- የጠረፍና ልዩ ልዩ የገጠር አካባቢዎችን የቴሌኮም አገልግሎት ተጠቃሚ ለማድረግ 7.5 ሚሊዮን ዶላር ፈንድ መገኘቱ ተነግሯል
የግል ዳታ እየሰበሰቡ ያሉና ወደፊትም የሚሰበስቡ የፌዴራል መንግሥትን ጨምሮ ማናቸውም ተቋማት ምዝገባ በማድረግ ፈቃድ እንዲያወጡ፣ የኢትዮጵያ ኮሙዩኒኬሽን ባለሥልጣን አሳሰበ፡፡
ባለሥልጣኑ ማሳሰቢያ የሰጠው፣ የግል ዳታ ጥበቃ አዋጅ ቁጥር 1321/2016 ትግበራና አፈጻጸምን በተመለከተ ግንቦት 5 ቀን 2018 ዓ.ም. የግል ዳታን ለሚሰበስቡና ለሚያቀናብሩ የፌዴራል ተቋማት ባዘጋጀው የምክክር መድረክ ላይ ነው።
የኢትዮጵያ ኮሙዩኒኬሽን ባለሥልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ሚሊዮን ኃይለ ሚካኤል፣ በአዋጁ መሠረት የግል ዳታ እየሰበሰቡ የሚገኙና ወደፊት የሚሰበስቡ የፌዴራል መንግሥት፣ መንግሥታዊ ያልሆኑና ሌሎች ተቋማት ምዝገባ በማድረግ ፈቃድ እንዲያወጡ ይገደዳሉ ብለዋል።
ባለሥልጣኑ አዋጁ ከፀደቀበትና በነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ ከወጣበት ጊዜ ጀምሮ ለአንድ ዓመት ከስድስት ወራት ለሚሆን ጊዜ ለሚመለከታቸው ተቋማት የማሳወቅ ሥራው ሲከናወን መቆየቱን፣ ለዚህም ይረዳ ዘንድ ባለሥልጣኑ አዲስ ፕላትፎርም ማዘጋጀቱንና በዚህም መሠረት ተቋማት እየተመዘገቡ ፈቃድ እንዲያወጡ ጥሪ አድርገዋል።
ፕላትፎርሙ ‹‹PDP.ECA.ET›› መሆኑን ባለሥልጣኑ በይፋ አስታውቋል። ፕላትፎርሙ ከቀናት በፊት ከመረጃና ኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር (ኢንሳ) የደኅንነት ማረጋገጫ በማግኘቱ፣ ከግንቦት 5 ቀን 2018 ዓ.ም. ጀምሮ ምዝገባ ማድረግ እንደሚቻል ገልጸዋል።
የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ዕቅድን ዕውን ለማድረግ የግል ዳታ ጥበቃ አዋጅ ወጥቶ ተግበራዊ ሊደረግ እንደሚገባው፣ በዚህም ተቋማት የግለሰቦችን ዳታ በኃላፊነት መጠበቅ እንዳለባቸው ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ አስረድተዋል።
አንድን ግለሰብ በአግባቡ መለየት የሚያስችሉ እንደ ስም፣ ስልክ ቁጥር፣ የኢሜይል አድራሻ ጄኔቲክ ሜካፕና መሰል መረጃዎች የግል ዳታ እንደሚባሉ አቶ ሚሊዮን ገልጸዋል።
From The Reporter Magazine
የአዋጁ ዓላማ እነዚህን መረጃዎች በመጠበቅ ኅብረተሰቡ በዲጂታሉ ዓለም ላይ እምነት እንዲኖረው አቅም መገንባት መሆኑን ተናግረዋል።
የፈቃድ ማውጣት ማሳወቅ ሥራው ከፍተኛ የግል ዳታ በሚሰበስቡና በሚያቀነብሩ ተቋማት መጀመሩን፣ በቀጣይ ወደ ክልሎችና አነስተኛ የግል ዳታ የሚሰበስቡ ሌሎች ተቋማት ለማስፋፋት ስምንት መድረኮች እንደሚዘጋጁም አቶ ሚሊዮን ገልጸዋል።
የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ባልቻ ሬባ (ኢንጂነር) በበኩላቸው የግል ዳታና መረጃን ያላግበብ መጠቀም፣ የሳይበር ጥቃቶች፣ የተቋማት ደካማ ዳታ ጥበቃዎችና የግንዛቤ ውስንነቶች ዜጎችን ለሕግ ጥሰቶች በመዳረጋቸው አዋጁ ይህንን ለመከላከል እንደሚያስችል ተናግረዋል። አዋጁ የግል መረጃን ለሚሰበስቡና ለሚያቀናጁ ተቋማት ኃላፊነት፣ ግዴታና ተጠያቂነት የሚያሰፍን መሆኑን አስረድተዋል። በዚህም የግለሰቦችን መረጃ ከታለመለት ዓላማ ውጪ የሚጠቀሙ ተቋማት ተጠያቂ የሚሆኑበት አሠራር እንዳለው ጠቁመዋል።
From The Reporter Magazine
ግለሰቦች የግል ዳታ ጥሰት ሲያጋጥማቸው ለተቆጣጣሪው አካል ሪፖርት ማድረግ እንደሚችሉ፣ ዳታ ሰብሳቢ ተቋሙም ቢሆን በ72 ሰዓታት ውስጥ ለባለዳታው ማሳወቅ እንዳለበት ተገልጿል።
አዋጁ ከያዛቸው አስተዳደራዊ ዕርምጃዎች መካከል ማንኛውም ሰው ባለቤቱ ተለይቶ እንዳይታወቅ የተደረገን የግል ዳታ ተለይቶ እንዲታወቅ ካደረገ፣ ተለይቶ የታወቀውን የግል ዳታ ካቀነባበረ፣ የግል ዳታን ከሸጠ ወይም ለሽያጭ ካቀረበ፣ የግል ዳታን በአዋጁ ከተደነገገው ውጪ ከአገር ውጭ ካስተላለፈ ከአምስት እስከ አሥር ዓመት እስራት ወይም ከ200 ሺሕ ብር እስከ 600 ሺሕ ብር፣ እንዲሁም በሁለቱም ቅጣት ይጣልበታል።
ማንኛውም የግል ዳታ ባለቤት የግል ዳታው እንዲደመሰስ የማድረግ፣ እንዳይቀናበር የመጠየቅ፣ ራስ አገዝ በሆኑ መሣሪያዎች በሚሰጡ ውሳኔዎች ላይ ያለውን መብቱን ካላከበረ ከሦስት እስከ አምስት በሚደርስ እስራትና ከ100 ሺሕ እስከ 200 ሺሕ ብር በሚደርስ ወይም በሁለቱ ቅጣት እንደሚጣልበት በአዋጁ ተደንግጓል።
የግል ዳታ የሚሰበስቡ ተቋማት የሰበሰቡትን ዳታ በአግባቡ የመጠበቅ ኃላፊነት እንዳለባቸው፣ ጥሰት ከተፈጠረ እንደሚጠየቁ በማወቅ የሚያደርጉትን ዝግጅት እንዲያጠናክሩ ባለሥልጣኑ አሳስቧል።
በሌላ በኩል የቴሌኮም አገልግሎት ተጠቃሚ ያልሆኑና 50 ልዩ ልዩ የገጠርና የጠረፍ አካባቢዎችን ተጠቃሚ ለማድረግ ከዓለም ባንክ ጋር የፋይናንስ ድጋፍ ስምምነት መፈረሙንና 7.5 ሚሊዮን ዶላር መሆኑንም ባለሥልጣኑ ገልጿል፡፡
የኢትዮጵያ ኮሙዩኒኬሽን ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ባልቻ ሬባ (ኢንጂነር) በተደረገ የተደራሽነት ክፍተት ዳሰሳ ጥናት ከሁሉም ክልሎች የተለዩ 50 ልዩ ልዩ የገጠርና የጠረፍ አካባቢዎችን ሁሉን አቀፍ ተደራሽነት ፈንድ (Universal Access Fund) አማካይነት፣ የቴሌኮም አገልግሎት ተጠቃሚ ይደረጋሉ ሲሉ ለሪፖርተር ተናግረዋል። ለዚሁ ፕሮጀክት ይረዳ ዘንድ ሁሉን አቀፍ ተደራሽነት ዓለም አቀፍ ፈንድ መሠረት ከዓለም ባንክ 7.5 ሚሊዮን ዶላር ፋይናንስ መገኘቱን ገልጸዋል።
የቴሌኮም ኦፕሬተሮች የኔትወርክ ዝርጋታ አድርገው ቢሠሩ አዋጭ ሊሆንላቸው የማይችሉባቸው ገጠራማና ጠረፍ አካባቢ የሚገኙ ቦታዎች ስለሆኑ፣ የፈንድ ድጋፍ ተደርጎላቸው አገልግሎት እንዲሰጡ እንደሚደረግ ተናግረዋል።
ይህንኑ አገልግሎት እንዲሰጡ የሚደረጉት የቴሌኮም ተቋማት መሆናቸውንም ገልጸዋል። ኢትዮ ቴሌኮምና ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ እኩል ጨረታ እንዲወዳደሩ እንደሚደረግም ተናግረዋል። ባለሥልጣኑ የቅየሳና የዲዛይን ሥራዎችን ሙሉ ለሙሉ መጠናቀቁን፣ በአሁኑ ወቅት የጨረታ ማውጣት ሒደት ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል።
በኮሙዩኒኬሽን አዋጅ ቁጥር 1148/2011 መሠረት፣ የሁሉን አቀፍ ተደራሽነት ፈንድ የገቢ መጠን ምንጭ ስለሚተዳደርበት ሁኔታ መወሰን የሚያስችል ደንብ በቅርቡ መፅደቁን አውስተዋል። በዚህም በኢትዮጵያ የቴሌኮም አገልግሎት እየሰጡ የሚገኙት ኢትዮ ቴሌኮምና ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ፣ ልዩ ልዩ የገጠርና የጠረፍ አካባቢዎችን የቴሌኮሙዩኒኬሽንና የፖስታ አገልግሎት ተጠቃሚ ለሚያደርገው የሁሉን አቀፍ ተደራሽነት ፈንድ (Universal Access Fund)፣ ከሚያገኙት ያልተጣራ ዓመታዊ ገቢያቸው ላይ 1.5 በመቶውን ከ2018 በጀት ዓመት ማጠናቀቂያ ጀምሮ መክፈል እንደሚጀምሩ ዳይሬክተሩ ጨምረው ተናግረዋል።
በዚህም ተቋማቱ በሦስት ወራት ጊዜ ውስጥ ኦዲት ሪፖርታቸውን ጨርሰው እንደሚያሳውቁ፣ ባለሥልጣኑ በበኩሉ፣ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ተቋማቱ መክፈል ያለባቸውን የ1.5 በመቶ ድርሻ አሰልቶ መልሶ እንደሚያሳውቅ፣ ከዚያም በቀጣዩ አንድ ዓመት ውስጥ ክፍያውን መክፈል እንዳለባቸው፣ ካልከፈሉ ቅጣት እንደሚጠብቃቸው፣ ሆኖም ከስድስት ወር በላይ ክፍያው ሳይከፈል መቆየት እንደማይቻል ባልቻ (ኢንጂነር) አስረድተዋል።
የተለያዩ የውጭ አገሮች ሁሉን አቀፍ ተደራሽነት ፈንድ የሚያወጡት ክፍያ ከ1.5 እስከ 3.5 በመቶ መሆኑንና ኢትዮጵያ ማስከፈል የምትጀምረው በአማካይ ዝቅተኛ የሚባለውን መሆኑን፣ ይህም የመሠረተ ልማትና አገልግሎት ማስፋፊያ ላይ እንዲያተኩሩ ታሳቢ ተደርጎ ስለመሆኑ ተናግረዋል።
የፋይናንስ ድጋፉ መቼ ይለቀቃል ፕሮጄክቱስ መቼ ይጀመራል የሚል ጥያቄ የቀረበላቸው ባልቻ (ኢንጂነር)፣ ፈንዱን ገንዘብ ሚኒስቴር የሚቀበል በመሆኑ፣ ዓለም ባንክና የገንዘብ ሚኒስቴር ያላቸው ስምምነት ላይ የተመረኮዘ መሆኑን ጠቁመዋል።
በሚሰበሰበው ገቢ ላይ በሚሠራው የቴሌኮሙዩኒኬሽንና አገልግሎት ላይ የሚገኙት ኢትዮ ቴሊኮምና ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ተወዳድረው እንዲሠሩ እንደሚደረግ፣ የሚሠሩት መሠረተ ልማትም ባለቤት እንደሚሆኑ ተናግረዋል። በተሰበሰበው ገቢ ምን ተሠራ የሚለው በየ ዓመቱ ኦዲት ሪፖርት ተደርጎበት ለሕዝብ ይፋ እንደሚደረግም (ኢንጂነር) ገልጸዋል።
ይህ በዚህ እያለ፣ የኢትየጵያ ኮሙዩኒኬሽን ባለሥልጣን ከቴሌኮም ኦፕሬተሮች ባሰባሰበው መረጃ፣ ወጪያቸውን መነሻ ያደረገ የመሠረተ ልማት መጋራት ዋጋ በማዘጋጀት ለሁለቱም ኦፕሬተሮች መላኩን አውስተዋል፡፡ ከጥር ወር 2018 ዓ.ም. ጀምሮ መመርያው ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን፣ ባለሥልጣኑም ክትትልና ቁጥጥር እያደረገ መሆኑን፣ እስካሁን ባለው ጊዜ የማያሠራ ተብሎ የቀረበ ቅሬታ አለመኖሩን ተናግረዋል።
