የመስኖና ቆላማ ሚኒስቴር የፌዴራሉ ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት በወልመልና ጨልጨል የመስኖ ፕሮጀክቶች ላይ ሰፋ ያሉ የኦዲት ግኝቶችን የያዘ ሪፖርት ይፋ ማድረጉን ተከትሎ ባወጣው መግለጫ፣ የተጀመረውን ስኬታማ ጉዞ ለማደናቀፍና ለማጠልሸት የሚከናወኑ ሥራዎች በፍፁም ተቀባይነት አይኖራቸውም አለ።
በተመሳሳይ በፕሮጀክቶቹ ተቋራጭ ሆኖ እየሠራ ያለውና በዋና ኦዲተር የክዋኔ ኦዲት ግኝቶች ላይ ስሙ የተጠቀሰው ዓለማየሁ ከተማ ጠቅላላ ተቋራጭ፣ ዋና ኦዲተር ይፋ ያደረገውን የክዋኔ ኦዲት ግኝቶች ሙሉውን ሪፖርት እንዳልተሰጠው ጠቁሞ፣ የኦዲት ግኝት ተብሎ በመገናኛ ብዙኃን የተገለጸው ሪፖርት እሱን (ተቋራጩን) የማይወክልና ትክክል ያልሆነ ነው ብሏል፡፡
ሚኒስቴሩ ሐምኬ 9 ቀን 2018 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ፣ የኮንትራትና የፕሮጀክት አስተዳደር ሥርዓትን በአግባቡ መረዳት ያቃታቸው ወይም መንግሥት የግብርና ክፍለ ኢኮኖሚውን አስተማማኝ ወደ ሆነው የመስኖ ምርታማነት ለመቀየር እያደረገ ያለውን ጥረት ለማደናቀፍና ለማጠልሸት ሆነ ተብለው የሚሠሩ ሥራዎች መኖራቸውን በመጥቀስ፣ ይህ በፍፁም ተቀባይነት ሊኖረው አይችልም ብሏል፡፡
‹‹አገራችን በተለያዩ ዘርፎች አስደናቂ የሆኑ ስኬቶችን እያስመዘገበች ትገኛለች፤›› ያለው የሚኒስቴሩ መግለጫ፣ ከዚህ አንፃር እንደ አገር የምናስመዘግባቸው ስኬቶች ለሕዝባችንና ለአጋሮቻችን የሚሰጠው ትርጉም ትልቅ የመሆኑን ያህል ይህ ጅምር እመርታ የማያስደስታቸው፣ በከፍተኛ የአመራር ቁርጠኝነትና የአጋሮች ጥረት የተገኙ ውጤቶች የሚያቅራቸው ኃይሎች መኖራቸው ግን ሳይታለም የተፈታ ነው ብሏል።
በዚህም ምክንያት በኢትዮጵያ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ በመስኖ ዘርፍ እየተገኘ ያለውን ስኬት ለመገንዘብና ዕውቅና ለመስጠት ሲቸገሩ እንደሚስተዋሉ ገልጿል። ይሁን እንጂ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ይህንን ሁኔታ ወደ ጎን በመተው የተቋቋመለትን ዓላማና የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ሉዓላዊነትና የሕዝብ ጥቅም ታሳቢ በማድረግ፣ በዘርፉ የሚገኙ አሠራሮችንና ሕጎችን መሠረት በማድረግ በአገሪቱ የጀመራቸውን በውጤት የታጀበ የመስኖ ፕሮጀክቶች የማጠናቀቅ ድሎችን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቋል፡፡
ሚኒስቴሩ ይህንን መግለጫ ያወጣው የፌዴራሉ ዋና ኦዲተር የሚኒስቴሩን የመስኖ ግንባታ ፕሮጀክቶችን በመገምገም ያገኛቸውን ከፍተኛ ጥሰቶች በቅርቡ ይፋ ማድረጉን ተከትሎ ቢሆንም፣ በመግለጫው ላይ ግን ለፌዴራል ዋና ኦዲተር የተሰጠ ምላሽ መሆኑን በግልጽ አያጠቅስም።
የፌዴራል ዋና ኦዲተር ሰሞኑን ይፋ ያደረገው የኦዲት ግኝት ሪፖርት፣ የጨልጨልና ወልመል ፕሮጀክቶች ግንባታ የመንግሥት የግዥ አፈጻጸም አዋጅንና የመንግሥት ንብረት አስተዳደር አዋጅ የሚደነግገውን የጨረታ ግዥ ያልተከተለ መሆኑን ያመለክታል።
From The Reporter Magazine
ኦዲቱ እንደሚያሳየው ከመነሻ ውል ውጭ ከአምስት ጊዜ በላይ ማሻሻል፣ ከውል በላይ ከፍያ መክፈል፣ የዋጋ ማስተካከያ ውሎችን መቀያየርና የዋጋ ጥናት ከስታትስቲክስ አገልግሎት ይልቅ አቅራቢው የሚያመጣውን መረጃ መቀበል፣ ተደጋጋሚ የሆኑና በዲዛይን ወቅት ያልተለዩ የሥራ ለውጦች መኖራቸውን ይዘረዝራል፡፡
የወልመል መስኖ ፕሮጀክትና ጨልጨል የመስኖ ፕሮጀክቶች ወደ ትግበራ ከመገንባታቸው በፊት የቅድመ አዋጭነት ጥናት ያልተደረገባቸው መሆኑ፣ የአዋጭነት ጥናትና ዝርዝር ዲዛይን በገለልተኛ አካል ያልተገመገመና ያልፀደቀ መሆኑ፣ ፕሮጀክቶቹ በጀት ውስጥ ከመካተታቸው በፊት የተዘጋጀ የፊስካልና ፋይናንሻል ዕቅድ ለሚመለከተው አካል ስለመቅረቡ ማስረጃ አለመገኘቱን ጨምሮ፣ ከኮንትራት ጋር የተያያዙ ችግሮች መኖራቸውንም ኦዲት ሪፖርቱ ገልጿል፡፡
የኦዲት ሪፖርቱ እንደሚያስረዳው በወልመል ወንዝ ሁለት ጊዜ የውል ማሻሻያ ተደርጎ ከአጠቃላይ ዋጋው 935 ሚሊዮን ብር ተጨማሪ ያስወጣ ሲሆን፣ በወልመልና ጨልጨል መስኖ ፕሮጀክቶች ከጅምሩ በግንባታ ውል ላይ የዋጋ ማስተካከያ አይደረግም ተብሎ ቢቀመጥም፣ የዋጋ ማስተካከያ ተደርጎ የ3.7 ቢሊዮን ብር ጭማሪ ተደርጓል፡፡
From The Reporter Magazine
ከጨልጨል ፕሮጀክት በጀት ላይ ዘጠና በመቶ የሚሆን ወጪያቸው ተሸፍኖ የተገዙ ሁለት ተሽከርካሪዎች ፕሮጀክቱን በሚገነባው የግል ተቋራጭ እጅ እንደሚገኙ የገለጸው የኦዲት ሪፖርቱ፣ በኦዲቱ ወቅት የተሽካርካሪዎች ሊብሬ እንዲቀርብ ተጠይቆ እንዳልቀረበለት አስታውቋል።
የኦዲት ሪፖርቱ አያይዞም፣ የተሽከርካሪዎቹ ግዥ በ83 ሚሊዮን ብር ሲፈጸም ዘጠና በመቶ የሚሆነው ወጪ በፕሮጀክቱ፣ ቀሪው አሥር በመቶ ደግሞ በተቋራጩ መሸፈኑን ጠቀሟል፡፡
በወልመል መስኖ በግንባታ መጀመሪያ ውል ከተገባባቸው ሥራዎች ጋር የማይገናኝ ለአረጋውያንና ችግር ተጋላጮች በሚል 24 ቪላ ቤቶችን በኮንትራት ማሻሻያ እንዲገነቡ መደረጋቸውን ሪፖርቱ ያመላክታል፡፡
የኦዲት ግኝቱ ይፋ ከመደረጉ በፊት የመውጫ ስብሰባ መደረጉንና በዚህም ወቅት የፕሮጀክቶቹ ባለቤት የሆነው የመስኖና ቆላማ ሚኒስቴር፣ ለኦዲት ግኝቶቹ ምላሽ መስጠቱን የፌዴራሉ ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት ሪፖርት ያስረዳል።
ሚኒስቴሩ በወቅቱ የሰጠው ምላሽም፣ በአገር አቀፍ ደረጃ የመስኖ ፕሮጀክቶች የጥናትና ዲዛይን ስታንዳርድ ያልነበረ በመሆኑ፣ ይህን የተመለከቱ የፕሮጀክቶች የጥናትና የዲዛይን ስታንዳርድ በአዲስ እየተዘጋጀ መሆኑን እንደገለጸ ያስረዳል።
ሚኒስቴሩ ያወጣው መግለጫ በቀጥታ ለዋና ኦዲተር የተሰጠ ምላሽ እንደሆነ ባይገልጽም፣ በርካታ በኦዲት ግኝቱ የተነሱ ነጥቦችን የሚያስተባብል ከመሆኑ ባሻገር፣ ሆን ተብሎም ይሁን ሳይታወቅ የመስኖ ፕሮጀክቶችን የማጠልሸት ሥራ ነው በማለት የሚከስ ነው።
ሚኒስቴሩ አክሎም የመስኖ ፕሮጀክቶችን የሚያስተዳድረው የመንግሥትን ሕግና ሥርዓትን በማክበር በኮንትራት ውል ስምምነት መሠረት ብቻ መሆኑን፣ የሲሚንቶና የነዳጅ እጥረትን ለመቅረፍ በቀጥታ ከአምራችና አቅራቢዎች ጋር ሥልታዊ ትስስር በመፍጠር፣ ከ2013 ዓ.ም. ጀምሮ በተሰጠው የመንግሥት ውሳኔ መሠረት ውሎችን በማሻሻል የዋጋ ማስተካከያ በማድረግ፣ የመስኖ ፕሮጀክቶች ልምድና አቅም ባላቸው አማካሪ ድርጅቶች ጥናትና ዲዛይን ተሠርቶ እንደሚጀመርና አስፈላጊ ሲሆን ማሻሻያ እንደሚደረግ አስታውቋል፡፡ በሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ከውል ውጭ የሚፈጸሙ ምንንም ዓይነት ግዥዎችና ጭማሪዎች እንደሌሉም አክሏል፡፡
የፌዴራል ዋና ኦዲተር በወልመል የመስኖ ግንባታ ፕሮጀክት፣ እንዲሁም በጨልጨል ግድብና ተያያዥ መዋቅሮች ግንባታን አስመልክቶ ይፋ ባደረገው የኦዲት ግኝት ሪፖርት ላይ እንዲሁም ይህንን ሪፖርት መሠረት በማድረግ ሪፖርተር ባለፈው ሳምንት ዕትሙ ባወጣው ዘገባ ላይ ስሙ የተጠቀሰው ዓለማየሁ ከተማ ጠቅላላ ሥራ ተቋራጭ በጉዳዩ ላይ ዝርዝር ምላሽ ሰጥቷል፡፡
የመስኖ ፕሮጀክቶቹን የተመለከተው የክዋኔ ኦዲት ግኝት ሙሉ መረጃ እንዳልደረሰው የገለጸው ተቋራጩ፣ ይህ ባልሆነበት ሁኔታ ስሙ አሉታዊ በሆነ መንገድ በመገናኛ ብዙኃን መነሳቱ ተገቢ አይደለም ብሏል።
ተቋራጩ አክሎም፣ የሁለቱም ፕሮጀክቶች የግንባታ ውል ‹‹የዋጋ ማስተካከያን አይፈቀድም››፣ እንዲሁም የውል ድንጋጌ ተጥሶ በተደጋጋሚ የውል ማሻሻያዎች ተፈጽመዋል መባሉ የተሳሳተ መረጃ ነው ሲል ተከራክሯል።
ይህንንም ሲያብራራ፣ በጨልጨል ግድብና ተያያዥ መዋቅሮች ግንባታ ፕሮጀክት ውል ላይ የዋጋ ማስተካከያ ክልከላ ድንጋጌ ፈፅሞ የሌለና የተፈቀደ ተግባር መሆኑን ገልጿል። ይህም የኦዲት ሪፖርቱ የፕሮጀክቱን ግንባታ ውል ይዘት በጥልቀት እንዳልዳሰሰ የሚያዝገነዝብ መሆኑን በመጥቀስ፣ ዋና ኦዲተሩ በዚህ ረገድ የደረሰበት ድምዳሜ ተቀባይነት የለውም ብሏል።
በወልመል የመስኖ ግንባታ ፕሮጀክት ውል ላይ ‹‹የዋጋ ማስተካከያ አይፈቀድም›› የሚል ድንጋጌ ቢኖርም፣ ከገንዘብ ሚኒስቴርና ከመንግሥት ግዥና ንብረት አስተዳደር ባለሥልጣን በተገኘው ይሁንታና የመመርያ አቅጣጫ መሠረት የፕሮጀክቱ አሠሪ በሆነው የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር አማካይነት በተሰጠው አቅጣጫ መሰጠቱንም አስረድቷል። በዚህም መሠረት በግንባታ የግብዓት ዕቃዎች፣ ነዳጅ፣ ማሽነሪዎች፣ ወዘተ ላይ የተከሰተውን ከፍተኛ የዋጋ ንረት ከግምት ውስጥ በማስገባት የውል ማሻሻያ መደረጉን ገልጿል።
‹‹የውል ማሻሻያው መመርያውን መሠረት በማድረግ ተፈጻሚ የሆነ ነው፡፡ ይህም የመንግሥትን ግልጽ መመርያ የተከተለና ሕጋዊ ተግባር ነው፤›› ብሏል፡፡ በመስኖ ፕሮጀክቶቹ ላይ ያልተገቡ የሥራ ለውጥ ትዕዛዞች ተፈጽመዋል ተብሎ በኦዲት ሪፖርቱ የተጠቀሰውን በተመለከተም ተቋራጩ ምላሽ ሰጥቷል።
‹‹የሥራ ለውጥ ትዕዛዞች በተለያዩ ምክንያቶች ተግባራዊ የሚደረጉ ሲሆን፣ ይህም በድርጅታችን አነሳሽነት የሚፈጸም አይደለም፡፡ እነዚህ የለውጥ ሥራዎች ተፈጻሚ የሆኑት በፀደቁ የዲዛይን ለውጦች [ተቋራጩ የፕሮጀክቱን ግንባታ ብቻ የሚሠራ ሲሆን፣ የዲዛይን ሥራ ተቋራጩን አይመለከትም፡፡ ተቋራጩ በሚሰጠው ዲዛይን መሠረት ነው ግንባታውን የሚከውነው]፣ የሥራ መጠን ለውጦች፣ ባልታሰቡ የምድር ውስጥ ሁኔታዎች (Geological Conditions)፣ የአለት ቁፋሮ ፍላጎቶች [ዋናው ውል የአፈር ቁፋሮ ሥራ ነው] እና በአሠሪው ሚኒስቴር መሥሪያ ቤት፣ በኢንጂነሩ፣ እንዲሁም በመንግሥት ግዥና ንብረት አስተዳደር ባለሥልጣን በፀደቁ ተጨማሪ የምሕንድስና ሥራዎች ምክንያት ነው። በዚህ አግባብ የተፈጸሙ የሥራ ለውጥ ትዕዛዝና ትግበራዎች ሕገ ወጥ ድርጊት አይደለም፤›› ብሏል።
ተቋራጩ የውል ዋጋ መጨመርን አስመልክቶ ለቀረበው የኦዲት ግኝት በሰጠው ምላሽም፣ በፕሮጀክቶቹ ላይ ማናቸውም የውል ዋጋ ጭማሪዎች ተግባራዊ የተደረጉት የፀደቁ የሥራ ለውጥ ትዕዛዞችን፣ ሕጋዊ የውል ማሻሻያዎችንና አስገዳጅ ምጣኔ ሀብታዊ ሁኔታዎችን መሠረት በማድረግ እንደሆነ የገለጸው ተቋራጩ ይህንንም ለማስረዳት ካጋጠሙ ሁኔታዎች መካከል አንዱን ጠቅሷል።
‹‹የወልመል ፕሮጀክት ውል በተፈረመበት ወቅት የአንድ ሊትር ነዳጅ ዋጋ 20.91 ብር ነበር። ሆኖም ፕሮጀክቱ በተጠናቀቀበት ወቅት የነዳጅ ዋጋ ወደ 107.93 ብር ከፍ በማለት በ516 በመቶ (ወይም በአምስት እጥፍ በላይ) ጨምሯል። ይህ ከፍተኛ የዋጋ ንረት በፕሮጀክቱ ወጪ ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ ያሳደረ ሲሆን፣ መንግሥትም ይህንን ኢኮኖሚያዊ ሁኔታ በመገንዘብ በግዥ (PPPA) መመርያና በመስኖና ቆላማ ልማት ሚኒስቴር የውል ማሻሻያ መመርያ መሠረት የዋጋ ማስተካከያ (Price Adjustment) እንዲተገበር ወስኗል፤›› ብሏል።
በመሆኑም የውል ዋጋ ማሻሻያዎች የተደረጉት በይፋ በፀደቁ የዋጋ ማስተካከያ አሠራሮች አማካይነትና ሕጋዊ ሒደቱን በመከተል በመሆኑ የቀረበው የኦዲት ግኝት ተቀባይነት ሊኖረው እንደማይችል ገልጿል።
በጨልጨል የመስኖ ፕሮጀክት ውል ውስጥ ያልተካተቱ ከ132 ሚሊዮን ብር በላይ የወጣባቸው ሦስት ቅንጡ ተሽከርካሪዎች ግዥ መፈጸሙን የሚጠቁመውን የኦዲት ግኝት አስመልክቶ በሰጠው ምላሽ፣ የተሽከርካሪዎቹ ግዥ የተፈጸመው ለፕሮጀክቱ የዕለት ተዕለት ሥራ የቅርብ ክትትል፣ ቁጥጥርና ድጋፍ የሚያገለግል ሲሆን፣ ለአሠሪው መሥሪያ ቤት (ባለቤት) መሐንዲሶችና ባለሙያዎች አገልግሎት እንዲሰጡ መገዛታቸውን ገልጿል።
‹‹ይህም የፕሮጀክቱን ቴክኒካዊ መሥፈርቶች ያማከለና በፀደቀው የውል ስምምነት መሠረት የቀረበና ሕግን ተከትሎ የተፈጸመ ነው። ከአገር ውስጥም ሆነ ከውጭ አገር ተቋራጮች ጋር በሚደረጉ ማናቸውም ታላላቅ የሲቪል ግንባታና የምሕንድስና (Mega Projects) ስምምነቶች ውስጥ፣ ለፕሮጀክቶች ክትትልና የሱፐርቪዥን ሥራ የሚያስፈልጉ ተሽከርካሪዎች በኮንትራት ስምምነቱ ውስጥ በልዩ ሁኔታ ተካተው እንዲቀርቡ ማድረግ የተለመደና ዓለም አቀፋዊ ደረጃውን የጠበቀ አሠራር ነው፤›› ብሏል።
በዚህ አሠራር መሠረት የተገዙት ተሽከርካሪዎች በፕሮጀክቱ ስም በጊዜያዊነት የሰሌዳ ቁጥራቸው በኮድ 3 (የድርጅት ሰሌዳ) ሆኖ እንደሚወጣ አገልግሎታቸውም በኮንትራት ስምምነቱ ላይ ለተቀመጠው የፕሮጀክት ክትትል ሥራ ብቻ መሆኑን የገለጸው ተቋራጩ፣ ግንባታው ወይም የኮንትራት ስምምነቱ ሲጠናቀቅና የፕሮጀክቱ ርክክብ ሲደረግ፣ ተሽከርካሪዎቹ ከኮድ 3 ወደ ኮድ 4 (የመንግሥት ሰሌዳ) ተቀይረው ሙሉ የባለቤትነት መብትና የንብረት አስተዳደር ሥርዓታቸው በቀጥታ ወደ አሠሪው የመንግሥት ተቋም እንደሚዞር አስረድቷል።
‹‹ይህ አሠራር በኢትዮጵያም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ በትላልቅ የመሠረተ ልማት ፕሮጀክቶች ላይ የሚሠራበት ሙሉ በሙሉ ሕጋዊና የተመሰከረለት አሠራር ነው፤›› ብሏል።
በተጨማሪም 75 ሚሊዮን ብር የፈጀ ሰባት የመስክ ተሽከርካሪዎች ግዥ የተጠናቀቀ የግንባታ ሥራ እንደሆነ በማስመሰል በተጭበረበረ ጊዜያዊ የክፍያ ማረጋገጫ በኩል ተፈጽሞ ለተቋራጩ ተጨማሪ ስድስት ሚሊዮን ብር ትርፍና የአገልግሎት ክፍያ እንዳስገኘ በሪፖርቱ ተጠቁሟል ቢባልም፣ ፍሬ ነገሩ ከእውነታው የራቀ ነው በማለት ሁኔታውን አስረድቷል።
በተቋራጩ ለተገነባው የወልመል መስኖ ፕሮጀክት የተገዛው የመስክ ተሽከርካሪ ብዛት ሁለት መሆናቸውንና እነዚህም ተሽከርካሪዎች በአሠሪው መሥሪያ ቤት እጅ እንደሚገኙ የገለጸው ዓለማየሁ ከተማ ጠቅላላ ሥራ ተቋራጭ፣ ከማንኛውም ንብረት ግዥ ያለአግባብ ያገኘው ጥቅም እንደሌለም ጠቅሷል።
ተቋራጩ አክሎም፣ ከማንኛውም ሕጋዊ፣ ገለልተኛና በማስረጃ ላይ ከተመሠረተ ምርመራ ጋር በተያያዘ ለመተባበር ሙሉ በሙሉ ዝግጁ መሆኑንና ተገቢውን ሰነድ ለሚመለከተው አካል ሁሉ ለማቅረብ ፈቃደኛ መሆኑን አስታውቋል።