በአሁኗ ኢትዮጵያ ሕዝብ የሚያስፈልገው ዋናውና አንገብጋቢው ነገር ሰላም እንደሆነ ከማንም የተሰወረ አይደለም፡፡ አስተማማኝና ዘለቄታዊ ሰላም እንዲገኝ ግን የጋራ ጥረት ያስፈልጋል፡፡ አስተማማኝ ሰላም ሲኖር መማር፣ ማረስ፣ መነገድና ለሕይወት አስፈላጊ የሆኑ ነገሮችን ማከናወን ይቻላል፡፡ ሰላም ሲጠፋ ግን እንኳንስ የተለያዩ ተግባራትን ማከናወን ወጥቶ መግባትም ያዳግታል፡፡ በሁሉም የኢትዮጵያ አካባቢዎች ከቦታ ወደ ቦታ ተዘዋውሮ መሥራትና ሀብት ማፍራት የሚያስችል አስተማማኝ ሰላም መስፈን ይኖርበታል፡፡ በተለያዩ አካባቢዎች የሚካሄዱ ግጭቶች በንግግርና በድርድር ተቋጭተው ሰላም እንዲሰፍን፣ የአንድ ወገን ፍላጎት ብቻ ሳይሆን ሁሉንም ያማከለ መግባባት መፍጠር ይገባል፡፡ ኢትዮጵያ በግጭቶች ምክንያት የዕልቂትና የውድመት ምድር ሆና እንዳትቀር፣ ሁሉም የፖለቲካ ኃይሎችና ትጥቅ ያነገቡ ወገኖች ጭምር ከግጭት አዙሪት ውስጥ የሚያስወጡ ዘዴዎች እንዲቀየሱ ቀናነት ማሳየት አለባቸው፡፡ ኢትዮጵያ ከአስከፊ ድህነት ውስጥ የምትወጣው በልማት እንጂ እርስ በርስ በመፋጀት አይደለም፡፡
በፕሪቶሪያ ስምምነት ተገቶ የነበረው ማዕከሉን ትግራይ ያደረገው የሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት፣ እንደገና አገርሽቶ ወደ ዕልቂትና ውድመት ሊያመራ እየተንደረደረ እንደሆነ ምልክቶች እየታዩ ነው፡፡ በፌዴራል መንግሥትና በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ዕውቅና በተነፈገው ሕወሓት መካከል የሚስተዋለው መካረር፣ በትግራይ ክልል ነዋሪዎች ዘንድ ከፍተኛ ሥጋት መፍጠሩ ይታወቃል፡፡ ከዚህ ቀደም የተካሄደው አውዳሚ ጦርነት ያደረሰው ሰብዓዊና ቁሳዊ ኪሳራ እንደገና እንዳይከሰት፣ በትግራይም ሆነ በሌሎች አካባቢዎች የሚገኙ ኢትዮጵያውያን በተለያዩ መንገዶች እያሳሰቡ ነው፡፡ በምንም ዓይነት ሁኔታ ወደ ጦርነት እንዳይገባ የሚረዱ የመፍትሔ ሐሳቦች ያስፈልጋሉ፡፡ ከዚህ በፊት በእልህና በግትርነት የተካሄደው ጦርነት የዜጎችን ሕይወት ከማስገበር፣ ከማፈናቀል፣ አካላዊና ሥነ ልቦናዊ ጉዳት ከማድረስ፣ ለተለያዩ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ከመዳረግና የአገር ሀብት ከማውደም የዘለለ አንዳችም ጥቅም ያልተገኘበት ኪሳራ እንደነበረ አይዘነጋም፡፡
በአማራና በኦሮሚያ ክልሎች ውስጥ የሚካሄዱ ውጊያዎችም የዜጎችን ሕይወት ከመቅጠፍ፣ ከማፈናቀልና ንብረት ከማውደም፣ እንዲሁም ለተለያዩ ጉዳቶች ከመዳረግ ውጪ የፈየዱት ነገር የለም፡፡ ይልቁንም በአውራ መንገዶች ላይ ዕገታ፣ ዘረፋ፣ ግድያና የመሳሰሉ አስከፊ ድርጊቶች እንዲባባሱ ነው ያደረጉት፡፡ በሕዝብና በጭነት ትራንስፖርት አገልግሎቶች ላይ እውክታ በመፍጠር ሰዎችና ምርቶች እንዳይንቀሳቀሱ በማድረግ ከፍተኛ ጉዳት አድርሰዋል፡፡ ከላይ ከተገለጹት መከራዎች በተጨማሪ በታዳጊው ትውልድ ላይ ከፍተኛ ችግር አስከትለዋል፡፡ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሕፃናትና ወጣቶች ከትምህርት ገበታቸው ተፈናቅለው የወደፊት ተስፋቸው ጨልሞባቸዋል፡፡ የትምህርት፣ የጤና፣ የመሠረተ ልማትና ሌሎች አገልግሎቶች እየተቋረጡ በዜጎች ላይ ተደራራቢ ችግሮች ተጋርጠዋል፡፡ ጦርነቶችን ወይም ግጭቶችን በሰላማዊ መንገድ አስቁሞ በንግግርና በድርድር መፍትሔ ማግኘት ካልተቻለ፣ ችግሩ በተራዘመ ቁጥር ለአገር ህልውና አደገኛ እንደሆነ በቀላሉ መገንዘብ ይቻላል፡፡
ኢትዮጵያ ከግጭትም ሆነ ከጦርነት ውስጥ የመውጫ መንገዶች ሊፈለጉላት የግድ ይላል፡፡ ከ130 ሚሊዮን በላይ ሕዝብ እንዳላት የሚነገርላት ኢትዮጵያ የተራዘመ ጦርነት ውስጥ መቆየት የለባትም፡፡ በሁሉም ዘርፎች የሚገኙ የተፈጥሮ ሀብቶችን ለሥራ ዝግጁ ከሆነ ወጣት ኃይል ጋር አቆራኝቶ ወደ ልማት በስፋት መሰማራት ሲገባ፣ መለስተኛ ቅራኔዎችን በንግግርና በድርድር መፍታት አቅቶ አገርን የጦር ሜዳ ማድረግ ጤነኝነት ስላልሆነ ለዘላቂ ሰላም መስፈን ጥረት ይደረግ፡፡ ሁሉም ኢትዮጵያውያን የአገራቸው ጉዳይ ስለሚያገባቸው ከፖለቲካ ወገንተኝነትና ከጎራ ፍትጊያ በላይ፣ ለኢትዮጵያ መፃኢ ዕድል ፈንታ በመጨነቅ ለሰላም አብሮ ለመሥራት ፈቃደኝነት ያሳዩ፡፡ የፖለቲካ ፉክክሩ ሕጋዊ፣ ሰላማዊና ቅቡልነት ያለው ሲሆን የህሊና ዳኝነቱ የሚተወው ለመራጩ ሕዝብ እንደሆነ መገንዘብ ይገባል፡፡ ከዚያ ውጪ ፍላጎትን በኃይል ለማስፈጸም የሚኬድበት ርቀት አገር አፍራሽ ነው፡፡
በተለይ ወጣቶች የነገ አገር ተረካቢ ስለሆናችሁ ትምህርታችሁን በርትታችሁ ተምራችሁ ራሳችሁን ለሕዝብ አገልጋይነት አሰናዱ፡፡ ራሳችሁን ስታዘጋጁ ደግሞ ሞጋችና ጠያቂ ለመሆን እንጂ፣ ሌሎች እንደፈለጉ የሚነዷችሁ እንዳትሆኑ ጥንቃቄ አድርጉ፡፡ ዘመኑ እጅግ በጣም ከመክበዱ የተነሳ በማኅበራዊ ሚዲያዎች በሚለቀቁ ምንጮቻቸው ለማይታወቁ መረጃዎች፣ እንዲሁም ለወደፊት ሕይወታችሁ ምንም ፋይዳ ለሌላቸው ዕርባና ቢስ ጉዳዮች ጀርባችሁን ስጡ፡፡ ለራሳችሁ፣ ለቤተሰባችሁ፣ ለማኅበረሰቡና ለአገር የማይጠቅሙና በኢሞራላዊ ድርጊቶች የተሞሉ ከንቱ ነገሮችን አትከተሉ፡፡ አገር የምታድገው በሥራ እንጂ በምናባዊ ግርግሮች ስላልሆነ፣ የጅምላ አጀብ ከሚበዛባቸውና የጋራ ማኅበራዊ እሴቶችን ከሚንዱ ድርጊቶች ተጠንቀቁ፡፡ የአገር ሰላም ከሚያደፈርሱ፣ የወጣቱን ትውልድ ሞራላዊና ሥነ ምግባራዊ እነፃ ከሚገዳደሩ፣ በአቋራጭ ሀብትና ዝና ከሚያስገኙ የሌብነትና የአጭበርባሪነት ጎዳናዎች በመራቅ ለአገራችሁ ሰላምና ዕድገት የሚፈለግባችሁን ለመወጣት ዝግጁ ሁኑ፡፡
ኢትዮጵያ የሚያምርባት ልጆቿ በሙሉ እርስ በርስ ሲከባበሩ፣ ሲረዳዱ፣ ዘመን ተሻጋሪ የጋራ ማኅበራዊ እሴቶቻቸውን ሲጠብቁ፣ አገራቸውን ከማናቸውም ዓይነት ጥቃት ለመከላከል በአንድነት ለመቆም ሲተባበሩ፣ ለልዩነቶቻቸው ዕውቅና ተሰጣጥተው በብሔራዊ ጉዳዮች ላይ ለመምከር ሲስማሙ፣ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች እንዲከበሩ ሲተጉ፣ ለፍትሕ መስፈን በጋራ ሲሠሩ፣ ሌብነት ወይም ሙስና ከሥሩ ተመንግሎ እንዲጣል ሲግባቡ፣ ሁሉንም ኢትዮጵያውያን በእኩልነት የምታስተናግድ ኅብረ ብሔራዊት አገር እንድትገነባ የሚያስችል መሠረት ሲጥሉና መሰል መልካም ተግባራት ላይ ሲተባበሩ ነው፡፡ ሁሉም ኢትዮጵያውያን ከልዩነቶቻቸው በላይ አገራቸውን ማስቀደም ሲችሉ ግጭት አይኖርም፡፡ ኢትዮጵያን እየጎዳት ያለውና ለታሪካዊ ጠላቶች ጭምር ተጋላጭ እያደረጋት ያለው ዋነኛ ችግር ልዩነቶችን በሕጋዊና በሰላማዊ መንገድ ፈር ለማስያዝ አለመቻል ነው፡፡ ከግጭት የፀዳች ኢትዮጵያ እንድትኖር ልዩነቶች ይከበሩ!