‹‹በፀጥታ መደፍረስ ውስጥ የዜጎች መብት እየተረገጠ ነው›› ሲሉ፣ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሕግና ፍትሕ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ወ/ሮ እፀገነት መንግሥቱ ተናገሩ፡፡
‹‹የዜጎች ሰብዓዊ መብቶች እየተጣሱ በርካታ ወንጀሎች እየተበራከቱ የመጡበት አዝማሚያ እንዳለ እናውቃለን›› ያሉት ሰብሳቢዋ፣ ቋሚ ኮሚቴው የፍትሕ ሚኒስቴርንና ተጠሪ ተቋማት የስድስት ወራት ዕቅድ አፈጻጸም ጥር 28 ቀን 2017 ዓ.ም. ሲገመገም ነው፡፡
የወንጀል መከላከል ፖሊሲን በበላይነት እያስተዳደረ ያለው የፍትሕ ሚኒስቴር ተበራክተው የሚፈጸሙ የወንጀል ድርጊቶችን ለምን ማስቆም አልቻለም ሲሉም ጠይቀዋል፡፡
በተመሳሳይ ሪፖርቱ በቀረበበት ወቅት የቋሚ ኮሚቴው አባል ወ/ሮ ከድጃ ያሲን ባቀረቧቸው ጥያቄዎች፣ በሴቶችና ሕፃናት ላይ የሚፈጸሙ ያሏቸው፣ ለአዕምሮ የሚከብዱና ዘግናኝ ወንጀሎች መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ኅብረተሰቡ ፍትሕ ሊሰጠን ይገባል ብሎ ለሚጠብቃቸው የፍትሕ ፍላጎቶች አስተማሪ የሆነ ዕርምጃ ለምን አልተወሰደም ሲሉም ጠይቀዋል፡፡
በሕገወጥ የሰዎች ዝውውርና በልዩ ልዩ ወንጀሎች በዜጎች ላይ የሚፈጸሙ ኢሰብዓዊ ድርጊቶች ሊታረሙ ይገባል ያሉት የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ፣ የሕገ መንግሥት መሻሻልን የሚጠብቁ ሕጎች እንደተጠበቁ ሆነው ሌሎች ሕጎች ካሉ ግን ሊስተካከሉ ይገባል ብለዋል፡፡
በሕፃናት፣ በእናቶችና በአጠቃላይ በዜጎች ላይ በአሰቃቂ ሁኔታ ወንጀል የሚፈጽም ሰው ላይ ምን ዓይነት ዕርምጃ መወሰድ እንዳለበት ከኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ አኳያ መዳሰስ እንዳለበት አሳስበዋል፡፡
‹‹የወንጀል ሕጉ መዳሰስ አለበት፣ ስለመሻሻል መታሰብ አለበት፣ ማኅበረሰቡ የሚፈልገውን ፍትሕ ሊያገኝ ይገባል፣ ኢሰብዓዊ ድርጊት የፈጸመ አካል የተወሰደበትን ዕርምጃ ማኅበረሰባችን ማወቅ ይፈልጋል፤›› ብለዋል፡፡
‹‹አንዳንድ ጊዜ ዓለም አቀፍ ስምምነቶች፣ ሰብዓዊ መብቶች እያልን በዚያ ሥር ውስጥ ሆነን ምን ማድረግ እንዳለብን ካላሰብን በስተቀር፣ አሁን በአገራችን ብቻ ሳይሆን በዓለም አቀፍ ደረጃ እየተፈጠሩ ያሉ ውስብስብ ወንጀሎችና ድርጊቶች እንዴት መከላከል እንዳለብን ማሰብ አለብን፤›› ሲሉም ተናግረዋል፡፡
ለዚህም ድርሻውን የሚወስደው የፍትሕ ሚኒስቴር በመሆኑ መሻሻል ያለባቸው ሕጎች ካሉ ሊታዩ እንደሚገባ ገልጸው፣ በአገሪቱ በከፍተኛ መጠን የፍትሕ ፍላጎት በመኖሩ ችግሮች ለነገ ሊባሉ አይገባም በማለት አሳስበዋል፡፡
የሕግና ፍትሕ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢዋ በተመሳሳይ በሰጡት አስተያየት፣ ከየትኛውም ተቋም ወይም ሚኒስቴር ወደ ፓርላማው የሚመጡ ሕጎች፣ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ከመድረሳቸው በፊት ተናበው፣ ተቀናጅተውና ተገምግመው መቅረብ አለባቸው ብለዋል፡፡
የፍትሕ ሚኒስትር ደኤታው አቶ በላይሁን ይርጋ በሰጡት ምላሽ፣ የወንጀል መከላከል ሥራ ሁሉንም አካላት የሚመለከት መሆኑን ጠቅሰው፣ ለፍትሕ ሚኒስቴር የተሰጠው ኃላፊነት ፖሊሲዎችንና ስትራቴጂዎችን ማዘጋጀትና የሚመለከታቸውን አካላት ማስተባበር ነው ብለዋል፡፡ በዚህ መሠረት የወንጀል ፍትሕ ፖሊሲና የወንጀል መከላከል ስትራቴጂን በማፅደቅ ተጨማሪ ሥራዎችን እያከናወንን ነው ብለዋል፡፡
የሕግ አወጣጥ ሥርዓትን በተመለከተ መሠረታዊ የሆኑ የሕግ ረቂቅ አወጣጥ መሥፈርቶችን ያሟላ መመርያ በመዘጋጀቱ፣ የሚወጡ ሕጎች በመመርያው መሠረት እንደሚስተናገዱ አስረድተዋል፡፡