- የቤቶች ኮርፖሬሽን ላይ ወቀሳ ያቀረቡት ኮሚሽነር ብርሃኑ ‹‹ቤት አይመደብ መኪና አይሰጥ ምን አድርጌ ነው የምሠራው›› ብለዋል
የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) በመጭው ሐምሌ 2018 ለሚጀመረው አዲሱ በጀት ዓመት ያቀረበው የ1.1 ቢሊን ብር በጀት ፍላጎት፣ በመገባደድ ላይ ላለው በጀት ዓመት ከፀደቀለት በጀት በሶስት እጥፍ ያደገና የተጋነነ ነው ሲል የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አስታወቀ፡፡
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የአምስት የዴሞክራሲ ተቋማትን የፋይናንስ አጠቃቀምና የመጪው ዓመት የበጀት ፍላጎት በገመገመበት ወቅት የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን የቀጣይ ዓመት የበጀት ጥያቄ ላይ ተወያይቷል፡፡
ኮሚሽኑ ለቀጣይ ዓመት በጀት ያቀረበው የተጋነነና በሦስት እጥፍ ያደገ መሆኑን ያስታወቀው ኮሚቴው፣ 753 ሚሊዮን ብር ከመንግሥት ግምጃ ቤት ለመደበኛ በጀት ፍላጎቱ መጠየቁ ተገልጿል፡፡ በሌላ በኩል ከውጭ ዕርዳታ 402 ሚሊዮን ብር፣ በአጠቃላይ 1.1 ቢሊዮን ብር በጀት ለማግኘት ፍላጎቱን ማቅረቡን አስታውቋል፡፡
የገንዘብ ሚኒስቴር ለኮሚሽኑ ባስቀመጠው የበጀት ጣሪያ መሠረት፣ ከመንግሥት ግምጃ ቤት 193 ሚሊዮን ብር ሲሆን፣ አሁን ከጠየቀው ከጣሪያው ጋር ሲተያይ በ560 ሚሊዮን ብር ልዩነት እንዳለው ተገልጿል፡፡ ልዩነቱ 290 በመቶ ከተቀመጠው ጣሪያ እንዲሁም በባለፈው ዓመት ከፀደቀበት የ2018 ዓ.ም. በጀት ጋር ደግሞ የ337 ሚሊዮን ብር ልዩነት እንዳለው ተገልጿል፡፡
ኮሚሽኑ የተጋነነ የበጀት ጥያቄ ያቀረበው በአማራ፣ ትግራይ፣ አፋርና አዋሳኝ አካባቢዎች በግጭት ምክንያት የሰብዓዊ ሁኔታ አሳሳቢ መሆኑን፣ ይህን ለመፍታት ምክክር በማድርግ በመግባባት ለመሥራት፣ የሪፎርም ሥራዎችን አጠናክሮ ለመቀጠል፣ ሪፖርቶችንና መግለጫዎችን በተጨማሪ ቋንቋ ለመሥራት፣ ተደራሽነታቸውን ለማስፋትና ተጨማሪ ጽሕፈት ቤት የመክፈት ዓላማ እንዳለው የገለጸው ኮሚቴው፣ ለተጋነነው በጀት የቀረበው ምክንያት ግን አሳማኝ ባለመሆኑ ማብራሪያ ይቅረብ ሲል ጠይቋል፡፡
የኢሰመኮ ኮሚሽነር ብርሃኑ አዴሎ በሰጡት ምላሽ ለ2019 በጀት ዓመት የቀረበው የገንዘብ ፍላጎት ታሳቢ የተደረገው የዓለም አቀፍን ሁኔታ በማየት ራስን የመቻል ጉዳይ ነው ብለዋል፡፡ አክለውም ባለው የፖለቲካ ሁኔታ የፋይናንስ ቅነሳ መኖሩን ገልጸው ለጋሽ አካላት ለተያዘው በጀትም ጥርጣሬ አላቸው ብለዋል፡፡ ዓለም አቀፉ የፖለቲካ ሁኔታ ከመካለኛው ምሥራቅ ጋር ተዳምሮ ለጋሽ አካላትን እያዳከመ ነው በማለት ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም ኢትዮጵያ በ2027 የአፍሪካ የሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ኮንፈረንስ የምታዘጋጅ በመሆኗ፣ ኮንፈረንሱን ለማዛጀት የሚደረገው ሥራ መንግሥት ሊደግፈው የሚገባ ነው ብለዋል፡፡ በተመሳሳይ የቢሮ ዕድሳትን ጨምሮ የገጽታ ማሻሻያ እንደሚሠሩ ገልጸው፣ የ46 አገሮች ተሳታፊዎች ወደ ኢትዮጵያ ሲመጡ ‹‹የተወለጋገደ ወንበር ላይ ቁጭ ብለን ኢሰመኮ እዚህ ላይ ሆኖ ነው የሚሠራው ብለን ብናስረዳ፣ ገጽታችን የሚጎዳ በመሆኑ በጀቱ ታሳቢ ያደረገው ይሄንን ሁሉ ነው፤›› በማለት ተናግረዋል፡፡ አክሎም አዳዲስ ቢሮዎችና ተሿሚዎች በጀት የሚፈልጉ በመሆኑ ደመወዝና ጥቅማ ጥቅሞችን ለማሻሻል በጀቱ የግድ መጨመር አለበት ብለዋል፡፡
የሰብዓዊ መብት ለውጥ በጩኸት አይመጣም የሚሉት ኮሚሽነሩ፣ መከላከልና ገንቢ ውይይት ማድረግ ላይ እንሥራ ብለው፣ ሕግ አስፈጻሚዎች መሠልጠንና መብቃት መቻል አለባቸው ብለዋል፡፡
From The Reporter Magazine
ኮሚሽኑ ተሽከርካሪ የለውም የሚሉት ኮሚሽነር ብርሃኑ፣ ተሽከርካሪ ከሌለ ተንቀሳቅሶ የማይሠራ ጽሕፈት ቤት ከፍቶ መቀመጡ መንግሥት ለኮሚሽኑ በጀት ባለመመደብ ጫና እያደረገ ነው የሚል ትርጉም ይሰጣል ብለዋል፡፡
የሥራ ነፃነት ላይ አደጋ እያመጣ ያለው ተሽከርካሪ ብቻ አይደለም ብለው፣ ‹‹እናንተ ፊት ማስቀመጥ የምፈልገው ከኮሚሽነር ዳንኤል ጀምሮ ለኮሚሽኑ ኮሚሽነሮች የመንግሥት ቤት እንኳ አይመደብም፣ በጣም የሚያሳዝን ነው፤›› ብለዋል፡፡ ኮሚሽነር ዳንኤል በነበሩበት ጊዜ ኮሚሽነሮች ቤት ሳይመደብላቸው ግማሻቻ ለቀዋል፣ አሁን ያሉትም የሹመት ጊዜያቸው በቅርቡ ያልቃል ብለው፣ ቤት አይመደብ፣ መኪና አይሰጥ ምን አድርጌ ነው የማሠራው፤›› በማለት ለኮሚቴው ሰብሳቢ ጥያቄ አቅርበዋል፡፡
‹‹የመንግሥት ቤቶች ኮርፖሬሽን እኛን አያስተናግድም›› ብለው፣ በቅርቡ በአፈ ጉባዔው በተጻፈ ደብዳቤ ቤት ይሰጣቸው ተብሎ ቢጠየቅም፣ ፈቃደኛ እንዳልሆነ ተናግረዋል፡፡ እነዚህን ሁኔታዎች ለማስገደድ የማንችልና ገለልተኛ በመሆናችን ለመደባችኋቸው ኮሚሽነሮች የተሽከርካሪና የቤት ጉዳይ የማይሟላ ከሆነ ከመንግሥት ድጋፍ የለም የሚል መግለጫ ለመስጠት አንድ ውሳኔ ላይ እንደርሳለን ብለዋል፡፡
From The Reporter Magazine
አንድ ኮሚሽነር፣ ከሚከፈለው ደመወዝ በላይ ተከራይቶ እንደሚኖር ጠቁመው፣ የቀረበው በጀት የግነት ጉዳይ ሳይሆን የተለያዩ ተፅዕኖዎች፣ አዳዲስ ኮሚሽነሮች መሾማቸውና የሥራ ጫናዎች በመኖራቸው መሆኑን ኮሚሽነር ብርሃኑ ተናግረዋል፡፡
