የጤና አገልግሎት ማስታወቂያዎች ሲዘጋጁ የሕክምና ተቋማትንና ሐኪሞችን በአገሪቱ ካሉ ሌሎች የሕክምና ተቋማት የተለዩና የመጠቁ (የበለጡ) አድርጎ በማስመሰልና በመግለጽ ማስተዋወቅን የሚከለክል፣ ሽልማቶችና ዕውቅናዎች በማስታወቂያዎች ሲካተቱም ለሕዝብ ግልጽ ማድረግ የሚገባቸውን ዝርዝር መሥፈርቶች ያካተተ መመርያ ፀደቀ።
በጤና ሚኒስትሯ መቅደስ ዳቦ (ዶ/ር) ተፈርሞ የፀደቀው በተያዘው ግንቦት ወር 2018 ዓ.ም. ጀምሮ በሥራ ላይ የዋለው ‹‹የጤና አግልግሎት ማስታወቂያ አዘገጃጀትና ሥርጭት መመርያ ቁጥር 1134/2018›› የጤና አገልግሎት ማስታወቂያዎችን በአየር ሰዓት፣ በኅትመት ገጽ፣ ወይም በሌሎች ተመሳሳይ መንገዶች የማሠራጫ ዘዴን በመጠቀም፣ ለሕዝብ የሚያደርስ ማንኛውንም ግለሰብ ወይም አካል ‹‹አሠራጭ›› በማለት ይገልጸዋል።
‹‹የማሠራጫ ዘዴ›› ማለት የመገናኛ ብዙኃን፣ ከቤት ውጭ ማስታወቂያ (Outdoor Advertising)፣ የጤና ትምህርት ፕሮግራሞች፣ በቴሌኮሙዩኒኬሽን መስመሮች ላይ የተመሠረቱ የጽሑፍና የድምፅ መልዕክቶች፣ ማኅበራዊ ሚዲያና ድረ ገጾች፣ ዲጂታል ሚዲያ ወይም ማንኛውንም የጤና አገልግሎት ማስታወቂያን ለማሠራጨት የሚያገለግሉ ተመሳሳይ የመገናኛ መስመሮች ማለት መሆኑንም ያትታል።
አሠራጮችንና ዘዴዎችን በግልጽና በዝርዝር ያሠፈረው በኢትዮጵያ የጤና አገልግሎት ማስታወቂያዎች አዘገጃጀትና ሥርጭትን የሚገዛው ይህ አዲስ መመርያ፣ የጤና ተቋማት አገልግሎቶቻቸውን ለሕዝብ ሲያስተዋውቁ ሊከተሏቸው የሚገቡ የሥነ ምግባር ደንቦችንና ግዴታዎችን በዝርዝር ይዟል፡፡ በመላው አገሪቱ በሚገኙ የማስታወቂያ አዘጋጆች፣ አሳታሚዎችና አሠራጮች ላይ ተፈጻሚ እንደሚሆንም ይገልጻል።
በመመርያው አንቀጽ ስድስት የሥነ ምግባር ተገዥነትን የተመለከቱ ድንጋጌዎች የተካተቱ ሲሆን፣ የጤና አገልግሎት ማስታወቂያዎች ዝግጅት ምን ምን መርሆዎችን ከግምት ውስጥ ማስገባት እንደሚኖርባቸው ተብራርቷል።
በዚህም የአንድ የሕክምና ተቋም የአገልግሎት ማስታወቂያ በሚዘጋጅበት ወቅት፣ የሌሎች የጤና ተቋማትና አገልግሎቶች ላይም ሆነ፣ የጤና ባለሙያዎቻቸውን ክብረ ነክ በሆነ መንገድ ከመግለጽ መቆጠብ እንዳለባቸው ተጠቅሷል።
በማስከተልም ማስታወቂያው በሚዘጋጅለት ሕክምና ተቋም ውስጥ የሚሠሩ የጤና ባለሙያዎች፣ ከሌሎች የበለጡ ወይም የተለየ የሙያ ክህሎትና ዕውቀት ያላቸው እንደሆኑ አድርጎ ከመግለጽና ከማስመሰል መቆጠብ እንደሚገባም ተደንግጓል።
From The Reporter Magazine
በሦስተኝነት የተጠቀሰው ደግሞ አንድ የሕክምና ተቋም በማስታወቂያው የሕክምና አገልግሎቱን ሲሰጥ ልዩ ንጥረ ነገር (Special Substance) እንደሚጠቀም፣ ወይም ተቋሙ ብቸኛ የፈውስ ቦታ (Place of Healing) እንደሆነ አድርጎ መግለጽም እንደማይፈቀድ ተገልጿል።
ከእነዚህ በተጨማሪ ታካሚዎች ማስታወቂያው በሚሠራለት የሕክምና ተቋም አገልግሎት ካላገኙ የጤና ጉዳት (Health Damages) እንደሚደርስባቸው አድርጎ ማቅረብም ሆነ፣ የደንበኞችን ክብርና ሥነ ልቦና የሚነኩ መረጃዎችን በማስታወቂያዎች ማጋራትም ክልክል እንደሆነ በመመርያው ተብራርቷል።
መመርያው በአንቀጽ ሰባት በጤና አገልግሎት ማስታወቂያዎች ውስጥ የታካሚዎችን ምስክርነት (Testimony) ማካተት ስለሚቻልባቸው፣ እንዲሁም የተከለከሉ የምስክርነት አሰጣጥ ሁኔታዎችንም በዝርዝር ይዟል።
From The Reporter Magazine
በዚህም ማንኛውም የጤና አገልግሎት ማስታወቂያ አዘጋጅ ምስክርን ማሳተፍ ሲፈልግ የሚሰጠው የምስክርነት ቃል ስለሕክምናው ሒደት (Clinical Treatment) መሆን እንደማይኖርበት፣ ማለትም ምስክሩ ስለተቋሙ ንፅህና፣ ስለባለሙያዎች መልካም መስተንግዶ ወይም ስለአገልግሎቱ ቅልጥፍና ምስክርነት መስጠት ቢችልም፣ ‹‹ይህ ሕክምና ፈውሶኛል››፣ ‹‹ከበሽታዬ ሙሉ በሙሉ ተፈውሻለሁ›› ወይም ‹‹ያገኘሁት መድኃኒት እንዲህ ዓይነት ሳይንሳዊ ለውጥ አመጣልኝ›› የሚሉና ስለሕክምናው የቴክኒክ ውጤታማነት የሚገልጹ ምስክርነቶችን መስጠት እንደማይፈቀድ ታውቋል።
ከዚህ በተጨማሪ በጤና አገልግሎት ማስታወቂያ ላይ ምስክር ሆኖ የሚሳተፍ ሰው አገልግሎቱን በትክክል ያገኘ መሆን እንዳለበት ሲጠቀስ፣ በማስታወቂያው ለመካተትም በጽሑፍ ስምምነቱን መግለጽ እንደሚኖርበት ተገልጿል።
በጤና አገልግሎት ማስታወቂያ ላይ የሚሳተፈው ሰው ለአካለ መጠን ያልደረሰ፣ የአዕምሮ ጤና እክል ያለበት ወይም በራሱ ውሳኔ መስጠት የማይችል ከሆነ ወላጆቹ፣ አሳዳጊዎቹ፣ ረዳቶቹ ወይም የቅርብ ዘመዶቹ የጽሑፍ ስምምነት መገኘት እንዳለበትም በመመርያው ተደንግጓል።
ከእነዚህ ድንጋጌዎች ባሻገር መመርያው ተቋማት ለማስታወቂያ የሚጠቀሙባቸውን ቃላት ጨምሮ ይዘታቸው ምን መምሰል እንዳለበትም የሚደነግግ ሲሆን፣ በተለይም ‹የሁሉም ምርጫ› (Everyone’s Choice) ወይም ‹ተቀዳሚ ምርጫ› (Prior Choice) የሚሉና የሰዎችን የውሳኔ ነፃነት የሚጋፉ የተጋነኑ ቃላትን መጠቀምን ይከለክላል።
በተመሳሳይ የጤና ተቋማት ያገኟቸውን ክልላዊም ሆነ ዓለም አቀፋዊ ዕውቅናዎችና ሽልማቶች ለማስተዋወቅ ሲፈልጉ ሽልማቱን የሰጠውን አካል፣ የተሰጠበትን ዘመንና የተሸለሙበትን ትክክለኛ ምክንያት ለሕዝብ ግልጽ የማድረግ ግዴታ ተጥሎባቸዋል፡፡ ይህም ኅብረተሰቡ ስለተቋማቱ ብቃት ትክክለኛና በማስረጃ የተደገፈ መረጃ እንዲኖረው ለማድረግ ያለመ ነው ተብሏል።
መመርያው ድንጋጌዎቹን ተላልፈው በሚገኙ አካላት ላይ ጠንካራ አስተዳደራዊ ዕርምጃዎችን ያስቀመጠ ሲሆን፣ በተለይም ለአካለ መጠን ያልደረሱ ልጆችን ወይም የአዕምሮ ጤና ችግር ያለባቸውን ዜጎች ያላግባብ በምስክርነት የሚያሳትፉ ተቋማት ከ50 ሺሕ እስከ 100‚000 ብር የሚደርስ ከፍተኛ የገንዘብ ቅጣት እንደሚጣልባቸው ይደነግጋል።
ማንኛውም የጤና ተቋም የኅብረተሰቡን ጤና ወይም ደኅንነት የሚጎዳ፣ ወይም የኅብረተሰቡን እሴትና ባህል ዝቅ የሚያደርግ የጤና አገልግሎት ማስታወቂያ አዘጋጅቶ ያሠራጨ ወይም በሌላ ወገን እንዲሠራጭ ያደረገ ከሆነ፣ ከ15 ሺሕ እስከ 50 ሺሕ ብር በሚደርስ የገንዘብ ቅጣት ይጣልበታል ይላል፡፡ የጽሑፍ ስምምነቱን ያልሰጠ ወይም በተቋሙ ውስጥ ሕክምና ያላገኘን ሰው በምስክርነት ያሳተፈ እንደሆነ፣ ከ20 ሺሕ እስከ 50 ሺሕ ብር በሚደርስ የገንዘብ ቅጣት በተቋሙ ላይ እንደሚጣልም ተገልጿል።
ማንኛውም አሠራጭ በመመርያ አሠራጮችን (Disseminators) አስመልክቶ የተደነገጉትን ድንጋጌዎች በመጣስ ማስታወቂያ ያስተላለፈ እንደሆነ፣ ከአሥር ሺሕ እስከ 30 ሺሕ ብር በሚደርስ የገንዘብ ቅጣት ይቀጣል ተብሏል።
በተጨማሪም የጽሑፍ ስምምነት ሳይኖር ምስክሮችን መጠቀምም ሆነ ተቋሙ ውስጥ ሕክምና ያላገኘን ሰው ምስክር አድርጎ ማቅረብ፣ ከ20 እስከ 50 ሺሕ ብር እንደሚያስቀጣ ተመልክቷል።
የተጣለባቸውን ቅጣት በሦስት ወራት ጊዜ ውስጥ የማይከፍሉ የጤና ተቋማት፣ ክፍያውን እስከሚፈጽሙ ድረስ የብቃት ማረጋገጫ ምስክር ወረቀታቸው (Certificate of Competence) እንደሚታገድ በመመርያው ተገልጿል፡፡ ሆኖም በዚህ መመርያ አንቀጽ 11 መሠረት በተጣሉ አስተዳደራዊ ቅጣቶች ላይ ቅሬታ ያለው ማንኛውም ሰው፣ በፌዴራል የአስተዳደር ሥነ ሥርዓት አዋጅ ቁጥር 1183/2012 ወይም አግባብ ባላቸው የክልል ሕጎች መሠረት ቅሬታውን ቅጣቱን ለሰጠው አካል ማቅረብ ይችላል።
