- ለጥቅል አገራዊ ምርት ያለው አስተዋጽኦ ስድስት በመቶ መድረሱ ተገልጿል

የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ከተመሠረተበት እ.ኤ.አ. 2010 ጀምሮ ወደ ሁለት ቢሊዮን ዶላር የሚጠጋ ሀብት ለአገራዊ ኢኮኖሚ አበርክቻለሁ አለ።
ኢንስቲትዩቱ የግብርናው ዘርፍ የተደቀነበትን የተለምዶ አስተራረስ ዘዴ በመቀየር፣ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ዘመናዊ ግብርናን በቀድሞው አደረጃጀት በአራት ክልሎች የጀመረውን ተልዕኮ፣ አሁን ወደ ዘጠኝ ክልሎች በማሳደግ የግብርናውን ዘርፍ ወደ ኢንዱስትሪ ለማሸጋገር እየሠራ መሆኑን የገለጹት የኢንስቲትዩቱ የኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተር ብሩክታዊት እጅጉ (ዶ/ር) ናቸው።
ከተቋቋመት ወዲህ በዘጠኝ ክልሎች 500 ሠራተኞችን በመያዝ በዘርፉ 400 ጥናቶችን በማካሄድ ከ70 በላይ ፕሮጀክቶችን መተግበሩን የገለጹት የኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተሯ፣ ኢንስቲትዩቱ በግብርናው ዘርፍ ለ600 ሺሕ ዜጎች የሥራ ዕድል የተፈጠረበት ‹‹አደይ›› የተሰኘ ፕሮግራም ማስተዋወቁን ገልጸዋል፡፡
ኢንስቲትዩቱ በዋነኝነት በመሬት አስተራረስና ምርታማነት ዙሪያ የሚታዩ ማነቆዎችንና ለማነቆዎቹ የመፍትሔ ምክረ ሐሳብ ማቅረብ፣ በጥናት የደረሰባቸውን ግኝቶች በራሱ ባለሙያዎች ለአርሶ አደሩ ሠርቶ ማሳያ እንደሚያቀርብ፣ እመርታ ያሳየባቸውን ሙከራዎች የግብርና ሚኒስቴር፣ የክልል ግብርና ቢሮዎችና ሌሎችም ተቀብለው እንዲተገብሯቸው ለማድረግ እንደሚሠሩ አስረድተዋል፡፡
በተጠናቀቀው እ.ኤ.አ. 2025 የዓለም የምግብና እርሻ ድርጅት (ፋኦ) ተሸላሚ የሆነው ኢንስቲትዩቱ፣ በ400 ወረዳዎች ሦስት ሚሊዮን ሔክታር መሬት በመስኖ ለማልማት የሚውል የተቀናጀ የጉድጓድ ውኃ ፕሮጀክት በመለየት፣ በ356 ወረዳዎች 6.1 ሚሊዮን አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ ማድረጉን ዳይሬክተሯ ገልጸዋል፡፡ ከ286 ሺሕ በላይ አርሶ አደሮች ከድህነት እንዲወጡ መደረጉንም አክለዋል፡፡
በአገሪቱ ከሚገኙ 748 ወረዳዎች ከ100 ሺሕ በላይ የአፈር ናሙናዎች በመውሰድ የአፈር አሲዳማነትን የአልካላይን ይዘት፣ የንጥረ ነገር ክምችት ይዘትና ለምነትን ጨምሮ የአፈር ምንነት መግለጫ የያዘ ሰፊ ማውጫ መዘጋጀቱን ተናግረዋል፡፡
መንግሥት የግብርናውን ዘርፍ ገበያ ተኮር ለማድረግ የተሻሻሉ ግብዓቶችን በማቅረብ አርሶ አደሮች ከፍተኛ ምርት እንዲያመርቱ ማድረግ፣ በቂ የአገር ውስጥ ፍጆታ ከማቅረብ ባለፈ ያመረቱትን እሴት ጨምረው ለውጭ ገበያ መላክ የሚችሉ የግብርና ኩባንያዎች እንዲፈጠሩ አበክሮ እየሠራ መሆኑን ብሩክታዊት (ዶ/ር) አብራርተዋል፡፡
From The Reporter Magazine
‹‹በግብርናው ዘርፍ የአቅም ግንባታ ሥልጠና መስጠትና ድጋፍ ማድረግ፣ እንዲሁም በመሬትና አርሶ አደር ዙሪያ የሚሠሩ አካላትን በማስተባበር የተመረተው ምርት፣ የእሴት ሰንሰለት የሚጨምርበትን አካሄድና የሚመለከታቸውን አካላት የማስተባበር ተግባርን ያከናውናል፤›› ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያን የአሥር ዓመታት የግብርና ዕቅድ ዝግጅትን በመምራት ዋና አስተባባሪ የነበረው ኢንስቲትዩቱ፣ ለክልሎች የግብርና ትራንስፎርሜሽን ፍኖተ ካርታ እንደሚያዘጋጅ፣ ለአርሶ አደሮች የገበያ መረጃ አገልግሎት የሚሰጡ የጥሪ ማዕከላትን በማስፋፋትና የግብርና መረጃዎችን ዲጂታላይዝ አድርጎ በማቅረብ፣ የዲጂታል ግብርና ፍኖተ ካርታ ማስተዋወቁን ዘርዝረዋል፡፡
በኢንስቲትዩቱ የሚደገፉ አርሶ አደሮች የቢራ ገብስ ሱፍሌ ለተሰኘው በኢትዮጵያ ለሚገኘው የፈረንሣይ የብቅል ኩባንያና ቦርት ማልት ለተሰኘ ኩባንያ እንዲሁም 54 ካፒታል ለተሰኘው አኅጉራዊ ድርጅት ደግሞ አኩሪ አተር፣ እንዲሁም ሱፍ ለዘይት ምርት እንደሚያቀርቡ የኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተሯ ተናግረዋል፡፡
From The Reporter Magazine
በተጠናቀቀው እ.ኤ.አ. 2025 የመጀመሪያ ምዕራፉ በሆነው የግብርና ኮሜርሻላይዜሽን ፕሮግራሙ ጤፍ፣ በቆሎ፣ የብቅል ገብስ፣ አኩሪ አተር፣ ሰሊጥ፣ አቮካዶ፣ ሙዝ፣ ሽንኩርት፣ ማንጎ፣ ቲማቲም፣ ወተትና እንቁላልን ጨምሮ በ311 ወረዳዎች፣ በዘመናዊ ግብርና ታግዘው እንዲያመርቱ በማድረግ 4.4 ሚሊዮን አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ ማድረጉን ገልጸዋል፡፡ በቅርቡ በጀመረው ሁለተኛ ምዕራፉ አርሶ አደሮችን የግብርና ኩባንያ ባለቤት ለማድረግ የሚያስችል ፕሮግራም ቀርፆ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን አክለው ተናግረዋል፡፡ በሁለተኛ ምዕራፍ 6.5 ሚሊዮን አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ ማድረግና 50 የአርሶ አደር ኩባንያዎችን ማቋቋም ዓላማ ነው ብለዋል፡፡
የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሤ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ በመጪዎቹ ዓመታት አርሶ አደሮች የሚያመርቱት ምርት እየበዛና ወደ ኩባንያ እያደጉ ዑደታቸው ወደ ኢንዱስትሪ እየተቀየረ መዋቅራዊ ሽግግር ማድረግን በዕቅድ ተይዞ እንቅስቃሴ መጀመሩን ገልጸዋል፡፡
በተጀመሩ ዘመናዊ የግብርና ትራንስፎርሜሽን ሒደቶች በቀጣይ ዓመታት በገጠሩ የኢትዮጵያ ክፍል የሚፈጠሩ ዕድሎችን በማስፋት ዘመናዊ ኢንዱስትሪዎች በሁሉም ወረዳዎች እንዲስፋፉ፣ ኢንዱስትሪው ሚዛኑን እየጠበቀ የግብርናውን ዕድገት እንዲቆጣጠር ይፈለጋል ብለዋል፡፡
የአገር የወደፊት ተስፋ የሚሆኑ የግብርና ኩባንያዎቹ ወደ ኢንዱስትሪ አድገው ከአገር አልፈው በሌሎች አገሮች እንዲስፋፉ በማድረግ፣ በኢትዮጵያ የሚመረቱ ግብዓቶችና የግብርና ምርቶች ለሌሎች አገሮች ዋነኛ ምንጭ እንዲሆኑ የታለመበት ትልቅ ተስፋ መሆኑን አስረድተዋል፡፡