ሪፖርተር – Ethiopian Reporter – #1 Best and reliable news source in Ethiopia
[ክቡር ሚኒስትሩ የቢሮ ሥራቸውን አጠናቀው ከውጭ አገር የመጣ ወንድማቸውን ለመጠየቅ ያረፈበት ገስት ሀውስ ሲደርሱ ወንድማቸው በቴሌቪዥን የሚተላለፈውን ፕሮግራም በመገረም እየተከታተለ አገኙት]
- ውይ መጣህ እንዴ? እስኪ አረፍ በል፡፡
- ምንድነው እንዲህ ያስደነቀህ?
- ተደንቄ ሳይሆን ግራ ግብት ብሎኝ ነው።
- ምኑ ነው ግራ ያጋባህ?
- የድልድይ ማስመረቅና የድልድይ ማፍረስ ነገር ነዋ።
- አልገባኝም?
- አለቃችሁ ድልድይ ሲያስመርቁ የተናገሩትን ሰምቼ ግራ ግብት ብሎኛል።
- ምንድነው የተናገሩት?
- ዛሬ ይህንን ድልድይ እንዳስመረቅነው ሁሉ የትርክት ድልድይ መገንባትም ያስፈልገናል አሉ።
- የምን ድልድይ?
- ቆይ የተናገሩትን ቃል በቃል ልንገርህ።
- እሺ…
- ‹‹በአማራና በኦሮሞ፣ በአማራና በትግራይና በሌሎችም ሕዝቦች መካከል በአልባሌ ትርክቶች ምክንያት እየላላ ያለውን ትስስር ሊያጠናክር የሚችል የትርክት ድልድይ መገንባትም እንፈልጋለን፤›› ነው ያሉት።
- እና እንደዚያ ማለታቸው ግራ ያጋባል እንዴ?
- ድልድይ መገንባት እንፈልጋለን ማለታቸውማ ጥሩ ነገር ነው።
- ታዲያ ድልድይ እያስመረቁ ድልድይ ማፍረስ ያልከው ምኑን ነው?
- ከቀናት በፊት ወደ ምዕራቡ አካባቢ ሄደው የተናገሩት ትዝ ብሎኝ ነዋ?
- እዚያ ሄደው የተናገሩትን እንኳ አልሰማሁም፣ ምንድነው ያሉት?
- ሕዝባችን በገዛ አገሩ ለመቶና ከዚያ በላይ ዓመታት እንደ ሁለተኛ ዜጋ ተቆጥሮ ቆይቷል፣ ዛሬ ግን ነፃ ወጥቷል።
- ታዲያ ይህን ማለታቸው ምን ችግር አለው?
- ኢትዮጵያ ውስጥ በመሪዎች የተጨቆነው አንድ ማኅበረሰብ ብቻ ነው እንዴ?
- እሱስ ልክ ነህ ሁሉም ተጨቁኗል።
- ዛሬ ደግሞ በአልባሌ ትርክቶች ምክንያት እየላላ ያለውን የሕዝቦች ትስስር ሊያጠናክር የሚችል የትርክት ድልድይ መገንባት አለብን ይላሉ፡፡
- ይህንን ማለታቸው ትክክል አይዳለም እያልክ ነው?
- ትክክል አይደለም!
- ምኑ ነው ትክክል ያልሆነው?
- ማኅበረሰባችን ቀደም ሲል የጨቆኑትን መሪዎች የብሔር ማንነት እየቆጠረ ዛሬ እርሱ በእርሱ ተካሮ ሳለ እንዲህ ያለ ንግግር ተገቢ አይደለም፡፡
- በእርግጥ እንደዚያ ባይናገሩ ጥሩ ነበር።
- ይኼን ብቻ መሰለህ እንዴ የተናገሩት?
- እ… ሌላ ምን ብለዋል?
- በታሪክም ቢሆን ሕዝባችን ለጠላት ጭቆና የተዳረገው የውስጥ አንድነት ስላልነበረው ነው፣ ዛሬ ከጠላት ጋር ውይይት ማድረግ ትልቅ ውርደት ነው፣ ስለዚህ ከዚህ ስህተት ተምረን በአንድነት በመቆም ጠላቶቻችንን እንመክት።
- እንደዚያ ማለት አልነበረባቸውም፣ ግን ያው…
- እ… ያው ምን?
- አልፎ አልፎ የአፍ ወለምታ ሊያጋጥም ይችላል።
- ከጭቆና ተነስተው ዛሬም ጠላቶቻችንን እንመክት እስከማለት የደረሱበትን ንግግር ነው የአፍ ወለምታ ነው የምትለኝ?
- ለእኔ ወለምታ ነው የሚመስለኝ።
- በጭራሽ! ይኼ የአፍ ወለምታ ሳይሆን አቅደው የተናገሩት ነው።
- እንደዚያ አንኳን እርግጠኛ መሆን የሚቻል አይመስለኝም።
- በደንብ ይቻላል፣ ከፈለግክ ንግግራቸውን ሲጀምሩ የተናገሩትን አድምጥ፣ ያኔ ጠላት ያሉት ማን እንደሆነ ጭምር ይገለጽልህ ይሆናል።
- ንግግራቸውን ሲጀምሩ ምንድነው ያሉት?
- ሕዝባችን ያሳለፈውን ጭቆና ለእናንተው መልሶ መናገር አልፈልግም፣ ነገር ግን አጠገቤ ላሉት እንግዶች እንዲገባቸው በደንብ እነግራቸዋለሁ።
- እንግዶቹ እነማን ነበሩ?
- በቦታው ላይ የተገኙ ናቸዋ!
- በሕዝብ ፊት እንደዚያ መናገር አልነበረባቸውም ቢሆንም ግን…
- እ… ቢሆንም ምን?
- እኔ አሁንም የአፍ ወለምታ እንደሆነ ነው የሚሰማኝ።
- በዝርዝር የተነገረ ሐሳብ እንዴት የአፍ ወለምታ ይሆናል?
- እኔ በበኩሌ እሳቸው እንዲህ ዓይነት አስተሳሰብ አላቸው ብዬ አላምንም።
- ምክንያት?
- ምክንያቱም እኔ ለአገራቸው ያላቸውን ፍቅር በደንብ አውቃዋለሁ።
- ምንድነው የምታወቀው?
- በየትኛውም አጋጣሚ ስለኢትዮጵያ እያወሩ ከሆነ…
- እ…?
- በዓይናቸው ዕንባ ግጥም ይላል።
- የምርህን ነው!?
- የምሬን ነው።
- ወንድሜን!
- ምነው?
- እንዲያው አንድ ወንድሜን!
[ክቡር ሚኒስትሩ ወደ መኖሪያ ቤታቸው ገብተው ከባለቤታቸው ጋር እየተጨዋወቱ ሳለ ባለቤታቸው ስለቴሌቶኑ ጥያቄ አነሱ]
- እንዲያው ምን ስትሉ ነው ቴሌቶን ውስጥ የገባችሁት?
- የምን ቴሌቶን?
- ቴሌቶኑን ነዋ? በአንድ ጀንበር 50 ሚሊዮን ብር ያላችሁትን?
- ኦ… እሱንማ ከዕቅዳችን በላይ አሳክተን አጠናቀቅነው እኮ፣ አልሰማሽም?
- እሱንማ ሰምቻለሁ፣ የእኔ ጥያቄ ገንዘቡን ለምን ፈልጋችሁት ይሆን ብዬ ነው?
- ዘመናዊ የሕዝብ መፀዳጃ ቤቶችን ለመገንባት ነዋ።
- የት ነው የምትገነቡት?
- አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ።
- አዲስ አበባ የት አካባቢ?
- የኮሪደር ልማቱ በሚያልፋባቸው አካባቢዎች።
- እኔም እኮ መጠየቅ የፈለግኩት እሱን ነው።
- ምኑን?
- በዚያ አካባቢ የሕዝብ መፀዳጃ ቤት ለምን ይገነባል?
- እንዴት? ምን ማለትሽ ነው?
- ሕዝብ በሌለበት?
- ለምን የለም?
- እንዲነሳ ተደርጓላ።
- ለምንድነው የሚነሳው?
- ለኮሪደር ልማቱ!
The post [ክቡር ሚኒስትሩ የቢሮ ሥራቸውን አጠናቀው ከውጭ አገር የመጣ ወንድማቸውን ለመጠየቅ ያረፈበት ገስት ሀውስ ሲደርሱ ወንድማቸው በቴሌቪዥን የሚተላለፈውን ፕሮግራም በመገረም እየተከታተለ አገኙት] first appear on ሪፖርተር – Ethiopian Reporter – #1 Best and reliable news source in Ethiopia and is written by በጋዜጣዉ ሪፓርተር