ለፓርላማው በቀረበው የምግብ ሥርዓትና ሥርዓተ ምግብ ምክር ቤትን በሚያቋቁመው ረቂቅ አዋጅ፣ የመቀንጨር ችግር አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱ ተመላከተ፡፡
ከመቀንጨርና ከሥርዓተ ምግብ መዛባት ጋር የተያያዙ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች መጠን መጨመር በጤና፣ በትምህርት፣ በአካባቢያዊ፣ በምርታማነትና በማኅበራዊ መስተጋብር፣ እንዲሁም በአገር ኢኮኖሚ ላይ እያሳደረ ያለውን አሳሳቢ ችግር ለመቀነስና ለማጥፋት ያግዛል የተባለ ረቂቅ ሕግ ቀርቦ ውይይት እየተደረገበት ነው፡፡
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ግንቦት 27 ቀን 2018 ዓ.ም. ባካሄደው መደበኛ ስብሰባ፣ የምግብ ሥርዓትና ሥርዓተ ምግብ ረቂቅ አዋጅ ላይ ተወያይቶ ለዝርዝር ዕይታ ለጤና ማኅበራዊና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ መርቶታል፡፡ ረቂቅ አዋጁ ለምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተጠሪ የሆነ የምግብ ሥርዓትና ሥርዓተ ምግብ ምክር ቤት ያቋቁማል፡፡ ምክር ቤቱ የምግብ ሥርዓትና ሥርዓተ ምግብን በተመለከተ ከፈጻሚ ተቋማት የሚቀርብለትን አፈጻጸም በመገምገም አቅጣጫ የሚሰጥ መሆኑ ተገልጿል፡፡
የመቀንጨር ችግር አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱን የሚያስረዳው ረቂቁ፣ ሁኔታው በዚሁ ከቀጠለ፣ ዜጎች ለልዩ ልዩ የጤና ችግሮች ለሞት፣ ለፈጠራ ችሎታና ለትምህርት አቀባበል ውስንነት እንደሚዳርግ ተብራርቷል፡፡
በ2018 ዓ.ም. ይፋ በተደረገው የጤና ሥነ ሕዝብ ዳሰሳ ጥናት መሠረት፣ በኢትዮጵያ 40 በመቶ ወይም 6.6 ሚሊዮን ሕፃናት የቀነጨሩ መሆናቸውን፣ አምስት በመቶ የቀጨጩና 18 በመቶ ወይም ሦስት ሚሊዮን ደግሞ ክብደታቸው ከሚጠበቀው በታች መሆኑን ረቂቁ ያብራራል፡፡
በአሁኑ ወቀት በሥራ ላይ ከሚገኘው አዋቂ አምራች ኃይል 67 በመቶ ያህሉ፣ ዕድሜው ከአምስት ዓመት በታች በነበረበት ወቅት የቀነጨረ እንደነበረም ያስረዳል፡፡
የመቀንጨርና የመቀጨጭ ችግሮችን የሚያባብሱ በርካታ ምክንያቶች መኖራቸውን የሚያስረዳው ረቂቁ፣ ለዚህም የሕዝብ ዕድገት ከምርት ዕድገት ጋር አለመመጣጠን፣ ዝቅተኛ ምርትና ምርታማነት፣ ደኅንነቱና ጥራቱ ያልተጠበቀ የምርት አያያዝ ጉድለት፣ የድኅረ ምርት ብክነት፣ ከፍተኛ የጥቃቅን ንጥረ ምግቦች እጥረትን ይዘረዝራል፡፡
From The Reporter Magazine
የምግብ ሥርዓትና ሥርዓተ ምግብ ሥራዎችን በመቀናጀትና ወጥነት ባለው መንገድ ትኩረት ተሰጥቶት የሚመራበት የሕግ ማዕቀፍ ባለመኖሩ፣ ሥራው በየዘርፉና በየደረጃው ባሉ አመራሮችና ባለሙያዎች የግል ተነሳሽነት ብቻ እየተመራ መሆኑን ረቂቁ ያስረዳል፡፡
የምግብ ዋስትና ምንም እንኳ መንግሥት አቅሙ በፈቀደ መጠን የሚያሟላው መብት ቢሆንም፣ እንደ በሕይወት የመኖር መብት፣ ተዘዋውሮ የመሥራት መብትና ሌሎቹም መብቶች በመሆኑ፣ የዜጎችን መብቶች የሚያረጋግጡ ድንጋጌዎች በአዋጁ መካተት እንዳለባቸው ታምኖበት ተዘጋጅቷል ይላል፡፡
የምግብ ዋስትና ማግኘት ‹‹መንግሥት ለእያንዳንዱ ዜጋ ምግብ የማቅረብ ግዴታ አለበት ማለት አይደለም›› የሚለው ረቂቁ፣ ዜጎች ደኅንነቱ የተጠበቀ በቂና በንጥረ ነገር ለበለፀገ ምግብ፣ አካላዊና ኢኮኖሚያዊ ተደራሽነት እንዲኖራቸው የማረጋገጥ ኃላፊነት እንዳለበት የሚያስገነዝብ መሆኑ ተብራርቷል፡፡
From The Reporter Magazine
ምግብ የማግኘት መብትን በሚያብራራው ረቂቅ፣ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ የምግብና የሥርዓተ ምግብ ዋስትናው የመረጋገጥ፣ የሥርዓተ ምግብ አገልግሎት የማግኘት፣ ስለምግብ ሥርዓትና ሥርዓተ ምግብ መሠረታዊ ዕውቀትና ግንዛቤ የማግኘት መብት እንዳለው ተደንግጓል፡፡
