በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የግብርና ዘርፍን የሚመርጡ ተማሪዎች ቁጥር እየቀነሰ በበመሆኑ፣ በትምህርት ሥርዓተ ትምህርት ውስጥ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እንዲሠራበት የዘርፉ ምሁራን ጥሪ አቀረቡ፡፡
ምሁራን ጥሪውን ያቀረቡት የኢትዮጵያ ሳይንስ አካዴሚ ‹‹የኢትዮጵያ የገጠር ትራንስፎርሜሽን ትልሞች ወደ መዋቅራዊ ሽግግር መግቢያ›› በሚል ርዕስ ሚያዝያ 29 ቀን 2018 ዓ.ም. የገለጻና ውይይት መርሐ ግብር ሲካሄድ ነው።
በውይይቱ ተሳታፊ የነበሩት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባሉና የግብርና ተመራማሪው ከፈና ኢፋ (ዶ/ር)፣ ግብርና በትምህርት ሥርዓቱ ውስጥ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ አጽንኦት ሰጥተዋል። እንደ ከፈና (ዶ/ር) ገለጻ፣ የግብርና ትምህርት በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ በተማሪዎች የሚመረጥ ዘርፍ መሆኑ እየቀረ፣ ውስን ቁጥር ያላቸው ተማሪዎች ብቻ እየገቡበት ይገኛል። የማስተርስ ፕሮግራሞች ሁሉ በተማሪዎች እየተመረጡ ባለመሆኑ ዲፓርትመንቶቹ እየተዘጉ መሆኑን እየሰማን ነው፣ ይህም ወደፊት በዘርፉ በቂ የሰው ኃይል እንዳይኖር ያደርጋል፣ ስለሆነው ልዩ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል ብለዋል፡፡
በተለይ በዘርፉ የሚሠሩ ከፍተኛ ልምድ ያላቸው ባለሙያዎች ፍልሰት ሌላኛው ችግር መሆኑንም ጠቅሰዋል። በመሆኑ በዘርፉ የተቀመጡ የአሥርና የ20 ዓመት ዕቅዶች እንዴት ማሳካት ይቻላል? የሚለው አብሮ መታሰብ እንደሚኖርበት ጠቁመዋል።
የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ሠራተኛ የሆኑት አምቢሳ ሙለታ፣ የሰው ኃይል ሲነሳ መነሻው የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መሆናቸውን፣ አሁን እየተማረ ያለው ተማሪ ብዛት ደግሞ አገራዊ ዘላቂ የልማት ግቦች እውን ለማድረግ ያስችላል ብለው እንደማያስቡ ጠቁመዋል። ከዚህ አንጻር በአሁኑ ወቅት እየተቀረፁ ያሉ አገራዊ ዘላቂ የልማት ግቦች እውን ይደራጋሉ ተብሎ ሲታሰብ፣ የትምህርት ሥርዓቱ በዚህ ልክ የተቃኘ መሆን እንዳለበት ገልጸዋል።
በዚሁ ረገድ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጋር የሚሠሩ ሥራዎች ትኩረት ሊሰጣቸው እንደሚገባ፣ እንደ ሌሎች ዘርፎች አጫጭር ሥልጠናዎች የሚሰጡበት ሁኔታ መታሰብ እንዳለበት ጨምረው ተናግረዋል።
‹‹የኢትዮጵያ የገጠር ትራንስፎርሜሽን ትልሞች ወደ መዋቅራዊ ሽግግር መግቢያ›› በሚል ርዕስ ገለጻ ያደረጉት የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሤ (ዶ/ር)፣ ትምህርት ላይ የተነሳው ጥያቄ የሳቸው ጥያቄ መሆኑን፣ ኢኮኖሚው የሚፈልገዉን የሰው ኃይል አብሮ እያሳደጉ መሄድ እንደሚገባና ዩኒቨርስቲዎች ላይ ቁጥሩን ከመገደብ ይልቅ ከታች ጀምሮ መሥራት እንደሚገ አስረድተዋል።
From The Reporter Magazine
የሰው ልጅ ጥቅማ ጥቅም እንደሚፈልግ፣ ይህንን ከፖሊሲ አውጪዎች ጋር በመመካከር ማስተካከል እንደሚገባ አስረድተዋል።
ማንደፍሮ (ዶ/ር) ባደረጉት ገለጻ፣ የገጠር ትራንስፎርሜሽን የግብርና ምርታማነትን መጨመር፣ የንግድ ልውውጥ፣ የአመራር ዘይቤዎች መተዳደሪያዎች መስፋፋትን እንደሚያካትት ጠቁመዋል። ከግብርና ውጪ የተስፋፋ የሥራ ሥምሪት፣ የሥራ ፈጥራ ዕድሎች የተሻለ የአገልግሎትና የመሠረተ ልማት ተደራሽነትን እንደሚያካትት ጠቁመዋል።
ከዚሁ በተጨማሪ፣ የተቀናጀ የገጠር መሠረተ ልማቶችና አገልግሎቶች እንዲስፋፉ፣ ግብርናን ክሌሎች ኢኮኖሚ ዘርፎች ጋር እንዲተሳሰር፣ በገጠር ከግብርና ውጭ ያሉ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎችና የከተማና ገጠር ትስስርን እንዲጠናክረ እንደሚረዳ አስረድተዋል።
From The Reporter Magazine
በዚህም እንደ አገር እየተሠሩ ባሉ ሥራዎች፣ ግብርናን ለቤተሰብ ፍጆታና በማደግ ላይ ግብርና ካለ ሒደት ወደ ሌሎች ዘርፎች አስተዋጽኦ ማድረግ፣ ግብርና ወይም ከ50 በመቶ እስከ 70 በመቶ ለገበያ ማምረት ደረጃ ላይ መደረሱን ጠቁመዋል። ከማክሮ ኢኮኖሚ ጋር የተቀናጀ ግብርናና የኢንዱስትሪ ኢኮኖሚ አካል የማድረግ ሒደት ወይም ከ75 በመቶ በላይ የማምረት አቅም ለመፍጠር እየተሠራ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።
ለዚህም ሰላምን ለማስፈንና ግጭቶችን ለመቀነስ ልማትን ማጠናከር እንደሚገባ፣ ይህን ለማድረግም የሰብዓዊ፣ ልማት፣ የሰላም ግንባታ ጥረቶች ፕሮጀክት እየተተገበረ እንደሚገኝም ተናግረዋል።
በተለይ ለዘርፉ አንዱ ተግዳሮት የሆነውን የፋይናንስ ችግር ለመፍታት የግብርና ባንክ ማቋቋም፣ ብሔራዊ የግብርና ፋይናንስ ፍኖተ ካርታ ትግበራ ላይ መሥራት፣ በክላስተር ግብርና የታቀፉ አርሶ አደሮችን የመበደር አቅም ማሳደግ፣ አዳዲስ የፋይናንስ መሳሪዎች (የእሴት ሰንሰለት ፋይናንስ፣ የተቀናበረ ፋይናንስ) መጠቀም የሚያስችሉ ንቅናቄዎችን ተግባራዊ ማድረግ እንደሚገባ ጠቁመዋል። በዚሁ ረገድ የግሉ ዘርፍ በገጠር አካባቢ ኢንቨስት እንዲያደርግ ሥራ እንደሚጠይቅ ጠቁመዋል።
ለአብነት ኢትዮጵያ 57 ሚሊዮን ኩታል ለሚሆን ምርት ማከማቻ መጋዘን የሚያስፈልጋት ሲሆን፣ አሁን ያላት 27 ሚሊዮን ኩንታል እህል ማከማቸውት የሚያስችል ብቻ በመሆኑና ባለሀብቶች እዚህ ጋር ኢንቨስት ማድረግ እንደሚቹሉ ገልጸዋል።
እነዚህ የልማት ጥረቶች አየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን የሚቀንሱ ወይም ተፅዕኖውን የሚቋቋሙ እንደሚደረጉም ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ሳይንስ አካዴሚ ወቅታዊና አገራዊ ፋይዳ ባላቸው ጉዳዮች ላይ ሳይንሳዊ ውይይቶችን የማካሄድ ተልዕኮ እንዳለው ይታወቃል።
