ዞሲማስ ሚካኤል በፌዴራላዊ ሪፐብሊኩ 7ኛ አገራዊ ምርጫ ላይ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትና ለአዲስ አበባ ምክር ቤት ምርጫ ድምፃቸውን በመኖሪያ ሠፈራቸው ሰኞ ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም. ከሰጡ መራጮች አንዱ ናቸው። በስድሳዎቹ አጋማሽ ዕድሜያቸው ላይ የሚገኙት አቶ ዞሲማስ፣ በኢትዮጵያ መንግሥታት የፓርላማ ምርጫ የሰባ ዓመታት ጉዞ ውስጥ ከተካሄዱት 13 አገራዊ ምርጫ መካከል በንጉሠ ነገሥት መንግሥት ዘመን የተካሄደውን አምስተኛውንና የመጨረሻውን ምርጫ ላይ ድምፅ ባይሰጡም፣ በወቅቱ የነበረውን በከተማዪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የተደረገውን የግለሰቦች የምረጡኝ ቅስቀሳ ያስታውሳሉ።


ከአዋሬ ወደ ቤልኤር በሚወስደው መንገድ በስተግራ ከሚገኘው ‹‹ምሥራቅ ማዘጋጃ ቤት›› (በዘመነ ደርግ የምሥራቅ ዞን ትምህርት ቤቶች ጽሕፈት ቤት ሆኖ ነበር) እስከ ካዛንቺስ የዕጩዎች የምረጡኝ ፖስተሮች በየአጥሩ ላይ መለጠፋቸውን ያስታውሳሉ። ይማሩበት የነበረው አስፋ ወሰን አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤትንና የግንፍሌ ወንዝን የሚጎራበቱት የ1965 ዓ.ም. ዕጩ ተወዳዳሪው አቶ ግርማቸው ፊሊክስ የብራዚል ስሪት የሆነችው ቮልስ ቫገን አውቶሞቢላቸውን እያሽከረከሩ ካዛንቺስ ቶታል አጠገብ ላይ ሆነው ‹‹ምረጡኝ›› እያሉ ሲቀሰቅሱም ያስታውሳሉ።


የሥርዓተ ዘውድ ሕገ መንግሥትና ምርጫው
በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመን (1923-1967) የወጣው የመጀመሪያው ሕገ መንግሥትን ንጉሠ ነገሥቱ ሲያውጁ፣ የሚቀጥለውን አጠቃላይ የሆነ መሪ ቃል ሰጥተው እንደነበር ከስድስት አሠርታት በፊት የማስታወቂያና ቱሪዝም ሚኒስቴር ባዘጋጀው ‹‹የኢትዮጵያ የድል መታሰቢያ ፳፭ኛው ዓመት ፲፱፻፴፫- ፲፱፻፶፰›› ግዙፍ መጽሐፍ ውስጥ ተጠቅሷል፡፡


ዓ.ም. የተመረጡት በጅሮንድ በላቸው ንግሩ የምርጫ ምልክታቸው የፋሲል ግንብ ነበር
‹‹የመንግሥት ሕግ አቋቋም የሚያስረዳው የኢትዮጵያ መንግሥት ወደፊት የሚጸናበት መሠረቱ – መሠረቱም የሚቆምበት ሕጉ – ሕጉም የሚፈጸምበት ኃይሉ እንደምን እንዲወሰን ታውቆ የመንግሥታትንም ሕግ አቋቋም ለዘለዓለም ቀዋሚና ጽኑ ሆኖ እንዲኖር የታመነ መጠበቂያ የሚያስፈልግ መሆኑን ማስታወቂያ ነው፡፡››
ለመጀመሪያው ፓርላማ ምርጫ ንጉሠ ነገሥቱ ከሚመርጧቸው መሳፍንትና መኳንንት በስተቀር ሕዝብ ግን እንዲመርጥ ሕገ መንግሥቱ አይፈቅድም ነበር።
From The Reporter Magazine
ሕዝብ እንዲመርጥ፣ የግል ተወዳዳሪዎችም የሕዝብ እንደራሴ ለመሆን ለፓርላማ እንዲወዳደሩ የፈቀደው የተሻሻለው የ1948ቱ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት መንግሥት ሕገ መንግሥት ነበር።


‹‹ተሻሽሎ የወጣው ሕገ መንግሥት የኢትዮጵያን ምክር ቤት ተግባርና ሥራ ሰፊ እንዲሆን አድርጎታል፡፡ በሕግ ሊጠበቅ የሚገባውን መብትና ነፃነት አብራርቷል፡፡ የኢትዮጵያ ዜጋ የሆኑ ሁሉ የሕዝብ እንደራሴያቸውን እንዲመርጡ መብት ሰጥቷል፡፡ ወንድ ሆነ ሴት በምክር ቤቱ አባል ሆነው እንዲመረጡ ፈቅዷል፡፡››
የኢትዮጵያ ምክር ቤት (ፓርላማ) ሁለት የምክር ቤቶች ሲኖሩት ሕግ መወሰኛና ሕግ መምርያ ተብለው የሚጠሩ ነበሩ፡፡
From The Reporter Magazine
እንደ መጽሐፉ ማብራሪያ፣ ‹‹የሕግ መወሰኛው ምክር ቤት አባል ሆኖ ለመሾም የመስፍንነት ወይም የመኳንንትነት ማዕረግ ያለው ወይም በጠቅላላው በጠባዩ በአስተያየቱና በብሔራዊ አገልግሎት በከፍተኛነት፣ የተገመተ ዕድሜውም ከ35 ዓመት ያላነሰ ሰው መሆን አለበት፡፡››


በሁለተኛው ሕገ መንግሥት መሠረት ኢትዮጵያ ውስጥ የመጀመሪያው የምክር ቤት ምርጫ የተደረገው በ1949 ዓ.ም. ነው፡፡ ‹‹በኢትዮጵያ የመገናኛ ችግር መኖሩ ሲታወቅ፣ እንዲሁም የፖለቲካ ፓርቲ አለመኖሩ ሲታወስ የመጀመሪያ የምክር ቤት ምርጫ በመላው የንጉሠ ነገሥቱ መንግሥት ግዛት ውስጥ ተደርጎ በቀላል ተፈላጊው ውጤት ማስገኘቱ የሚያስደንቅ ነው፡፡››
የእንደራሴዎች ምርጫ በየአራት ዓመቱ ይካሄድ ስለነበረ ሁለተኛው የሕዝብ እንደራሴዎች ምርጫ በ1953 ዓ.ም.፣ ሦስተኛው ምርጫ በ1957 ዓ.ም.፣ አራተኛውና አምስተኛው ምርጫ በ1961 እና 1965 ዓ.ም. ተደርገዋል፡፡
አምስተኛው ምርጫ በተደረገ ባመቱ ፓርላማው ጥቅምት 23 ቀን ሲከፈት፣ የዘውድ በዓላቸውን ሉልና ዘውድን በጨበጡበት በመናገሻ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ያከበሩት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ፣ በሠረገላ ሆነው ፓርላማው ሲደርሱና ከፓርላማው ሰገነት እንደወጡ /በሰገነቱ ግድግዳ ላይ የኢትዮጵያ ገበዝ (patron saint of Ethiopia) የፈረሰኛው ቅዱስ ጊዮርጊስ ሥዕል ነበረ/ በደቡብ አቅጣጫ በሚገኘው ‹‹የሕገ መንግሥት አደባባይ›› (የአሁኑ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤትና ጉባዔ አዳራሽ የሚገኝበት) ተሰብስቦ ይጠብቃቸው ለነበረ ሕዝብ ሰላምታ ሲያቀርቡ፣ በዚያው ዓመት ከፓርላማው ከሚጎራበተው ቅድስት ሥላሴ ትምህርት ቤት ተማሪ የነበሩት አቶ ዞሲማስ መገኘታቸውን ያስታውሳሉ፡፡
በዘመነ ደርግ እስከ ሕዝባዊ ሪፐብሊከ
ዘውዳዊው ሥርዓት በ1967 ዓ.ም. መስከረም 2 ቀን አብቅቶ የኢትዮጵያ ጊዜያዊ ወታደራዊ አስተዳደር ደርግ (የኅብረተሰብአዊት ኢትዮጵያ ጊዜያዊ ወታደራዊ መንግሥት) መንበሩን ከጨበጠ በኋላ ለ12 ዓመታት ሕገ መንግሥትም የፓርላማ ምርጫም አልነበረም። የኢትዮጵያ ሕዝባዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክን (ኢሕዲሪ) የወለደው ሕገ መንግሥት በ1979 ዓ.ም. መፅደቁን ተከትሎ ግን በዚያው ዓመት 835 አባላት ለሚኖሩበት ‹‹ብሔራዊ ሸንጎ›› ምርጫ አካሂዷል።
በዚህ ዘመን ላይ ነው አቶ ዞሲማስ ለመጀመሪያ ጊዜ ለአምስት ዓመት ለሚቆዩት የፓርላማ ዕጩዎች ድምፅ የሰጡት። የመረጡበት ‹‹ከፍተኛ 15›› እንዳሁኑ አንድ ዕጩ ብቻ የሚመረጥበት ሳይሆን እስከ አምስት የተመረጡበት ነበር። መሀል ካዛንቺስ ላይ ከተወዳደሩትና ከተመረጡት መካከል የኢትዮጵያ ደራስያን ማኅበር ፕሬዚዳንት የነበሩት ደራሲና ገጣሚው አቶ ደበበ ሰይፉ፣ እንዲሁ በምሥራቅ ካዛንቺስ ተወዳድረው የተመረጡት የሕግ ባለሙያው አቶ ገመዳ ጎንፋ (በኢሕዲሪ መንግሥት ምክር ቤት የፍትሕና ቁጥጥር ሚኒስትር ነበሩ) ይገኙበታል። የአሸናፊዎቹ ምልክትም ‹‹ዝሆን›› ነበር።
ኢሕዲሪ የመጀመሪያውን የምርጫ ዘመን ሊፈጽም ከሁለት ዓመት ያነሰ ጊዜ ሲቀረው፣ ለዓመታት የትጥቅ ትግል ባደረገው የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢሕአዴግ) ተገርስሷል።
ዘመነ ኢሕአዴግ እስከ ፌዴራላዊ ሪፐብሊክ
ኢሕአዴግ ለአንድ ወር ‹‹የኢትዮጵያ ጊዜያዊ መንግሥት›› ከሆነ በኋላ የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎችና ድርጅቶችን ያካተተ ጉባዔ አካሂዶ ለአራት ዓመት የዘለቀውን የሽግግር መንግሥትን ባፀደቀው ቻርተር መሠረት መሥርቷል።
በ1987 ዓ.ም. በፀደቀው የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ (ኢፌዴሪ) ሕገ መንግሥት መሠረት 547 የሕዝብ ተወካዮች ለሚገኙበት ምክር ቤት ፓርቲዎችና የግል ተወዳዳሪዎች የተሳተፉበት ምርጫ ተካሂዶና አሸናፊዎቹን ያካተተው ሸንጎ/ፓርላማ ከቆመ በኋላ ሪፐብሊኩ በመስከረም 1988 ዓ.ም. እውን ሆኗል። እስከ 2013 ዓ.ም. በተካሄዱት ስድስት ምርጫዎች አቶ ዞሲማስ ድምፃቸውን መስጠታቸው ያስታውሳሉ። ለየት ያለው ነገር ግን ስድስተኛው ምርጫ በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ምክንያት መካሄድ ከነበረበት 2012 ዓ.ም. በአንድ ዓመት እንዲራዘም መደረጉ ነው።
ሐምሌና ጥቅምት ጥርና ኅዳር የሕገ መንግሥት ወራትና ዕለታቱ
የኢትዮጵያ ዘውዳዊ መንግሥት የመጨረሻው ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ፣ የመጀመሪያውን ዘመናዊ ሕገ መንግሥት፣ በልደታቸው ቀን ሐሙስ ሐምሌ 16 ቀን 1923 ዓ.ም. ሲያወጡ፣ ከሩብ ምዕት ዓመት በኋላ ሐሙስ፣ በዘውድ በዓላቸው ቀን ጥቅምት 23 ቀን 1948 ዓ.ም. እንዲከለስ አድርገዋል፡፡ እንዲሻሻል የተደረገው ሕገ መንግሥት 131 ልዩ ልዩ አንቀጾች ነበሩት፡፡
ባጭር ተቀጨ እንጂ የ1966 ዓ.ም. አብዮት ሲፈነዳ ያልተተገበረና በረቂቅነት የቀረ ‹‹የብሔረ ኢትዮጵያ›› ሕገ መንግሥትም ለውይይት ቀርቦ ነበር፡፡
ደርግ (የኅብረተሰብአዊት ኢትዮጵያ ጊዜያዊ ወታደራዊ መንግሥት) መስከረም 2 ቀን 1967 ዓ.ም. መንበረ መንግሥቱን ከተቆናጠጠ በኋላ ለ12 ዓመታት ያለ ሕገ መንግሥት በአዋጆች ብቻ አገርን ሲያስተዳድር ኖሯል፡፡ በመሪ ፓርቲው የኢትዮጵያ ሠራተኞች ፓርቲ (ኢሠፓ) አማካይነትና በኢትዮጵያ ብሔረሰቦች ጥናት ኢንስቲትዩት አጋፋሪነት የተረቀቀው የኢትዮጵያ ሕዝባዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ (ኢሕዲሪ) ሕገ መንግሥት፣ በተለያዩ መድረኮች በአገር ውስጥና በባሕር ማዶ ውይይቶች ከተደረጉበት በኋላ በውሳኔ ሕዝብ (ሪፈረንደም) የጸደቀው፣ ከ39 ዓመት በፊት እሑድ ጥር 24 ቀን 1979 ዓ.ም. ነበር፡፡ በአሥራ ሰባት ምዕራፎችና በ119 አንቀጾች የተደራጀው የሕገ መንግሥቱ ሰነድ በሥራ ላይ መዋል የጀመረው የካቲት 15 ቀን 1979 ዓ.ም. ሲሆን፣ ኢሕዲሪም እውን የሆነው መስከረም 1 ቀን 1980 ዓ.ም. ነበር፡፡
ለአገሪቱ ሦስተኛ የሆነው የኢሕዲሪ ሕገ መንግሥት ከአራት ዓመት በላይ ማለፍ አልቻለም፡፡ ኢሠፓ/ኢሕዲሪን (የጥቂት ወራት ዕድሜ ሲቀረው ባይተገበርም ኢሠፓ ስሙን ወደ ኢዲአፓ- የኢትዮጵያ ዲሞክራሲያዊ አንድነት ፓርቲ ቀይሮ ነበር) ግንቦት 20 ቀን 1983 ዓ.ም. የፈነቀለው ኢሕአዴግ፣ ባቋቋመው ጊዜያዊ መንግሥት ቀጥሎም የሽግግር መንግሥቱን በነደፈው ቻርተር መሠረት፣ ለአራት ዓመት ካስተዳደረ በኋላ ኢፌዴሪ እውን የሆነበት ሕገ መንግሥት ሐሙስ ኅዳር 29 ቀን 1987 ዓ.ም. በሕዝብ ተወካዮች አማካይነት ያፀደቀበት ነበር፡፡
ዘመናዊት ኢትዮጵያ ያሳለፈቻቸው አራቱ ሕግጋተ መንግሥት የሐምሌና የጥቅምት፣ የጥርና የኅዳር ትሩፋቶች ሲሆኑ፣ የኢሕዲሪ ሕገ መንግሥት በውሳኔ ሕዝብ [ሕዝበ ውሳኔ አይደለም] በእሑድ ዕለት ከመፅደቁ ውጪ፣ ሦስቱ ማለትም የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ሁለቱና የኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት የፀደቁት በተመሳሳይ ዕለት ሐሙስ ነበር፡፡
