የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) የሥነ ሕዝብ ፈንድ፣ መንግሥት በአሥር ሚሊዮን ለሚቆጠሩ ሴቶች ወሳኝ ነው ያለው የንፅህና መጠበቂያ ቁሳቁስ ላይ የታክስና ቀረጥ ክፍያ እንዲያሻሽል ጠየቀ፡፡
ሐምሌ 12 ቀን 2018 ዓ.ም. የመንግሥት ባለሥልጣናትና ተቆጣጣሪ አካላት፣ የጉመሩክ ኮሚሽን የሥራ ኃላፊዎችን ጨምሮ የተመድ አጋር ድርጅቶችና ሌሎችም በኢትዮጵያ ታክስ ፖሊሲ ምኅዳር ውስጥ ያተኮረ ውይይት ሲያካሂዱ ነው ጥያቄው የቀረበው፡፡
በኢትዮጵያ 47 ሚሊዮን ሴቶች የንፅህና መጠበቂያ እየተፈተኑበት ያለ ቁሳቁስ ነው ያለው ተቋሙ፣ በድህነት ውስጥ ከሚኖሩ ሴቶች መካከል 43 በመቶ የሚሆኑት ወርኃዊ ገቢያቸው ሁለት እሽግ ብቻ ለመግዛት ያውሉታል ብሏል፡፡ በዚህ አስቸጋሪ ሁኔታ ምክንያት ሴት ሕፃናት ትምህርት ቤት መሄድ እንዳይችሉ፣ ሴቶች ገቢያቸውን በከፍተኛ መጠን እንደሚበላውና ለችግር ተጋላጭነት እንዲዳረጉ አድርጓቸዋል ብሏል፡፡
ከውጭ ለሚገቡ የንፅህና መጠበቂያዎች በመንግሥት ከሚጣለው ታክስና ቀረጥ በተጨማሪ፣ በአገር ውስጥ የሚመረቱ የንፅህና መጠበቂያ ቁሳቁሶች የጥራታቸው ጉዳይ አሳሳቢ በመሆኑ፣ ጥራቱ ሊስተካከል እንደሚገባ የገለጸው የተመድ የሥነ ሕዝብ ፈንድ፣ ከጥራቱ እኩል የታክስና የቀረጥ ማሻሻያዎች እንዲደረጉ ጥሪ አቅርቧል፡፡
የጤና ተቆጣጣሪ ተቋማት የሴቶች ንፅህና መጠበቂያ ቁሳቁሶችን እንደ ወሳኝ የጤና ግብዓቶች እንደሚያዩዋቸው፣ የኢትዮጵያ የታክስ ሥርዓት ቁሳቁሶቹን እንደ ቅንጦት ዕቃ ለ15 በመቶ ተጨማሪ እሴት ታክስና የጉምሩክ ቀረጥ፣ እንዲሁም ተጨማሪ የክፍያ ግዴታዎች እንደተጣለበት ገልጿል፡፡
በኢትዮጵያ ለሴቶች የንፅህና መጠበቂያ ቁሳቁሶች ጊዜያዊ ዕርዳታ ከሚመስልና በልግስና ከሚደረግ ሥርጭትና የበጎ አድራጎት ተግባር ባለፈ፣ የሴቶች የድህነት መጠን መቀነስ ያስፈልጋል ብሏል፡፡
አገር በቀል ድርጀቶች ጥራቱን የጠበቀ ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያቀርቡ የሚያስችል አቅም በመፍጠር ችግሩን መፍታት እንደሚያስፈልግ አሳስቧል፡፡
From The Reporter Magazine
የተመድ የሥነ ሕዝብ ፈንድ ችግሩ እንዲፈታ ከሚመለከታቸው ተቋማት ጋር በቁርጠኝነት እንደሚሠራ ገልጾ፣ የታክስ ፖሊሲው አገሪቱ ከገባችው የጤናና የፆታ እኩልነት ቁርጠኝነት ጋር አቀናጅታ እንድታከናውን ጥሪ አቅርቧል፡፡