
የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ባለሥልጣን በዓለም አቀፍ መመዘኛዎች መሠረት፣ ሽብርተኝነትን በገንዘብ በመደገፍ ለሥጋት ተጋላጭ ናቸው ተብለው የተለዩ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ላይ ክትትል እንደሚያደርግ አስታወቀ፡፡
የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ድጋፍ የሚያገኙት ከፍተኛ ሥጋት ተብለው ከተለዩ አካባቢዎች ከሆነ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚሠሩበት አካባቢ ግጭት ያለበት ከሆነና ድንበር አካባቢ የሚገኝ ወይም በተለያዩ መመዘኛዎች ከሽብርተኝነት ጋር የተያያዘ ጉዳይ ይኖራል ተብሎ የሚገመት ከሆነ፣ ክትትል እንደሚደረግ፣ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ባለሥልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ፋሲካው ሞላ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
ድርጅቶቹ በዓለም አቀፍ መመዘኛ መሠረት የሚያገኙት የገንዘብ ድጋፍ ከፍተኛ በሆነ መጠን ሥጋቱም ይጨምራል ተብሎ ስለሚገመት፣ ክትትሉ እንደሚከናወንና ነገር ግን፣ ‹‹ሁሉም የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ሽብርተኝነትን በገንዘብ የመደገፋቸው ሥጋት ውስን በመሆኑ ተጋላጭነታቸውም በጣም አነስተኛ ነው፤›› ብለዋል፡፡
የክትትል ሥራ የሚከናወነው በሁሉም የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ላይ እንዳልሆነ፣ ሽብርተኝነትን በገንዘብ የሚደግፉ ድርጅቶች ተገኝተው ሳይሆን ተጋላጭ ሊሆኑ ይችላሉ የሚባሉት በመለየታቸው እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ ‹‹ባለሥልጣኑ የጥንቃቄ ዕርምጃ እየወሰደ ነው፤›› ያሉት ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ፣ በመሥፈርቱ መሠረት ተጋላጭ ይሆናሉ ተብለው ለተለዩ ድርጅቶች ግንዛቤ ከማስጨበጥ ጀምሮ የክትትልና የቁጥጥር ሥራ እንደሚከናወን አስረድተዋል፡፡
‹‹አንዳንድ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ሳያውቁም የሌሎች መጠቀሚያ ሊሆኑ ይችላሉ፤›› ብለው፣ ራሳቸውን ከዚህ ድርጊት እንዲከላከሉ የሚያደርግ ሥልጠና እንደሚሰጥ፣ ነገር ግን እስካሁን በዚህ ድርጅት ውስጥ ተሰማርቶ የተገኘ ድርጅት የለም ብለዋል፡፡
ድርጊቱን ለመከላከል በዓለም አቀፍ ደረጃ የተለያዩ ስምምነቶችና ተቋማት መኖራቸውን፣ ኢትዮጵያም የተቋማቱ አባል በመሆኗ ዓለም አቀፍ ግዴታ ጭምር እንዳለባት አስረድተዋል፡፡ በሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች አዋጅ ቁጥር 1113/2011 ለባለሥልጣኑ የተሰጠው አንደኛው ሥልጣንና ኃላፊነት ሽብርተኝነትን በገንዘብ መርዳት፣ እንዲሁም በሕገወጥ መንገድ የተገኘ ገንዘብን ሕጋዊ አስመስሎ ማቅረብን መከላከል መሆኑንና ሥራውንም ከሚመለከታቸው ተቋማት ጋር በመተባበር ማከናወን እንዳለበት መደንገጉን አስታውሰዋል፡፡
ባለሥልጣኑ በዋናነት ኃላፊነት ተሰጥቶት ከሚሠራው የፋይናንስ ደኅንነት አገልግሎት ጋር በትብብር እንደሚሠራና ዋናው ሥራ በጋራ ክትትል ማድረግና መረጃዎችን መለዋወጥ መሆኑን፣ ከዚህ ቀደም የፋይናንስ ደኅንነት አገልግሎት እያስተባበረ ከተለያዩ ተቋማት ጋር በመቀናጀት አገር አቀፍ ሥጋት ላይ የተመሠረተ ቁጥጥር መደረጉን ገልጸዋል፡፡
From The Reporter Magazine
ከዚህ ጋር ተያይዞ የፋይናንስ ደኅንነት አገልግሎት ሁለት ዋና ዋና የሥጋት ምንጮችን መሠረት ያደረገ የቁጥጥር ሥርዓት መመርያ ሰሞኑን ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ የሥጋት ምንጮች ተብለው የተጠቀሱትም የድርጅቶቹ የገንዘብ ዝውውር፣ አሸባሪ ተብለው ከተለዩ ድርጅቶች ጋር ይኖራቸዋል ተብሎ የሚገመት ግንኙነት ወይም ፕሮግራሞቻቸውን ያላግባብ የመጠቀም ሥጋት፣ እንዲሁም በተፈጥሮ ያላቸው ተጋላጭነት ማለትም የድርጅቶቹ አወቃቀርና ገንዘብ የሚያስተላልፉበት ዘዴ እንደሆነ መመርያው ያስረዳል፡፡
በአጠቃላይ ግምገማው የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ከመካከለኛ እስከ ዝቅተኛ መጠን ያላቸውን ተጋላጭነት የተመለከተ መሆኑንና በዚህ ድርጊት ተሳትፎ የሚያውቅ ድርጅት እንደሌለ፣ ነገር ግን አጠራጣሪ በሆነ የፋይናንስ እንቅስቃሴ ላይ በርካታ ምርመራዎች እየተካሄዱ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
ምንም እንኳን የቁጥጥር ሥርዓቱ የተከናወነው እ.ኤ.አ. በ2024 ቢሆንም፣ አገልግሎቱ መረጃውን ይፋ ያደረገው ሰሞኑን ነው፡፡ በአገሪቱ የነበሩ የፀጥታ ችግሮች በተለይም በሰሜኑ ጦርነት ወቅት በአሸባሪነት ተፈርጆ የነበረውን ሕውሓትንና አልሸባብን በሚመለከት ከፍተኛ ቁጥጥር መደረጉ ተገልጿል፡፡
From The Reporter Magazine
የፋይናንስ ደኅንነት አገልግሎት በኦሮሚያ፣ በሶማሌና በሐረሪ ክልሎች የሚንቀሳቀሱ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶችን በሚመለከት አጠራጣሪ የገንዘብ ዝውውሮች መኖራቸውን ተመልክቶ እንደነበር፣ እ.ኤ.አ. በ2025 ከሲቪል ማኅበረሰብ ደርጅቶች ባለሥልጣን ጋር ባደረገው የመግባቢያ ስምምነት ወቅታዊ መረጃዎችን መለዋወጥ መቻላቸው በመመርያው ተመላክቷል፡፡ የመግባቢያ ስምምነቱ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ራሳቸውን እንዲቆጣጠሩ የሚያግዝ ነው ተብሏል፡፡
በወዲያኛው ሳምንት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሕግና ፍትሕ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ፣ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ባለሥልጣንን የ2018 ዓ.ም. የዘጠኝ ወራት የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት መገምገሙ ይታወሳል፡፡
በፊት ለፊት የግምገማ መድረክ የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ወ/ሮ ዕፀገነት መንግሥቱ በምዝገባ ሒደት ባለሥልጣኑ መከተል ያለበትን ጥንቃቄ ሲያብራሩ፣ ምንም እንኳን የዴሞክራሲ ምኅዳር እንዲሰፋ ቢደረግም ሁሉም ድርጅት ጤነኛ አስተሳሰብ ይዞ ስለማይቀርብ የማጣራትና ጥንቃቄ የማድረግ ሥራ ማከናወን እንደሚገባ ማሳሰባቸው ይታወሳል፡፡
ጥንቃቄውም የውጭ ድርጅቶችን ብቻ የሚመለከት ሳይሆን አገር በቀል ድርጅቶችም ከተቋቋሙበት ዓላማ ውጪ በመሆን አገርን የሚያፈርስና የጋራ አንድነት የሚሸረሽር ሥራ እንዳያከናውኑ፣ ፈቃድ ከመሰጠቱ በፊትና በሥራ ሒደት በመፈተሽ መፍትሔ መስጠት አስፈላጊ መሆኑን ገልጸው ነበር፡፡