
በተሳሳተ ሰነድ ኢትዮጵያ የገቡ ወይም በሕጋዊ መንገድ ኢትዮጵያ ገብተው በየጊዜው ማሟላትና ማሳደስ የነበረባቸውን ሰነድ ሳያሟሉ በሕገወጥ መንገድ ውስጥ የቆዩ 6‚395 የውጭ አገር ዜጎችን፣ ተጠያቂ ሆነው ቅጣት እንደተበየነባቸው ተገለጸ፡፡
የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት የኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ አምቦ መቀሳ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ‹‹ኢትዮጵያውያንንም ሆነ የውጭ ዜጎችን ተጠያቂ የምናደርገው የኢሚግሬሽን ሕግ ጥሰው ሲገኙ ነው፤›› ኢትዮጵያ ውስጥ ሊያቆያቸው የሚገባውን ሰነድ ሳያሟሉ ወይም ወደ አገር ውስጥ ሊያስገባቸው የሚችለውን ሰነድ ሳይዙ የተገኙ የውጭ አገር ዜጎች ተጠያቂ ተደርገዋል፡፡ የኢሚግሬሽን መሥፈርት ሳያሟሉ ኢትዮጵያ ሊገቡ የሞከሩ 10,243 የውጭ ዜጎችም ወደ አገራቸው እንዲመለሱ መደረጋቸውን አክለዋል፡፡
ለተለያየ ዓላማ ወደ አገር ውስጥ በሕጋዊ መንገድ የገቡ ግለሰቦችና ድርጅቶች የመኖሪያ ወይም የንግድ ፈቃዳቸውን ማሳደስ ወይም ማቋረጥ ሲኖርባቸው፣ ይህን ባላደረጉ ላይ ሕጋዊ ዕርምጃ መወሰዱንም ተናግረዋል፡፡
‹‹አንድ የውጭ አገር ዜጋ ወደ ኢትዮጵያ ሲገባና ሲቆይ መፈጸም ያለበት ክፍያና ማሟላት የሚገባው መረጃዎች አሉ፡፡ ይህ በሕግ የተደነገገ ውሳኔ ነው፤›› ያሉት ዳይሬክተሩ፣ በዚህ መሠረት ለሚቆዩበት ጊዜ ቀነ ገደብ ተቀምጦላቸው በጊዜው የሚፈለግባቸውን ሳይከፍሉ ሲቀሩ ቅጣት እንደሚጣልባቸው፣ ከገንዘብ ቅጣት ባለፈም ባለፉት ስድስት ወራት አብዛኞቹ ወደ አገራቸው እንዲመለሱ መደረጋቸው አብራርተዋል፡፡
የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት የኢሚግሬሽን ሕግ ጥሰው በተለያዩ ወንጀሎች ተሰማርተው የተገኙ 3,126 ኢትዮጵያውያን ላይም ክስ ተመሥርቶባቸው የተወሰኑት ቅጣት እንደተወሰነባቸውና የተወሰኑት ደግሞ ተጠያቂ መደረጋቸውን፣ የፍርድ ሒደታቸውን እየተከታተሉ መሆናቸውን ዳይሬክተሩ ገልጸዋል፡፡
ባለፉት ስድስት ወራት 6,395 የውጭ ዜጎችና 3,126 ኢትዮጵያውያን ላይ ሕጋዊ ዕርምጃ መወሰዱን፣ ዕርምጃ የተወሰደባቸው ኢትዮጵያውያን በሕገወጥ መንገድ በድለላ ሥራ የተሰማሩ መሆናቸውን፣ ከኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ጋር በጋራ እንደሚሠሩ በማስመሰል ማኅበረሰቡን ሲያጭበረብሩ የተገኙ፣ ከውጭ ዜጎች ጋር ተመሳጥረው የአገርን ጥቅም በሚጎዳ ሥራ ላይ የተሰማሩ ግለሰቦች መሆናቸውን የአገልግሎቱ የኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ አሞቦ መጎሳ ተናግረው፣ አገልግሎቱ ለየትኛውም ግለሰብም ሆነ ድርጅት የሰጠው የሥራ ውክልና እንደሌለ ገልጸዋል፡፡
‹‹በየሶሻል ሚዲያው የኢሚግሬሽን ቀጠሮ እናስይዛለን እያሉ ኅብረተሰቡን ሲያታልሉና ከአቅም በላይ ገንዘብ ሲያስከፍሉ የሚውሉ ድርጅቶች ከአገልግሎቱ ዕውቅና ውጪ ናቸው፤›› ያሉት አቶ አምቦ፣ በእነዚህ ሰዎች ላይ ሕጋዊ ዕርምጃ መውሰድ ከተጀመረ መቆየቱንና እንዲህ ዓይነት ድርጊት ሲፈጽሙ የተገኙ 11 ድርጅቶች መዘጋታቸውን ተናግረዋል፡፡
From The Reporter Magazine
የሕግ ተጠያቂነትን በሚመለከት ሲያብራሩ፣ ሕገወጥ ሥራ ሲያከናውኑ የነበሩ ሰዎች ክስ ተመሥርቶባቸው በፍርድ ቤት ተጠያቂ መደረጋቸውን፣ ጉዳያቸውም በፍርድ ሒደት ላይ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ አገሪቱ በሌሎች አገሮች ተግባራዊ እንደተደረገው የኢሚግሬሽን ፍርድ ቤትና ዓቃቤ ሕግ እንደሌላት ጠቅሰው፣ ‹‹ይህ የሕግ ክፍተት መፍትሔ ቢያገኝ ወንጀሎችን ለመከላከል ይረዳ ነበር፤›› ብለዋል፡፡ ነገር ግን ተቋሙ አሁን ባሉት ሕጎች መሠረት ተጠያቂ የማድረግ ሥራውን እንደሚቀጥል አብራርተዋል፡፡