የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የአካውንቲንግ (የሒሳብ አያያዝ) ትምህርት አሰጣጣቸውን መከለስና ጊዜው ከደረሰበት ደረጃ ጋር አብሮ እንዲሄድ ማድረግ እንዳለባቸው፣ የኢትዮጵያ የተመሰከረላቸው የሒሳብ ባለሙያዎች ኢንስቲትዩት ጥያቄ አቀረበ፡፡
የኢትዮጵያ የተመሰከረላቸው የሒሳብ ባለሙያዎች ኢንስቲትዩት የኢትዮጵያ የሒሳብ አያያዝ ቴክኒካዊ ብቃት (Accounting Technician Qualification Ethiopian – ATQE) ሥልጠናን መስጠት የሚያስችል ስምምነት ከ11 የመንግሥትና የግል ተቋማት ጋር ሐምሌ 6 ቀን 2018 ዓ.ም. ተፈራርሟል።
በመድረኩ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንትና የኢትዮጵያ የተመሰከረላቸው የሒሳብ ባለሙያዎች ኢንስቲትዩት የቦርድ አባል ሳሙኤል ክፍሌ (ዶ/ር)፣ የአካውንቲንግ ዘርፍ ትምህርትና በኢትዮጵያ በሥራው ውስጥ ሰፊ ልዩነት እንዳለውና አንድ ሰው ዲግሪ ይዞ ተመርቆ ሥራ ቦታ ሲሄድ የሚያጋጠመው ተጨማሪ ሥልጠና እንደሆነ ገልጸዋል።
ከዚህም አንፃር በዘርፉ ያለውን የከፍተኛ ተቋማት ሥርዓተ ትምህርት ቀረብ ብሎ ማየትና ክለሳ በማድረግ ከሙያው ጋር የተናበበ እንዲሆን መሥራት ይገባል ሲሉ አሳስበዋል።
እንደ ኬንያ፣ ኡጋንዳና ታንዛኒያ በመሳሰሉ ጎረቤት አገሮች የዘርፉ ሥርዓተ ትምህርት ከሙያው ጋር የተናበበ መሆኑን ተናግረዋል። የእነዚህ አገሮች የሒሳብ ባለሙያዎች፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትና የሙያ ማኅበራት በጋራ ተቋማት ተቀራርበው በመሥራታቸው ያፈሩት የሠለጠነ የባለሙያ ቁጥር ከኢትዮጵያ እንደሚበልጥ ገልጸዋል። እንደ አገር ያለው የሒሳብ አያያዝ ሙያ ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ መሆን እንዳለበት፣ የካፒታል ገበያን ጨምሮ የተጀመሩ ሌሎች የኢኮኖሚ ለውጦች በሙያተኛ የተሠራ፣ ተዓማኒነት ያለው፣ እሴት የጨመረ የሒሳብ ሪፖርት እንደሚፈልጉም ተናግረዋል።
ይህን ለማድረግ በአገር ደረጃ ያሉ ሙያተኞች ቁጥር በቂ አይደሉም ያሉት ሳሙኤል (ዶ/ር)፣ በሦስትና አራት እጥፍ ቢበዛ እንኳን የሚኖረው ጉድለት ከፍተኛ ነው ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ የተመሰከረላቸው የሒሳብ ባለሙያዎች ኢንስቲትዩት ቦርድ ሰብሳቢ አቶ ፍቃዱ አጎናፍር፣ ኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ለውጥ ውስጥ መሆኗንና ለአብነትም የካፒታል ገበያ መጀመሩን፣ በርካታ የውጭ ኢንቨስትመንቶች እየመጡ መሆናቸውን፣ የውጭ ባንኮችም ወደ አገር ውስጥ መግባት መጀመራቸውን፣ በሙያቸው ብቁ፣ ጠንካራና ሥነ ምግባር የተላበሱ የሒሳብ አያያዝ ባለሙያዎች ማፍራት እንደሚያስፈልግ አስረድተዋል።
From The Reporter Magazine
ይህንን ኃላፊነት የኢትዮጵያ የተመሰከረላቸው የሒሳብ ባለሙያዎች ኢንስቲትዩት ብቻውን የሚያከናውነው ሊሆን እንደማይችል፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትና የሥልጠና ተቋማትን የጋራ ሥራ እንደሚጠይቅ ተናግረዋል። በተለይ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የአካውንቲንግ ትምህርት ከሙያው ጋር የተናበበ እንዲሆን ተቀራርበው መሥራት ይኖርባቸዋል የሚለውን የሳሙኤል (ዶ/ር) ሐሳብ አፅንኦት ሰጥተዋል። ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትም ጉዳዩን በትኩረት ተመልክተው እንዲሠሩ አደራ ብለዋል።
የኬንያ የተመሰከረላቸው የሒሳብ ባለሙያዎች ኢንስቲትዩት እ.ኤ.አ. በ1978 እንደተቋቋመ፣ በተከናወኑ ሥራዎች 60 ሺሕ ዓለም አቀፍ በሒሳብ አያያዝ የሠለጠኑ ባለሙያዎች ማፍራታቸውን፣ በኢትዮጵያም በተለያዩ ተቋማት ተሰማርተው እንደሚገኙ ጭምር ገልጸዋል።
የዓለም አቀፍ የሒሳብ ሪፖርት አቀራረብ በኢትዮጵያ እንዲጀመር ሲደረግ በስፋት የተሳተፉት እነዚሁ ኬንያውያን እንደነበሩ አውስተዋል። ይህም የኢትዮጵያን የገበያ ሥርዓት ለመቆጣጠር እንደሚያስችላቸው፣ ገበያው በውጭ ባለሙያዎች ከመወረሩ በፊት በቅንጅት በመሥራት በኢትዮጵያውያን እንዲያዝ ማድረግ መሠረታዊ ጉዳይ መሆኑን አስረድተዋል።
From The Reporter Magazine
በኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ደረጃዎችን የሚያሟሉ የሒሳብ አያያዝ ባለሙያዎች ቁጥር 550 ገደማ መሆኑን፣ በአብዛኛው የሚጠበቀውን ሙያዊ አቅም ተላብሰው እየሠሩ አለመሆኑን፣ ከዚህም በመነሳት የሥልጠና ኢንስቲትዩት በሚያዚያ ወር 2017 ዓ.ም. በአዋጅ በማቋቋም ወደ ሥራ መገባቱን አቶ ፍቃዱ አውስተዋል።
ኢንስቲትዩቱ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ተግባር ያስገባውን የሒሳብ አያያዝ ቴክኒካዊ ብቃት ሥልጠና ለመውሰድ 2,000 ባለሙያዎች ማመልከታቸውን፣ ከእነዚህም ውስጥ 700 የሚሆኑ ተምረው ከሁለት ሳምንት በኋላ ፈተና እንደሚወስዱ ገልጸዋል። ኢንስቲትዩቱ በስፋት ሥልጠና መስጠት የሚያስችለውን ቴክኖሎጂ እያበለፀገ መሆኑን፣ በሚቀጥሉት ስድስትና ሰባት ዓመታት ውስጥ ዓለም አቀፍ ደረጃዎችን ያሟሉ ኢትዮጵውያን የሒሳብ ባለሙያዎችን ቁጥር አሥር ሺሕ ለማድረስ ዕቅድ መያዙን አስታውቀዋል።
ይህ በዚህ እንዳለ፣ የኢትዮጵያ የተመሰከረላቸው የሒሳብ ባለሙያዎች ኢንስቲትዩት ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ የሒሳብ ባለሙያዎችን ለማፍራት ከሚሰጣቸው ሥልጠናዎች አንዱ የሆነውን ‹‹የሒሳብ አያያዝ ቴክኒካዊ ብቃት ሥልጠና›› መስጠት የሚያስችል ስምምነት፣ ከስምንት የመንግሥትና ከሦስት የግል ተቋማት ጋር ተፈራርሟል።
ስምምነቱ ኢንስቲትዩቱ ያዘጋጀውን ሥርዓተ ትምህርት መሠረት በማድረግ ተማሪዎች ባሉበት አካባቢ ሆነው፣ ሥልጠናውን በተመረጡ ዩኒቨርሲቲዎች እንዲከታተሉ የሚያደርግ መሆኑን አቶ ፍቃዱ ገልጸዋል።
አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ ባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ፣ ጎንደር ዩኒቨርሲቲ፣ ሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ፣ ጅማ ዩኒቨርሲቲ፣ ሃረማያ ዩኒቨርሲቲ፣ ፐብሊክ ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ፣ ጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ ስምንቱ የመንግሥት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ሲሆኑ፣ ዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ፣ አይፓስና ኤችኤስቲ ደግሞ ሥልጠናውን ለመስጠት ስምምነት የፈረሙ የግል ተቋማት ናቸው።
ተቋማቱ ሲመረጡ የሥራ ቦታ አደረጃጀት፣ የሰው ኃይል አቅም፣ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምና ተያያዥ ጉዳዮችን መሠረት ያደረገ ምዘና ተደርጎ መሆኑን አቶ ፍቃዱ ገልጸዋል። በዚህ ረገድ አምስት የግል ተቋማት ጥያቄ አቅርበው ምዘናውን አልፈው የተመረጡት ሦስት መሆናቸውን አስረድተዋል። ሥልጠናው ባለሙያዎች ከኢትዮጵያ አልፈው በአፍሪካና በተለያዩ የዓለም አገሮች በሒሳብ አያያዝ ዘርፍ እንዲሰማሩ የሚያስችላቸው መሆኑን አስረድተዋል።
የሒሳብ አያያዝ ሙያ በተለያዩ ምክንያቶች ለአገር ማበርከት የሚጠበቅበትን ሚና ሳይወጣ ቆይቷል ያሉት የቦርድ ሰብሳቢው፣ በአሁኑ ወቅት በማንም ማሳበብ እንደማያስፈልግ፣ ኢንስቲትዩት ከተቋቋመና ወደ ሥራ ከተገባ በኋላ ይህ ሁኔታ ከተደገመ ኃላፊነቱ ወደ ኢንስቲትዩትና ሥልጠና ለመስጠት የተፈራረሙ ተቋማት ላይ እንደሚወድቅ ገልጸዋል።
የሥልጠናው መጀመር ኢትዮጵያ በዘርፉ ማግኘት ያለባትን ጥቅም እንድታገኝ፣ የሚዘጋጁ የሒሳብ ሪፖርቶች ለኢንቨስተሮች ትክክለኛውን መረጃ እንዲሰጡ፣ የኢትዮጵያ ድርጅቾች ወደ ሌላ አገር ቢሄዱ ቅቡልነት ያላቸውና የሚመስክረላቸው እንዲሆኑ የሚያስችል ይሆናል ያሉት ደግሞ ሳሙኤል (ዶ/ር) ናቸው። በዚህ ሥልጠና በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ካለው የወጣት የሰው ኃይል አንፃር በአፍሪካና በዓለም አቀፍ ደረጃ ብቁ የሆኑ የሒሳብ አያያዝ ባለሙያዎችን ለማፍራት ይረዳል ብለው እንደሚጠበቁ አክለዋል። በመሆኑም ይህን ዕድል አሟጦ መጠቀም ይገባል ሲሉ ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጥሪ አቅርበዋል።
ሙያተኝነትን ከሁሉም መስክ ጋር ማገናኘት አስፈላጊ ነው ብለው እንደሚያምኑ የገለጹት ደግሞ የዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት አረጋ ይርዳው (ዶ/ር) ናቸው። ሥልጠናው ባለሙያዎች በየትኛውም የዓለም ክፍል ተንቀሳቅሰው እንዲሠሩ የሚያስችል በመሆኑ ጥሩ ነው ሲሉ ገልጸውታል። ተማሪዎች ተመርቀው ወደ ሥራው ዓለም ሲቀላቀሉ የሚጠብቃቸውን የመግቢያ ፈተና ለማለፍ፣ ይህንን ዓይነት ሥልጠና መውሰዳቸው ስኬታማ እንዲሆኑ እንደሚያደርጋቸው ተናግረዋል።
በአደጉ አገሮች እንደ ኢትዮጵያ የተመሰከረላቸው የሒሳብ ባለሙያዎች ኢንስቲትዩት ያሉ ተቋማት በግሉ ዘርፍ እንደሚቋቋሙ፣ በኢትዮጵያም ሃያና ሰላሳ ዓመት ሊወስድ እንደሚችል፣ እንዲህ ያለው ኢንስቲትዩት የግል የሚሆንበትን መንገድ ለማመቻቸት ዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ የተቻለውን ጥረት እንደሚያደርግ አስረድተዋል። ተማሪዎችን መርዳት ዓላማው የሆነው ኢንስቲትዩት እንዲያድግ ዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ የተቻለውን ድጋፍ እንደሚያደርግም ፕሬዚዳንቱ ገልጸዋል።
የኤችኤስቲ ኮንሰልቲንግ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ተወካይ አቶ ጎበዜ ደሳለኝ የተጀመረው ይህ ጉዞ የንግድና የፉክክር ጉዳይ እንዳልሆነ፣ ይልቁንም እጅ ለእጅ ተያይዞ ሙያውን አንድ ዕርምጃ ወደፊት ለመውሰድ፣ የሥራ ልምድንና ዕውቀትን ለቀጣዩ ትውልድ ለማስተላለፍ የሚያስችል ወሳኝ ምዕራፍ ነው ብለዋል።