
የሚዲያ ምኅዳሩ እ.ኤ.አ ከ2018 ወዲህ በነበሩት ሁለትና ሦስት ዓመታት በታሪኩ አግኝቶት የማያውቀውን አስቻይ ሁኔታ የተቀዳጀበት ወርቃማ ዘመን ሊባል በሚያስችል ደረጃ ደርሶ እንደነበር በርካቶች የሚስማሙበት ቢሆንም፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተፈጠረው የፋይናንስና የነፃነት ማጣት ተቋማቱ እየተዘጉ፣ ባለሙያዎች ደግሞ ዘርፍ እየቀየሩ መሆናቸውን የሚዲያው ባለቤቶችና ጋዜጠኞች እየገለጹ ነው፡፡
በአገሪቱ እ.ኤ.አ. በ2018 ወደ ሥልጣን በመጡት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር)፣ መንግሥት በተካሄዱ ዘርፈ ብዙ የሕግና የአሠራር ማሻሻያዎች ምክንያት፣ የዓለም የሚዲያ ነፃነት ቀን በዓለም አቀፍ ደረጃ በአዲስ አበባ መከበሩ ይታወሳል፡፡
የሕግ ማሻሻያ ከመካሄዱ ቀደም ብሎ በነበሩ ጊዜያት በዚሁ ዓመት ድንበር የለሽ የጋዜጦች ቡድን ባወጣው የሚዲያ ምኅዳር ደረጃ፣ ኢትዮጵያን 150ኛ ላይ መድቧት የነበረ ቢሆንም፣ ይህ ምኅዳር በቀጣዮቹ ሦስት ዓመታት በርካታ መሻሻሎችን አሳይቶ ነበር፡፡
ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ. በ2019 110ኛ፣ በ2020 99ኛ፣ በ2021 101ኛ ደረጃ አግኝታ የነበረ ቢሆንም፣ ነገር ግን የሚዲያ ምኅዳሩ እያሽቆለቆለ እ.ኤ.አ. በ2022 114ኛ፣ በ2023 130ኛ፣ በ2024 141ኛ፣ እንዲሁም በ2025 145ኛ ደረጃ ስትይዝ፣ አንድ ሳምንት ባስቆጠረው እ.ኤ.አ. በ2026 ደረጃዋ ከወራት በኋላ ይታወቃል፡፡
የአውሮፓ ኅብረት፣ የአሜሪካ መንግሥት፣ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅትና ሌሎች በሚዲያና በዴሞክራሲ ቁመና ላይ የሚሠሩ፣ የሚከታተሉና የሚደግፉ ዓለም አቀፍ ተቋማት፣ በኢትዮጵያ የመገናኛ ብዙኃን ተቋማትና ባለሙያዎች ላይ የሚደርሰው ዛቻ፣ ማስፈራሪያ፣ ዕገታና እስር መጨመሩን በተለያዩ ጊዜያት አስታውቀዋል፡፡
ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በተወሰኑ የመንግሥት ከፍተኛ ኃላፊዎች ዘንድ፣ ‹‹የብሔራዊ ጥቅምንና አገርን የሚጎዳ ዘገባ ሠርተሃል፣ አስተባብል›› በሚል የተለመደ ማስጠንቀቂያ አዘል ማሳሰቢያዎችን መስማትና እንደ ሪፖርተር ጋዜጣ ላሉ የግል የሚዲያ ተቋማት እየተደወለ ወይም ደብዳቤ እየተላከ፣ ‹‹ወደ ተቋማችን መጥታችሁ አብራሩልን›› የሚሉ ከሕግ ያፈነገጡ አካሄዶች በስፋት እየተስተዋሉ ነው።
ሪፖርተር በማዕድን፣ በኢንቨስትመንት፣ በፋይናንስና በሌሎች ጭምር የሕዝብንና የአገርን ጥቅም ሊታደጉ የሚችሉ ዘገባዎች በመሥራቱ፣ ‹‹ብሔራዊ ጥቅምን ነክታችኋል፣ ማስተባበያ ስጡ›› በሚል ተደጋጋሚ ምልልሶችን አድርጓል፣ እያደረገም ይገኛል፡፡
From The Reporter Magazine
በተመሳሳይ የኑሮ ውድነት አሳሳቢነትንና የዋጋ ንረትን ወይም የፖለቲካ አመለካከታቸውን በተመለከተ ለሪፖርተር አስተያየታቸውን የሰጡ ታዋቂ ስም ያላቸው ግለሰቦች ሳይቀሩ እንዲያስተባብሉ ተደውሎ ማስጠንቀቂያ የተሰጣቸው ቢሆንም የተናገሩትን ሀቅ መልሰው እንደማይውጡ ምላሽ መስጠታቸውን ሪፖርተር ከአስተያየት ሰጪዎቹ ሰምቷል። በሌላ በኩል የመንግሥት ባለሥልጣናት ለመረጃ ሲደወልላቸውም፣ ‹‹ለሪፖርተር መግለጫ መስጠት አንችልም›› በማለት ምክንያታቸውን ሳይናገሩ በደፈናው መረጃ ከመስጠት ይቆጠባሉ፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅም ለትርጉም አሻሚ ባልሆነ መንገድ ለማንኛውም የኅብረተሰብ ክፍል ተደራሽ እንዲሆን ተተርጉሞና ተደንግጎ በግልጽ ባይቀመጥም፣ የአገሪቱን ደኅንነትና ጥቅም የሚጎዱ አስተሳሰቦችን ሕዝቡ በደቦ ሲያወግዘው እንደሚታይ፣ በሚዲያ ተዘግቦ ሲገኝም ኅብረተሰቡም ተጠያቂነትን አጥብቆ እንደሚሻ የሚናገሩ አሉ፡፡
ይሁን እንጂ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ዕድገቱ ገና በጨቅላነት ደረጃ እንዳለ በሚነገርለት የሚዲያ ምኅዳር ውስጥ በተወሰነ መንገድም ቢሆን የመንግሥት ተቋማትንና ኃላፊዎችን ያልተገባ አሠራር የሚጎነትሉና የሕግ ተጠያቂነት የሚያነሱ ከሆነ፣ የተቋማት ኃላፊዎች ብሔራዊ ጥቅም በማሳበብ የሚዲያ ተቋማቱን አፍ ለማዘጋት የማያደርጉት ጥረት እንደሌለ ይነገራል፡፡
From The Reporter Magazine
የማኅበረሰብ የጋራ ዕሳቤንና ዕይታን በመቀየር ሚዲያ ከፍተኛ ሚና እንዳለው በመናገር የሚታወቀውና ዘሊዛርድ ኪንግ እየተባለ የሚጠራው የሮክ ባንድ አቀንቃኝ ጂም ሞሪሰን፣ ‹‹ሚዲያን የተቆጣጠረ አዕምሮን ይቆጣጠራል›› በማለት ያደረጉት ንግግር አሁን ድረስ በምሳሌነት ይጠቀሳል።
የአቀንቃኙ ጠንካራ ንግግር ከዛሬ 50 ዓመታት በፊት ገና ኢንተርኔትና ማኅበራዊ ሚዲያ ከመወለዳቸው አስቀድሞ የተነገረ ነው፡፡ የንግግሩ ጥንካሬ ከኢንተርኔትና ከማኅበራዊ ሚዲያ ውልደትና ዕድገት ጋር እየተዳከመ የመጣ ነው ቢባልም፣ አንዳንዶች የአቀንቃኙ ንግግር በኢትዮጵያ በግልጽ እንደሚንፀባረቅ ይናገራሉ።
በአፍሪካ አኅጉር በሕዝብ ቁጥራቸው ከኢትዮጵያ በእጅጉ ያነሰና ተቀራራቢ ቁጥር ያላቸው እንደ ደቡብ አፍሪካ፣ ኬንያ፣ ሞሮኮ፣ ታንዛኒያ፣ ጋና፣ ኡጋንዳ፣ ናይጄሪያና ግብፅ ጠንካራ ተደማጭ፣ ተመራጭና ተገዳዳሪ የሆኑ የቴሌቪዥንና የሬዲዮ ጣቢያዎች፣ እንዲሁም በኅትመት ሚዲያ ከኢትዮጵያ የተሻሉ ስለመሆናቸው መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ በበርካታ አመላካቾች የኢትዮጵያ የሚዲያ ኢንዱስትሪ ከበርካታ የዓለም አገሮች ጋር ሲወዳደር በብዛት፣ በጥራት፣ በዕድገት፣ በስፋትና በይዘት ገና ግርጌ ላይ የሚገኝ ነው።
በኢትዮጵያ ከጥቂት ዓመታት በፊት ተስፋ ሰጪ ነው ተብሎለት በነበረው የሚዲያ ምኅዳር፣ የሕግ ማሻሻያዎች በመደረጋቸው፣ አየር ላይ ወጥተው የነበሩ የሚዲያዎች ቁጥር ተስፋ ሰጪ ነበር። ይሁን እንጂ በፋይናስ እጥረት፣ በምኅዳር ጥበትና በነፃነት ዕጦት፣ እንዲሁም በሚዲያ ተቋማቱ የራሳቸው የይዘት ደካማነት ምክንያት በርካቶች በየጊዜው እየተመናመኑ ከገበያ ወጥተዋል።
ለአብነት ያህል ገበያ ውስጥ ከጠፉት የኅትመት ውጤቶች መካከል ፍትሕ መጽሔት፣ ደይሊ ሞኒተር ጋዜጣ፣ ሲራራ ጋዜጣ፣ አዲስ አድማስ ጋዜጣና አዲስ ማለዳ ጋዜጣ ሲሆኑ፣ ከቴሌቪዥን ሥርጭት ደግሞ ናሁ ቴሌቪዥን፣ አሐዱ ቴሌቪዥን፣ አሻም ቴሌቪዥን፣ አፍሪ ሔልዝ ቴሌቪዥን፣ ኤል ቲቪ፣ ኢሳትና ጄ ቲቪ በመጠኑ የሚጠቀሱ ናቸው።
የአዲስ አድማስና የአዲስ ማለዳ ጋዜጦች ከኅትመት ከወጡ በኋላ በድረ ገጽ ዜና ማስነበባቸውን ቀጥለዋል። እንደ አሐዱ፣ ናሁና ኢሳት የመሳሰሉ ቴሌቪዥን ጣቢያዎች ደግሞ ሥርጭታቸውን ወደ ዩቲዩብ በማዘዋወር ቀጥለዋል።
ሥርጭት ወይም ኅትመት አቋርጠው ከወጡት የሚዲያ ተቋማት መካከል፣ በራሳቸው የይዘትና የፕሮግራም ደካማነትና በፋይናንስ ችግር ምክንያት የወጡ በርካቶች ናቸው።
በሥርጭት ላይ ከሚገኙት መካከል አንዳንዶቹ የተቋቋሙበትን ዓላማ ለማስቀጠል ሞዳሊቲ ለመቀየር ስለመገደዳቸው ይናገራሉ። ለረዥም ዓመታት በጋዜጠኝነት ሙያ ውስጥ ያገለገሉ አንድ በግል የንግድ ሚዲያ ውስጥ በኃላፊነት እየሠሩ የሚገኙ ጋዜጠኛ ስሜ አይጠቀስ ብለው ለሪፖርተር በሰጡት አስተያየት፣ በኢትዮጵያ ሚዲያ ውስጥ ያሉት ዘርፈ ብዙ ችግሮችና ተፅዕኖዎች ከመብዛት ባለፈ በቴሌቪዥን ሥራ ለማከናወን የሚያስፈልገው ኢንቨስትመንት ከፍተኛ መሆኑ ተግዳሮቱን ያገዝፈዋል ይላሉ።
ይህ ደግሞ ሥርጭታቸውን በሳተላይት አማካይነት ለማከናወን የውጭ ምንዛሪ አስፈላጊ በሆነባቸው ተቋማት ላይ የባሰ መሆኑን ጠቅሰው፣ በእነዚህ ሁኔታዎች የተነሳ በርካታ የቴሌቪዥን ጣቢያዎች ከሳተላይት ሥርጭት እንዲወርዱና ዲጂታል ላይ ብቻ እንዲሠሩ፣ የተወሰኑት ደግሞ ሙሉ ለሙሉ ሥራ ለማቆም መገደዳቸውን ያብራራሉ።
ባለሙያው እንደሚሉት የፕሮዳክሽን ወጪ መጨመር፣ የማስታወቂያና የስፖንሰርሺፕ ሥራው በኤጀንሲዎች የበላይነት ሊባል በሚችል ደረጃ የተያዘ በመሆኑና ኤጀንሲዎችም ከራሳቸው ትርፍና ኪሳራ አንፃር የማስታወቂያ ፍሰቱን ወደ ተወሰኑ የሚዲያ ተቋማት ብቻ የመላክ ሁኔታ አለ ይላሉ፡፡ ይህ ዓይነቱ ሒደት ጀማሪና አዳጊ የሆኑ ሚዲያዎችን በእጅጉ መጉዳቱንና ሥራቸውን ፈታኝ እንዳደረገው አክለው ገልጸዋል፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ ማስታወቂያ የሚያስነግሩት በአመዛኙ መንግሥታዊ የልማት ድርጅቶች ቢሆኑም፣ የማስታወቂያ አሰጣጡ ኢፍትሐዊነት ስለሆነና ለመግሥትና መንግሥታዊ ይዘት ያላቸው ሚዲያዎች ብቻ በመሆኑ ይህ ደግሞ የግሉ ሚዲያ አቅም ፈጥሮ ለመሥራት አዳጋችና ፈታኝ እንዳደረገበት አስረድተዋል፡፡
በኢትዮጵያ ሥራ ላይ ከሚገኙ ጥቂት የግል ሚዲያዎች መካከል ሀገሬ ቴሌቪዥን አንዱ ሲሆን፣ ጣቢያው አስቸጋሪ ያላቸውን ሁኔታዎች ተቋቁሞ ለማለፍ በቅርቡ የአስተዳደር፣ የይዘትና የባለቤትነት ለውጥ ጭምር በማድረግ በአየር ላይ ለመቆየት ጥረት ማድረጉን ሪፖርተር ከተቋሙ ኃላፊዎች ሰምቷል።
የሀገሬ ቴሌቪዥን ጣቢያ ቀጣይነት ለማረጋገጥና በርካታ ሚዲያዎቸ እየተፈተኑበት ያለውን ችግር ለመሻገር የሚያስችል አማራጭ ተደርጎ የተወሰደው፣ ባለቤትነቱን መቀየርና አዲስ የሥራ አመራር ቦርድ ማቋቋም መሆኑን የተናገሩት የተቋሙ የቀድሞ የቦርድ ሰብሳቢ አቶ ሰማው ንጋቱ ናቸው።
የሀገሬ ቴሌቪዥን ባለአክሲዮኖች ሚዲያው ከሚዘጋ ይልቅ እንደ ሚዲያ መቆየት እንዲችልና ጣቢያው በጥናት አዘጋጅቶ ሸልፍ ላይ ያስቀመጣቸውን የፕሮግራም ይዘቶች በጥሩ ይዘት ለማስቀጠል፣ ሁለት የተሻለ ሀብት ያላቸው ባለአክሲዮኖችን በማካተት አዲስ የቦርድ አመራር መዋቀሩን የቀድሞው የቦርድ ሰብሳቢ ይናገራሉ።
‹‹ሀገሬ ቴሌቪዥን ጠንካራ ጋዜጠኞች አሉት፣ እነዚህን ጋዜጠኞች የተሻለ የፋይናንስ አቅም ያላቸው ባለቤቶች ወደ ጣቢያው በማምጣት በቀጣይ በአየር ላይ መቆየት ብቻ ሳይሆን፣ የተሻለ አቅም ያለው ተወዳዳሪ እንዲሆን ያደርገዋል፤›› ብለዋል፡፡ አቶ ሰማው አክለውም ባለሙያውን ይዞ የተሻለ ሀብት አፍስሶ ጥሩ ሥራ ለሚሠራ አካል ማስተላለፍ፣ የተሻለ ሚዲያ ለመፍጠር ትክክለኛ ምርጫ ተደርጎ ተወስኖ የገባንበት ነው ብለዋል፡፡
ለማኅበረሰብ ዕድገት የሚበጁ አማራጭ የሚዲያ ድምፆች መሬት ላይ በተግባር መኖር አለባቸው የሚሉት አቶ ሰማው፣ ፖለቲካው ያለ ሚዲያ የማይሠራ መሆኑን፣ የሚዲያ ተቋማት የሕዝብን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ሊያረጋግጡ ለሚችሉ ተግባራት ቅድሚያ በመስጠት አገርን ማስቀደም ያስፈልጋል ሲሉም አብራርተዋል፡፡
በአጠቃላይ ሁሉም ሚዲያዎች ፍትሐዊ ማስታወቂያዎችን እንዲያገኙ የሚያደርግ አሠራር በመፍጠር፣ የግል ባለሀብቶችና ባለሙያዎች ገንዘባቸውንና ዕውቀታቸውን አቀናጅተው እንዲሠሩ የሚያደርግ አሠራርን በመዘርጋት፣ የመንግሥትን ድጋፍ በማጠናከር የኢትዮጵያን ሚዲያ ኢንዱስትሪ መታደግ ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
የሰብዓዊ መብቶች፣ የሲቪክና በአጠቃላይ የዴሞክራሲ ምኅዳሩ በከፍተኛ ፍጥነት ማሽቆለቆሉን ስሜ አይጠቀስ ያሉ አንድ ጋዜጠኛ፣ በአሁኑ ጊዜ ሚዲያዎች አራተኛ መንግሥት የሚባለው ዕሳቤ ቀርቶ የመንግሥት አካላት የሥጋት ምንጭ ተደርገው እየታሰቡ ነው ይላሉ፡፡ ጋዜጠኛ ሆነው በመሥራታቸው ምክንያት ከአገራቸው የተሰደዱ፣ የታሰሩ፣ የታገቱና ሙያቸውን የቀየሩ በርካቶች ናቸው የሚሉት ባለሙያው ይህ ሊሆን የቻለው መንግሥት በተቀያየረ ቁጥር ራሳችውን ችለው የማይቆሙ የዴሞክራሲ ተቋማት በመጥፋታቸው ነው ብለዋል፡፡
በዚህ ጫናው በበዛው የመገናኛ ብዙኃን ዘርፍ በጋዜጠኞች ከለላ ላይ የሚሠራው ሲፒጄ የተሰኘው ድርጅት አ.እ.ኤ. ከ2020 ጀምሮ 54 ጋዜጠኞች ከአገር መሰደዳቸውን አስታውቋል፡፡ አብዛኛዎቹ በአፍሪካ አኅጉር ውስጥ ጥገኝነት የጠየቁ ናቸው ብሏል፡፡
ናሁ ቴሌቪዥን ባለፉት ጥቂት ዓመታት ጠንከር ያሉ ሐሳቦችን በዘገባና በውይይት ለተመልካቾች ሲያቀርብ የቆየ ሚዲያ ሲሆን፣ ከሳተላይት ላይ ወርዶ በኢንተርኔት አማካይነት ፕሮግራም እያስተላለፈ ይገኛል።
የተቋሙ መሥራችና ባለቤት አቶ ቴዎድሮስ ሽፈራው የጣቢያውን መዘጋት በተመለከተ ለሪፖርተር በሰጡት አስተያየት፣ የሚዲያ ምኅዳሩ እየጠበበ የመጫወቻ ሜዳው የማይመች፣ ሁሉም ጉዳይ ወደ ፖለቲካ እየተተረጎመ ለሚዲያው ማስታወቂያ ሲያስነግሩ የነበሩ ድርጅቶች እየፈሩ፣ የመንግሥት ኃላፊዎችም ስፖንሰር እያደረጋችሁ ታሰድቡናላችሁ ተባልን እያሉ በዚያው መጥፋታቸውና የሚዲያው ወጪ ከአቅሙ በላይ በመሆኑ ወደ ዲጂታል አማራጭ መገባቱን ይገልጻሉ።
ናሁ ቴሌቪዥን አገርንና ሕዝብን ሊጠቅሙ የሚችሉና ለመንግሥት የፖሊሲ ግብዓት የሚሆኑ አማራጭ ሐሳቦች ላይ በሳል ውይይት ያደርግ ነበር ያሉት አቶ ቴዎድሮስ፣ ከቴሌቪዥን ጣቢያው ጋር ተያይዘው የሚመጡ ችግሮች ሌሎች የሚያስተዳድራቸው ቢዝነሶችን ወደ ማወክ በመሄዳቸው ጣቢያውን ወደ ኢንተርኔት ሚዲያ ለመቀየር መገደዳቸውን ያብራራሉ።
ለሳተላይት ኪራይ፣ ለሠራተኛ ደመወዝ፣ ለፕሮዳክሽን ወጪ፣ ለታክስና ለሌሎች ጉዳዮች ጭምር ለሚያስፈልገው ወጪ ማስታወቂያ ከሌለ የማይቻል ነው የሚሉት አቶ ቴዎድሮስ፣ በርካታ ድርጅቶች ስፖንሰር ማድረግ የምንፈልገው አጠር አጠር ያለ ቀሚስ ለብሰው የሚሳሳቁ ሴቶች ያሉበትን ፕሮግራም እንጂ፣ ከመንግሥት ጋር የሚያነካካንንና ደፍሮ የሚያወራ ሚዲያን አይደለም እንደሚሏቸውም ያስረዳሉ፡፡
ይሁን እንጂ አቶ ቴዎድሮስ ‹‹ኢትዮጵያ የቸገራት እንደ ሕዝብ ቁጭ ብሎ መመካከርና መነጋገርን የሚጋብዝ፣ ፖሊሲ የሚተችበትና ለመንግሥት ምክረ ሐሳብ የሚቀርብበት መድረክ እንጂ ሲሳቅና ሲጨበጨብበት የሚውል ሚዲያ በየቦታው ሞልቷል፤›› ብለዋል፡፡
መንግሥት ነገሮችን ‹‹ሳይቃጠል በቅጠል›› እንደሚባለው ከወዲሁ ችግሮችን የሚነግረውና ጥሩ ጅማሮዎችን ደግሞ አይቶ በርታ የሚለው እንጂ፣ አብሮ የሚያጨበጭብለት መፍትሔ የሌለው በመሆኑ፣ የግል ሚዲያን እንደ መስታወቱ ሊጠቀምበት ይገባል በማለት አሳስበዋል፡፡ ነገር ግን የግል ሚዲያ በሌለበት ጉድፉን፣ ጠባሳውንና መድኃኒት የሚያስፈልገውን ማየት ተስኖት ችግሩን የመሸከም አደጋ ያስከትልበታል ብለዋል፡፡
የቀድሞ ነገሥታት በሥልጣን ዘመናቸው ‹‹እረኛ ምን አለ?›› የሚል ብሂል እንደነበራቸው ይነገራል። በዘመኑ የሕዝቡን ሐሳብ ሊነግራቸው የሚችል ሚዲያ ባይኖርም፣ አሁን ግን መረጃውን ለመንግሥት የሚያቀርቡ በተለይ ወገንተኝነት የሌለባቸው የግል የሚዲያ ተቋማት ናቸው ይላሉ፡፡
የመንግሥት የሚዲያ ተቋማት እንደ ገደል ማሚቶ ቀጥታ የተነገረውን፣ በሉ የተባሉትንና ክፍያ የፈጸመላቸውን አካል አጀንዳ ከማራመድና ከማስተጋባት ባሻገር ሕዝባዊ የሆነና የተመዛዛነ ጠንካራ ሐሳብ ማራመድ የተሳናቸው ናቸው በማለት ይገልጿቸዋል።
አቶ ሰሎሞን ጎሹ ጋዜጠኛ፣ የሕግና የሚዲያ ጉዳዮች ባለሙያ ሲሆኑ፣ ከዓመታት በፊት በኢትዮጵያ የመንግሥት ለውጥ መካሄዱን ተከትሎ በተካሄዱ የሕግ ማሻሻያዎች፣ በተለይም የሚዲያ ማሻሻያዎችን በተመለከተ ከፍተኛ ተሳትፎ ነበራቸው፡፡ የኢትዮጵያ የሚዲያ ምኅዳር ወቅታዊ ቁመናን በተመለከተ ለሪፖርተር አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
ከዓመታት በፊት በወጣው የሚዲያ ፖሊሲ መንግሥት የሚዲያ ዘርፉን ለመደገፍ ቁርጠኝነት እንደነበረው የሚገልጹት አቶ ሰሎሞን፣ ይህንን የፖሊሲ ዕሳቤ በመረዳት የመገናኛ ብዙኃን አዋጁ ሲሻሻል ሚዲያውን ሊደግፍ የሚችል ኤጀንሲ ወይም ዲፓርትመንት የሚቋቋምበት ድንጋጌ እንዲካተት ብዙዎች በሐሳቡ ተማምነውበት የነበረ ቢሆንም፣ መንግሥት ወደፊት ይታያል ለጊዜው ይቆይ በሚል እንዳሳደረው ይናገራሉ።
የመገናኛ ብዙኃን አዋጁ የተሻሻለበት መንገድ ብዙ ለውጦች ተካተውበት የነበረ ቢሆንም፣ ከዚያ ወዲህ ባሉት ዓመታት የሚዲያ ነፃነትንና ገለልተኝነትን ችግር ውስጥ ሊከቱ የሚችሉ፣ እንዲሁም በአስፈጻሚው የመንግሥት አካል የመጠምዘዝ ዕድልን የሚጨምሩ ድንጋጌዎች እንደገና በተደረገው ማሻሻያ መካተታቸውን አስረድተዋል፡፡
የሕግ ማሻሻያ ድንጋጌዎቹ ሚዲያዎች በመንግሥት ቁጥጥር ሥር እንዲወድቁ ስለማድረጋቸው የሚናገሩት አቶ ሰሎሞን፣ ከዚህ ባለፈ ግን የሚዲያ ተቋማቱ ያላቸው የቢዝነስ ሞዴል አወዳደቃቸውን የሚያፋጥንና ለመዘጋታቸው አንዱ ምክንያት እንደሚሆን ይናገራሉ፡፡ ቀጣይነቱን ይዞ በቁርጠኝነት ማገልገል የሚፈልግ ሚዲያ እንደ ማንኛውም ዓይነት ቢዝነስ ትርፍ ለማግኘት ሳይሆን፣ አገለግለዋለሁ የሚልለት ሕዝብና ዓላማን ይዞ መሆን አለበት ይላሉ፡፡
በመንግሥት አካላት በኩል ከሚዲያ ሥራ ጋር አብረው የማይሄዱና በዓለም ላይ የሐሳብ ነፃነትን ለመገደብ አገልግሎት የሚውሉ ብሔራዊ ጥቅምና ብሔራዊ ደኅንነት እያሉ የተዛቡ ዕሳቤዎችን በማምጣት፣ ያልተገባ ትርጉም በመስጠት ሚዲያዎችን ለመቆጣጠርና ለማፈን ጥረት እንደሚደረግ ያብራራሉ፡፡
ብሔራዊ ጥቅም የማንኛውም ሰው የሞራል ግዴታ ነው የሚሉት አቶ ሰሎሞን፣ ይህን የሚናገሩ አካላት ትርጉሙ ጠፍቷቸው ሳይሆን አንሸዋሮ በመተርጎም ለዕሳቤው ተገቢ ያልሆነ ትርጉም በመስጠት ሚዲያዎቹን ለመገደብ ይፈልጋሉ ሲሉ አክለዋል፡፡
የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ምክር ቤት የሥራ አስፈጻሚ አባልና የቁምነገር መጽሔት ባለቤት አቶ ታምራት ኃይሉ ለሪፖርተር በሰጡት አስተያየት፣ የሚዲያ ተቋማት መዘጋት ወይም አጠቃላይ የሚዲያ ምኅዳሩ መጥበብን በተመለከተ በሚዲያ ካውንስሉ በጥናት ባይረጋገጥም፣ ከሚዲያ ተቋማት ችግሩ ሲነሳና የተለያዩ አመላካከቶች እንደሚሰሙ ተናግረዋል።
‹‹በፋይናንስ እጥረት ምክንያት የሚዘጋ የሚዲያ ተቋም እንዳይኖር ተቋማቱ የሚደገፉበትን አሠራር ለመፍጠር በመገናኛ ብዙኃን ምክር ቤት በኩል የሚዲያ ፈንድ ለማቋቋም ሥራዎችን እየሠራን ነው፤›› ያሉት አቶ ታምራት፣ ይህንን ፈንድ ከተለያዩ የገንዘብ ምንጮች በማሰባሰብ አንድ ቋት ውስጥ ገብቶ ሚዲያዎች አደጋ ላይ ሲወድቁ ለመታደግና ለማጠናከር አገልግሎት ላይ የሚውል ነው ብለዋል፡፡
በቀጣይ ከመንግሥት ጋር መነጋገርና ፈቃደኝነቱ ያስፈልጋል ያሉት አቶ ታምራት፣ ‹‹ምንም እንኳ የመገናኛ ብዙኃን ዘርፍ ውስጥ በርካታ ችግሮች መኖራቸውን ቀጥተኛ ባልሆነ መንገድ ብንሰማም፣ የመገናኛ ብዙኃን ተቋማቱ በግልጽ የደረሰባቸውን ጫና ዘርዝረው ሲያቀርቡ አይታይም፡፡ ይህ ሊስተካከል የሚገባውና ችግሮች ሲፈጠሩ ሊመጡና ልንነጋገርባቸው ይገባል፤›› ብለዋል፡፡
በፋይናንስ እጥረት ምክንያት ዘግተን ሠራተኛ በትነን ልንወጣ ነው እያሉ አቤቱታ ለምክር ቤቱ የሚያቀርቡ ሚዲያዎች እንዳሉ ገልጸው፣ ጫና ያለባቸው ተቋማትም በግልጽ ችግራቸውን ይዘው በመቅረብ መነጋገርና መወያየት የመፍትሔ አማራጭ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
ጫና የበረታባቸውና ሥጋት ያንዣበባቸው ሚዲያዎችና ባለሙያዎች ሥጋታቸውን እየገለጹ በሚገኙበት በዚህ ወቅት፣ ሰባተኛውን አገራዊ ምርጫ ለማካሄድ ዝግጅት ላይ የምትገኘው ኢትዮጵያ፣ ምርጫው ከመድረሱ አስቀድሞ አሁን የሚታየው የሚዲያ ምኅዳር የት ይደርሳል? የሚለው ጉዳይ ብዙዎችን እያሳሳበ ነው፡፡