- በምትኩ የንግድ ተቋማት በአስገዳጅነት የንግድ ምክር ቤት አባል ይሆናሉ ተብሏል
ግለሰብ ነጋዴዎች በአስገዳጅነት የንግድ ምክር ቤቶች አባል እንዲሆኑ የተደረጉ ጥረቶች ውጤት አለመሳካቱና በምትኩ ኩባንያዎች በአስገዳጅነት አባል እንዲሆኑ የሚደነግግ ረቂቅ አዋጅ ስለመዘጋጀቱ ተጠቆመ፡፡
ከንግድ ምክር ቤቶች የማቋቋሚያ አዋጅ ጋር አከራካሪ ከነበሩ ጉዳዮች አንዱ አባልነት አስገዳጅ ይሁን አይሁን የሚለው ጉዳይ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት የመጨረሻ ምዕራፍ ላይ በሚገኘው ረቂቅ አዋጅ ግን የግለሰብ ነጋዴዎች የንግድ ምክር ቤት አባልነት በአስገዳጅነት ሳይሆን በፈቃደኝነት ላይ የተመሠረተ እንዲሆን መደንገጉ ታውቋል፡፡ ግለሰብ ነጋዴዎችን በአስገዳጅነት የንግድ ምክር ቤቶች አባል ማድረግ ሕገ መንግሥታዊ መብቶቻቸው ጋር የሚፃረር በመሆኑ ሐሳቡ ተቀባይነት ሳያገኝ መቅረቱ ተጠቁሟል፡፡ በዚህም ምክንያት የመጨረሻ ምዕራፍ ላይ በሚገኘው የንግድ ምክር ቤቶች አዋጅ ውስጥ ሊካተት እንዳልቻለ ሰሞኑን በተካሄደው የኢትዮጵያ ንግድ ምክር ቤት ጠቅላላ ጉባዔ ላይ ተገልጿል፡፡
ባለፉት ስድስት ዓመታት የተለያዩ ማሻሻያዎች እየተደረጉበት በቆየው አዲሱ የንግድ ምክር ቤቶች ማቋቋሚያ ረቂቅ አዋጅ ዝግጅት ላይ ተሳታፊ ሆነው የቆዩት የቀድሞ የኢትዮጵያ ንግድ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት መላኩ እዘዘው (ኢንጂነር)፣ የአባልነት ጉዳይ አስገዳጅ ይሁን በሚል ብዙ ምክክር ሲረግበት የቆየ መሆኑን ሰሞኑን በተካሄደው ጠቅላላ ጉባዔ ላይ ገልጸዋል፡፡ ሆኖም ይህ ሐሳብ ተቀባይነት አለማግኘቱን ጠቁመዋል፡፡
ነጋዴዎች በአስገዳጅነት የንግድ ምክር ቤቶች አባል ይሁኑ በሚለው ሐሳብ ላይ እስከ ጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ድረስ ባሉ ባለሙያዎች ተመክሮበታል፡፡ ከዚያም ቀደም ብሎ በንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር፣ በፍትሕ ሚኒስቴርና ጉዳዩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በተደረገው ውይይትም መግባባት ላይ የተደረሰው አባልነትን አስገዳጅ ማድረግ ያለመቻሉን ጠቁመዋል፡፡
በመጀመሪያ በተዘጋጀው ረቀቂቅ አዋጅ ላይ የፀና የንግድ ሥራ ፈቃድ ያለው ማንኛውም ሰውና የንግድ ማኅበር አግባብነት ባላቸው የረቂቅ አዋጅ ድንጋጌዎች መሠረት የንግድ ምክር ቤት አባል የመሆን ግዴታ እንዳለበትና ዝርዝር አፈጻጸሙ ቀጥሎ በሚወጣ መመርያ እንደሚወሰን ተመላክቶ ነበር፡፡
የንግድ ምክር ቤት አባል የሆነ ማንኛውም ነጋዴ አባል ከሆነበት ምክር ቤት የአባልነት ማረጋገጫ መታወቂያ የማግኘት መብት የሚኖረው ሲሆን፣ ማንኛውም የንግድ ድርጅት በንግድ ምክር ቤት የሚወከለው የተፈጥሮ ሰው ከሆነ በድርጅቱ ባለቤት ወይም በዋና ሥራ አስኪያጁ፣ የንግድ ማሕበር ከሆነ በሥራ አስኪያጁ ወይም በዳይሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢ ወይም የዳይሬክተሮች ቦርድ በሚወክለው ሰው አማካይነት ይሆናል በሚል ተቀምጧል፡፡
አሁን ባለው ረቂቅ አዋጅ ላይ ግን አባልነት በፈቃደኝነት ላይ የተመሠረተ እንዲሆን መደረጉን የገለጹት መላኩ (ኢንጂነር)፣ ይህም የሆነበት አንዱና ዋነኛው ምክንያት በሕገ መንግሥቱ የተቀመጠውን መብት የሚነካ በመሆኑ ነው፡፡
አባልነት በፈቃደኝነት ላይ የተመሠረተ ይሁን የሚለው ድንጋጌ ቢካተትም ግለሰብ ነጋዴዎች ሰብዓዊ መብታቸው መከበር ያለበት በመሆኑ የንግድ ምክር ቤት አባልነትን በአስገዳጅነት መጣል አስቸገሪ በመሆኑ ነው ብለዋል። ነገር ግን የግል ኩባንያዎች ወይም ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበርና መሰል የንግድ ተቋማት በግዴታ አባል ይሆኑ የሚል ሐሳብ ቀርቦ ተቀባይነት ማግኘቱን አብራርተዋል፡፡ በዚህም መሠረት አዲሱ ረቂቅ ውስጥ አዋጅ ኩባንያዎችና ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር የግዴታ አባል ይሁኑ የሚል አንቀጽ እንዲካተት መደረጉን ጠቅሰዋል፡፡
የአዲስ አበባ ንግድ ምክር ቤት የግል ተቋም ዳይሬክተርና የሕግ ባለሙያ የሆኑት አቶ ዮሐንስ ወልደገብርኤል ግን ለሪፖርተር እንደገለጹት እንዲህ ያለውን አመለካከት ፍጹም ሕጋዊ አለመሆኑ ነው፡፡ የረቂቅ አዋጁ ብዙ ሊሻሻሉ የሚገባቸው አንቀጾች እንዳሉትም ይገልጻሉ፡፡ አባልነትን የተመለከተ ጉዳይም አንዱ መሻሻል ይኖርበታል ብለው ያምናሉ፡፡
በተለይ በኢትዮጵያ ሕግ የሕግም ሆነ የተፈጥሮ ሰው እኩል መብትና ግዴታ ያለው ከመሆኑ አንጻር ኩባንያዎችን በአስገዳጅነት አባል እንዲሆኑ አድርጎ ማቅረብ፣ ግለሰቡ ነጋዴዎችን ደግሞ በፈቃደኝነት ላይ በተመሠረተ መንግድ አባል ይሁን ማለት ስህተት እንደሆነም ይጠቅሳሉ፡፡ በሕግ ሰውነትና በተፈጥሮ ሰውነት መካከል ምንም ልዩነት መፍጠር አይቻልም የሚሉት አቶ ዮሐንስ፣ ለአንዱ መብት የሚሰጥበት ለሌላው የሚነፈግበት ሕግ አለመኖሩንና በየትኛውም የሕግ አስተምሮ የሕግ መርሕ ላይ የሌለ ነው፡፡
ግማሹን በአስገዳጅነት የማኅበር አባል ትሆናለህ የተፈጥሮ ሰውን ደግሞ መብትህ ስለሚጣስ አባል አትሆንም ሊባል አይችልም፡፡ ይኼ የኢንተርናሽናል ሒውማን ራይት ድንጋጌን ጭምር የሚጥስ መሆኑንም አስረድተዋል፡፡
በዓለም አቀፍ የሒውማን ራይት ድንጋጌ የማኅበር አባል ለመሆንም ላለመሆንም መብት ይሚሰጥ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ሕገ መንግሥት አንቀጽ 31 ላይ የሚጥስም ነው ያሉት አቶ ዮሐንስ ኮሚንስታዊ ምልክታ ያለው ነው ብለው በረቂቁ ኩባንያዎችና ግለሰቦችን ነጣጥሎ በአስገዳጅነትና በፈቃደኝነት ላይ የተሠረተ አባል ይሁኑ በሚል የተቀመጠውን ድንጋጌ ከሕጋዊነትም አንጻር ትክክል አለመሆኑን ያመለክታሉ፡፡
ይህንን አቋማቸውን የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት በሚገባ ዘርዝሮ ያቀረበ ሲሆን፣ በአገራችን የማኅበር አባላት የሰዎችን ፈቃደኝነትና ፍላጎትን መሠረት ያደረገ መሆን ይገባዋል በማለት ገልጸዋል፡፡
አባልነት አስገዳጅ ይሁን መከራከሪያ ያላቸው ወገኖች ደግሞ በሌሎች አገሮችም አባልነት በአስገዳጅነት በማስቀመጥ ንግድ ምክር ቤቶች ቋሚ የሆነ ገቢ እንዲያገኙ ያደርጋል አሁን የሚታየውን የንግድ ምክር ቤቶች ደካማ የፋይናንስ አቅም በማጎልበት ለንግድ ኅብረተሰቡ የተሻለ አገልግሎት ለመስጠት ያስችላቸው በሚል ይከራከራሉ፡፡
ሰሞኑን በተካሄደው የኢትዮጵያ ንግድ ምክር ቤት ጠቅላላ ጉባዔ ላይም ይህ የተንፀባረቀ ሲሆን፣ ንግድ ምክር ቤቶች ከዓመታዊ የንግድ ፈቃድ ዕድሳት ገቢ የሚያገኙበትን ሁኔታ የሚያመቻች ሌሎች በውክልና የሚሠሩ የመንግሥት ሥራዎችን በመሥራት የገቢ አቅማቸውን ማሳደግ ይችላሉ በማለት የአንዳንድ የአውሮፓ አገሮች አሠራሮች በምሳሌነት ይጠቅሳሉ፡፡
መላኩ (ኢንጂነር) አባልነት አስገዳጅ እንዲሆን በአዋጁ ረቂቅ ዝግጅት ላይ እንደ መነሻ የኢትዮጵያ ጠበቆች ማኅበር አዋጅን በመጥቀስ ጭምር አስፈላጊነቱን አመልክተው ነበር፡፡ የኢትዮጵያ ጠበቆች ማኅበር አዋጅ ማንኛውም ጠበቃ የኢትዮጵያ ጠበቆች ማኅበር አባል የመሆን ግዴታ አለበት ስለሚል በዚሁ አግባብ የንግድ ባንክ ቤቱም አዋጅ እንዲቃኝ ተፈልጎም ነበር፡፡
አባልነትን በአስገዳጅ ሁኔታ ካስቀመጠው የኢትዮጵያ ጠበቆች ማኅበር ሌላ የኢትዮጵያ የሒሳብ አያያዝና ኦዲት ቦርድ ማኅበርም ተመሳሳይ አሠራር እንዳለው በመጠቀስ ይህ አሠራር በንግዱ ዘርፍም ሊተገበር ይገባል ይላሉ፡፡
በኢትዮጵያ ንግድ ምክር ቤት ጠቅላላ ጉባዔ ላይ የተገኙ አንድ የሒሳብ አያያዝ ኦዲት ቦርድ ማኅበር አባል መሆናቸውን የገለጹ ተሳተፎም ንግድ ምክር ቤቶች ማቋቋሚያ አዋጅ አባልነትን አስገዳጅ ማድረግ ይገባዋል ብለዋል፡፡
ለምሳሌ የሒሳብ አያያዝና ኦዲት ቦርድ አንድ አባል የማኅበሩ አባል ያልሆነ ማንኛውም ሰው ፈቃዱን ማደስ የማይችል በመሆኑ በዚሁ አግባብ እየተሠራበት ነው፡፡ ስለዚህ ንግድም ሙያ ነውና አባልነት አስገዳጅ መሆን አለበት ብለው ሞግተዋል፡፡
አያይዘውም ምርጫ ሲካሄድ ፈቃድ ላደሰ ነጋዴ ብዛት የምንዳኝ ከሆነ ማንኛውም ነጋዴ በአስገዳጅነት የንግድ ምክር ቤቱ አባል መሆን አለበት፡፡ ምክንያቱም እኛ አባል ሆነን ያቋቋምነው ንግድ ምክር ቤት ላይ አባል ያልሆኑ ፈቃድ ያደሱ ሰዎች ተጠቃሚ እየሆኑ ነው፡፡ እኛ ተጎድተናል ስለዚህ አዋጅ መሻሻል ይገባል፡፡
አባልነት አስገዳጅ ይሁን በሚለው የማይስማሙት አቶ ዮሐንስ ኩባንያዎችንና ግለሰቦችን ለይቶ የአባልነትን ጉዳይ የሚጠቅሰው ረቂቅ ላይም ቢሆን ድንጋጌውን አንጠልጥሎ የተወው መሆኑ ነው፡፡
ይህም አባልነት በተመለከተ በሕግ የተቋቋመ ኩባንያ በአስገዳጅነት አባል ይሁን የሚለው በመመርያ ይወሰናል በሚል የተቀመጠ መሆኑን ያስታወሱት አቶ ዮሐንስ እነዚህ ኩባንያዎች የእኛ አባል ይሆናሉ አይደለም ያለው፡፡ ስለዚህ በአዋጁ ላይ ይህንን ካስቀመጠ በኋላ ንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር አስገዳጅ መመርያ እንዲወጣ ለማድረግ ስለሆነ ይህም ተገቢ አይደለም የሚል ምልክት አላቸው፡፡
የንግድ ምክር ቤት አባልነት በአውሮፓ አስገዳጅ ስለመሆኑ በተጠቀሰው ዙሪያ አቶ ዮሐንስ በሰጡት ማብራሪያ ይህ ትክክል ቢሆንም በአውሮፓ አስገዳጅ የሆነበት ምክንያት መንግሥት ለእነዚህ ማኅበራት ከሥልጣኑ ከፍሎ አስገዳጅ በሆነ መንገድ ሥራ ስለሰጠ ነው፡፡
ለምሳሌ የንግድ ፈቃድ ዕድሳትና ከዚህ ጋር የተያያዙ ሥራዎችን በሙሉ ማኅበራቱ እንዲሠሩ ሰጥቷቸዋል፡፡ እንዲህ ያለው ድንጋጌ ከተቀመጠ እንደ ንግድ ፈቃድ ዕድሳት ያሉ አገልግሎቶች የግድ በንግድ ምክር ቤቶች በኩል ማለፍ ይኖርባቸዋል፡፡
በኢትዮጵያ ሁኔታ ግን መንግሥት እንዲህ ያለ ሥራዎችን ለመስጠት ፈቃደኛ አይደለም ይላሉ፡፡ በአዲሱ ረቂቅ አዋጁ ግን በውክልና እነዚህን ሥራዎች እንደሚሰጥ ቢጠቅስም ሥራውን ለመስጠት የታሰበው በውክልና ነው የሚለው አገላለጽ አያስኬድም ይላሉ፡፡
ይህንንም ሲያብራሩ አንድን ሥራ በውክልና ለመስጠት በጣም ቀላል ነው፡፡ ለምሳሌ የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት የአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከልን በውክልና ሲሠራ ነበር፡፡ ሌሎች ሥራዎች ከዚያም ከመንግሥት ወስደን በውክልና የምንሠራው ሥራ አለ፡፡ ስለዚህ በውክልና የሚሠራ ሥራ በማንኛውም ሰዓት ሊሰጥህና ሊነፍግህ የሚችል በመሆኑ የአውሮፓን አሠራር እንደ ምሳሌ መውሰድ ተገቢ አለመሆኑን ያመለክታሉ፡፡
የውክልና ሥልጣን መብት አይደለም፡፡ እንደ መብት ከሰጠኸው ማስገደድ አለበት፡፡ ስለዚህ አባልነትን አስገዳጅ አድርጎ የመንግሥት ሥራን እሰጣለሁ ከተባለ ይህም አስገዳጅ መሆን ያለበትና በውክልና የሚሰጥ ተብሎ ሊጠቀስ አይገባም የሚለው ሐሳብ ሰጥተዋል፡፡
በጥቅሉ ግን ሕጋዊ ሰውነት ያለውን ሰው ሕጋዊ ኩባንያ ለይቶ አንዱን አባል ማድረግ ፍጹም ስህተት እንደሆነ አመልክተዋል፡፡ አሁን ያለው ረቂቅ ኩባንያዎችን በአስገዳጅነት አባል ማድረግ ግለሰብ ነጋዴዎችን ደግሞ ለይቶ በፈቃደኝነት ላይ በተመሠረተ መንገድ አባል ይሁኑ የሚለው አመለካከታቸውን የገለጹት አቶ ዮሐንስ በእርሳቸው እምነት አባልነት አስገዳጅ ይሁን የሚለውንም አይቀበልም፡፡
ለዚህም እንደ ምሳሌ የሚያነሱት በአፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመን ይሠራበት የነበረውን አሠራር ነው፡፡ በዚያ ወቅት የንግድ ምክር ቤትን የሚያግዝ በሕግ የተቀመጡ ከቴምብር ቀረጥ፣ ከንግድ ፈቃድ ዕድሳትና ከመሳሰሉ አገልግሎቶች በሚገኝ ገቢ የሚሰበሰበውን ገንዘብ 25 በመቶውን የንግድ ሚኒስቴር እየሰበሰበ ለንግድ ምክር ቤት ይሰጣል ይላል፡፡ ይህ ሕግ ቢሆንም አባልነትን በፈቃደኝነት ላይ የተመሠረተ አድርጎ ነው የደነገገው፡፡
ስለዚህ አሁንም አባልነት በፈቃደኝነት ላይ የተመሠረተ ሆኖ ከመንግሥት የሚሰጡ ሥራዎች ካሉ በአስገዳጅነት ሊቀመጥ ይገባል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ ረቂቅ አዋጅ ውስጥ ተገቢ ያልሆነ አንቀጽ መካተቱን ያስታወሱት አቶ ዮሐንስ ንግድ ምክር ቤት ከመንግሥት በጀት የሚያገኘው ድጋፍ መኖሩን ይገልጻል፡፡
አንድ የንግድ ምክር ቤት ከመንግሥት በጀት ድጋፍ ካገኘ የመንግሥት ተቋም ሆነ ማለት ነው፡፡ ጉዳይ አስፈጻሚ ነው የሚሆነው እንዲህ ያሉ ነገሮች ሁሉ ደግሞ ሊታዩ እንደሚገባ አመልክተዋል፡፡
አባልነት በግዴታ ያለመሆኑ ንግድ ምክር ቤቶችን አዳክሟል ለሚለው ምልከታም አቶ ዮሐንስ ንግድ ምክር ቤቶች ተዳከሙ የሚባለው ‹‹ያዳከመው የማይሠራ ንግድ ምክር ቤት ነው፤›› በማለት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
‹‹እኛ ደግሞ እየተፋን ነጋዴውን እያገለገልን ነው›› በማለት ድክመቱ በአግባቡ ባለመሥራት የመነጨ እንደሆነም ያሰምሩበታል፡፡ ምክር ቤቶች የነጋዴው መሆን አለባቸውም ይላሉ፡፡
ንግድ ምክር ቤት ተጣጥሮ ከአባሉ ጋር ሆኖ አብሮ እየተራመደ መሥራት አለበት፡፡ ምንም ሳይሠራ ገንዘብ ካገኘ ችግር ስለመሆን አባልነት በፈቃደኝነት ላይ የተመሠረተ ሆኖ አባልነትን ለማበርከት ደግሞ ለንግድ ኅብረተሰቡ በሚሰጡት አገልግሎት ማበራከት ይቻላል ይላሉ፡፡
በዚህ ረቂቅ አዋጅ ላይ የከተማ ንግድ ምክር ቤቶች ሁነኛ ሚና እንዳይኖራቸው ያደረገ ስለመሆኑም አቶ ዮሐንስ ተችተዋል፡፡
አዋጁ የንግድ ምክር ቤቶችን አደረጃጀት ከመንግሥት መዋቅር ጋር የተሳሰረ እንዲሆን ዓማ ያለው መሆኑን የጠቆሙት አቶ ዮሐንስ እንዲህ ያለውን ነገር እንደ ንግድ ምክር ቤት ያሉ ማኅበራት ሊጫን አይገባም የሚል እምነት አላቸው፡፡
‹‹የንግድ ምክር ቤት ማኅበር ነው፡፡ ማኅበር ደግሞ ከአባላቱ በጎ ፈቃድ ይመሠረታል እንጂ የግዴታ የአገሪቱን የፖለቲካ መዋቅር መከተል የለበትም፤›› በማለት በዚህ ረቂቅ አዋጅም ይዘት የንግዱን ኅብረተሰብ አደረጃጀት መከተል እንጂ የግዴታ የመንግሥትን መወቊ መከተል እንደሌለበት ጠቅሰዋል፡፡
ማኅበሩ የእኛ እንጂ የመንግሥት ባለመሆኑ ረቂቅ አዋጁም በዚህ መቃኘት የሚኖርበት ሲሆን፣ የግዴታ የመንግሥት መዋቅሩን ተከትሎ ይደራጅ ከተባለ ንግድ ማኅበር አለ ለማለት ይከብዳል በማለት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
ይህ በእንዲህ የንግድ ምክር ቤቶችን እንደገና ለማቋቋምና አሠራራቸውን ለመደንገግ የወጣው ረቂቅ አዋጅ አሁንም ሊሻሻሉ የሚገቡት ነገሮች አሉ የሚሉ ወገኖች ያሉ ቢሆንም ረቂቁ በ2017 የበጀት ዓመት ፓርላማው ሥራ ሲጀምር በመጀመርያ ያፀድቃቸዋል ተብለው ከሚጠበቁ ረቂቆች መካከል አንዱ መሆኑ ታውቋል፡፡
የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ ከአዲሱ የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት የቦርድ አባላት ጋር ከትናንት በስቲያ በተዋወቁበት ወቅት ረቂቅ አዋጁ ፓርላማው ሥራ ሲጀምር እንደሚፀድቅ መግለጻቸው ተጠቁሟል፡፡
በረቂቅ ሕጉ አባልነትን የተመለከተው አንቀጽ የፀና የንግድ ሥራ ፈቃድ ያለው ማንኛውም የተፈጥሮ ሰው አግባብነት ባላቸው የዚህ አዋጅ ድንጋጌዎች መሠረት የንግድ ምክር ቤት አባል መሆን ይችላል ይላል፡፡