- ምርጫ ቦርድ ቅሬታዎች እየተመረመሩ ነው ብሏል
ጎጎት ለጉራጌ አንድነትና ፍትሕ ፓርቲ በጉራጌና በምሥራቅ ጉራጌ ዞኖች በምርጫው ሒደት ከፍተኛ የሕግ ጥሰት በመፈጸሙ፣ ድጋሚ ምርጫ እንዲደረግና ምርጫውን ያስፈጸሙ አካላት የሕግ ተጠያቂ እንዲሆኑ ጠየቀ፡፡
ፓርቲው በሰባተኛው አገራዊ ምርጫ ዕለትና ድኅረ ምርጫ የሚመለከቱ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ሰኔ 4 ቀን 2018 ዓ.ም. ሲሰጥ ነው ጥያቄውን ያቀረበው፡፡
ፓርቲው በተወዳደረባቸው አካባቢዎች ምርጫው ከሞላ ጎደል ሰላማዊ ሆኖ መጠናቀቁን የገለጹት የሥራ አስፈጻሚና የማዕከላዊ ኮሚቴ አባልና የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ወልዴ ብርሃኑ፣ ይህ ማለት ግን ምርጫው ፍትሐዊ፣ ነፃና ዴሞክራሲያዊ ነበር ማለት አይደለም ብለዋል፡፡
በጉራጌና በምሥራቅ ጉራጌ ዞኖች በድምፅ መስጫ ዕለትና በቆጠራው ዕለት ሒደቱ ሙሉ በሙሉ በገዥው ፓርቲ ቁጥጥር ሥር የወደቀበት፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በሒደቱ ላይ የነበረው ቁጥጥር ከእጁ የወጣበት እንደነበር ፓርቲው መገንዘቡን ገልጸዋል፡፡
‹‹በአካባቢው ገለልተኛ ታዛቢዎችና ነፃ ሚዲያዎች አለመኖራቸው፣ የፀጥታ ኃይሎች የሕግ ጥሰት ሲፈጸም ለማስቆምና ሕጋዊ ዕርምጃ ለመውሰድ ፈቃደኛ አለመሆናቸው፣ የምርጫ አስፈጻሚዎች በገዥው ፓርቲ ካድሬዎች ተፅዕኖ ሥር መውደቃቸውና የገዥው ፓርቲ ዕጩዎችና ካድሬዎች ያለ ምንም ከልካይ ዋነኛ የምርጫ አስፈጻሚና ቆጣሪ የሆኑበትን ሁኔታ ተመልክተናል፤›› ብለዋል፡፡
የድምፅ አሰጣጡ ‹‹አንድ ሰው አንድ ድምፅ›› ከሚለው መርህ አፈንግጦ መራጮች መታወቂያ ሳይጠየቁና የጣት ምልክት ሳይቀቡ መርጠው መውጣታቸው፣ በካርድ አወሳሰድ ወቅት ከነበረው ከፍተኛ መዛነፍ ጋር ተዳምሮ በገዥው ፓርቲ የተደራጁ ቡድኖች ያለ ምንም ከልካይ በተደጋጋሚ ድምፅ እንዲሰጡ ዕድል የሚሰጥ እንደነበር ፓርቲው በሰጠው መግለጫ አስታውቋል፡፡
የዜጎችን ካርድ በመሰብሰብ ወደ ድምፅ መስጫ ሳይሄዱ በስማቸው ድምፅ መስጠት፣ ሐሰተኛ የድምፅ መስጫ ወረቀቶች በብዛት ጥቅም ላይ መዋል፣ መራጮች ወደ ድምፅ መስጫ ቦታዎች ሲመጡ በገዥው ፓርቲ ላይ ምልክት የተደረገበት የድምፅ መስጫ ወረቀት መስጠት፣ እንዲሁም ድምፅ መስጠት ከመጀመሩ በፊት ተሞልተው የተቀመጡ የድምፅ መስጫ ሳጥኖች መገኘታቸውን አቶ ወልዴ አስረድተዋል፡፡
From The Reporter Magazine
የድምፅ ቆጠራውም ገለልተኛ ሚዲያዎችና ታዛቢዎች በሌሉበት በገዥው ፓርቲ ሹሞችና ዕጩዎች ቀጥተኛ ፍላጎትና ቁጥጥር ሥር የተደረገ ነበር ብለዋል፡፡
የጎጎት ፓርቲ ፕሬዚዳንት አቶ መሐመድ አብራር በበኩላቸው፣ ‹‹ቅሬታ ባቀረብንባቸው ቦታዎች ምርጫ መድገም በትንሹ የምንጠብቀው ውጤት ነው፡፡ ነገር ግን በዚህ አሠራር ምርጫው ከተደገመ ፋይዳ እንደማይኖረው ግልጽ ነው፤›› ብለዋል፡፡
ምርጫውን ባስፈጸሙ አካላት ላይ የወንጀል ተጠያቂነት ሊኖር እንደሚገባ፣ ከፈጸሙት ወንጀል አኳያ ወደፊት በየትኛውም የምርጫ ሒደት መሳተፍ እንደሌለባቸው የፓርቲያቸው አቋም መሆኑን ገልጸዋል፡፡
From The Reporter Magazine
ከምርጫው በፊት አስፈጻሚዎቹ በገንዘብ ተይዘው እንደነበር መረጃ እንደነበራቸው የገለጹት ፕሬዚዳንቱ፣ አስፈጻሚዎቹ ከአንድ ምርጫ ክልል ወደ ሌላ ምርጫ ክልል እንዲቀየሩ ቦርዱን ጠይቀው እንደነበርና ነገር ግን ይህ እንዳልሆነ አስረድተዋል፡፡
ምርጫው እስከተደረገበት ዕለት ድረስ በአካባቢዎቹ ስንት መራጮች እንደተመዘገቡ የሚገልጽ መረጃ በምርጫ ክልል ደረጃ ማግኘት ባለመቻላቸው፣ ለቦርዱ አቅርበው መልስ ሳያገኙ መቅረታቸውን አቶ መሐመድ ተናግረዋል፡፡
‹‹አስተማማኝና እምነት ሊጣልበት የሚችል ማጣራት ከተደረገ የምርጫ ውጤቱ ምንም ሆነ ምን ለመቀበል አንቸገርም፡፡ ነገር ግን አጣሪ ጉባዔው በምስክሮች ብቻ መፍትሔ ያገኛል ብለን አናምንም፤›› ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ወ/ሮ ሜላትወርቅ ኃይሉ ሰኔ 4 ቀን 2018 ዓ.ም. በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ለቦርዱ ቅሬታቸውን ካቀረቡ ፓርቲዎች መካከል አንዱ ጎጎት መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በ120 የምርጫ ክልሎች የፖለቲካ ፓርቲዎች ቅሬታ አቅርበው በሕግ ባለሙያዎች እየታዩ መሆናቸውን፣ እሳቸው መግለጫውን እስከሰጡበት ዕለት ድረስ 148 ምስክሮች መሰማታቸውን፣ በእነዚህ የምርጫ ክልሎች ላይ ውሳኔ ሳይሰጥ ውጤት እንደማይገለጽ አስረድተዋል፡፡
