- በተጭበረበረ ሰነድ የፖስፖርትና ሌሎች የጉዞ አገልግሎቶች ፈላጊዎች ቁጥር ጨምሯል ተብሏል
አዲሱን የኤሌክትሮኒክ ፓስፖርት በውጭ አገሮች ለሚገኙ ዜጎች በቆንስላ ጽሕፈት ቤቶች በኩል ከሐምሌ 15 ቀን 2018 ዓ.ም. ጀምሮ መስጠት እንደሚጀምር፣ የኢሚግሬሽን ዜግነት አገልግሎት ገለጸ፡፡
አገልግሎቱ ይህን ያስታወቀው የ2018 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸሙን በተመለከተ ሐምሌ 9 ቀን 2018 ዓ.ም. በሰጠው መግለጫ ነው። መግለጫውን የሰጡት የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር (ወ/ሮ) ሰላማዊት ዳዊት፣ ተቋሙ አዲሱን የኤሌክትሮኒክ ፓስፖርት በአገር ውስጥ በአዲስ አበባ ከዋና መሥሪያ ቤት ጀምሮ በክልሎች በሚገኙ 23 ቅርንጫፎቹ፣ እንዲሁም በ14 የመሶብ አንድ መስኮት አገልግሎት መስጫ ማዕከላት እየሰጠ መሆኑን ተናግረዋል።
ይህንን አገልግሎት በተለያዩ የውጭ አገሮች ለሚኖሩ ዜጎች ለመስጠት ዝግጅት ሲደረግ መቆየቱን፣ ከሐምሌ 15 ቀን 2018 ዓ.ም. ጀምሮ ደግሞ የኢትዮጵያ ቆንስላ ጽሕፈት ቤቶች በሚገኙባቸው የውጭ አገሮች መሰጠት እንደሚጀመር አስታውቀዋል። በእነዚህ አገሮች የሚገኙ ዜጎች የተቋሙ አዲሱን ድረ ገጽ (www.immigration.gov.et) በመጠቀም የኤሌክትሮኒክ ፓስፖርት አገልግሎት ማግኘት ይችላሉ ብለዋል።
በመሆኑም ቆንስላ ጽሕፈት ቤቶች ባሉባቸው የውጭ አገሮች የሚገኙና የኤሌክትሮኒክ ፓስፖርት የሚፈልጉ ዜጎች በአዲሱ የተቋሙ ድረ ገጽ በማመልከት አገልግሎቱን ማግኘት እንደሚችሉ ገልጸዋል።
የተጭበረበረ ሰነድ በመጠቀም የፖስፖርትና ሌሎች የጉዞ አገልግሎቶችን ለማግኘት የሚመጡ ዜጎች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መሆኑን ዋና ዳይሬክተሯ ተናግረዋል። ይህ ደግሞ ትክክለኛ ሰነዶችን ከየት ማገኘት እንደሚቻል ካለማወቅ የሚመነጭ ሆኖ በመገኘቱ፣ ዜጎች በአግባቡ ከሚመለከታቸው ተቋማት ብቻ ማስረጃዎቻቸውን በመውሰድ ለሚፈልጉት አገልግሎት ጥያቄ ማቅረብ እንደሚኖርባቸው አሳስበዋል።
ዋና ዳይሬክተሯ በመግለጫቸው፣ የቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቶችን ብዛት ከ12 ወደ 23 በማሳደግ በሁሉም የፓስፖርት አገልግሎት እየተሰጠ እንደሚገኝ ጨምረው ተናግረዋል። ተቋሙ ያበለፀገውን አዲስ ሲስተም ሙሉ ለሙሉ ወደ ሥራ ማስገባት መቻሉ እንደ ስኬት ይወሰዳል ብለዋል።
ተቋሙ በሐምሌ ወር 2015 ዓ.ም. ሪፎርም ከጀመረ በኋላ ስኬቶችን እያስመዘገበ እንደሚገኝ፣ ለአብነት ባለፉት አራት ዓመታት የተሰጠው ፓስፖርት ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ መጨመሩን ተናግረዋል። በ2015 ዓ.ም. 268 ሺሕ፣ በ2016 ዓ.ም. 1.06 ሚሊዮን፣ በ2017 ዓ.ም. 1.44 ሚሊዮን፣ በ2018 ዓ.ም. 1.63 ሚሊዮን፣ በአጠቃላይ ከአራት ሚሊዮን በላይ ፓስፖርቶች ለዜጎች መሰጠታቸውን አብራርተዋል።
From The Reporter Magazine
የተቋሙ ገቢ ማደጉን ዋና ዳይሬከተሯ በመግለጫው ወቅት ተናግረዋል። በዚህም በ2015 ዓ.ም. 4.3 ቢሊዮን ብር፣ በ2016 ዓ.ም. 14.7 ቢሊዮን ብር፣ በ2017 ዓ.ም. 34.07 ቢሊዮን ብር፣ በ2018 ዓ.ም. 42.7 ቢሊዮን ብር፣ በአጠቃላይ ከ95 ቢሊዮን ብር በላይ መድረሱን ዋና ዳይሬክተሯ አክለዋል።
ለውጭ ዜጎች የሚሰጥ አገልግሎት በ2016 ዓ.ም. ከነበረበት 369 ሺሕ፣ በ2018 ዓ.ም. ወደ 1.2 ሚሊዮን፣ የድንበር አገልግሎት (ከትራንዚት ውጪ) ከ3.9 ሚሊዮን ወደ 7.22 ሚሊዮን ማደጉንም ገልጸዋል። ዋና ዳይሬክተሯ እንደተናገሩት፣ የቁጥጥር ሥራዎች ከአራት ሺሕ ወደ 47 ሺሕ ገደማ፣ የተገልጋዮች እርካታ ደግሞ ከ32 በመቶ ወደ 81.9 በመቶ ደርሷል።
አገልግሎቱ የጀመራቸውን የሪፎርም ሥራዎች አጠናክሮ በመቀጠል፣ በ2019 በጀት ዓመት የተሻለ አፈጻጸም ለማስመዝገብ ዕቅድ መፅደቁን የተቋሙ መረጃ ያሳያል።