- ጥቃቅንና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች ራሱን የቻለ ስታንዳርድ እንደሚወጣላቸው ተገልጿል
እ.ኤ.አ. ከ2030 ዓለም አቀፍ የሒሳብ ሪፖርት አቀራረብ ዘላቂነትን የተመለከቱ ሁለት ስታንዳርዶች (International Financial Reporting Standard-Sustainability Disclosure Standards) ትግበራ አስገዳጅ እንደሚሆን፣ የኢትዮጵያ ሒሳብ አያያዝና ኦዲት ቦርድ አስታወቀ፡፡
ቦርዱ ይኼን ያስታወቀው የኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ሪፖርት አቀራረብ ስታንዳርዶች (Sustainability Disclosure Standards – IFRS) የዘላቂነት ትግበራ ፍኖተ ካርታ ይፋ ማድረጊያ ሁለተኛ ዙር ዓውደ ጥናት፣ ከሰኔ 15 እስከ 17 ቀን 2018 ዓ.ም. ሲካሄድ ነው።
የኢትዮጵያ ሒሳብ አያያዝና ኦዲት ቦርድ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ ፅዋዬ ሙሉነህ፣ ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የሒሳብ ሪፖርት አቀራረብ ስታንዳርድን በአዋጅ በተደነገገው መሠረት እየተገበረች እንደምትገኝ፣ በአሁኑ ወቅት ደግሞ ከፋይናንስ ባሻገር ዘላቂነት ላይ ያተኮሩ (IFRS S1) እና (IFRS S2) የተሰኙ ስታንዳርዶችን እንዲተገበሩ ልታደርግ እንደሆነ ገልጸዋል።
ዓለም አቀፉ የሒሳብ ሪፖርት ደረጃ ዘላቂነት ስትራቴጂካዊ ፍኖተ ካርታ ሲወጣ አገሮች መቼ መተግበር አለባቸው የሚለውን ዕድል መስጠቱን የተናገሩት ወ/ሮ ፅዋዬ፣ በኢትዮጵያ እ.ኤ.አ. ከ2024 ጀምሮ ሁለት ዓመት ወስዶ ሲዘጋጅ እንደነበር፣ እ.ኤ.አ. በ2030 ሙሉ ለሙሉ መተግበር ይሮርባታል ተብሎ መፅደቁን አስረድተዋል።
ሆኖም አቅም ያላቸው መሥሪያ ቤቶች በግላቸው መተግበር እንፈልጋለን የሚሉ ከሆነ አሁን መጀመር እንደሚችሉ፣ ሆኖም የሰው ኃይል ማሟላትና ዕቅድ ማውጣት የሚፈልጉ ከሆነ ደግሞ እ.ኤ.አ. ከ2030 ጀምሮ መተግበር ይኖርባቸዋል ብለዋል።
‹‹IFRS S1›› ኩባንያዎች ከዘላቂነት (Sustainability) ጋር የተያያዙ ማናቸውንም ሊያጋጥሟቸው የሚችሉ ሥጋቶችና መልካም አጋጣሚዎችን በሙሉ የፋይናንስ ሪፖርታቸው ላይ እንዲያካትቱ የሚያዝ ነው። ‹‹IFRS S2›› ደግሞ በተለይ በአየር ንብረት ለውጥ ላይ ያተኩራል። አንድ ኩባንያ በአየር ንብረት መዛባት ምክንያት ምን ያህል የገንዘብ አደጋ ሊደርስበት እንደሚችል ለምሳሌ በጎርፍ፣ በድርቅ ወይም በሕግ ለውጦች ሳቢያ፣ እንዲሁም የበካይ ጋዝ ልቀትን ለመቀነስ ምን እየሠራ እንደሆነ በዝርዝር የሚያስረዳበት ነው።
ኢትዮጵያ እነዚህን ደረጃዎች እንደ አንድ የዓለም አገር መተግበር እንዳለባትና ለዚህም መቼ? እንዴት? በምን ሁኔታ? ትተገብረዋለች የሚሉ ጥያቄዎችን የያዘ ስትራቴጂካዊ ዕቅድ ማዘጋጀቷን ምክትል ዋና ዳይሬክተሯ ገልጸዋል። ዓውደ ጥናቱም ስትራቴጂካዊ ፍኖተ ካርታው ሰዎች ጉዳያቸውን ወደ ቤታቸው ወስደው ለመተግበር እንዲዘጋጁ፣ በተለይ ባንኮች፣ ኢንሹራንሶችና የተለያዩ የመንግሥት የልማት ድርጅቶችና መሥሪያ ቤቶች እንዲሰናዱ ለማድረግ የሚረዳ ነው ብለዋል።
From The Reporter Magazine
ስትራቴጂካዊ ፍኖተ ካርታው ለአብነት የአንድ ተቋም የፋይናንስ ደረጃ ወይም አቅም ምን ላይ እንደሚገኝ፣ ለአየር ንብረት ያለው ተጋላጭነት ምን እንደሚመስልና በዚህ ላይ ለመሥራት ከየት መነሳት እንዳለበት መሥፈርቶችን የሚያስቀምጥ መሆኑን አብራርተዋል። እነዚህ ደረጃዎች መተግበር አንድ ኢንቨስተር ወደ ኢትዮጵያ ለመምጣት ሲያስብ ያለውን ሥጋት እንዲያውቅ እንደሚያስችል፣ የፋይናንስ ውድቀት እንዳይመጣ በማድረግ የማኅበረሰብን ጥቅም ለማስጠበቅ እንደሚረዳም ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ የሰነድ ሙዓለ ንዋይ ግብይት መጀመሯን ያወሱት ምክትል ዋና ዳይሬክተሯ፣ ወደ አገር ውስጥ የሚመጡ የውጭ ኢንቨስተሮች በሳይንሳዊ መንገድ የተሠራ የሒሳብ ሪፖርት ካለ ግን እምነት ኖሯቸው እንዲሠሩ እንደሚያስችል አስረድተዋል። እነዚህ ስታንዳርዶች ተቋማት ዘላቂ እንዲሆኑ በማድረግ የአገር ኢኮኖሚ እንዲጠናከር፣ የሕዝብና የመንግሥት ጥቅም እንዲጠበቅ የሚያደርጉ በመሆናቸው ትግበራው አስፈላጊ ነው ብለዋል።
የዓለም አቀፉ የሒሳብ ሪፖርት አቀራረብ ትግበራ ጅምር መኖሩን፣ ሆኖም የዕውቀት ክፍተትና የሰው ኃይል እጥረት በሚገባ እንዳይተገበር ተግዳሮት መፍጠሩን አስረድተዋል።
From The Reporter Magazine
ለዚህም እንደ አገር ባለፈው ዓመት የተመሰከረላቸው የሒሳብ ባለሙያዎች ኢንስቲትዩት በአገር ደረጃ መቋቋሙን፣ ይህም ከተለያዩ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በጋራ በመሥራት በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን በተለያዩ የዓለማችን አገሮች የሚሠሩ ብቁ ባለሙያዎች ለማፍራት፣ ያለውን ውስን የባለሙያዎችን ቁጥር ለማሳደግ እንደሚረዳ ተናግረዋል።
የሚሰጠው ሥልጠና ብቁ በሆነ ኢኒስቲትዩት መሰጠት እንደሚኖርበት፣ ሆኖም ተማሪዎች ስለጉዳዩ ዕውቀት ጨብጠው እንዲያድጉ በሥርዓተ ትምህርት ውስጥ ማካተት እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል። ለአብነት በኬንያ ተማሪዎች ከሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ጀምሮ የሒሳብ አቀራረብ ሪፖርት ዕውቀት እንዲጨብጡ እየተደረገ መሆኑን አውስተዋል።
የሒሳብ አያያዝና ኦዲት ቦርድ አማካሪ አቶ ደረጀ ኦላና በበኩላቸው፣ ስትራቴጂካዊ ፍኖተ ካርታው ሁለት ጉዳዮች ላይ መሠረት ማድረጉን፣ አንደኛው እንደ አገር ቶሎ ቢተገበር ምን ጥቅም ያስገኛል የሚለው ላይ እንደሚያተኩር፣ ይህም የውጭ ኢንቨስትመንትን ለመሳብና ምርትን ወጪ ንግድን መላክን ያበረታታል ተብሎ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል።
ሁለተኛ አካባቢያዊ ተግዳሮቶች አንድ ድርጅት የሚያገኘው ገቢ እንዲቀንስ፣ ብድር ለማግኘት እንዲቸገር ወይም ወለዱ እንዲጨምርበት ሊያደርጉ እንደሚችሉ ጠቁመዋል። ፖሊሲው በድርጅቶች ላይ የሚያደርሰውን ተፅዕኖ መከላከል በተመለከተ ትኩረት መሰጠቱን፣ በተለይ የሚደርሰው ተፅዕኖ ሪፖርት ቀርቦ ድርጅቶች ኢንቨስተሮችን መሳብ፣ በቀላሉ ብድር ማግኘት እንዲችሉና ገቢያቸውን እንዲያሳድጉ የሚረዳ ነው ብለዋል።
በአገር ደረጃ የተዘጋጀው ስትራተጂካዊ ፍኖተ ካርታ ሦስት መሠረታዊ ጥያቄዎች እንደሚፈታ፣ አንደኛው ተግባሪ ተቋማት እነ ማን እንደሆኑ እንደሚለይ፣ መቼ ነው የሚተገበረው የሚለው ሁለተኛ ጉዳይ መሆኑን፣ በሪፖርታቸው ምን ጉዳይ ነው የሚያካትቱት የሚለው ሦስተኛ መሆኑን አማካሪው አስረድተዋል።
ተግባሪ ተቋማት በአራት ቡድን መከፈላቸውንና ቡድን አንድ ውስጥ ሁለት ትልልቅ የመንግሥት ልማት ድርጅቶች፣ ስድስት ትልልቅና መካከለኛ አቅም ያላቸው ባንኮች፣ ትልልቅ የግል ድርጅቶች መካተታቸውንና ትግበራውን በሞዴልነት ይጀምራሉ ብለዋል። እነዚህ ተቋማት ከመጪው ሐምሌ ወር ጀምሮ ደረጃ በደረጃ የዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ የሒሳብ ሪፖርት ማዘጋጀት እንደሚጀምሩና እ.ኤ.አ. በ2030 ሙሉ ለሙሉ እንደሚያጠናቅቁ ገልጸዋል። ጊዜው የረዘመበት ምክንያቱን ሲያስረዱ የአቅም ውስንነት፣ የተደራጁ የዳታ ማዕከላት አለመኖርን ሳይጠቅሱ አላለፉም።
በተለይ ያለውን የሰው ኃይል አቅም ለማሳደግ ኢንስቲትዩት መቋቋሙን፣ ከዚህም ጎን ለጎን የሥልጠና ስትራቴጂ እየተዘጋጀ መሆኑንም አስረድተዋል። በሥልጠና ስትራቴጂው ከሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች አንስቶ እስከ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሥርዓተ ትምህርት ውስጥ ተካቶ እንዲሰጥ መታቀዱን፣ ከትምህርት ሚኒስቴር ጋር ሥራዎች እንደሚከናወኑ አስረድተዋል።
በምሥራቅ አፍሪካ ኬንያ፣ ሩዋንዳ፣ ታንዛኒያና ኡጋንዳ ፍኖተ ካርታውን እየተገበሩ መሆናቸውን ጠቅሰው፣ ኢትዮጵያ ፈጥና ወደ ትግበራው መግባት እንዳለባት አሳስበዋል።
ጥቃቅንና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች በዚህ ፍኖተ ካርታ አለመካተታቸውን፣ ሆኖም በሞዴልነት ከጀመሩ ተቋማት ልምድ ተወስዶ ራሱን የቻለ ስታንዳርድ እንዲዘጋጅላቸውና እንዲተገብሩ እንደሚደረግ ተናግረዋል።
እ.ኤ.አ. ከ2030 ጀምሮ እንደ አገር የዘላቂነት ስታንዳርዶች የተከተለ የሒሳብ ሪፖርት ማቅረብ አስገዳጅ እንደሚሆን፣ ቦርዱም ተቋማት መሥፈርቶችን ተከትለው እንደሚሠሩ ክትትል እንደሚያደርግ አክለዋል።
የኢትዮጵያ ሒሳብ አያያዝና ኦዲት ቦርድ፣ ከፋይናንሺያል ሴክተር ዲፕኒንግ አፍሪካ (FSD Africa)፣ ከፋይናንሺያል ሴክተር ዲፕኒንግ ኢትዮጵያና የጀርመን ተራድኦ ድርጅት በመተባበር ያዘጋጀው የሦስት ቀናት ዓውደ ጥናት ተቆጣጣሪ ባለሥልጣናት፣ ኦዲተሮችና ተዛማጅ ባለሙያዎች በአገር ደረጃ ስለተዘጋጀው ስትራቴጂካዊ ፍኖተ ካርታ አተገባበር፣ በውስጡ ስለያዛቸው እንደ የዘላቂነት ሪፖርት አቀራረብ፣ የአየር ንብረት አደጋዎችና ዕድሎች፣ የተቋማት አስተዳደርና የአደጋ አስተዳደር መሥፈርቶች አስመልክቶ የተሻለ ግንዛቤ እንዲኖራቸው የሚያደርግ መሆኑን የቦርዱ መረጃ ያሳያል።
