- ግንኙነቱ በኢመደበኛ መንገድ እየተመራ መሆኑ ተገልጿል
የክልል መንግሥታት ግንኙነት የሚመራበት አዋጅ ከወጣ አምስት ዓመታት ቢሆነውም፣ ግንኙነቱ በኢመደበኛ መንገድ እየተመራ አዋጁ ግን ተግባራዊ አለመደረጉን የፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት በጥናቱ ማረጋገጡን አስታወቀ፡፡
‹‹የመንግሥታት ግንኙነት ተስፋዎች፣ መሰናክሎችና መፍትሔዎች›› በሚል ርዕስ ሰሞኑን ባካሄደው ውይይት፣ በኢትዮጵያ የመንግሥታት ግንኑነትን በተመለከተ የተደነገጉ ሕጎችና የፖሊሲ ማዕቀፎች፣ እንዲሁም የተቋማት አደረጃጀት መተግበር አለመቻሉንና ይህም ለግንኙነቱ ዋነኛ መሰናክል መሆኑ ተጠቁሟል፡፡
የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔን፣ የሰላም ሚኒስቴርና ሌሎች ተወካዮችን ጨምሮ በመድረኩ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ ተመራማሪዎችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል፡፡ የመንግሥታት ግንኙነትን በተመለከተ ጥናት ያቀረቡት ንጉሤ አፌሻ (ዶ/ር)፣ እ.ኤ.አ. በ2021 የመንግሥት ግንኙነትን ለመምራት የወጣው አዋጅና ሌሎች የክልሎቹን ግንኙነት ሕጋዊ ለማድረግ የወጡ ድንጋጌዎች ባለፉት አምስት ዓመታት መተግበር ባለመቻሉ፣ ወይም ባለበት በመቆሙ ግንኙነቱ ኢመደበኛ በሆነ መንገድ እየተመራ ነው ብለዋል፡፡
የክልሎችን ግንኙነት በአገር አቀፍ ደረጃ ለመምራት ቴክኒካዊና ሙያዊ ድጋፍ ለመስጠት ታስቦ የተቋቋመው አገራዊ የመንግሥታት ግንኙነት ሴክሬታሪያት በሥራ ላይ አለመሆኑን ገልጸዋል፡፡ በዚህ ምክንያት የክልል መንግሥታት ግንኙነትን የተመለከቱ የፖሊሲ ሪፎርሞችና ውይይቶች፣ እንዲሁም ቅንጅታዊ ተግባራት በሕጉ መሠረት መካሄዳቸው ቀርቶ በኢመደበኛ ወይም በከፊል መበደኛ ሥርዓት እየተካሄዱ ነው በማለት አስረድተዋል፡፡
ጥናቱ በጠንካራ የፖለቲካ ቁርጠኝነትና ተጠያቂነት ተቋማዊ ባለቤትነትን በማጠናከር የትብብር ፌዴራሊዝምን መገንባታ ያስፈልጋል እንደሚል ገልጸዋል፡፡ ይህ ዕርምጃ የተዋሀደ፣ ሰላማዊና ጠንካራ የፌዴራል ሥርዓትን ለመፍጠር የሚያግዝ ቁልፍ መሣሪያ ነው ያሉት አጥኝው፣ በዓለም ላይ የተሳካ ፌዴራሊዝም ሥርዓት ያላቸው አገሮች መሠረታቸው ጠንካራ የሆነው የመንግሥታት ግንኙነትን በጋራ ኃላፊነት በመምራትና ተጠያቂነትን በመዘርጋት ነው ብለዋል፡፡
በቀደመው የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲ ግንባር (ኢሕአዴግ) የሥልጣን ዘመን የመንግሥት ግንኙነት በከፍተኛ ሁኔታ በፓርቲ መዋቅርና በሚኒስትሮች መዋቅር መደበኛ በሆነ መንገድ ይመራ እንደነበር፣ ይህ ዓይነቱ አሠራር ትብብርን በማጠናከር የብቻ ውሳኔን ያስቀረ ነበር በማለት አስረድተዋል፡፡
የመንግሥታት ግንኙነት ሴክሬታሪያት በጠቅላይ ሚኒስትሩ ለሚመራው የብሔራዊ የሥራ አስፈጻሚዎች ግንኙነት ፎረም ተጠሪ ቢሆንም፣ ግንኙነቱ ደካማ ወይም መንቀሳቀስ የማይችልና በአዋጁ በሠፈሩት ድንጋጌዎች መሠረት የጎንዮሽ ግንኙነት፣ ከላይ ወደ ታች የሚደረጉ ግንኙነቶች፣ እንዲሁም የዘርፍ ፎረሞች ምንም ዓይነት እንቅስቃሴ እያደረጉ አይደለም ብለዋል፡፡
From The Reporter Magazine
በፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ተመራማሪ ሙሉጌታ ጌጡ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ በፌዴሬሽን ምክር ቤትና በክልል መንግሥታት መካከል ያለው ፎረም ባለበት የቆመ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ አልፎ አልፎ ቢካሄድ እንኳ በአዋጁ ድንጋጌ መሠረት ከተቀመጡት ስታንዳርዶች ውጪ በኢመደበኛ መንገድ እንደሚመራ ገልጸዋል፡፡
የትምህርት፣ የግብርና፣ የማዕድን፣ የመከላከያ፣ የሰላምና ደኅንነት ጉዳዮች ምንም እንኳ መደበኛ የሆነ የመንግሥታት ግንኙነት፣ የጋራ ዕቅድና ዝግጅት፣ እንዲሁም የውጤት ግምገማና የመረጃ ሥርጭት የሚያስፈልጋቸው ቢሆንም ከተቀመጠው ሕግ፣ መሠረታዊ ዕሳቤ፣ የፖሊሲ ጉዳዮች ስምምነትና የጋራ ውሳኔ ይልቅ የተለመዱ አስተዳደራዊ ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ ናቸው ሲሉም አስረድተዋል፡፡
ጥናቱ በኢመደበኛ ግንኙነቶች ወቅት አብዛኞቹ ግንኙነቶች በፌዴራል መንግሥት ሚኒስትሮች የበላይነትና አጀንዳ የሚመራ መሆኑን፣ በጊዜያዊ የኮሙዩኒኬሽን መስመሮች የተመሠረተ፣ ነገር ግን ግልጽነት፣ ተጠያቂነትና ቀጣይነት የሌለው ነው ይላል፡፡ በዚህም የተነሳ በርካታ ወሳኝ የሚባሉ የፖሊሲ፣ ጥንቃቄ የሚፈልጉ የፖለቲካ ጉዳዮችና ስምምነቶች በሕጉ ከተቀመጠው ድንጋጌና አሠራር ውጪ ባሉ መንገዶች መመራታቸውን ቀጥለዋል ሲልም ያስረዳል፡፡
From The Reporter Magazine
ይህ ዓይነቱ አካሄድ በመንግሥት ተቋማት የቅድሚያ አሰጣጥን፣ የፖለቲካ ቁርጠኝነትንና የትኩረት ማነስን የሚያሳይ ነው ያሉት ሙሉጌታ (ዶ/ር)፣ የመንግሥት ግንኙነት ጉዳይ አጣዳፊ በመሆኑ እየተፈጠሩ ያሉ አገራዊ ችግሮችን ለመፍታት ግንኙነቱን በሕግ መምራት ወሳኝ ነው በማለት አስረድተዋል፡፡
