ከ1986 ዓ.ም. በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ የወጣው አዲሱ የኢነርጂ ፖሊሲ፣ የኃይል ማስተላለፊያና ማሠራጫ መስመሮችን በማስፋፋት በሚቀጥሉት አራት ዓመታት ውስጥ 78 በመቶ የሚሆነውን የኢትዮጵያ ሕዝብ፣ ከብሔራዊ የኃይል ቋት (National Grid) የኤሌክትሪክ ተጠቃሚ ለማድረግ ቅድሚያ ግብ መስጠቱ ታወቀ፡፡
የሚኒስትሮች ምክር ቤት ግንቦት 18 ቀን 2018 ዓ.ም. ያፀደቀውና ሪፖርተር የተመለከተው አዲሱ የኢነርጂ ፖሊሲ፣ 78 በመቶ የሚሆነውን ሕዝብ ከብሔራዊ የኃይል ቋት ተጠቃሚ ከማድረግ ባሻገር ቀሪውን 22 በመቶ እንደ የፀሐይ ኃይል የመሳሰሉ ቴክኖሎጂዎችን በማልማት ለገጠር ቤተሰብ፣ ለማኅበራዊ ተቋማትና ለኢኮኖሚ ዘርፎች አስተማማኝ የኤሌክትሪክ ኃይል ማድረስን ታሳቢ ያደረገ ነው፡፡
በአሁኑ ወቅት በተለያዩ አማራጮች የኤሌክትሪክ ኃይል ተጠቃሚ የሆነው ሕዝብ 65 በመቶ (29 በመቶ ከዋናው የኃይል ቋት፣ 36 በመቶ ደግሞ ከፀሐይ ኃይል) መሆኑንና ሥርጭቱ የተዛባ እንደሆነ ፖሊሲው ያስረዳል፡፡
የኤሌክትሪክ ቆጣሪ ያላቸው ደንበኞች ቁጥር ከ5.2 ሚሊዮን ወይም 22 በመቶ የማይበልጥ መሆኑን፣ ቀሪው ኅብረተሰብ በተዘዋዋሪ መንገድ የኤሌክትሪክ ቆጣሪ ካላቸው ገመድ ስቦ እንደሚጠቀም፣ አብዛኛው የገጠሩ ኅብረተሰብ ከፀሐይ ኃይል የሚገኝ ኢነርጂ የሚጠቀም መሆኑን፣ ዓመታዊው የነፍስ ወከፍ የኤሌክትሪክ ፍጆታ ከ236 ኪሎ ዋት ሰዓት እንደማይበልጥ፣ ከአፍሪካ አገሮች አማካይ (ከ600 ኪሎ ዋት ሰዓት በላይ) ጋር የኢትዮጵያ ሲነፃፀር በብዙ ርቀት ወደኋላ የቀረ መሆኑን ፖሊሲው ያመላክታል፡፡
በዓለም ላይ በአሁኑ ወቅት ኤሌክትሪክ ያልደረሰው ኅብረተሰብ ዘጠኝ በመቶ ወይም ከ750 ሚሊዮን የማይበልጥ መሆኑን፣ ከዚህ ውስጥ 600 ሚሊዮን ያህሉ ኤሌክትሪክ የሚያገኙ ኢትዮጵያን ጨምሮ ከሰሃራ በታች ባሉ አፍሪካ አገሮች ውስጥ በመሆኑ፣ በአገር ደረጃ የኤሌክትሪክ ተደራሽነትን ማፋጠን ወሳኝነት በፖሊሲው ተጠቅሷል፡፡
በልማት አጋሮች ድጋፍ የሚካሄዱ የኤሌክትሪክ መሠረተ ልማት ማስፋፊያና ማሻሻያ ፕሮግራሞች ከኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ብርሃን ተደራሽነትና የኤሌክትሪፊኬሽን ፕሮግራም ጋር ተዳምሮ፣ ከ200 በላይ የፀሐይ ኃይል ሚኒግሪድና ተጓዳኝ መሠረተ ልማቶችን በመዘርጋት ከ15 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ዜጎች ተጠቃሚ ይደረጋሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ በፖሊሲው ተብራርቷል።
በተጨማሪም የኃይል ዘርፉን የማሻሻልና የማዘመን ሥራ የሚያግዝ ፕሮግራም በመተግበር ለ72 ከተሞች የማሠራጫ መስመሮች በመገንባትና በማሻሻል፣ አስተማማኝና ጥራቱን የጠበቀ የኤሌክትሪክ አገልግሎት ማረጋገጥ ዋነኛ ግቦች ተደርገው በፖሊሲው ተካተዋል፡፡
From The Reporter Magazine
የአጭርና የመካከለኛ ጊዜ ፕሮግራሞችን የያዘ ፍኖተ ካርታ ተጠናቆ የኢንቨስትመንት ፕላን እንዲዘጋጅ መደረጉን የሚገልጸው ፖሊሲው፣ ፕሮግራሙ በዋነኛነት የተሻሻሉና ኢነርጂ ቆጣቢ ቴክኖሎጂዎችና የታዳሽ ኢነርጂ አማራጭ በማስፋፋት እ.ኤ.አ. በ2030. ብቻ ከ57 በመቶ በላይ የገጠር ቤተሰቦችን ተደራሽነትን ለማሳደግ ግብ አስቀምጧል።
በዚህም የባዮጋዝ ማብላያዎችን ግንባታና ሥርጭት ማስፋፋት፣ የክልል ኢነርጂ ቴክኖሎጂ ማበልፀጊያ ማዕከላት አቅምን ማሳደግ፣ በኢነርጂ ቴክኖሎጂ ምርምር ማድረግ፣ ቴክኖሎጂዎችን ማምረት፣ ማሠራጨትና ሌሎች ተግባራት ይጠበቃሉ ይላል፡፡
የኤሌክትሪክ ተቋማት በረጅም ጊዜ ሒደት ከገቢ ወጪ አንፃር ያጋጠማቸውን ከፍተኛ የብድር ጫና ለመቀነስ ወቅቱን የጠበቀና በጥናት ላይ የተመረኮዘ የታሪፍ ማሻሻያ ፕሮግራም ተግባራዊ እያደረጉ እንደሚገኝ፣ በዚህም በቀጣዮቹ ሁለት ዓመታት ወጪያቸውን መመለስ የሚችሉበት ታሪፍ ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ እንደሚያደርጉ በፖሊሲው ተካቷል፡፡ የተቋማቱን የአገልግሎት አሰጣጥና ገቢያቸውን ማሳደግ የሚያስችሉ የማሻሻያ ፕሮግራሞች ተዘጋጅተው እየተተገበሩ መሆናቸውን ፖሊሲው ይገልጻል።
From The Reporter Magazine
በዚህም የኤሌክትሪክ ታሪፍ ወጪን ያገናዘበ በየወቅቱ በግልጽ አሠራር እየተጠና ተግባራዊ እንዲሆን እንደሚደረግ፣ በዘርፉ ያለውን የጅምላ ታሪፍ ድጎማ በማስቀረት አቅም ለሌላቸውና ተጋላጭ ለሆኑ ዜጎች የድጎማ አሠራር እንደሚተገበር በፖሊሲው ተጠቅሷል።
የውኃና ኢነርጂ ሚኒስቴር፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት፣ የነዳጅና ኢነርጂ ባለሥልጣን፣ በኢትዮጵያ የዴንማርክ ኤምባሲና የኢነርጂ ስትረልሰን የጋራ ጥምረት ውጤት የሆነውና ከወራት በፊት ይፋ የሆነው ሁለተኛው የኢትዮጵያ ኢነርጂ ምልከታ 2025 (Ethiopian Energy Outlook 2025) ሪፖርት፣ እ.ኤ.አ. በ2028 በኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ አገልግሎት ታሪፍ ጭማሪ በትንሹ 400 ፐርሰንት እንደሚሆን መዘገባችን አይዘነጋም፡፡
የአነስተኛ ወጪ የኃይል ማስፋፊያ ዕቅድ እንዲዘጋጅ እንደሚደረግ፣ በዚህም የውኃ ኃይል ኢነርጂ ልማት ፕሮግራም ዋነኛው የኃይል መሠረት ሆኖ የንፋስ፣ የፀሐይ፣ የጂኦተርማል፣ የተፈጥሮ ጋዝና የባዮማስ ኢነርጂ ልማት እንደ አዋጭነታቸው በማስፋፋት የኃይል ስብጥሩን ለማሳደግ እንደሚሠራ ፖሊሲው ያስረዳል፡፡ የኃይል ስብጥሩን ለማሳደግ በርካታ የታዳሽ ኢነርጂ ምንጮች በግሉ ዘርፍ ተሳትፎ ወይም በመንግሥትና በግል አጋርነት እንደሚገነቡ በፖሊሲው ተካቷል።
በኢነርጂ ዘርፍ በርካታ የግል ባለሀብቶች እንዲገቡ ስለሚጠበቅ ከኃይል ማመንጨት በተጨማሪ፣ በማስተላለፊያ መስመር ዝርጋታና አስተዳደር እንዲሳተፉ አመቺ የሆነ የሕግ ማዕቀፍ እንዲኖር ማስቻል ከፖሊሲው እንደሚጠበቅ ተገልጿል።
በብሔራዊ የኃይል ቋት ውስጥ በኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጨትና ማስተላለፍ ሥራ፣ ከብሔራዊ ኃይል ቋት ውጪ ደግሞ በማሠራጨትና መሸጥ ሥራዎች የአገር ውስጥና የውጭ የግሉ ዘርፍና ሌሎች ባለድርሻ አካላት እንዲሳተፉ ማበረታቻዎችን በጥናት በመለየት ተግባራዊ እንደሚደረግ ፖሊሲው ያትታል፡፡
የአምራች ኢንዱስትሪዎችን የኃይል ፍላጎት መሠረት ያደረገ፣ የአገር ውስጥ ግብዓቶችን እንዲያመርቱና በከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ የሚገቡና ለኃይል ልማትና አቅርቦት የሚውሉ ግብዓቶችን የሚተኩ የምርትና አቅርቦት ሰንሰለቶች እንዲፈጠሩ ማድረግ ከፖሊሲው እንደሚጠበቅ ተመላክቷል።
አምራች ኢንዱስትሪዎች ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይልና ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ከሚያገኙት ኢነርጂ በተጨማሪ፣ የራሳቸውን ኢነርጂ እንዲያመነጩና የሚተርፋቸውን ለኃይል ቋት (Grid) እንዲሸጡ የሚያደርግ አሠራር መዘርጋት፣ የአምራች ኢንዱስትሪዎች የኃይል አቅርቦት ውጤታማና ብቃት ያለው እንዲሆን ኢነርጂ ቆጣቢ የሆኑ ቴክኖሎጂዎችን እንዲጠቀሙ እንደሚደረግ ፖሊሲው ያስረዳል።
ለኢነርጂ ዘርፍ ልማትና አቅርቦት የሚያስፈልጉ ባለሙያዎችን ማፍራት፣ የአጭርና የረጅም ጊዜ ሥልጠናዎችን መስጠት ከፖሊሲው ከሚጠበቁ ጉዳዮች መካከል ተጠቃሽ ሆነዋል።
ኢትዮጵያ ያላትን ከፍተኛ የታዳሽ ኢነርጂ ሀብት በማልማት ከጎረቤትና ከሌሎች የአፍሪካ አገሮች ጋር በኤሌክትሪክ ኃይል በመተሳሰር የውጭ ምንዛሪ ከማግኘትም ባለፈ፣ የአገሮቹን የእርስ በርስ ትብብር ለማጠናከር የጎላ ሚና ያለው በመሆኑ፣ የውጭ ግንኙነት ፖሊሲው የኢነርጂውን ዘርፍ ኢንቨስትመንት ከማሳደግ አኳያ ከፍተኛ ሚና ይኖረዋል ተብሎ እንደሚጠበቅ በፖሊሲው ተገልጿል።
ኢትዮጵያ የመጀመሪያውን የኢነርጂ ፖሊሲ በወቅቱ በነበረው የሽግግር መንግሥት የማዕድንና ኢነርጂ ሚኒስቴር አማካይነት በግንቦት 1986 ዓ.ም. አውጥታ፣ እስከ 2018 ዓ.ም. ድረስ ስትተገብር መቆየቷን አዲሱ ፖሊሲ ያስረዳል።
አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ ፖሊሲው በነባራዊ ሁኔታ ላይ ተመሥርቶ እየተገመገመ በየአምስት ዓመቱ እንደሚሻሻል ተገልጿል።
