
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ እ.ኤ.አ. እስከ 2040 ድረስ በዓለም ላይ ካሉ 20 ቀዳሚና ተወዳዳሪ የአቪዬሽን ተቋማት አንዱ ለመሆን፣ ዓመታዊ ገቢውንም ወደ 29 ቢሊዮን ዶላር ለማሳደግ ያለውን ግዙፍ ስትራቴጂካዊ ዕቅድ ይፋ አደረገ።
አየር መንገድ ግሩፑ ዕቅዱን ይፋ ያደረገው ከሚያዚያ 9 እስከ 12 ቀን 2018 ዓ.ም. የቆየው፣ የኢትዮጵያ የመሠረተ ልማትና ኮንስትራክሽን ሳምንት መክፈቻ ሥነ ሥርዓት፣ በአዲስ ኢንተርናሽናል ኮንቬንሽን ሴንተር ሲካሄድ ነው።
‹‹እንደ አገር የመሠረተ ልማት ግንባታን እንዴት እንመራለን?›› በሚል መነሻ ሐሳብ፣ የኢትዮጵያ የአየር መንገድ ለ80 ዓመታት በዘርፉ ያለውን ልምድ አጋርቷል።
የአየር መንገዱ የንግድ ዘርፍ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ለማ ያደቻ ባቀረቡት ማብራሪያ መሠረት፣ አየር መንገዱ አሁን ያለውን 7.6 ቢሊዮን ዶላር ዓመታዊ ገቢ በማሳደግ እ.ኤ.አ. እስከ 2040፣ 29 ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ ግብ አድርጎ እየሠራ መሆኑ ገልጸዋል።
በ“ራዕይ 2040” ዕቅድ ውስጥ የተካተቱ ዋና ዋና ዓላማዎች መካከል አሁን ያለውን የአውሮፕላኖች ብዛት ከ145 ወደ 356 ማሳደግ፣ የመዳረሻዎችን ብዛት አሁን ካለው የዓለም አቀፍ መዳረሻዎች ከ144 ወደ 290 እና የአገር ውስጥ መዳረሻዎች ከ24 ወደ 47 ለማድረስ ታቅዷል ተብሏል።
በተጨማሪም አየር መንገዱ በዓመት የሚያጓጉዛቸውን መንገደኞች ቁጥር ወደ 63.9 ሚሊዮን ለማድረስ፣ የካርጎ አገልግሎቱንም ወደ 1.9 ሚሊዮን ቶን ከፍ ለማድረግ ማቀዱንም አቶ ለማ ገልጸዋል።
ይህ በዚህ እንዳለ አየር መንገዱ ሚያዚያ 12 ቀን 2018 ዓ.ም. በይፋ እንዳስታወቀው፣ ስድስት የቦይንግ 787 ድሪምላይነር አውሮፕላኖችን ለመግዛት የነበረውን አማራጭ (Options) በመቀየር የግዥ ትዕዛዝ (Firm Order) ፈጽሟል።
From The Reporter Magazine
በአሜሪካ አርሊግተን ቨርጂኒያ ውስጥ ባለው የቦይንግ ቢሮ በተካሄደው የፊርማ ሥነ ሥርዓት፣ የቦይንግ የንግድ ሽያጭና ግብይት ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ አንበሴ ይትባረክ፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ መስፍን ጣሰው፣ የአሜሪካ የንግድ ዲፓርትመንት የአድቮኬሲ ማዕከል (Advocacy Center) ኃላፊ ሂሮ ሮድሪጌዝ እንዲሁም፣ የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሽዴና በአሜሪካ የኢትዮጵያ አምባሳደር ብናልፍ አንዷለም በተገኙበት መከናወኑን አውሮፕላን አምራቹ ኩባንያ አስታውቋል።
አየር መንገድ ግሩፑ የግዥ ትዕዛዝ በፈጸመባቸው ስድስት 787 ድሪምላይነር (Dreamliner) አውሮፕላኖች አኅጉር ተሻጋሪ (Intercontinental) የጉዞ መስመሮቹን ለማስፋፋትና የካርጎ አቅሙን ለማሳደግ እንደሚያውልም ተጠቅሷል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ በአሁኑ ወቅት በአፍሪካ ትልቁን የ787 ድሪምላይነር አውሮፕላኖች (Dreamliner Fleet) ፍሊት ያስተዳድራል፣ 787-8 እና 787-9 አውሮፕላኖቹን ከአዲስ አበባ ወደ አውሮፓ፣ እስያና ወደ ሰሜን አሜሪካ ለሚያደርጋቸው በረራዎች እንዲሁም፣ በአፍሪካ ውስጥ ላሉት ዋና ዋና መስመሮች እንደሚጠቀም ተገልጿል።