ከየካቲት ወር 2014 ዓ.ም. ጀምሮ የኢትዮጵያ አገራዊ ምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነር በመሆን ሲያገለግሉ የነበሩትና ባደረባቸው ሕመም በሕክምና ሲረዱ ቆይተው ግንቦት 3 ቀን 2018 ዓ.ም. በ84 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩት ኮሚሽነር ዘገየ አስፋው፣ የቀብር ሥነ ሥርዓት በነገው ዕለት ግንቦት 6 ቀን 2018 ዓ.ም. ከቀኑ 6፡00 ሰዓት በቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የሚፈጸም መሆኑን የኢትዮጵያ አገራዊ ምክክር ኮሚሽን አስታወቀ፡፡
ኮሚሽነር ዘገየ አስፋው በ1934 ዓ.ም. በምዕራብ ሸዋ የተወለዱ ሲሆን፣ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ከቀድሞው ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ (ከአሁኑ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ) እንዲሁም፣ የማስተርስ ዲግሪያቸውን አሜሪካ ከሚገኘው ከዊስኮንሲ ማዲሲን ዩኒቨርሲቲ በሕግ ማግኘታቸውን የምክክር ኮሚሽን የሕይወት ታሪክ መዝገባቸውን አስመልክቶ ያወጣው መረጃ ያሳያል።
ኮሚሽነር ዘገየ አስፋው ሥራ ከጀመሩበት ዘመን ጀመሮ በተለያዩ የመንግሥት ተቋማት የሠሩ ሲሆን፣ በተለይም በቀድሞዎቹ የመሬት አስተዳደር ሚኒስቴር፣ የግብርናና የሠፈራ ሚኒስቴር፣ የፍትሕ ሚኒስቴር እንዲሁም፣ የሥራና ማኅበራዊ ጉዳዮች ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች በሚኒስትርነት ካገለገሉባቸው ተጠቃሾች መሆናቸው ተገልጿል፡፡ የግብርና ሚኒስቴርን ከ1968 እስከ 1970 ዓ.ም. እና ከ1983 እስከ 1984 ዓ.ም. በሚኒስትርነት ማገልገላቸውን የግብርና ሚኒስቴር መረጃ ያሳያል።
ኮሚሽነር ዘገየ አስፋው በ1967 ዓ.ም. የወጣው የ‹‹መሬት ላራሹ››ን አዋጅ በማርቀቅና በማስፈጸም ጉልህ ሚና እንደነበራቸው በብዙዎች ዘንድ እንደሚታወስ ኮሚሽኑ ገልጿል፡፡
ከሕግ ሙያቸው ባሻገር በተለያዩ ሰብዓዊ ተግባራት የሚታወቁት ኮሚሽነር ዘገየ፣ ‹‹ሁንዴ›› የሚባል ለትርፍ ያልተቋቋመ ግብረ-ሰናይ ድርጅትንና ቡሳ ጎንፋ የተባለ ማይክሮ ፋይናንስን በማቋቋምና በመምራት በርካታ ግብረ ሰናይ ተግባራትን ሲያከናውኑ መቆየታቸውን የግል ማኅደራቸው እንደሚያስረዳ፣ በዚህም የብዙዎችን ሕይወት በመቀየር ጠንካራ የሚባል ሥራን መሥራታቸውን ኮሚሽኑ ገልጿል፡፡
ኮሚሽነር ዘገየ ከእነዚህ ሥራዎቻቸው ባሻገር ከተለያዩ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ጋር በመሆን በሰብዓዊ መብት አያያዝ ዙሪያ በርካታ ሥራዎችን መሥራታቸውን፣ በተለይም የሰብዓዊ መብት አንቂ በመሆን የኢትዮጵያ ክፍል በሚኖሩ ሴቶች ላይ የሚፈጸሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን በማውገዝ፣ የሚሻሻልበትን መንገድ በመንደፍና ትምህርቶችን በማስተማር ረገድ በርካታ ተግባራትን ማከናወናቸውን ኮሚሽኑ ጠቅሷል፡፡
በሌላ በኩል ኮሚሽነር ዘገየ በአካባቢ ጥበቃና ተያያዥ ጉዳዮች ከአርሶ አደሮች ጋር ለውጥን ሊያመጣ የሚችል ሥራ እንዲሠራ በማድረግ ረገድ ፊት አውራሪ እንደነበሩ፣ ይህም ተነሳሽነታቸው በአንዳንድ አካባቢዎች የአርሶና የአርብቶ አደሮችን ኑሮ እንዲሻሻል ጉልህ ሚና እንደነበረው እንደሚወሳ ተመላክቷል።
From The Reporter Magazine
አቶ ዘገየ አስፋው የኢትዮጵያ አርሶ አደሮች በግፍ የተነጠቁት መሬት እንዲመለስላቸውና የመሬት ሥሪት እንዲቀየር ግንባር ቀደም ሚና የተጫወቱ መሆናቸውንና በተለያየ ጊዜያት በሚኒስትርነት አገራቸውን ማገልገላቸውን፣ ከዚህም በተጨማሪ በመጨረሻው የዕድሜ ዘመናቸው ነባር ችግሮች በምክክር ለመፍታት በተቋቋመው አገራዊ የምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነርነት እያገለገሉ የነበሩና እጅ አጠሮችን በመደገፍ ዕድሜያቸውን ሙሉ አገራቸውን ያገለገሉ ብርቱ አባት ነበሩ በማለት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓቢይ አህመድ (ዶ/ር) ሐዘናቸውን ገልጸዋል።
ፕሬዚዳንት ታየ አጽቀ ሥላሴ በበኩላቸው፣ የኢትዮጵያ አርሶ አደሮች የዘመናት ፍትሐዊ ጥያቄ የሆነው መሬት ለአራሹ መልስ እንዲያገኝ በግንባር ቀደምትነት ጉልህ አስተዋጽኦ ያደረጉ ተራማጅ ነበሩ ሲሉ ገልጸው፣ በማረፋቸው ሀዘን እንደተሰማቸው ተናግረዋል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትን ጨምሮ የተለያዩ ተቋማትና ግለሰቦች ኮሚሽነር ዘገዬ ሞት የተሰማቸውን ሐዘን እየገለጹ ይገኛሉ።
