
ጉዞ ከፒያሳ ወደ ካዛንቺስ። መነሻችን ከጥንት የጠዋቱ ጣይቱ ሆቴል ደጃፍ ላይ ነው። በኢትዮጵያ የመጀመሪያው ሆቴል ጊዜያዊ የታክሲ መናኸሪያ መሆኑ ግር ቢልም፣ ለማንኛውም ሠልፋችንን ይዘን ተረኛውን ታክሲ መጠበቃችንን ቀጥለናል፡፡ ጎዳናው ላይ ግራ የገባው፣ በከፊል የገባው የመሰለው፣ ምንም ያልገባው፣ የሚሄድበትን የሚያውቀው፣ እግሩ በዘፈቀደ የሚመራው፣ መድረሻውን የወሰነው፣ እንኳን መድረሻ መነሻ የሌለው ሁሉ ከዚያም ከዚህም እየተግተለተለ ይተራመሳል። የትናንቱ አሰልቺ እንግልት ዛሬ በአዲስ ጉልበት ሊደገም ጎህ ቀዷል። ለአንዳንዱ ደግሞ ገና ሳይነጋ መሽቶበታል። አስቀድሞ የክስረት ሒሳቡን ላወራረደ የሰማይ ዓይን መግለጥና የምድር ዓይን መክደን ትርጉም አይኖራቸውም። ብቻ ጎዳናው የሁሉም መድረክ ስለሆነ፣ ይኼኛው ከዚያኛው እኩል ትከሻ ለትከሻ ተጠባብቀው የታክሲ ወረፋ ይጠብቃሉ። ሕይወት እንዲህ ናት!
ከረጅም ጥበቃ በኋላ የተገኘው አሮጌ ሚኒባስ ላይ በቅደም ተከተል ገብተን ተሳፍረናል። አስቀድሞ ራሱ በከፋፈታቸው መስኮቶች በኩል አንገቱን ያስገባው ወያላ ተሳፈሪዎችን ይለክፋል። ‹‹እሺ እዚህ ጋ… አንቺኛዋ ትንሽ ጠጋ በይ… እዚያ ጋ እናንተ ውሪዎች ነግሬያለሁ ወንበር ላይ ብትጽፉ… በተለይ ፖለቲካን በተመለከተ አንድ ነገር ጻፉና እናንተን አያድርገኝ። አዎ ይኼን ጊዜ ስንት ያልሠራችሁት የቤት ሥራ አለ…›› ይላል ታዳጊ ተማሪዎችን። በዋናው በር በኩል ዞሮ ደግሞ፣ ‹‹ገና በጠዋቱ እንዳንለካከፍ ዝርዝር ብር አዘጋጁ። አዳሜ በብላክ ማርኬት እየዘረዘርሽ አገር ማራቆት ለምደሽ እኔ መልስ ብትሉኝ አልሰማችሁም…›› ይላል። ‹‹ዛሬ ቁርስ የበላኸው የፍየል ምላስ ነው እንዴ ፍሬንድ? ይልቅ ሞልቷል ሳበው በለው…›› የቸኮለ ወጣት ተናገረ፡፡ ይኼኔ ታክሲያችን መንቀሳቀስ ጀመረ። የግድ ነው!
ተማሪ፣ ነጋዴ፣ ሸማች፣ አሠሪ፣ ሥራ ፈላጊ በታክሲያችን ጣሪያ ሥር ተሰባስበን ጉዞ ጀምረናል። መሀል መቀመጫ ላይ የተሰየመች ወይዘሮ በሞባይል ስልኳ፣ ‹‹…ይኼ የፖለቲካ ፓርቲ ከመደገፍ ወይም ከመቃወም ጋር የተያያዘ አይደለም…›› ስትል ፈዘዝ ብለን የነበርነው ተነቃቃን። ሁላችንም እርስ በእርስ ተያይተን ወደ ወይዘሮዋ አፈጠጥን። ወይዘሮዋ ቀጥላለች፣ ‹‹ነገር ግን መስዋዕትነት ተከፍሎበታል የተባለውን ለውጥና ነፃነት እንዳሻቸው ሲፈነጩበት ማየት ከምንም በላይ ስለሚያም ነው። አሁንም ድሮም ሆነ ወደፊት ሥልጣንን ተገን በማድረግ የሚፈጸሙ ድርጊቶችን በፅኑ እቃወማለሁ…›› ብላ ስታበቃ እጇን ወደ ላይ ማንሳት ነበር የቀራት። ስልኳን ወዲያው ዘግታ አብሯት ከተመቀመጠ ጎልማሳ ጋር ማውራት ቀጠለች። መጨረሻ ወንበር ከተመቀጡ ተሳፋሪዎች አንዱ፣ ‹‹ባላሰብነውና ባልጠበቅነው ሰላማዊ ሠልፍ ስንሳተፍ ዝም ትላላችሁ? ሴትየዋን ኧረ አንድ በሏት…›› ከማለቱ፣ ‹‹ሰው ያለ ከልካይ የበላ የጠጣውን የሚለጥፍበት የፌስቡክ ግድግዳና ቲክቶክ አልበቃ ብሎት ደግሞ ጎዳናውን በብሶት ፖለቲካ ካላተራመስኩት ይላል። መተሳሰብ እኮ ትተናል…›› ስትል አንዲት ወጣት የእንኑርበት መልዕክቷን ታስተላልፋለች። ጎመን በጤና!
ወያላው በበኩሉ፣ ‹‹ሰው ዘንድሮ ምን ነክቶታል እባካችሁ፣ ምናለበት መደማመጥ ትቶ ለመነታረክ ባይቸኩል?›› እያለ ሾፌሩ ሲናገር፣ ‹‹ስለሰው ስለሰው ቀድጄ ልልበሰው ብላለች ዘፋኟ። ይልቅ ወሬውን ትተህ ስፖክዮውን አስተካክለው አይታየኝም…›› ብሎ ኩም ያደርገዋል። ከወገቡ በላይ በመስኮት ሾልኮ ሲወጣ ከሾፌሩ ጀርባ የተቀመጡ ሁለት ተሳፋሪዎች ስለአፍሪካ ዋንጫ ጥሎ ማለፍ ጨዋታ ያወራሉ። አላደርስ ብሎን ዜና ያልሰማን ማን ዋንጫውን አሸነፈ የሚለውን ለመስማት ጆሯችንን ወደ እነሱ ቀና ስናደርግ፣ ‹‹ኑሯችን ትላለህ ፖለቲካው፣ ትዝብታችን፣ ሐዘናችን ሳይቀር ገና ከጥለዛ የማይወጣበት ምክንያት ነው እኮ የማይገባኝ። ተግዳሮታችንና ችግራችን ሁሉ የትናንት ናቸው፡፡ እንዲያው መቼ ይሆን ነገራችን ሁሉ ወደ ጥሎ ማለፍ የሚሸጋገረው?›› የሚል ቀጭን ድምፅ ስንሰማ ግን የባከነ ሰዓት ላይ መድረሳችን ታወቀን። በስንቱ እንደምንባክን አልገባን አለ እኮ!
ወያላው ሒሳብ መሰብሰብ ጀምሯል። ጋቢና የተየሰሙትን ሴቶች ሾፌሩ እንዳትቀበል ስላለው ወያላው ተነጫንጯል። ‹‹በቃ አጠገቡ ሴት ከተቀመጠች እኮ በነፃ አላስካ ደርሶ ይመለሳል ምን አገባኝ እኔ?›› እያለ ለራሱ እያጉተመተመ መጨረሻ ወንበር ተጠባብቀው ወደ ተቀመጡት ታዳጊ ተማሪዎች ሲደርስ፣ ‹‹ሒሳብ!›› ብሎ ጮኸባቸው። ነገረ ሥራቸው ሁሉ ፈገግ የሚሰኝ እነዚያ ታዳጊዎች የሞባይል ስልካቸውን እየጎረጎሩ ቀና ብለው እንኳ ሳያዩት ዝም አሉት። ‹‹እነ ጩጬ አትከፍሉም?›› ወያላው ደገመላቸው። ‹‹ቆይ አንዴ ተረጋጋ ይሰጥሃል…›› እያለ ጌም የሚጫወተው አንደኛው መለሰ። ወይዘሮዋ አፏን ሸፍና ሳቀች። አጠገቧ የተሰየመች ቀዘባ ደግሞ ፈገግ ብላ፣ ‹‹አይ ኢትዮጵያ አገሬ በዱር በገደሉ ለነፃነትሽ የተዋደቁ አርበኞች ልጆችሽን ባየሽበት ዓይን ዛሬ የጌም አርበኞች ሲተኩዋቸው ስታይ ምን ትይ ይሆን?›› ብላ ወደ ሰማይ ቀና አለች። መሀል መቀመጫ ያለ ጎልማሳ ዘወር ብሎ፣ ‹‹እነሱ ምን ያውቃሉ? እኛ ነን እንደጠቀምናቸው እያሰብን በዚህ ዕድሜያቸው ያውም ወደ ትምህርት ቤት ይዘው እንዲሄዱ እየፈቀድን ሞባይል ገዝተን የምንሰጥ። ወላጆች ነን ልጆቻችንን እያበላሸናቸው ያለነው…›› ብሎ ተነፈሰ። ኡፍፍፍፍ…!
ታዳጊዎቹ ግማሽ መንገድ ላይ ወርደው አዲስ ተሳፋሪ ተጫነ፡፡ እሱም ከመግባቱ፣ ‹‹…ታክሲ አሁን አግኝቼ ገና ተደላድዬ አልተቀመጥኩም፡፡ ችግሩ ምንድነው ስል ‹አይ አንተ ከሄድክ ስለማትመለስ ኬዝህን አላመነበትም› አትለኝም አስተርጓሚዋ። ኧረ ድርጅት አለኝ ይኼው የባንክ ወጪና ገቢዬ ብል ማን ይስማኝ? ለነገሩ እነሱ ምን አለባቸው ለኮቴ የሚቀበሉት ብቻ እኮ በዓመት የትናየት ሚሊዮን ብር መሰለህ? በትንሹ በቀን በሰላሳ ሺሕ ብር ሒሳብ 100 ሰው ይገባል ብለህ አስላውማ፡፡ ማን መፅዋች ማን ተመፅዋች እንደሆነ እኮ ነው ግራ የሚገባህ። ግድ የለም ቆይ ብቻ…›› እያለ በብስጭት በሞባይል ስልኩ እያወራ ሰማነው። ‹‹የአሜሪካ ቪዛ ተከልክሎ ነው መሰለኝ…›› አለ ይኼን ያህል ጊዜ ዝምታ ውጦት የነበረ ተሳፋሪ። ‹‹የአሜሪካ ቪዛ የመንግሥተ ሰማያት ያህል ራቀን አይደል…›› እያለ አንዱ ሲናገር፣ ‹‹አይዞን እኛም ጠንክረን ከሠራን አሜሪካን ኢትዮጵያ ውስጥ መፍጠር እንችል ነበር፡፡ ምን ያደርጋል፣ ልቡ የሸፈተ ትውልድ ይዘን ስንቀዋለል ይኸው ትራምፕ የሚሉት ሰውዬ አትድረሱብኝ ብሎ ቪዛውን ጥርቅም አደረገው…›› ብላ ወይዘሮዋ አንበለበለችው፡፡ ወይ አሜሪካና ቪዛዋ!
ከሾፌሩ ጀርባ የተቀመጠ ስለቢዝነስ አብዝቶ የሚያወራ ተሳፋሪ ደግሞ፣ ‹‹የእኔም ወንድም እንዳንተ አጋጥሞት ነበር። ምን አደረገ መሰለህ? አንድ የአውሮፓ አገር ቪዛ ጠይቆ ከዚያ ላጥ አለና ዋሽንግተን ዲሲ ገባ እልሃለሁ። ዋናው ተስፋ ሳትቆርጥ በሩን ማንኳኳት ነው። ወጣ ወጣ እያልክ ካልሆነ የእኛን ነገር ታውቀዋለህ…›› ይለዋል። ‹‹አይ ወንድሜ፣ ትራምፕ የ75 አገሮችን የቪዛ ጥያቄ ከልክሎ በየት ተደርጎ ነው አሜሪካ የሚገባው ብለህ ነው…›› እያለ ተብሰለሰለ። በዚህ አያያዛችን አሜሪካ እንደተባለው በጣም እየራቀች ነው አትሉም? ሾፌራችን ጋቢና ከተሰየሙት የሚያውቃቸው እህቶች ጋር አፍ ለአፍ ገጥሞ መቆየቱ ወያላውን ክፉኛ አበሳጭቶታል። ጨዋታውን ለማቆርፈድ ይመስላል፣ ‹‹ኮካ በስሜ አትጋብዝልኝም?›› ሲል ከወሬው ያደናቅፈዋል። ሾፌሩ ነገሩ ገብቶት፣ ‹‹ቀበሌ የማያውቅህ ወያላ ማን በአንተ ስም ኮካ ይሰይማል?›› ብሎ አጠገቡ ካሉት ጋር ተጠቃቅሶ ፈገግ አለ። ወያላው ሴራው እንዳልተሳካለት አውቆ ዝም ሲል ጎልማሳው፣ ‹‹ምን ይሻለናል ዘንድሮ? በየራሳችን ፈተናዎች ጩኸት አበድን እኮ፡፡ የአንዱን ብሶት ሰምተን ሳንጨርስ ሌላው ደግሞ የእኔስ የባሰው ብሎ ይመጣል…›› እያለ ተብሰከሰከ። ብሶት ብቻ!
From The Reporter Magazine
ወደ ካዛንቺስ እየተቃረብን ነው፡፡ በጎልማሳው ትዝብትና ቁጭት እኛም ተብሰልስለን ሳንጨርስ የመንገዱ መጠናቀቂያ መቃረብ አልታወቀንም ነበር። ‹‹ወይ ካዛንቺስ ወይ አዲስ አበባ፣ ከተማ እንዲህ መልኩ እስከማያስታውቅ ድረስ ይቀየራል ብሎ ማን ጠብቆ ነበር…›› እያለ አንዱ በመደነቅ ሲያወራ፣ ‹‹ዕጦት ያደቀቀውን ሰውም ማግኘት ማዲያቱን ጭምር አጥፍቶ እንደሚያሳምረው ማለትህ ነው አይደል…›› ትላለች ወይዘሮዋ። ‹‹አልሰማችሁም እንዴ፣ በአዲስ አበባ ቅጽበታዊ ለውጥና ማማር በርካታ የአፍሪካ አገሮች ዜጎች መንግሥታቶቻቸውን የእኛስ ከተሞች ለምን ድብርት ውስጥ ይኖራሉ ብለው እየወተወቱ መሆናቸውን…›› ብሎ አንድ ወጣት በፈገግታ ተሞልቶ ሲናገር፣ ‹‹የተሟላ ሰላም ቢኖር ደግሞ በሁሉም ነገር ኢትዮጵያ አፍሪካን እየመራች ዓይን ገላጭ ትሆን ነበር…›› የሚሉት እስካሁን ድምፃቸው ያልተሰማ መሀል መቀመጫ የተቀመጡ እናት ነበሩ። ‹‹እናታችን እውነት ብለዋል፣ ድሮም የአፍሪካ የነፃነት ዓይን ገላጭ ኢትዮጵያ ነበረች…›› ጎልማሳው እያለ ታክሲያችን ስትቆም ሳለ ወያላው ‹‹መጨረሻ…›› ብሎን አሰናበተን፡፡ መልካም ጉዞ!