በሲሳይ ሳህሉ
ቅዳሜ ግንቦት 22 ቀን 2018 ዓ.ም. በአማራ ክልል መቀመጫ ባህር ዳር ከተማ የተገኘው የሪፖርተር ዘጋቢ፣ የመራጩን ሕዝብ፣ የምርጫውን ድባብ ሒደትና በአካባቢው የነበረውን ምኅዳር ለመመልከት ችሏል። በባህር ዳር ከተማ በምርጫው ዋዜማ በነበሩ ቀናት በአጠቃላይ ከምርጫ ድግስ ይልቅ በሕዝቡ ላይ የተደበላለቀ ስሜትና በአመዛኙ ሥጋት የሚነበብባቸው ፊቶች ተስተውለዋል። በአማራ ክልል ከ23 በላይ የፖለቲካ ፓርቲዎች በምርጫው መሳተፋቸው ቢገለጽም፣ በዋና ከተማዋ ባህር ዳር አደባባዮች የመንገድ አካፋዮችና የመብራት ፖሎች ላይ ተሰቅለው የሚታዩት ከብልፅግና ፓርቲ ተመራጮች ፎቶዎቸና የፓርቲው የምርጫ ምልክቶች ብቻ ናቸው ማለት ይቻላል፡፡


በዋዜማው በነበሩ ቀናት በሕዝቡ ላይ ጉጉትና በምርጫው ተስፋ ያደረጉ ስሜቶችን ለመለየት የሚከብድ ቢሆንም፣ እሑድ ግንቦት 23 ቀኝ 2018 ዓ.ም. የነበረው የምርጫ ዝግጅት በሁሉም አካባቢ የተሟላ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ሪፖርተርም ተንቀሳቅሶ ማረጋገጥ ችሏል፡፡ ከ164 በላይ የምርጫ ጣቢያዎችን የያዘውን የባህር ዳር የምርጫ ክልል የሚመሩትና በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የባህር ዳር ምርጫ ክልል አስተባባሪው አቶ ሞላልኝ ደሳለኝ ይህንኑን ማረጋገጫ ለሪፖርተር ገልጸው፣ የምርጫ ዝግጅቱ ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ተጠናቆ ለሰኞ ዝግጁ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በባህር ዳር ከተማ በምርጫው ዋዜማና በምርጫው ዕለት የነበረው አጠቃላይ የማኅበራዊ ሕይወት ድባብ ሲታይ፣ በአዘቦት ቀናት በጎዳናዎች ይታይ ከነበረው የነዋሪዎች እንቅሰቃሴ በተለየ ገና መጨላለም ሲጀምር፣ በሁለቱም ቀናት አመሻሹ ላይ በተለይ ከአንድ ሰዓት በኋላ መንገድ ላይ ሰው አይንቀሳቀስም ነበር፡፡ የከተማው ድባብ ፀጥ ረጭ ከማለቱ በተጨማሪ፣ ደመናማ የነበረው የአየር ሁኔታ በየሰዓቱ ያወርደው የነበረው ዝናብ አንዱ ምክንያት ሊሆን ይችላል፡፡ ባህር ዳር ከተማ መንግሥት በሠራው የኮሪደር ልማት የተሽከርካሪና የእግረኛ መንገዶቿ ሰፍተው ነዋሪዎች እንደ ልብ ለመንቀሳቀስ የሚችሉባትና ጎዳናዎቹ በሰዎች የሚደምቁ ብትመስልም፣ እንዲህ የተወጠሩ በሚመስሉ ምሽቶች የመንገዶቹ ስፋት ፍርኃትን ይጋብዛል፡፡


በምርጫው ቀን ማለዳ 11 ሰዓት ጎህ ሲቀድ በከተማው ውስጥ የምርጫ ዝግጅትና የመራጩን ሕዝብ እንቅስቃሴ በቦታው ተገኝቶ ለመረዳት በተደረገው ጥረት፣ በርካታ የምርጫ ጣቢያዎች ከብልፅግና ፓርቲ የምርጫ ታዛቢዎች ውጪ ሌላ ታዛቢ ባለመገኘቱ ምርጫውን በሕግ በተደነገገው መሠረት ከማለዳው 12 ሰዓት ለማስጀመር አስቸጋሪ አድርጎባቸው እንደነበር ተመልክተናል፡፡ ከአስፈጻሚዎቹም ሰምተናል፡፡ ይሁን እንጂ አብዛኞቹ ጣቢያዎች እስከ ማለዳው 12፡30 ሰዓት በመጠበቅ አስፈጻሚዎች ከተገኙ ታዛቢዎች ጋር ቃለ ጉባዔ ተፈራርመው በመያዝ የምርጫ ሒደቱን መጀመራቸውን ለመረዳት ተችሏል። በከተማው በተከፈቱት አብዛኞቹ የምርጫ ጣቢያዎች የተፎካካሪ ፓርቲ ታዛቢዎች ያልመጡበት ምክንያት፣ ‹‹ሰሞኑን በክልሉ በተፈጠረ የፀጥታና የደኅንነት ሥጋት›› እንደሆነ አስተባባሪዎች ሲናገሩ ተደምጧል፡፡ ‹ሰፈነ ሰላም› ከተሰኙ ጣቢያዎች መካከል በአንዱ ጣቢያ የነበረ አንድ የምርጫ አስፈጻሚ ሲናገር፣ ‹‹ብዙ ፓርቲዎች በምርጫ ከተሳተፋችሁ ብሎ የፎከረባችው አካል ስላለ ታዛቢ ቢመደቡም እንደማይመጡ ‹ኢንፎርማሊ› ሰምተናል፤›› ሲሉም ተሰምቷል፡፡
From The Reporter Magazine
በአማራ ክልል ባህር ዳር ከተማ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ (ኢዜማ)ን በመወከል ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የተወዳደሩት አቶ ኃይለ ማርያም ብርሃኑ ድምፃቸውን በሰጡበት የምርጫ ጣቢያ ምርጫውን በተመለከተ ላቀረብንላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ፣ ፓርቲያቸው ኢዜማ በተለያዩ ምክንያቶች በቂ ቅስቀሳ አለማድረጉን ተናግረዋል፡፡ ከብልፅግና ተመራጩ ከምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ አቶ ተመስገን ጥሩነህ ጋር ለፓርላማ የተፎካከሩት የኢዜማው አቶ ኃይለ ማርያም፣ ‹‹የምርጫ ሒደቱ ችግር ያለበት፣ ነፃና ገለልተኛ አለመሆን፣ ምርጫ ጣቢያ ውስጥ ከመራጮች ጋር በሚስጥር ድምፅ የሚሰጥበት ቦታ ድረስ በመግባት ካርድ እንዴት ማስገባት እንዳለባቸው ሲያሳዩ እንደነበር አይተናል፤›› ብለዋል፡፡ ‹‹ዴሞክራሲው ወደ ታች አለመውረዱን አይተናል፤›› ብለው፣ ‹‹በቀጣይ ቅሬታዎች ካሉን በሕጉ መሠረት ለምርጫ ቦርድ እናቀርባለን ያሉት፤›› አቶ ኃይለ ማርያም፣ ምርጫ እንደ ተመራጭም ይሁን እንደ መራጭ በቀላል የማይገኝ ዕድል በመሆኑ ኅብረተሰቡ በሚያደርገው የዴሞክራሲ ልምምድ ላይ የሚታዩ ተገቢ ያልሆነ ጫናዎች አግባብ አይደሉም በማለት አስረድተዋል፡፡
በምርጫ ጣቢያዎች ከምርጫ እንድንወጣ ውስጣዊ ጫና ሲደረግብን ነበር ያሉት የኢዜማው ተፎካካሪ፣ በየምርጫ ጣቢያዎች የተፎካካሪ ፓርቲ ታዛቢዎች አለመገኘትን ሲያብራሩ፣ ‹‹አገር እንደ አገር እንድትቀጥል ሁሉም ይፈልጋል፡፡ ነገር ግን ‹ከራሴ ጀምሮ ነፍሴን አስይዤ ነው የምወዳደረው፡፡ ለሕይወትህ ዋስትና የሚሆንልህ የለም፡፡ በምርጫ ጣቢያዎች ውስጥ ታዛቢ ለመሆን ፍላጎት ያለው የለም፡፡ ምክንያቱም አይደለም እኛ በእግራችን የምንጓዝ ሰዎች ታጅበው የሚሄዱ ሰዎች ራሳቸውን አደጋ ውስጥ የጣሉ ናቸው፤›› ብለዋል፡፡ በተደረገው ጫና ራሳቸውን ያገለሉ አሉ የሚሉት አቶ ኃይለ ማርያም፣ ‹‹የምርጫ ሥራው የተሠራው ቀበሌ ለቀበሌ እየተዞረ ነው፡፡ ይህን ደግሞ ራሳቸው ይህን የሠሩት ሰዎች ያውቁታል፤›› ሲሉ አክለዋል፡፡
በምርጫው ቀን በአመዛኙ ሴቶችና በዕድሜ የገፉ የባህር ዳር መራጮችን ማልደው በመነሳት ተሠልፈው የታዩ ሲሆን፣ ሪፖርተር በየምርጫ ጣቢያዎች ያሉ ሒደቶችን ለመገንዘብ በምርጫ ጣቢያዎች በተገኘበት ወቅት፣ ከምርጫ አስፈጻሚዎች መካከል ሰፈነ ሰላም 05/1 በተሰኘ ጣቢያ አገሬ ታደለ የተባሉ የቦርዱ አስተባባሪ ፎቶ ማንሳት ክልክል በማስታወቅ፣ ‹‹በሥልጠና የተነገረን ነው፡፡ ማንሳት አይቻልም፤›› ብለዋል፡፡ መሰል ከሕግ ያፈነገጡ ጅምላ ክልከላዎች ይስተዋሉ ነበር። ሪፖርተር በየምርጫ ጣቢዎች ፎቶ ለማንሳት ወይም ቃለ መጠይቅ ለማድረግ ጥረት ባደረገበት ወቅት ከአስፈጻሚዎች ጋር የሚፈጠሩ እሰጥ አገባዎችን አልፎ በተወሰኑ ጣቢያዎቾ የብልፅግና ፖርቲ ታዛቢዎች ከመቀመጫቸው በመነሳት የቦርዱ አስፈጻሚዎችን በማነጋገር ሕጉ እንደሚፈቅድ ለማስረዳት ሲሞክሩ፣ በተወሰኑ ጣቢያዎች ደግሞ የሞርጫ አስፈጻሚዎች ማብራሪያ መስጠት በሚገባቸው ጉዳዮች ላይ የብልፅግና ፓርቲ ታዛቢዎች ስለሒደቱ ማብራሪያ ሲሰጡ ነበር።
From The Reporter Magazine
በየምርጫ ጣቢያዎች ለመምረጥ የተሠለፉ ዜጎችን ከምርጫ ጣቢያው ጋር አገኛኝቶ ፎቶ ለማንሳትና ቃለ መጠይቅ ለማድረግ ሲጠየቁ አብዛኞቹ ፈቃደኛ አልነበሩም፡፡ ፎቶ የሚያነሳ ሰው ሲቀርባቸው ፊታቸውን ማዞርና በለበሱት ነጠላ ሲሸፋፈኑ ነበር።
በባህር ዳር ከተማ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የተወዳደሩት የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንትና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ተመስገን ጥሩነህ፣ ባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ አካባቢ በተከፈተው ግሽ ዓባይ ክፍለ ከተማ 02/1 በተሰኘ ጣቢያ ከክልሉ ፕሬዚዳንት አቶ አረጋ ከበደ ጋር ድምፃቸውን ሰጥተዋል፡፡ አቶ ተመስገን ድምፃቸውን በሰጡበት ጣቢያ ለጋዜጠኞች በሰጡት አጭር ማብራሪያ፣ ‹‹ሕዝቡ ይሆነኛል ያለውን፣ ልማት ያሳልጥልኛል ያለውን ተወካይ ለመምረጥ የሚያደርገው ቃል ኪዳን ነው፤›› ብለው፣ ‹‹ምርጫው ምንም ይሁን ምንም ሕዝቡ የመረጠውን ብልፅግና ፓርቲ ይቀበላል፡፡ እኔም ሕዝቡ የመረጠውን ወኪል ወደፊት እቀበላለሁ፡፡ እኔ ካልተመረጥኩ የሚል ፍላጎት የለኝም፤›› ብለዋል፡፡ ‹‹ሕዝቡ የፈለገውን ይምረጥ፣ አንድ ፓርቲ ከአገር በላይ አይደለም፡፡ ፍላጎታችን የአገር ቀጣይነት እንጂ የፓርቲ ቀጣይነት አይደለም፡፡ ለአገር ግንባታ ይሆናል የሚሉትን ወኪል መምረጥ ያስፈልጋል፡፡ ይህንም እንደተወዳዳሪ እቀበላለሁ፤›› በማለት አስረድተዋል፡፡
የክልሉ ፕሬዚዳንት በበኩላቸው፣ ‹‹ምርጫው ሕዝቡ በነቂስ የተሳተፈበት መሆኑን አይቻለሁ፤›› ብለው፣ ‹‹በኢትዮጵያ አሁን ድረስ በአገር ውስጥም በውጭም የሽግግር መንግሥት የሚመኙ አሉ፡፡ ነገር ግን በሽግግር መንግሥት የፀና መንግሥትና ሥርዓት የማያመጣ በመሆኑ፣ ሕዝባዊና ሕጋዊ በሆነ መንገድ መንግሥት ለመመሥረት ብቸኛው መንገድ ምርጫና የሕዝብ ድምፅ ነው፤›› ብለዋል፡፡
ሪፖርተር ተንቀሳቅሶ በተመለከታቸው የምርጫ ጣቢያዎች የብልፅግና ፓርቲ በርካታ የምርጫ ታዛቢዎችን ማሰማራቱን ማወቅ የተቻለ ሲሆን፣ የተፎካካሪ ፓርቲዎችን ማግኘት አልተቻለም፡፡ ይሁን እንጂ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) እና የምሥራቅ አፍሪካ በይነ መንግሥታታ ድርጅት (ኢጋድ) የምርጫ ታዛቢ ቡድኖች በተለያዩ አካባቢዎች ሲንቀሳቀሱ ታይተዋል፡፡ የክልሉ የሚሊሻ አባላት ፋሲሎ በተባለ የምርጫ ጣቢያ መሣሪያቸውን አስቀምጠው ከኅብረተሰቡ ጋር ተቀላቀልው ሲመርጡ ነበር፡፡ የምርጫ ሒደቱን በተመለከተ ከማንኛውም አካል በግልጽ የደረሰ ሪፖርት እንደሌላቸው ተናግረዋል፡፡
በከተማዋ በሚገኙ የምርጫ ጣቢያዎች በርካታዎቹ ስማቸውን አስተባባሪዎችን በመጠየቅ ካልሆነ ምንም ዓይነት አመላካች ስም ያልተለጠፈባቸው፣ እንዲሁም የፀጥታ አካላት መራጮችን እየፈተሹ ሲያስገቡ ተስተውሏል፡፡ ይህ ዓይነቱ ተግባር በአዲስ አበባ ከተማ የምርጫ ጣቢያዎች መከሰቱን የሚገልጹ ጥቆማዎች ደርሶኛል ያለው ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፣ አጣሪ ቡድን ማሰማራቱን በምርጫው ዕለት ያሰታወቀ ሲሆን፣ በባህር ዳር በተካሄደው የምርጫ ሒደት ላይ ግን ቦርዱ የገለጸው ጉዳይ የለም፡፡ ሪፖርተር በባህር ዳር ከተማ የውስጥ ለውስጥ መንገዶች የተቋቋሙ የምርጫ ጣቢያዎችን እየቃኘ በነበረበት ወቅት፣ አራት አባላትን የያዘ ተንቀሳቃሽ ቡድን በግሽ ዓባይ ክፍለ ከተማ የነዋሪዎችን በር እያንኳኳና የነዋሪዎችን ስም እየጠራ ‹‹ካርድ መልሱ›› የሚል ማሳሰቢያና የማስታወሻ ጥሪ ሲያደርጉ ተመልክቷል፡፡
ሪፖርተር ድርጊቱን ሲፈጽሙ የነበሩትን ግለሰቦች ማንነትና ምን እያደረጉ እንደሆነ ሲጠይቃቸው፣ መንግሥትን የወከሉ መሆናቸውንና ዜጎች የወሰዱት ካርድ ዋጋ ያለው በመሆኑ ድምፅ እንዲሰጡ ለማሳሰብ ነው የሚል ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ በአብዛኞቹ የባህር ዳር ከተማ የምርጫ ጣቢያዎች በአመዛኙ የተመዘገቡ መራጮች ቁጥር ከ1,500 በታች የመራጮች ቁጥር ያለው ሲሆን፣ ሰኞ በተካሄደው የምርጫ ውሎ በርካቶቹ ከምሽቱ 12 ሰዓት በማጠናቀቅ የቆጠራ ሥራው ወዲያውኑ ዘግተው ሲያካሂዱ ነበር፡፡
በምርጫው ዕለት በከተማዋ ውስጥ የይለፍ ካርድ ከተሰጣቸው ተሽከርካሪዎች ውጪ ምንም ዓይነት እንቅስቃሴ ያልነበረ ሲሆን፣ ለምርጫው የሚመጡ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ቁጥራቸው በዛ ባሉ በታጠቁ ኃይሎች ታጅበው ነው፡፡ ሰኞ አመሻሽ በከተማዋ የነበረው የሰዎች እንቅሰቃሴ ገና ጀምበር መግባቷን ተከትሎ ነዋሪው ወደ ጎጆው በመግባቱ በከተማ ውስጥ ከፀጥታ አካላት ውጪ የተለይ እንቅስቃሴ አልነበረም፡፡ የምርጫ ውሎ መጠናቅን ተከትሎ የአማራ ክልል የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት የምርጫውን ሒደት በተመለከተ በባህር ዳር ከተማ ጊዮን ኢኮ ሎጅ ቅጥር ግቢ ምሽት ላይ በሰጠው መግለጫ፣ 7ኛው አገራዊ ምርጫ በክልሉ በሰላም ተጠናቋል ብሏል።
ለሕዝቡ ተወካዮች ምክር ቤት የሚወዳደሩት የኢዜማው አቶ ኃይለ ማርያምና የጋራ ምክር ቤቱ ሰብሳቢ አቶ ተስፋሁን ዓለምነው በተገኙበት መግለጫ፣ ‹‹ምርጫው ለአገራችን ትልቅ ዕድል ይዞ ነው የመጣው፤›› በሚል የገለጹ ሲሆን፣ አቶ ተስፋሁን በማብራሪያቸው የክልሉ ሕዝብ ፀሐይና ዝናብን ጨምሮ የትኛውንም ጫና ተቋቁሞ ሲመርጥ በመዋሉ፣ ‹‹ሕዝባችንን አጥብቀን አብዝተን ማመስገን እንፈልጋለን፤›› ብለዋል፡፡
‹‹ሕዝቡ በድምፁ መንግሥት መመሥረት እንደሚችል በተግባር ያሳየበት ‹‹ትልቅ ምርጫ ነው፡፡ ይህ ምርጫ ካለፉት ምርጫዎች በብዙ መሥፈርቶች ቢታይ የተሻለና እንደ ፖለቲካ ፓርቲም አሳታፊነቱን ያየንበት ነው፤›› ሲሉ አስረድተዋል፡፡ በክልሉ 23 የፖለቲካ ፓርቲዎች መሳተፋቸውን የገለጹት ሰብሳቢው፣ ‹‹እንደ ባለፉት ምርጫዎች ሰበብ እየተፈጠረ ፓርቲዎች ከምርጫው እንዲደናቀፉ አልተደረገም፤›› በማለት ተናግረዋል፡፡
በምርጫው ማግሥት ማክሰኞ ማለዳ በጊዜያዊነት የተቋቋሙ የምርጫ ጣቢያዎች የፈረሱ ሲሆን፣ በአብዛኞቹ ጣቢያዎች የምርጫ ውጤቱ ለዕይታ አስቸጋሪ በሆነና ለንባብ እምብዛም በማይስቡ የካርቦን ኮፒ ወረቀቶች በየግድግዳውና በየመብራት ፖሎች ተለጥፈው ነዋሪዎች ተጠግተው ሲያነቡ ተስተውሏል፡፡ ተሽከርካሪና ነዋሪዎች ጠፍተውባቸው የነበሩ የባህር ዳር ከተማ አውራ ጎዳናዎች ማክሰኞ ወደ ነበሩበት የዕለት ተዕለት ሕይወት እንደገና ተመልሰዋል፡፡
የምርጫውን ውሎ በተመለከተ በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የባህር ዳር ቅርንጫፍ አስተባባሪ አቶ ሞላልኝ ደሳለኝ ማክሰኞ ከሰዓት በኋላ ለሪፖርተር በሰጡት ማብራሪያ፣ በባህር ዳር ከተማ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አንድ፣ እንዲሁም ለክልል ምክር ቤት ሁለት መቀመጫዎች መቅረባቸውን ጠቅሰው፣ በ164ቱም ጣቢያዎች በሰላማዊና የቀረበ ቅሬታ ሳይኖር ምርጫው መጠናቀቁን ተናግረዋል፡፡
ሁሉም የምርጫ ጣቢያዎች እስከ ማክሰኞ ግንቦት 25 ቀን ከቀኑ ሰባት ሰዓት ድረስ ጊዜያዊ ወጤት መለጠፋቸውንና የምርጫ ቁሳቁሶች ወደ ምርጫ ክልሉ ተልከዋል ብለዋል፡፡ በባህር ዳር ክተማ ለመራጭነት ከተመዘገቡ 184 ሺሕ አካባቢ መራጮች 177,400 ድምፅ መስጠታቸውን ተናግረዋል፡፡ በባህር ዳር ያሉ የምርጫ ጣቢያዎች በዛ ያሉ በመሆናቸው አጠቃላይ የማዳመር ሥራው ለአምስት ቀናት ያህል እንደሚፈጅ ጠቅሰው፣ በቀጣይ ቀናት ውጤቱ ተደምሮ ለሕዝብ ይፋ ይደረጋል ብለዋል፡፡
