መንግሥት በቀዳማይ ልጅነት (ዕድሜአቸው ከስድስት ዓመት በታች የሆኑ ሕፃናት) ላይ ትርጉም ያለው ኢንቨስትመንት ማድረግ አማራጭ ሳይሆን የግዴታ ሥራው መሆኑን ማስተዋል እንደሚገባ፣ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ አስታወቁ፡፡
ከንቲባዋ ይህንን ያስታወቁት ግንቦት 3 ቀን 2018 ዓ.ም. አዲስ ዓለም አቀፍ የቀዳማይ ልጅነት ጉባዔ፣ ‹‹አፍሪካ በቀዳማይ ልጅነት ሥርዓተ ለውጥ የግንባር ቀደምትነት ሚና ከአካባቢያዊ ሞዴሎች ወደ ዓለም አቀፍ እንቅስቃሴ›› በሚል መሪ ሐሳብ ውይይት ሲካሄድ ነው፡፡
የተቀናጀ ሁለንተናዊ የሕፃናት ዕድገትን ለማረጋገጥ የቀዳማይ ልጅነት ልማት አገልግሎቶችን፣ ለሁሉም ልጆች በፍትሐዊነትና አካታች በሆነ መንገድ ተደራሽነቱን ማረጋገጥ ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡
በመሆኑም አስፈላጊ መዋቅርና ብቃት ያላቸው ባለሙያዎችን ማፍራት፣ በመንግሥት የሚደረግ ሀብት ምደባን ማሳደግ፣ የፕሮግራሙን ዘላቂነት ለማረጋገጥ የክትትልና የግምገማ ሥርጭትን በተዋረድ ማጠናከር እንደሚያስፈልግ አስረድተዋል፡፡
‹‹ሕፃናት የአዲስ አበባ የነገ ተስፋዎች›› በሚል መሪ ቃል ፍኖተ ካርታ ተቀርፆ ከስድስት ዓመት በታች የሆኑ 1.3 ሚሊዮን ሕፃናት ሁለንተናዊ ዕድገት መረጋገጡን፣ 330 ሺሕ የሚጠጉ ለችግር የተጋለጡ ቤተሰቦች ላይ ትኩረት በማድረግ የቤት ለቤት ጉብኝት የሚያደርጉ ከአምስት ሺሕ በላይ ባለሙያዎች ሠልጥነው በቋሚነት እየሠሩ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
የተቀናጀ የቀዳማዊ ልጅነት አገልግሎት በሁሉም የመንግሥት ሆስፒታሎችና ጤና ጣቢያዎች በመደበኝነት እየሰጡ እንደሚገኙ የገለጹት ከንቲባዋ፣ መንግሥት የቅድመ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችን ምቹ እንዲሆኑ በማድረግ፣ በቀን ሁለት ጊዜ ምግብ በማቅረብ፣ የትምህርት ቁሳቁስና ሌሎች የትምህርት ግብዓቶች ከክፍያ ነፃ እየቀረቡ መሆናቸውን አብራርተዋል፡፡
በመንግሥትም ሆነ በግል ሥራ ምክንያት ከቤታቸው ርቀው መሄድ ለማይችሉ ወላጆችም ሆኑ አሳዳጊዎች አገልግሎት የሚሰጡ ወደ 1‚100 የሕፃናት ማቆያዎች ማዕከላት መቋቋማቸውን የተናገሩት ወ/ሮ አዳነች፣ በተጨማሪም ከአምስት ሺሕ በላይ የሕፃናት መጫወቻዎች ተገንብተው ለአገልግሎት መብቃታቸውን ተናግረዋል፡፡
From The Reporter Magazine
እንደ ከንቲባዋ ገለጻ፣ ፕሮጀክቱ ከአዲስ አበባ ከተማ ውጪ በአምስት ክልሎች ከአጋር አካላት ጋር በመሆን የቴክኒክ ድጋፍ እየሰጠ ነው፡፡
አገር አቀፉ የቀዳማዊ ልጅነት ልማትና ትምህርት የፖሊሲ ማዕቀፍ በ2003 ዓ.ም. ፀድቆ በ2015 ዓ.ም. ማሻሻያ ተደርጎበት በሥራ ላይ መዋሉን የተናገሩት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ተመስገን ጥሩነህ፣ በ2017 ዓ.ም. የፀደቀው አጠቃላይ የትምህርት አዋጅ ነፃና አስገዳጅ የቅድመ አንደኛ ደረጃ ትምህርት እንዲሰጥ ይደነግጋል ብለዋል፡፡
ይህንን መሠረት በማድረግ ከ35 ሺሕ በላይ በቅድመ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተዘጋጅተው አገልግሎት እየሰጡ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም በፌዴራል መንግሥት ሠራተኞች አዋጅ የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች በቀን አገልግሎት የሚሰጡ የሕፃናት እንክብካቤ ማዕከላት እንዲቋቋሙ ይደነግጋል ያሉት አቶ ተመስገን፣ በዚህም መሠረት በመንግሥት ተቋማት ውስጥ የሕፃናት ማቆያዎች ተሠርተው አገልግሎት እየሰጡ መሆናቸውን አክለዋል፡፡
From The Reporter Magazine
የሕፃናትን ደኅንነት ለማሻሻል የሚያስችል ብሔራዊ መርሐ ግብር መጀመሩን ያስረዱት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ በሰቆጣ ቃል ኪዳን አማካይነት የ15 ዓመት ፍኖተ ካርታ ተዘጋጅቶ ከሁለት ዓመት ዕድሜ በታች ያሉ ሕፃናት ላይ የሚደርሰውን መቀንጨር በ2022 ዓ.ም. ዜሮ ለማድረስ እየተሠራ ነው ብለዋል፡፡
ከ2008 ዓ.ም. የሙከራ ትግበራ ጀምሮ በአሁኑ ወቅት በአገር አቀፍ ደረጃ የማስፋፊያ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውን አብራርተዋል፡፡
የሰቆጣ ቃል ኪዳን የፌዴራል መንግሥት ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶት ከብሔራዊ የምግብና ሥርዓተ ምግብ ካውንስል እየተመራ መሆኑን የገለጹት አቶ ተመስገን፣ በብዝኃ ዘርፍ ተጠያቂነትን ለማስፈን በየስድስት ወራት በከፍተኛ መድረክ ግምገማ እየተደረገበት መሆኑንና ውጤቱም እያስመዘገበ እንደሚገኝ አብራርተዋል፡፡
የመቀንጨርና የመቀጨጭ ችግርን በአገሪቱ ሙሉ በሙሉ ለማጥፋት በሚል ዓላማ የሰቆጣ ቃልኪዳን መቋቋሙ ይታወሳል፡፡ በ2007 ይፋ የሆነው የሰቆጣ ቃልኪዳን ፕሮግራም ዕድሜአቸው ከሁለት ዓመት በታች በሆኑ ሕፃናት ላይ የሚከሰተውን የመቀንጨር ችግር በ2022 ዜሮ ለማድረግ በሚል ሐሳብ መጀመሩ ይታወሳል፡፡
