- የፕሪቶሪያውን ስምምነት ሙሉ በሙሉ እንዲተገብር ተጠይቋል
ሕወሓት በትግራይ ክልል ያወጣውን ሕግ የሚያወግዝና የፕሪቶሪያውን ስምምነት ሙሉ ለሙሉ እንዲተገበር የሚጠይቅ ሰላማዊ ሰልፍ በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ ዛሬ ሐምሌ 11 ቀን 2018 ዓም ተካሄደ።
ሰልፉ በትግራይ ክልል የሰላምና ለውጥ ምክር ቤት አስተባባሪነት የተደረገ ነው።
የምክር ቤቱ የኮሙዩኒኬሽ አስተባባሪ አቶ ከበደ አሰፋ የህወሓት ቡድን በትግራይ ክልል ያወጣው አፋኝ አዋጅ እንዲነሳና የፕሪቶሪያው ስምምነት ሙሉ በሙሉ እንዲከበር ለመጠየቅ የተጠራ ሰልፍ መሆኑን ተናግረዋል።


የትግራይ ሕዝብ ዳግም ከተደገሰለት ጦርነት ነፃ እንዲሆን ለፌዴራል መንግሥትና ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ጥሪ አቅርበዋል።
ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብና የፕሪቶሪያው ስምምነት አስተባባሪዎች፣ ሥምምነቱ ሙሉ በሙሉ እንዲተገበር፣ የትግራይ ክልል ሰላም እንዲጠበቅ፣ ሕዝቡም ወደ ልማት እንዲገባና ከዳግም ጥፋት እንዲጠበቅ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል።
በሰላማዊ ሰልፉ ላይ የተገኙት የጠቅላይ ሚኒስትሩ የምስራቅ አፍሪካ ጉዳዮች አማካሪ አቶ ጌታቸው ረዳ፣ የዚህ ሰልፍ ዋና ዓላማ የፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት እንዲከበር ለመጠየቅ ነው ብለዋል።
From The Reporter Magazine
የትግራይ ሕዝብ ሰላም ፈላጊና ወደ ዳግም ጦርነት መግባት እንዳማይፈልግ ተናግረዋል።
አቶ ጌታቸው በንግግራቸው በምዕራብ ትግራይ የተያዙ ቦታዎች እንዲመለሱ ጠይቀዋል።


From The Reporter Magazine
በህወሓት ቡድን እየተጣሰ ያለው የፕሪቶሪያ ስምምነት እንዲከበር፣ የኢትዮጵያ መንግሥት የትግራይን ሕዝብ የመጠበቅና የመታደግ ግዴታውን እንዲወጣ የሚጠይቁ መፈክሮች በሰልፉ ታይተዋል።
“ወደ ሱዳን የሚደረገውን እኩይ የሰዎች ዝውውርን በፅኑ እናወግዛለን፣ በህወሓት ቡድን የተጣለው አዋጅ በአስቸኳይ ይነሳ፣ ተፈናቃይ ወገኖቻችን ወደ ቀያቸው ይመለሱ፣ ሰላም የትግራይ ሕዝብ ቀዳሚ ምርጫ ነው፣ ጦርነት ይብቃ” የሚሉ መፈክሮች በሰልፉ ታይተዋል።
በሰልፉ ላይ የነበሩት ሌተና ጀነራል ፃድቃን ገብረ ትንሳኤ፣ ክንደያ ገብረ ሕይወት (ፕሮፌሰር)፣ አቶ ኃፍታይ ገብረ እግዚአብሔር ጨምሮ ሌሎች ዕንግዶችም ተገኝተዋል።