የኢትዮጵያን ንግድ ባንክ ያቋቋመውና ላለፉት 60 ዓመታት በሦስተኛ ወገን አገልግሎት ሰጪነት ሲሠራ የቆየው ኮሜርሻል ኖሚኒስ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር፣ በውጭ አገር የሥራ ሥምሪትና በሪል ስቴት ዘርፍ ለመሰማራት ዝግጅት እያደረገ መሆኑን አስታወቀ::
ላለፉት ስድስት አሠርት ዓመታት በተለያዩ ዘርፎች አገልግሎቶችን በመስጠት ላይ የሚገኘው ድርጅቱ በሰው ኃይል አቅርቦት አስተዳደር፣ በፅዳት አገልግሎት፣ ሕንፃዎችንና ቤቶችን፣ እንዲሁም የባንክ ውክልናና የሦስተኛ ወገን አካቶ በሌሎች ከ13 በላይ የአገልግሎት ዓይነቶችን በማቅረብ ይታወቃል፡፡ አሁን ግን በውጭ አገር የሥራ ሥምሪትና በሪል ስቴት ዘርፍ ለመሰማራት ዝግጅት እያደረገ መሆኑን፣ የተቋሙ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኮማንደር ጥላሁን ፀጋዬ ገልጸዋል፡፡
ዋና ሥራ አስፈጻሚው ይህንን ያሉት ድርጅቱ 60ኛ ዓመት የምሥረታ በዓል ዓርብ ሚያዝያ 30 ቀን 2018 ዓ.ም. ሲከበር ነው፡፡
በውጭ አገር የሥራ ሥምሪት ለመሰማራት ከሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ጋር ስምምነት ላይ መድረሳቸውን የተናገሩት ኮማንደር ጥላሁን፣ ለዚሁ አገልግሎት የሚውል የማሠልጠኛ ማዕከል መቋቋሙን አስረድተዋል፡፡
የመንግሥትና የግል ሕንፃዎችን የማስተዳደር ሥራዎችን እንደሚሠራ የገለጹት ኮማንደር ጥላሁን፣ ለዚህም ንግድ ባንክ የሚያስተዳድራቸውን ሁሉንም ሕንፃዎች፣ እንዲሁም መንግሥት በዕዳና በሙስና የሚይዛቸውን ንብረቶች በሙሉ እያስተዳደረ እንደሚገኝ አክለዋል፡፡
በዚህም አብዛኞቹ ሕንፃዎች የሚተዳደሩበት በዘመድ ወይም በግለሰብ በመሆኑ፣ ይህንንም ለመቀየር እየሞከሩ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ በአጠቃላይ የመንግሥትና የግለሰቦችን፣ እንዲሁም መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት ሕንፃዎችን ተረክበን ለማስተዳደር ነው ያሉት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፣ በዚህም ተከራዮቻቸውን መንግሥት የሚጥላቸውን ግዴታዎች ለማስፈጸም ነው ብለዋል፡፡
በአዲስ መልክ ሌሎች የሥራ መስኮች ላይ በስፋት ሊሰማራ መሆኑን የተናገሩት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፣ ከሚጀምሯቸው አገልግሎቶች መካከል ከዚህ ቀደም በአገር ውስጥ ብቻ ያቀርብ የነበረውን የሰው ኃይል በማሠልጠን ወደ ውጭ አገሮች መላክና በአገር ውስጥ ለንግድና ለመኖሪያ የሚሆኑ የቤት ግንባታዎች ይገኙበታል ብለዋል።
ከዚህ ባሻገር በልብስ ነክ መስኮች፣ በኬሚካሎች፣ በተቀናጀ ቆሻሻ ማስወገድ፣ እንዲሁም በኤሌክትሪክ ተሽከርከሪዎች ኃይል ሙሌት ላይ እንደሚሳተፍ አክለዋል፡፡
From The Reporter Magazine
ዋና ሥራ አስፈጻሚው እንደገለጹት፣ ወደ ፊት ራሱን በአዲስ መልክ ለአዳዲስ አገልግሎቶች ተደራጅቶ ሥራ ይጀምራል፡፡ በ2014 ዓ.ም. ገቢው 2.6 ቢሊዮን ብር እንደነበረ ያስታወሱት ኮማንደር ጥላሁን፣ በ2017 ዓ.ም. ደግሞ ከ5.6 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰቡን ተናግረው፣ በ2018 ዓ.ም. ያለው ገቢ ስምንት ቢሊዮን ብር እንደሚደርስና ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ ትርፍ እንደሚሰበስብ ተናግረዋል፡፡
ከ42 ሺሕ በላይ ለሚሆኑ ሠራተኞች የሥራ ዕድል መፍጠሩን የተናገሩት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፣ ከ30 በላይ ቅርጫፎችን በማደራጀት በበርካታ አካባቢዎች ላይ ተደራሽ መሆናቸውን ተናግረው በዚህም በየዓመቱ ትርፋማ እየሆነ መምጣቱን ገልጸዋል፡፡
‹‹የሥራ ዕድል ከተፈጠረላቸው መካከል አብዛኛዎቹ ወጣቶች ናቸው፤›› ያሉት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፣ 48 በመቶ የሚሆኑት ደግሞ ሴቶች ናቸው ብለዋል፡፡
From The Reporter Magazine
ከደመወዝና ከጥቅማ ጥቅም ጋር ተያይዞ ማብራሪያ የሰጡት ኮማንደር ጥላሁን፣ ተቋማት የሚፈልጉት የሰው ኃይልና የሙያ ብቃት የተለያየ በመሆኑ ዝቀተኛ የሚባለው የሠራተኞች ደመወዝ ሰባት ሺሕ ብር መሆኑንና የትራንስፖርትና የቤት ኪራይ፣ የ24 ሰዓት ኢንሹራንስ፣ በዓመት እስከ የአሥር ሺሕ ብር ሕክምና፣ በየዓመቱ 30 በመቶ የደመወዝ ዕድገት፣ እንዲሁም በየዓመቱ መጨረሻ ላይ የሁለት ወራት ደመወዝ ቦነስ አላቸው ብለዋል፡፡
‹‹በሌላ በኩል አንድ ሠራተኛ በዓመት ቢያንስ አንድ ጊዜ ሥልጠና የመውሰድ ግዴታ አለበት፤›› ያሉት ኮማንደር ጥላሁን፣ ይህም ከደመወዝና ከጥቅማ ጥቅም አንፃር ሲታይ የመንግሥት ተቋማትም ሆነ ግለሰቦች ከሚከፍሉት ደመወዝ 58 በመቶ ጭማሪ እንዳለው አክለዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት ካለው የኑሮ ውድነት አንፃር ለሠራተኞች መነሻ የደመወዝ ወለል ተብሎ የተገለጸው በቂ ነው ብለው ይገምታሉ ተብሎ ለቀረበላቸው ጥያቄ ሲመልሱ፣ ‹‹ደመወዝ የሚነፃፀረው ከኑሮ ጋር አይደለም፡፡ ደመወዝ የሚከፈለው በሠራተኛው ክህሎት፣ በሚኖረው በሥራ ልምድና የትምህርት ዝግጅት በመሆኑ፣ ሠራተኞቻችን ደግሞ በብዛት ዝቅተኛ ትምህርት ዝግጅት ያላቸው በመሆናቸው የሚከፈላቸው ክፍያ ከሌሎች አንፃር ሲታይ ተመጣጣኝ ነው ብለን እንገምታለን፤›› ሲሉ አብራርተዋል፡፡
‹‹ደመወዝን ከኑሮ ጋር ካነፃፀራችሁ እኔም አይበቃኝም፡፡ ደመወዝ ከኑሮ ጋር አይነፃፀርም፤›› ያሉት ኮማንደር ጥላሁን፣ ለአብነት የጥበቃ ሠራተኞች ደመወዝ ከሌሎች ቀጣሪዎች ጋር ሲነፃፀር 58 በመቶ ከፍ ያለ ነው ብለዋል፡፡
