በሁሉም የአገሪቱ አካባቢዎች የሚገኙ አገር በቀል ዕውቀቶችን ለመመዝገብ 47 ዩኒቨርሲቲዎች የጀመሩት ሒደት 90 በመቶ መጠናቀቁ ተገለጸ፡፡
ይህ የተገለጸው የኢትዮጵያ ሳይንስ አካዴሚ በቋንቋ፣ በጤና፣ በግብርናና በእንስሳት እንክብካቤ ዘርፍ ትኩረቱን ያደረገ ‹‹አገር በቀል የዕውቀት ሥርዓት ለኢትዮጵያ ዘላቂ ልማት›› በሚል ርዕስ ግንቦት 27 ቀን 2018 ዓ.ም. በተካሄደ የውይይት መድረክ ነው፡፡
ውይይቱን የመሩትና የፕሮጀክቱ አስተባባሪ የኅብረተሰብ ጤና ሳይንስ ተመራማሪ መንገሻ አድማሱ (ፕሮፌሰር)፣ የአገር በቀል ዕውቀቶች ምዝገባው 90 በመቶ መጠናቀቁንና በሚቀጥሉት ሁለት ሳምንታት ሙሉ በሙሉ እንደሚያልቅ ተናግረዋ፡፡
በመጀመሪያው ዙር በ47 ዩኒቨርሲቲዎች ስምንት ዘርፎች ተለይተው ምዝገባው እየተከናወነ መሆኑንና እነዚህም ጤና፣ የሰላም ግንባታና የግጭት አፈታት፣ የተፈጥሮ ሀብት አጠቃቀም፣ የመንግሥት አስተዳደር፣ የአየር ንብረት፣ የልጆች አስተዳደግ፣ የቀን አቆጣጠርና ግብር መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡
ምዝገባው ከተጠናቀቀ በኋላ ወደ ሰነድነት የመቀየሩ ሥራ ረዥም ሒደት የሚጠይቅ እንደሆነ፣ ትንታኔውን እንዴት ማከናወን እንደሚቻል ሥልጠና እንደሚሰጥ ገልጸዋል፡፡
ሥራውን በዋናነት ኃላፊነት ወስዶ እያከናወነ የሚገኘው የትምህርት ሚኒስቴር መሆኑን ያስታወሱት መንገሻ (ፕሮፌሰር)፣ ይህንን ከግምት ውስጥ በማስገባት የአገር በቀል ዕውቀት ምዝገባ ሲጠናቀቅ፣ የትምህርት ሥርዓት በማድረግ በካሪኩለም መልክ ይዘጋጃል የሚል የተሳሳተ ግምት በበርካታ ሰዎች ዘንድ መፈጠሩን አብራርተዋል፡፡ ሆኖም ካሪኩለም ማዘጋጀት አንዱ የሒደቱ ውጤት መሆኑን፣ በዋናነት ግን አገሪቱ ያላትን የአገር በቀል ዕውቀት መረጃ በሰነድ ማዘጋጀት መሆኑን ገልጸዋል፡፡
‹‹የትምህርት ሚኒስቴርም ካሪኩለሙን በማዘጋጀት ለትምህርት ቤቶች አስተላልፏል፡፡ ነገር ግን ተማሪዎች የሚያጣቅሱት መጽሑፍ ወይም ሰነድ የለም፤›› በማለት፣ የሚዘጋጀው ሰነድ ይህን ክፍተት የሚሞላ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም በሁሉም ዘርፎች የተሰማራ ተቋም ሊጠቀምበት የሚችል መሆኑን አስረድተዋል፡፡
From The Reporter Magazine
በውይይቱ ወቅት፣ ‹‹ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የግብርና ባህላዊ ሥልቶች እንዴት ይገለጻሉ?›› በሚል ርዕስ ያዘጋጁትን ጽሑፍ ያቀረቡት የግብርና ኤክስቴንሽን ተመራማሪ ዳንኤል ተመስገን (ፕሮፌሰር)፣ የባህላዊ ግብርና ከአገር በቀል ዕውቀት ዘርፎች አንዱ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በግብርና ዘርፍ የሚከሰቱ ችግሮችን መፍታት የሚያስችሉ በርካታ የአገር በቀል ዕውቀቶች መኖራቸውንና በተለይም ከበሽታዎች፣ ከተባዮችና ከአዝዕርቶች ጋር በተያያዘ በማኅበረሰቡ ውስጥ ያለው ዕውቀት የማይናቅ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ የደን፣ የአፈርና የውኃ አጠባበቅን ጨምሮ በመሬት እንክብካቤ ዙሪያ የአገር በቀል ዕውቀት ሚና ከፍተኛ ነው ብለዋል፡፡
ሆኖም ከአመለካከት ጀምሮ አገር በቀል ዕውቀትን የተመለከቱ በርካታ ችግሮች መኖራቸውን፣ የፖሊሲ ክፍተትና ዕውቀቱን የማጣት ዝንባሌ በሥጋት መታየት ያለባቸው ጉዳዮች እንደሆኑ አሳስበዋል፡፡
From The Reporter Magazine
በመንግሥት ጭምር በተደጋጋሚ የሚገለጸው ዘላቂ ልማት (Sustainable Development) የማኅበረሰብ መሠረት ያስፈልገዋል ያሉት የኅብረተሰብ ጤና ተመራማሪው ሚርጊሳ ካባ (ፕሮፌሰር)፣ ይህ ካልሆነ ግን የማኅበረሰቡ ችግር ሊቀረፍ እንደማይችል ገልጸዋል፡፡
ከሰባት ዓመታት በፊት በማኅበረሰብ ጤና ላይ የሚሠሩ ምሁራንን በማሰባሰብ የሚሰጠው የማኅበረሰብ ጤና ትምህርት አሁን ያሉትን ችግሮች መፍታት ስለመቻሉ ምልከታ ማድረጋቸውን፣ በዚህም ችግሮቹን ለመፍታት የሚያስችሉ እንዳልሆኑ መረዳታቸውንና ምክንያቱ ደግሞ የሚሰጡት ትምህርቶች አገር በቀል ዕውቀትን ባለማካተታቸው መሆኑን አስረድተዋል፡፡ በተለይም የአገር በቀል የጤና አገልግሎት፣ ዕውቀትና ሀብት መኖሩን የመረዳት ችግር መኖሩን ገልጸዋል፡፡
የሥነ ልሳን ተመራማሪው ዘለዓለም ልየው (ፕሮፌሰር) በበኩላቸው፣ አገር በቀል ዕውቀትና ቋንቋ ሊነጣጠሉ እንደማይችሉና ከትውልድ ትውልድ የሚተላለፍበት አንዱ መሣሪያ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ አገር በቀል ዕውቀትን ለማጥናት መልካም ጅማሮዎች መኖራቸውን፣ በተለይም አንዳንድ ዩኒቨርሲቲዎች ሥርዓተ ትምህርት ቀርፀው ወደ ሥራ እየገቡ ነው ብለዋል፡፡ ነገር ግን የሚሰጠው ትኩረት አነስተኛ መሆንና እንደ ኋላቀር ዕውቀት እየተቆጠረ መሆኑን አክለዋል፡፡
