- ደረሰ የተባለው ጥቃት ከፍተኛ የሕዝብ ቁጣ ቀስቅሷል
- መንግሥት የማያዳግም ዕርምጃ እየወሰደ መሆኑን የሚኒስትሮች ምክር ቤት ባወጣው መግለጫ አስታውቋል
መንግሥት በኦሮሚያ ክልል አርሲ ዞን አሰኮ፣ ሽርካ፣ ሆንቆሎ፣ ዋቤና ሙኔሳ ወረዳዎች ውስጥ በኦርቶዶክስ ምዕመናን ላይ የሚደርሱ ተደጋጋሚ ጥቃቶችን እንዲያስቆም ተጠየቀ፡፡
በኦሮሚያ ክልል ውስጥ የሚገኘው የአርሲ አገረ ስብከት ለመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽሕፈት ቤት፣ ግንቦት 23 ቀን 2018 ዓ.ም. የደረሰውን ሞትና የንብረት ውድመት ለማሳወቅ በተጻፈው ደብዳቤ ነው ጥያቄው የቀረበው፡፡
አገረ ስብከቱ ከዚህ ቀደም በቤተ ክርሲያንና በምዕመናን ላይ በተደጋጋሚ የሚደርሱ ጥቃቶችን ለማስቆም፣ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ደረጃ ከከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት ጋር ውይይት ተደርጎ በዘላቂነት መፍትሔ እንዲያገኝ መሞከሩን፣ ነገር ግን አሁንም ጥቃቶቹ መቀጠላቸውን ገልጿል፡፡
በሰረካ ወረዳ ለ101 ዓመታት የቆየውና የአገር ቅርስ የሆነው የተለታ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ሙሉ በሙሉ በእሳት ተቃጥሎ መውደሙን፣ በአጥቢያው ነዋሪ የሆኑ ዘጠኝ ምዕመናን በአሰቃቂ ሁኔታ በታጣቂዎች ሕይወታቸው ማለፉን አገረ ስብከቱ በደብዳቤው አስታውቋል፡፡
በሰረካ ወረዳ በጠለታ፣ ካራ ኩፍቴ፣ ዘዲቡ እሬቻ፣ ቅዱስ ሚካኤል፣ ሱንቴ ቅድስት ማርያም፣ በቦንግዶ አቦ፣ ሌንጫ ኦዳ፣ በጂንሶና ኳስ ሜዳ በሚባሉ አካባቢዎች የነበሩ የክርስቲያኖች መኖሪያ ቤቶች ሙሉ በሙሉ መውደማቸውንና በአጠቃላይ ከ280 በላይ አባወራዎች አካባቢያቸውን ለቀው መሰዳቸውን ገልጿል፡፡
በአርሲና በሶማሌ ክልል ጅግጅጋ አኅጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በአባ ኤልሳዕ ተፈርሞ በተላከው በዚህ ደብዳቤ፣ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነትና ቅዱስ ሲኖዶስ ዓመታትን ያስቆጠረውን የአብያተ ክርስቲያናት ውድመት፣ የምዕመናን ግድያና ስደት እንዲያበቃ፣ ከሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ጋር ውይይት በማድረግ ዘላቂ መፍትሔ እንዲሰጥ ጠይቋል፡፡
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትሪያሪክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ግንቦት 26 ቀን 2018 ዓ.ም. ባስተላለፉት መልዕክት፣‹‹በአርሲ ሀገረ ስብከት በአሶኮ፣ በሽርካ፣ በሆንቆሎ፣ በዋቤና በሙኔሳ ወረዳዎች፣ በመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችንና በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ላይ ስለደረሰው አሰቃቂ ጥቃት የሰማነው በተሰበረ ልብ ነው፤›› ብለዋል።
From The Reporter Magazine
ቤተ ክርስቲያን በምድራዊ መከራ ውስጥ ያሉትን ምዕመናን በምታፅናናበት ወቅት ፈተና ውስጥ ሆና ከመቸገሯ በላይ፣ በአርሲ በተደጋጋሚ የሚስተዋለው በደልና ግፍ በሁሉም ልብ ውስጥ ‹‹እስከ መቼ?›› የሚል የቁጭትና የሐዘን ጥያቄን መፍጠሩን ገልጸዋል፡፡
የፀጥታ አካላትና በየመዋቅሩ የሚገኙ አካላት የዜጎችን ደኅንነት የመጠበቅና ሰላም የማስፈን አደራ አለባቸው ያሉት ፓትሪያርኩ፣ ይህን የጥቃት ሰንሰለት በማስቆምና ወንጀለኞቹን ለሕግ በማቅረብ ከታሪክ ባለዕዳነት ይድኑ ዘንድ በቤተ ክርስቲያኗ ስም አሳስበዋል፡፡
አክለው በየአካባቢው የሚገኙ ምዕመናንና መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ የተፈናቀሉ ዜጎችን በመደገፍና በፀሎት ከቤተ ክርስቲያኗ ጎን እንዲቆሙ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡
From The Reporter Magazine
የኢትዮጵያ ሃይማኖት ተቋማት ጉባዔ በተመሳሳይ ቀን ባወጣው የሐዘን መግለጫ፣ በአርሲ ዞን በንፁኃን ላይ የደረሰውን ግድያና በቤተክርስቲያናት ላይ የደረሰውን ቃጠሎ አውግዟል፡፡
‹‹ቀደም ሲል አሁን ችግር በተከሰተባቸው አካባበዎች ተመሳሳይ ጥቃት እንዳይፈጸም መንግሥት ለንፁኃን ዜጎች አስተማማኝ ጥበቃና ከለላ እንዲያደርግላቸው ጉባዔያችን መጠየቁ የሚታወስ ነው፤›› ያለው ጉባዔው፣ ‹‹ሆኖም ችግሩ ሳይቀረፍ ተጨማሪ ጉዳትና ሥቃይ በእነዚሁ ቦታዎች በድጋሚ መከሰቱ ሐዘናችንን እጥፍ ድርብ አድርጎታል፤›› ብሏል፡፡
መንግሥት የዜጎችን ሰላምና ደኅንነት የማረጋገጥ ቀዳሚ ኃላፊነቱን እንዲወጣና ከቤት ንብረታቸው ለተፈናቀሉ ዜጎች፣ አሁንም የጥቃት ሥጋት ላለባቸው ወገኖች ጥበቃ እንዲያደርግ ጠይቋል፡፡
ጉዳዩን በማስመልከት በጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ በብፁዕ አቡነ ሳዊሮስና በቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የተመራ የቤተ ክርስቲያኗ ልዑክ ከሰላም ሚኒስትር አቶ መሐመድ እድሪስና ከሚኒስትር ደኤታው ኸይረዲን ተዘራ (ዶ/ር) ጋር ግንቦት 27 ቀን 2018 ዓ.ም. መወያየታቸው ተገልጿል፡፡
መንግሥት የችግሩን ምንጭ አጣርቶ ዘላቂ መፍትሔ እንዲፈልግና በአካባቢው አስተማማኝ ሰላም እንዲያሰፍን ሁለቱ የቤተ ክርስቲያኗ አመራሮች መጠየቃቸው ተመላክቷል፡፡
ከአካባቢዎቹ የተፈናቀሉ ዜጎች ወደ ቀዬአቸው እንዲመለሱና እንዲቋቋሙ እንዲደረግ፣ ወንጀሉን የፈጸሙ ሰዎችም ለፍርድ ቀርበው ቅጣታቸውን እንዲያገኙ በውይይቱ ወቅት ጠይቀዋል ተብሏል፡፡
የሰላም ሚኒስትሩ አቶ መሐመድ እድሪስ በበኩላቸው በመንግሥት በኩል አጣሪ ቡድን ተቋቁሞ ወደ ቦታው መላኩን፣ የቡድኑን ሪፖርት መሠረት በማድረግም አስፈላጊው ዕርምጃ እንደሚወሰድ መግለጻቸው ተነግሯል፡፡
በተጨማሪም የቤተ ክርስቲያኗ አባቶች በኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት ጽሕፈት ቤት ከክልሉ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና ከብልፅግና ፓርቲ ጽሕፈት ቤት አመራሮች ጋር ውይይት ማድረጋቸው የተገለጸ ሲሆን፣ የክልሉ መንግሥት ከፍተኛ ተጋድሎ በማድረግ ሊከሰት የነበረውን የከፋ ችግር ማስቀረቱ በኃላፊዎች መገለጹ ተጠቁሟል፡፡
የኦሮሚያ ክልል መንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ኃይሉ አዱኛ ግንቦት 26 ቀን 2018 ዓ.ም. በሰጡት መግለጫ፣ አልፎ አልፎ በአንዳንድ የክልሉ ዞኖች ሽብርተኛ ሲሉ የጠሩት ቡድን በንፁኃንና በሕዝብ አገልግሎት ላይ ያነጣጠረ የጭካኔ በትር ሲሰነዝር ይታያል ብለዋል፡፡
ሰባተኛውን አገራዊ ምርጫ ለማደናቀፍ ‹‹ከታሪካዊ ጠላቶቻችን›› ተልዕኮ ወስዶ ተንቀሳቅሶ እንደነበር ገልጸው፣ ነገር ግን ሕዝቡ መንግሥት መሆን የሚቻለው በምርጫ ብቻ ነው በሚል ድምፅ መስጠቱን ተናግረዋል፡፡
ጥቃቱን ያደረሰውም በዚህ የተደናገጠው ቡድን መሆኑን የገለጹት ኃላፊው፣ ንፁህን ዜጎች ሕይወት ማለፉንና በቤተ ክርስቲያን ላይ ያነጣጠረ ጥቃት መፈጸሙን አስታውቀዋል፡፡ የብሔርና ሃይማኖት ግጭት በማስነሳት አብሮ የኖረውን ማኅበረሰብ እሴት ለመሸርሸርና የእርስ በርስ ጦርነት ለመቀስቀስ ታቅዶ ነበር ብለዋል፡፡
‹‹ሙስሊሙም ክርስቲያኑም፣ አማራውም ኦሮሞውም በጋራ የሚኖርበት አካባቢ ስለሆነ ሕዝቡ ሳይከፋፈል የጠላትን ተልዕኮ ማክሸፍ ተችሏል፤›› ያሉት አቶ ኃይሉ፣ ‹‹ማኅበረሰቡም መንግሥትም መስዋትነት ከፍለው ቀበሌውን መቆጣጠር ባይችሉ ኖሮ ከዚህ የከፋ ጉዳት ይደርስ ነበር፤›› በማለት አክለዋል፡፡
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ቋሚ ሲኖዶስ ዓርብ ግንቦት 28 ቀን 2018 ዓ.ም. ባካሄደው መደበኛ ስብሰባ፣ በአርሲ አገረ ስብከት በመገኘት፣ ጉዳት የደረሰባቸው ምዕመናንን የሚያፅናኑና አስፈላጊውን ጊዜያዊ ድጋፍ የሚያደርጉ አባቶችን መመደቡን አስታውቋል፡፡
በአርሲ ዞን በኦርቶዶክስ ቤተ እምነቶችና ምዕመናን ላይ የተፈጸመው ግፍ የተሞላበት ድርጊት ሁሉንም ኢትዮጵያዊ ያስቆጣና መንግሥት የማያዳግም ዕርምጃ እንዲወስድ ያስጠየቀ ነው፡፡
በአርሲ ዞን በኦነግ ሸኔ አማፅያን በንፁኃን ዜጎች ላይ በተለይም በሃይማኖት ተቋማት ዓላማ ተደርገው የተፈጸሙ ጥቃቶችን ያወገዙት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር)፣ የቤተሰቦቻቸውንና የወዳጆቻቸውን ሕይወት ላጡ፣ የአካል ጉዳት ለደረሰባቸውና የቤት ንብረታቸው ለወደመባቸው በኢትዮጵያ መንግሥት ስም የተሰማቸውን ጥልቅ ሐዘን መግለጻቸውን የሚኒስተሮች ምክር ቤት ግንቦት 28 ቀን 2018 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
ጥቃቶቹ የአገሪቱን ብሔራዊ ዕድገት ለማደናቀፍ ከሚሹ አካላት፣ በአማራ ክልል ከሚንቀሳቀሱ የአገር ውስጥ አማፂ ቡድኖችና ለአገሪቱ ሁለንተናዊ ዕድገት ጥላቻ ካላቸው የውጭ ኃይሎች ጋር በቅንጅት የተከናወኑ መሆናቸውንና ዓላማቸውም በኢትዮጵያ አለመረጋጋትንና የምርጫ መስተጓጎልን ለመፍጠር ሲደረግ የነበረ የጥፋት ውጥን ተከታይ መሆኑን በመግለጫው ተጠቁሟል።
መንግሥት 7ኛው ጠቅላይ ምርጫ ያለ አንዳች የፀጥታ ችግር ፍትሐዊና አሳታፊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ከአንድ ዓመት በላይ የዘለቀ ልዩ ትኩረትና ዝግጅት በማድረግ በቁርጠኝነት ሲሠራ መቆየቱን የሚገልጸው መግለጫው፣ በሌላ በኩል የጥፋት ኃይሎች ከባዕዳን ጋር ቅንጅት በመፍጠር እኩይ ዓላማቸውን ለማሳካት ሰፊ የጥፋት ዝግጅት ሲያደርጉ ቆይተዋል ብሏል፡፡ አገራዊ ምርጫው እንዳይከናወን ሰፊ ርብርብ አድርገዋል። በተጨማሪም በቅድመ ምርጫና በምርጫ ወቅት የዜጎችን የመምረጥ መብትና ነፃነት ለመንፈግና ለማደናቀፍ የጥፋት እጅ ዘርግተዋል ብሏል።
የጥፋት ኃይሎች በመደጋገፍና በመናበብ አመፅና ሁከት ለማነሳሳት፣ ከተሞችን በሽብር ጥቃት ለማወክ፣ በመንገዶች የደፈጣ ጥቃት በመፈጸም፣ እንቅስቃሴን ለመግታትና በተወሰኑ አካባቢዎች ዓላማ አድርገው ነጥሎ ለማጥቃት መንቀሳቀሳቸውን መግለጫው ያብራራል። የጦር መሣሪያ፣ ተተኳሾችና ሌሎች የሎጂስቲክስ ድጋፍ በማቅረብ፣ በደቡባዊ ትግራይ በሚገኙ አዋሳኝ የአማራ ክልል አንዳንድ ቦታዎች ላይ ትንኮሳ መፈጸማቸውንም ጠቁሟል። በአማራ ክልል ባህር ዳር፣ ጎንደር፣ ደብረ ብርሃንና ወልድያ ከተሞችን ጨምሮ በክልሉ ዋና ዋና ከተሞችና በሌሎች ላይ ዓላማ በማድረግ ያካሄደው የሽብር እንቅስቃሴና ግጭቶች፣ በአዲስ አበባ ከተማ ባደራጃቸው ሌሎች አማፅያን በተመረጡ አካባቢዎች ላይ ጥቃት እንዲፈጽሙ ተንቀሳቅሰው የነበረ ቢሆንም፣ የጥፋት ሥራው ሳይሳካ እንዲከሽፍ ማድረግ መቻሉን መግለጫው ያብራራል።
በተመሳሳይ በኦሮሚያ ክልል የሸኔ ሽብር ቡድን ከፀረ ሰላሙ ፋኖ ታጣቂ ቡድን ጋር በመናበብ፣ በአንዳንድ አካባቢዎች መንገዶችን በመዝጋት እንቅስቃሴን ለማስቆምና ለማስተጓጎል የተንቀሳቀሰ ቢሆንም፣ በፀጥታ ኃይል በተወሰደበት የተጠናከረ ዕርምጃ ፍላጎቱን ማሳካት አልቻለም ብሏል፡፡
ቡድኑ በፀጥታ ኃይሉ የተወሰደበትን ዕርምጃ መቋቋም ባለመቻሉና ፍላጎቱን ማሳካት ባለመቻሉ፣ የሃይማኖትና የብሔር ግጭት ለመቀስቀስ በማለም፣ በአርሲ ዞን አስኮና አካባቢው ጥቃት ለመፈጸም ሁለቱ አሸባሪ የጥፋት ኃይላት ርብርብ ያደረጉ ቢሆንም፣ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ሁኔታውን በመቆጣጠር ዕርምጃ እየወሰዱ እንደሚገኙ መግለጫው ያብራራል።
መንግሥት በምርጫው ወቅት በብዙ የአገሪቱ አካባቢዎች ሊከናወኑ የነበሩ የጥቃት ዕቅዶችን በስኬት ማክሸፍ መቻሉንና በንፁኃን ዜጎች ላይ የሚፈጸሙ ጥቃቶችን፣ ፍርኃትና ክፍፍልን ከሚያመጡ የብቀላ ዘመቻዎች በመንግሥት የደኅንነት መዋቅርና ኦፕሬሽኖች አማካይነት በከፍተኛ ሁኔታ እንዲበታተን ማድረጉን መግለጫው ያብራራል፡፡ ሃይማኖታዊ ክፍፍልን ለመዝራት የኃይል ጥቃትንና ውድመትን እንደ መሣሪያ የሚጠቀሙ አካላት በሁሉም ኢትዮጵያውያን ዘንድ በግልጽ ሊወገዙ እንደሚገባም አሳስቧል። በታገጣቂዎችም ይሁን በሌላ ፅንፈኛ አካል በኢትዮጵያ ውስጥ ምንም ዓይነት የወደፊት ዕድል እንደሌላቸው ለማሳየት የተቀናጀ ብሔራዊ ምላሽ በመስጠት ወሳኝ ዕርምጃዎችን መውሰድ እንደሚቀጥልም አክሏል፡፡
በንፁኃን ዜጎች ላይ ጥቃት የሚፈጽሙ አካላት፣ ድርጊታቸውን ምክንያታዊ ለማስመሰል ምንም ዓይነት የፖለቲካ ንግግር ቢጠቀሙ፣ ወሳኝ ዓላማን እያሳኩ ሳይሆን ወንጀል እየፈጸሙ ነው። የፖለቲካ ቅሬታዎች በኢትዮጵያ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓት፣ በብሔራዊ ምክክር ሒደትና በዴሞክራሲያዊ ተቋማት አማካይነት መፍትሔ ሊያገኙ የሚችሉና ሊያገኙ የሚገባቸው መሆናቸውን በመግለጫው ጠቁሟል።
