በትግራይና በአፋር ክልሎች በሰብዓዊ መብትና በዴሞክራሲ ግንባታ ላይ ትኩረት አድርገው የሚሠሩ 50 የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች የሚሳተፉበት፣ የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነትን የሚያጠናክር ፕሮጀክት በይፋ ተጀመረ፡፡
የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብቶች ድርጅቶች ኅብረት (ኢሰመድኅ) በትግራይና በአፋር ክልሎች፣ በሰብዓዊ መብትና በዴሞክራሲ ግንባታ ላይ የተሰማሩ የሲቪል ማኀበረሰብ ድርጅቶችን ያሳተፈ ፕሮጀክት ዓርብ ሰኔ 12 ቀን 2018 ዓ.ም. በይፋ አስጀምሯል፡፡
የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኅብረት ዳይሬክተር አቶ መሱድ ገበየሁ ትግራይና አፋር ክልሎች ለፕሮጀክቱ የተመረጡበትን ምክንያት ለሪፖርተር ሲያስረዱ፣ እንደ ማንኛውም ፕሮጀክት የፍላጎት ዳሰሳ በማከናወን መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም ከዚህ ቀደም በሁለቱ ክልሎች ሲሠሯቸው የነበሩ ፕሮጀክቶች እንደነበሩ፣ አንዱ ክፍተት ሆኖ ያገኙት በሰብዓዊ መብት፣ በዴሞክራሲና በተጠያቂነት ጉዳዮች ላይ በጋራ መሥራት መሆኑን አስረድተዋል፡፡
የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች የሚሰጡት ሐሳብ በክልሎቹ እንደ ጠቃሚ አለመወሰዳቸው በክፍተትነት መታየቱንና ይህ ልምድ ካልመጣም በግጭት፣ በአየር ንብረት ወይም በተለያዩ ምክንያቶች ለሚፈጠሩ ችግሮችን መፍትሔ ማምጣት ስለማይቻል የምክክር ባህል ማዳበር እንደሚገባ በማመን መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ኅብረቱ አሁን ባለው አቅም ከሁለት ክልሎች በላይ መሥራት እንደማይችልም ጠቁመዋል፡፡
በአፋር ክልል 20፣ በትግራይ ክልል ደግሞ 30 በአጠቃላይ 50 በሰብዓዊ መብትና በዴሞክራሲ ግንባታ ላይ ትኩረት አድርገው የሚሠሩ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶችን ማካተታቸውን፣ በመንግሥት በኩል ደግሞ በሁለቱም ክልሎች 12 ተቋማት ላይ ትኩረት መደረጉን ተናግረዋል፡፡
በፕሮጀክቱ መብት ተኮር ፖሊሲዎች የሚወጡበት፣ ተግባራዊ የሚደረጉበትና የሚገመገሙበት ሒደትን በሚመለከት ለመንግሥት ተቋማት ራሱን የቻለ የአቅም ግንባታ እንደሚሰጥ ገልጸዋል፡፡
‹‹ዜጎችን በሚመለከት ያለ ማንም ጣልቃ ገብነት መብታቸውን ሊጠይቁ ስለሚችሉበት ሁኔታ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎችን ትኩረት አድርገው እንደሚሠሩ ይጠበቃል፤›› ብለዋል፡፡
From The Reporter Magazine
በፕሮጀክት ማስጀመሪያ መርሐ ግብሩ ላይ የተገኙት የኢትዮጵያ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ባለሥልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ፋሰካው ሞላ፣ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ትልቁ ሚና አገር ግንባታ መሆኑንና በዴሞክራሲ ግንባታ ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከት እንደሚጠበቅባቸው ገልጸዋል፡፡
የሕግ ማሻሻያዎች ሲደረጉም ትኩረት የተሰጠው በዴሞክራሲ፣ በሰብዓዊ መብትና በሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ላይ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ አገር በቀል የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ጋር በተያያዘ ከለውጡ በፊት የውጭ ድርጅቶች ድጋፍ እያገኙ የሰብዓዊ መብት፣ የዴሞክራሲና ሌሎች ተመሳሳይ ጉዳዮች ላይ ለመሥራት ተከልክለው እንደነበር አስታውሰዋል፡፡
‹‹የዴሞክራሲ ጉዳይ እንደ አገር የሚፈትነን መሆኑ ይታወቃል፤›› ብለው፣ ‹‹ነገር ግን ወደኋላ መለስ ብለን ስናስተውል ዜጎች የሚያነሷቸው ጥያቄዎች በብዙ መንገድ መልስ ያገኙ ናቸው፤›› በማለት አስረድተዋል፡፡
From The Reporter Magazine
ነገር ግን ከነፃነት፣ ከእኩልነትና ከዴሞክራሲ ጋር በተያያዘ ያለው ጥያቄ ብዙ ያልተነካ መሆኑንና በለውጡ ዓመታትም የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶችና ሌሎች አካላት በዚህ ዘርፍ በጋራ በመሥራት ውጤት ማምጣት ይገባል በማለት እየተሠራ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
በሌላ በኩል ለሰብዓዊ መብትና ለዴሞክራሲ መርሆዎች መከበር የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ራሳቸው ምሳሌ መሆን እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡ ከዚህ አኳያ ምንም እንኳን ፕሮጀክቱ በሁለት ክልሎች ብቻ የሚተገበር ቢሆንም አስተዋጽኦ ያበረክታል የሚል እምነት እንዳላቸው ተናግረዋል፡፡
በትግራይ ክልል የሲቪል ማኅበራት ጥምረት ዳይሬክተር ይካዕሎ ወሉ (ዶ/ር) በትግራይ ክልል ያለው ሁኔታ ከፖለቲካ አኳያ ጭምር የተበታተነ መሆኑን ለሪፖርተር ገልጸው፣ ሆኖም ለሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች የዕለት ተዕለት ሥራቸውን ለማከናወን የሚያግድ ነው ብለው እንደማያምኑ አስረድተዋል፡፡
ለዚህ ማሳያ አድርገው ያቀረቡትም በክልሉ 185 ፕሮጀክቶች በሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች እየተከናወኑ መሆናቸውን ሲሆን፣ ከአምናው ዘንድሮ የተለየ ነገር እንደሌለ፣ ነገር ግን ዕርዳታ የሚያቀርቡ ድርጅቶች ግምት የተለየ ስለሆነ ወደ ክልሉ ላይመጡ እንደሚችሉ አስረድተዋል፡፡
የፌዴራል መንግሥት አስቸኳይ የሰብዓዊ ዕርዳታ ከሰኔ 30 ቀን 2018 ዓ.ም. ጀምሮ አቋርጣለሁ ማለቱን ገልጸው፣ በትግራይ ክልል ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ተፈናቃዮች በመኖራቸው ከሌሎች ክልሎች የተለየ መሆኑን ከግምት ውስጥ ማስገባት እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በክልሉ በሚንቀሳቀሱ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶችና የመንግሥት ተቋማት መካከል መተባበር መኖሩን፣ በክልሉ የሚወጡ ሕጎች በረቂቅ ደረጃ እያሉ ጭምር የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ተመልክተው አስተያየት እንዲሰጡበት እንደሚደረግ በአፋር ክልል ፍትሕ ቢሮ የሕግ ማርቀቅ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ሙሳ ያሲን ገልጸዋል፡፡
ክልሉ ከፌዴራሉ ጋር የሚጣጣም የራሱን የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች አዋጅ በቅርቡ ማውጣቱን፣ በመንግሥትና በሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች መካከል ያለው አብሮ የመሥራት ልምድም እየዳበረ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
