የሪል ስቴት ኩባንያዎች ለቤት ግንባታ ወጪ ያደረጉትን መሠረት ያደረገ አማካይ የሽያጭ የዋጋ ተመን እንዲኖር የሚያስችል ጥናት እየተካሄደ መሆኑን፣ የኢትዮጵያ ሪል ስቴት አልሚዎች ማኅበር አስታወቀ፡፡
የኢትዮጵያ ሪል ስቴት አልሚዎች ማኅበር ዋና ጸሐፊ ዝናቡ ተበጀ (ኢንጂነር) እንደገለጹት፣ በኢትዮጵያ የሚገኙ ሪል ስቴቶች ቤት የሚሸጡበት አማካይ ዋጋ ተመን እንዲኖር የሚያስችል ጥናት እየተደረገ ነው፡፡ ጥናቱ አንድ ቤት ከተቆረጠለት ዋጋ በታች መሥራት እንደማይቻል፣ ዋጋው አነሰ ብቻ በሚል ገዥዎች በመወሰን ተጎጂ የሚሆኑበትን አካሄድ ለመቀየር እንደሚረዳ ተናግረዋል።
በገበያው ውስጥ ከ50 ሺሕ እስከ 400,000 ሺሕ ብር በካሬ ሜትር የሚሸጡ የሪል ስቴት ኩባንያዎች መኖራቸውን፣ በተለይ መነሻው ዋጋው አንድ የሪል ስቴት ኩባንያን ያሠራል ወይ? የማርኬቲንግ፣ የፋይናንስ፣ የግብር፣ እንዲሁም የመሬት ክፍያን ጨምሮ ግንባታው በአጠቃላይ የሚፈጀው ወጪ (Total Development Cost) መሠረት ያደረገ እንዲሆን ጥናቱ እንደሚያስችል ተናግረዋል። በጥናቱ መሠረት በከፊልና ሙሉ ለሙሉ ያለቁ ቤቶች ዋጋቸው ስንት ይሁን የሚል አማካይ የዋጋ ተመን እንደሚቆረጥ አስረድተዋል።
ጥናቱን ማድረግ ያስፈለገበትን ምክንያት ሲያስረዱ አንዳንድ የሪል ስቴት ኩባንያዎች ሌሎች ኩባንያዎች የሚሸጡበት ዋጋ ተፅዕኖ አሳድሮባቸው ተመሳሳይ ዋጋ የሚያስከፍሉበት አሠራር መኖሩን፣ ማኅበሩ ከደረሰበት ግንዛቤ መነሻ በማድረግ መሆኑን ዝናቡ (ኢንጂነር) ገልጸዋል።
አጠቃላይ ወጪዎችን መሠረት ያደረገ የዋጋ ተመን እንዲኖር ጥናቱ እንደሚረዳ አስረድተው፣ ጥናቱ የሪል ስቴት ኩባንያዎችን በዚህ ዋጋ ሽጡ ለማለት እንዳልሆነና አንድን ቤት ያለ ዋጋው ልሽጥላችሁ ብሎ የሚመጣ ሪል ስቴት ኩባንያን እንዴት ብሎ መጠየቅ የሚያስችል እንደሚሆን ጠቁመዋል።
ከዚህ በፊት ዋጋው ርካሽ ነው በሚል ገንዘባቸውን ሰጥተው የከሰሩ ዜጎች መኖራቸውን ያስታወሱት ዝናቡ (ኢንጂነር)፣ የዋጋው ተመን ቤቶች የተገነቡበትን ቦታ ያማከለ እንዲሆን እንደሚያስችልም ተናግረዋል። በተለይ የዋጋ ተመን ሲወጣ ግንባታው አካባቢ እንደ ትምህርት ቤትና ጤና ተቋማት ያሉ መሠረተ ልማቶች ያሉበት ነው የሚለውን መሠረት የሚያደርጉ ሌሎች ተጨማሪ ደረጃዎችን ማውጣት እንደሚያስፈልግም አብራርተዋል።
የማኅበሩ አባል የሆኑ የሪል ስቴት ኩባንያዎች የዋጋ ተመኑን ለማውጣት የሚረዳ ዝርዝር ፎርም እንዲሞሉ መደረጋቸውንም ይህም የአንድ ካሬ ሜትር ዋጋን ጨምሮ ግንባታው በአጠቃላይ የሚፈጀው ወጪ (Total Development Cost) ምን ያህል ነው የሚለውን እንዲያውቁ መደረጉን ተናግረዋል።
From The Reporter Magazine
ይህን መሠረት በማድረግም አማካይ ዋጋ ወደ ማውጣት ሒደት እንደሚገባ አስረድተዋል። ይህ የዋጋ ተመን ሲቆረጥ የአካባቢው አቀማመጥ ታሳቢ ሊደረግ እንደሚችል ጠቁመዋል። የሪል ስቴት ኩባንያዎች አማካይ ዋጋው እስከሚወጣ የራሳቸውን አጠቃላይ የግንባታ ወጪያቸውን መሠረት ያደረገ ተመን እንዲኖራቸው በኃላፊነት እንዲሠሩ አሳስበዋል።
