያና የኤርትራ ሰሞነኛ የተጋጋለ የመግለጫ ልውውጥ በቅርቡ በሰሜን ኢትዮጵያ በተለይም በጸለምት፣ በራያና በአፋር አዋሳኝ አካባቢዎች ከተፈጠሩ መለስተኛ ግጭቶች ጋር እየተያያዘ ከመቅረብ ባለፈ በቀደመው ጦርነት ከደረሱ የሰብዓዊ ቀውሶች፣ እንዲሁም ከባህር በር አጀንዳ ጋር ተገናኝቶ ጭምር እየተነሳ ነው የሚገኘው፡፡
ባለፈው ሳምንት አጋማሽ በፓርላማ ቀርበው ማብራሪያ የሰጡት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር)፣ ከኤርትራ ጋር ስላለው በውጥረት ስለተሞላው ግንኙነት የመንግሥታቸውን አቋም አቅርበዋል፡፡ ጥር 26 ቀን 2018 ዓ.ም. በዋለው አሥረኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ የኢትዮጵያና ኤርትራ ፀብ የተፋፋመው ገና በመጀመሪያው ዙር የሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ወቅት ጀምሮ መሆኑን አስታውሰዋል፡፡
From The Reporter Magazine
‹‹ሽሬን ካስለቀቅን በኋላ የኤርትራ ጦር ከኋላ ገብቶ የአንዳንድ ሰዎችን ቤትና ፎቅ ማፍረስ ሲጀምር በመካከላችን ፀብ ተጀምሯል፡፡ አክሱምን ይዘን ስናልፍ ከኋላ ገብቶ ወጣቶችን በጅምላ ሲረሽን ፀብ ተፋፍሟል፡፡ ዓድዋን ይዘን ስናልፍ ዓድዋ ሄዶ ፋብሪካ ሲፈታታና ሲሰርቅ ፀብ ተጋግሏል፡፡ አዲግራት ደርሰው መድኃኒት ፋብሪካውን ጨምሮ የሚነቀለውን ነቅለው የማይነቀለውን ሲያፈራርሱ ፀቡ ጫፍ ደርሷል፡፡ ይህ ፀብ ተፋፍሞ ሄዶ የፕሪቶሪያ ሰላም ስምምነት ሲፈረም እንዴት ሕወሓት ሳይጠፋና ትግራይ ሙሉ ለሙሉ ሳይወድም ስምምነት ይፈረማል የሚል አቋም በመያዙ ነው ፀባችን የመጨረሻው ጫፍ ጋ የደረሰው፤›› በማለት፣ ከዚህ ቀደም ያልተሰማ ከኤርትራ መንግሥት ጋር የተፈጠረውን ውጥረት አጀማመር አስረድተዋል፡፡
ከኤርትራ ጋር ኢትዮጵያ ወደ ውጥረት የገባችው በቀይ ባህር የባህር በር ለማግኘት ጥያቄ በማቅረቧ ምክንያት እንዳልሆነ የገለጹት ዓብይ (ዶ/ር)፣ ይልቁንም አለመግባባቱ የኤርትራ ሠራዊት በሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ወቅት ከነበረው ተሳትፎ እንደሚጀምር ነው ያብራሩት፡፡ አያይዘውም የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄም ቢሆን በሰላምና በድርድር መፈታት የሚችል መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ለአብነት የአፍሪካ ትልቁ የኃይል ማመንጫ ከሆነው ከታላቁ የህዳሴ ግድብ ድርሻን በመውሰድ፣ ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ድርሻ በመውሰድ፣ አለበለዚያም የመሬት መቀያየር/ልውውጥ በማድረግ፣ እንዲሁም በሊዝ በማኮናተር በሰላም ጥያቄው እንደሚፈታ ነው ያብራሩት፡፡
‹‹የኢትዮጵያ መንግሥት አሰብ ወደብ ገነባ፣ አየር ማረፊያ ገነባ፣ መንገድ ገነባ፣ ነዳጅ ማጣሪያም ገነባ፡፡ ስንጋጭ ግን የኢትዮጵያ ሀብት እዚያው ቀረ፡፡ ከ20 ዓመታት በኋላ ዳግም ስንታረቅ ግን ኤርትራውያን እዚህ መጥተው በኢትዮጵያ ፍርድ ቤት፣ ቤቴ ይመለስ፣ መሬቴ ይመለስ ብለው ንብረታቸውን ወሰዱ፡፡ ስለታረቅን ያኔ ስንጣላ ከኢትዮጵያ የተባረሩ ናቸው የተባሉ ኤርትራውያን ተመልሰው መጥተው ንብረቶቻቸውን ወስደዋል፡፡ ታዲያ የኢትዮጵያ መንግሥትስ ንብረቱ የሆኑትን የአሰብ ወደብን፣ አየር ማረፊያውንና ነዳጅ ማጣሪያውን ቢወስድ ከዚህ አንፃር እንዴት ነው የሚታየው?›› በማለት የጠየቁት ዓብይ (ዶ/ር)፣ ኢትዮጵያ ያቀረበችው የባህር በር ጥያቄ በኢፍትሐዊነትና በሥጋትነት የሚታይ ሳይሆን በንግግርና በሰላም የሚያልቅ ጉዳይ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የኤርትራ ባለሥልጣናት ግን የኢትዮጵያን የባህር በር ጥያቄ በዚህ መንገድ ከመቀበል ይልቅ፣ እንደ ወረራ ሥጋትነትና ቀጣናውን እንደማተራመስ ሲመለከቱት ነው የቆዩት፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ (ዶ/ር) የፓርላማ ንግግር በተሰማ ዕለት በኤክስ (ትዊተር) ላይ ምላሽ የሰጡት የኤርትራ የማስታወቂያ ሚኒስትር የማነ ገብረ መስቀል፣ የኢትዮጵያ መንግሥት የጦርነት አጀንዳውን እንደገፋበት ገልጸው ነበር፡፡ የኤርትራ ባለሥልጣናት ባለፉት ሁለት ዓመታት ኢትዮጵያ ስታቀርብ የቆየችውን የባህር በር ጥያቄ የጦርነት አጀንዳ አድርገው ሲያቀርቡት የቆዩ ሲሆን፣ ይህ ደግሞ በሁለቱ አገሮች መካከል ጠንካራ የቃላት ልውውጥን ማስከተሉ ይነገራል፡፡ በሒደት ኤርትራ ከግብፅና ከሶማሊያ ጋር ፀረ ኢትዮጵያ የሆነ ጥምረትና አጋርነት ስትፈጥር ታይታለች፡፡ የኤርትራ መንግሥት ከዚህ ባለፈም በትግራይ ካለው ሕወሓት ጋር ፅምዶ የተባለ ጥምረት ሲፈጥር ነበር፡፡ ሁለቱ አገሮችም በተለያዩ መንገዶች የእጅ አዙር ጦርነት ወደ ማድረግ ተሸጋግረዋል ሲባል መቆየቱም አይዘነጋም፡፡
ይህ ሁኔታ መባባሱ አስግቶናል ያሉት ተመድ፣ የአፍሪካ ኅብረትና የአውሮፓ ኅብረት ከአንድ ወር ቀደም ብሎ ሁለቱ አገሮች ወደ ግጭት ከመግባት እንዲቆጠቡ የሚያሳስብ መግለጫ ማውጣታቸው አይዘነጋም፡፡ የአልጄርስ ስምምነት 25ኛ ዓመት መድፈንን በማስመልከት ተቋማቱ ባወጡት መግለጫ፣ ያንን ስምምነት መተግበር ለሁለቱም መፍትሔ መሆኑን ሲናገሩ ተደምጠዋል፡፡ የአልጄርስ ስምምነት በሥራ ላይ እንዲውል ተመድ ድጋፍ እንደሚያደርግ የድርጅቱ ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉተሬስ አስታውቀዋል፡፡ ከሰባት ዓመት ቀደም ብሎ ስምምነቱን ያለ ቅድመ ሁኔታ ሁለቱ አገሮች ለመቀበልና ለመተግበር ዳግም መስማማታቸውን አስታውሰው፣ ለስምምነቱ ወደ መገዛት እንዲመለሱና ገቢራዊ እንዲያደርጉት ጠይቀዋል፡፡ የአውሮፓ ኅብረትም ባወጣው መግለጫ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ሁለቱ አገሮች ስምምነቱን ከዳር እንዲያደርሱ ድጋፍ እንደሚያደርጉ ቃል ገብቶ ነበር፡፡ የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ማህሙድ ዓሊ ዩሱፍ በበኩላቸው፣ የአልጄርስ ስምምነት ለሁለቱ አገሮችና ለሕዝቦቻቸው ሰላምና መረጋገት ወሳኝ መሆኑን ገልጸው ነበር፡፡
የኢትዮጵያና የኤርትራን አሁናዊ ውጥረት በጥልቀት ለመፈተሽ የሞከሩ አንዳንድ ወገኖች የግጭቱ ጥንስስ ከኤርትራ ተገንጥሎ ነፃ አገር መሆን ወቅት ጀምሮ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ ኤርትራ ተገንገጥላ ስትሄድ ጉዳዩ የተከወነበት መንገድ የሕግ አግባብ የጎደለው ነበር የሚለውን ጉዳይ መንግሥት ጭምር ሲያነሳው ይደመጣል፡፡ ሕጋዊ ፍቺ ሳያደርጉ በመለያየታቸውም የባድመ ጦርነት የሚባለው የድንበር ጦርነት መቀስቀሱንም ይጠቅሱታል፡፡ ይህን ጦርነት ዕልባት ለመስጠት የተፈረመው የአልጄርስ ስምምነትና የድንበር ኮሚሽኑ ውሳኔም ቢሆን ፍትሕና ርትዕ የጎደለው መሆኑን ይገልጻሉ፡፡ ከ20 ዓመታት ውዝግብ በኋላ ሁለቱ አገሮች ዳግም ቢታረቁም፣ ነገር ግን የሰሜን ኢትዮጵያው ጦርነት ውስጥ የኤርትራ ጦር መሳተፉን ተከትሎ ግንኙነታቸው እየተወሳሰበ መምጣቱን ይጠቁማሉ፡፡
በርካታ ዓለም አቀፍ ተቋማት ከፕሪቶሪያ ሰላም ስምምነት በኋላም ቢሆን ኤርትራ ከያዘቻቸው የኢትዮጵያ መሬቶች ለቃ እንድትወጣ ሲወተውቱ ቆይተዋል፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት ስለጉዳዩ በዝምታ ቢቆይም በስተኋላ በሰጣቸው መግለጫዎች ኤርትራ መሬቴን ለቃ ትውጣ የሚሉ ክሶችን ማሰማቱ ይታወሳል፡፡ የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትር አብረሃም በላይ (ዶ/ር) ከዓመት ቀደም ብሎ ኤርትራ ከያዘችው መሬት እንድትወጣ በይፋ የተናገሩበት አጋጣሚ፣ በዚህ ጉዳይ ከኢትዮጵያ ባለሥልጣናት ቀድሞ የተሰማ መግለጫ ሲባል ነበር፡፡ የቀድሞው ፕሬዚዳንት ሙላቱ ተሾመ (ዶ/ር) በአንድ ወቅት በጻፉት መጣጥፍም ይህንኑ ደግመውታል፡፡ ከዚያ ወዲህም የተለያዩ የኢትዮጵያ ባለሥልጣናት አጠንክረው እየተናገሩት ነው፡፡ ይሁን እንጂ ኤርትራ ለቃ ትውጣ እያሉ ያሉት በአልጄርስ ስምምነት የድንበር ኮሚሽን ተፈርዶልኛል ብላ ከያዘችው መሬት? ወይስ ከዚያ ባለፈ ገፍታ ገብታ ከያዘቻቸው አካባቢዎች ጭምር የሚለው ጉዳይ በጠራ ሁኔታ ሲገለጽ አይታይም፡፡
የአልጄርስ ስምምነት 25ኛ ዓመት መድፈንን ተከትሎ ዓለም አቀፍ ተቋማት መግለጫ በሚሰጡበት ሰሞን ስለዚሁ ስምምነት ትግበራና መፍትሔነት አስተያየታቸውን የተጠየቁት አንጋፋው ፖለቲከኛ አቶ ገብሩ አሥራት፣ የአልጄርስ ስምምነትን የኤርትራ መንግሥት እንደገደለው ነበር የተናገሩት፡፡
‹‹የአልጄርስ ስምምነት ለሁለቱ አገሮች ችግር መፍትሔ አይሆንም፡፡ በመሠረታዊነት ስምምነቱ የሁለቱን አገሮች ጥቅም በእኩል የሚያይ አልነበረም፡፡ ጦርነቱን በእርግጥ አስቁሟል፡፡ ሆኖም አልጄርስ ኤርትራ ተገንጥላ ነፃ እንድትሆን የተፈቀደበትን ሁኔታ ያፀና ስምምነት ነበር፡፡ አልጄርስ በወቅቱ ኢትዮጵያና ኤርትራ ወደ ጦርነት የገቡበት የድንበር ውዝግብ በቅኝ ግዛት ውል መሠረት እንዲፈታ መንገድ የጠረገ ነው፡፡ ስምምነቱ ለኤርትራ ሉዓላዊ አገርነቷ ተጠብቆና ያልተካለለ ድንበሯ ተሰምሮ እንዲቀጥል የሚያደርግ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ስምምነቱ የኢትዮጵያ መሠረታዊ ጥቅም እንዲጠበቅ ያደረገ አልነበረም፡፡ ኤርትራ ነፃነት መፈለጓም ሆነ ነፃ ሆና መገንጠሏ ሕጋዊ እስከሆነ ድረስ መብቷና የሚገባትም ነው፡፡ ነገር ግን ይህ ሲሆን የኢትዮጵያ ጥቅም እንዴት መጠበቅ እንደሚኖርበት በአልጄርስ ስምምነት አልተቀመጠም፡፡ ይህ ስህተት የተፈጠረው ደግሞ ቀደም ብሎ በ1983 ዓ.ም. ኤርትራ ስትገነጠል ጀምሮ ሲሆን፣ የአልጄርስ ስምምነትም ይህንኑ ሁኔታ ያጠናከረ ነበር፡፡ አልጄርስ በወቅቱ በሁለቱ አገሮች መካከል የነበረውን ተጨባጭ ሁኔታ በተለይም ሻዕቢያ ጦርነቱን ከለኮሰ ጀምሮ፣ የተፈጠረውን ሁኔታ ፍፁም ያላገናዘበ ስምምነት ነው፡፡ ሻዕቢያ ወረራ ሲፈጽም የኢትዮጵያን የባህር በር መብት ብቻ ሳይሆን፣ በዓለም አቀፍ ሕግ መሠረት ወደቡን የመገልገል መብቷንም ሙሉ ለሙሉ ዘግቶታል፡፡ ይህ ሁኔታ ተፈጥሮ ሳለ የአልጄርስ ስምምነት በዚያ መንገድ ተረቆ መፈረም ነበረበት ወይ የሚለው መሠረታዊ ችግር ነው፡፡ ይህን እያወቀ የፈረመውና የተቀበለው የወቅቱ የኢትዮጵያ መንግሥት ስለሆነ ይሁን ተብሎ ወደ መቀበል ቢገባም እንኳን፣ ነገር ግን በትግበራም ሒደት የኤርትራ እንጂ የኢትዮጵያን ጥቅም በሚያስጠብቅ መንገድ አልነበረም የሄዱበት፡፡ መሬት ውሰዱ ተፈርዶላችኋል ሲባል ራሱ የእኛ አይደለም ይውሰዱት የሚሉ መሪዎች ነበሩ በኢትዮጵያ በኩል የነበሩት፡፡ ይህ ሁሉ የእኛው ችግር ነው ምንም አይደለም ቢባል ደግሞ፣ ከሁሉም በላይ ሻዕቢያዎች ስምምነቱን ሲያፈርሱ መኖራቸውንም ማስታወስ ያስፈልጋል፡፡ በስምምነቱ መሠረት 25 ኪሎ ሜትር በኤርትራ ውስጥ ገባ ብሎ የሚሰመር ዓለም አቀፍ ሰላም አስከባሪ ኃይል የሚሰማራበት ቀጣና ይኖራል ተብሎ ነበር፣ ይህን ሻዕቢያ ጥሶታል፡፡ የሰላም አስከባሪውን ኃይልም እንቅስቃሴውን ከማስተጓጎል ጀምሮ በመጨረሻ እስከማባረር መድረሱ ይታወሳል፡፡ በስምምነቱ መሠረት መፈጸም የነበረባቸውን ብዙ ጉዳዮች ሻዕቢያ አፍርሷል፡፡ ግጭት በዘላቂነት ማስወገድ የሚለውን ድንጋጌ ጥሶ የኢትዮጵያን ጠላቶች ሲረዳ፣ ኢትዮጵያን የሚወጉና የሚያሸብሩ ኃይሎችን ሲያሠለጥን፣ ሲያደራጅና ሲያስታጥቅ መኖሩም ዓለም ያወቀው ሀቅ ነው፡፡ እነዚህን ኃይሎች ወደ ኢትዮጵያ ሲልክ ኖሯል፡፡ ስለዚህ በእኔ እምነት ሻዕቢያ ስምምነቱን ሙሉ ለሙሉ አፍርሶታል፡፡ አሁን ሰላም ይፈጠር ሲባል አልጄርስን ዳግም ተግብሩ ማለት ሳይሆን እንደ አዲስ መደራደር ነው የሚበጀው፡፡ በሻዕቢያ ስሌት መሠረት አልጄርስ ለመሬት ጉዳይ ተቀባይነት አለው፣ ለድንበር ማካለል ሲሆን ተቀባይነት አለው፡፡ ነገር ግን የኢትዮጵያን መሠረታዊ ጥቅም በሚመለከት አይመለከተውም፣ የኢትዮጵያን ደኅንነት በሚመለከትም አይሠራም የሚል አመለካከት ነው ሻዕቢያ ይዞ የቆየው፡፡ ሻዕቢያ በስምምነቱ መሠረት ድንበሩን አካሉልኝ እያለ ነገር ግን የኢትዮጵያን ጥቅም በተቃራኒው አደጋ ላይ በመጣል ስምምነቱን አፍርሶታል፡፡ አሁን ይህንን የፈረሰ ስምምነት ከማምጣት ይልቅ ሁለቱን መሠረታዊ ጉዳዮች ማለትም ሉዓላዊ ዳር ድንበር ማረጋገጥና ብሔራዊ ጥቅም ማስጠበቅን አብሮ የሚያስኬድ አዲስ ድርድር ነው ሊደረግ የሚገባው፡፡ ከዚያ ውጪ አልጄርስ የፈረሰና የማይሠራ ስምምነት ነው በእኔ አስተያየት፤›› በማለት ነበር አቶ ገብሩ ሰፋ ያለ ማብራሪያ የሰጡት፡፡ የኤርትራ መንግሥት አልጄርስ ፈቀደልኝ ብሎ በውል ተለይቶ ያልተካለለ መሬትን ከመውረር ባለፈ፣ ወደ ውስጥ ጠልቆ መግባቱ ሁኔታውን እንዳባባሰው ነው በርካቶችም የሚናገሩት፡፡