የፌዴራል ሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ሙስናን አስመልክቶ ያለውን ግንዛቤ የተመለከተ የዳሰሳ ጥናት በማካሄድ፣ የመሬትና የገቢዎች ተቋማትን ጨምሮ በበርካታ ተቋማት ውስጥ ሙስና አሳሳቢ መሆኑን አረጋግጫለሁ አለ፡፡
የመሬት አስተዳደርና የይዞታ ምዝገባ፣ የገቢዎችና ታክስ ጽሕፈት ቤቶች፣ የኮንስትራክሽን ፈቃድ ቁጥጥር፣ የንግድና ትራንስፖርት ቢሮዎች፣ የወረዳና የቀበሌ አስተዳደሮች በከፍተኛ ደረጃ ለሙስና ተጋላጭ መሆናቸው በጥናቱ ተለይቷል ብሏል፡፡
ኮሚሽኑ ለዳሰሳ ጥናት በተወሰደ ናሙና ከ60 በላይ የሚሆኑት ኢትዮጵያውያን ሙስና በማኅበራዊ፣ በኢኮኖሚያዊና በፖለቲካዊ ተግባራት ከፍተኛ እንቅፋትና ችግር የፈጠረ አሳሳቢ ችግር መሆኑን እንደነገሩት ገልጿል፡፡
በአቋራጭ የመበልፀግ ፍላጎት፣ የሥነ ምግባር ጉድለት፣ ውስብስብና ግልጽ ያልሆኑ የአገልግሎት አሰጣጥ ሒደቶችና የሕግ ማስከበር ድክመቶች ለሙስና መስፋፋት ዋነኛውንና ቀዳሚውን ድርሻ እንደሚይዙ የኮሚሽኑ የጥናት ሪፖርት ያመለክታል፡፡
በጥናቱ ጉቦ ለመስጠት የሚገደዱ ሰዎች ለድርጊታቸው የሚያቀርቡት አንዱ ምክንያት አገልግሎቱን ለማግኘት ሌላ አማራጭ በማጣታቸው እንደሆነ ተገልጿል፡፡ ግለሰቦች ጉቦ የሚሰጡት የሚፈልጉት አገልግሎት እንዲፈጸምላቸውና የሚጠበቅባቸውን ባለማድረጋቸው ሊደርስባቸው የሚችለውን እንግልት ለማስቀረት መሆኑን ጥናቱ ያመለክታል፡፡ የሙስና ድርጊትን ለመጠቆም የሚፈልጉ ግለሰቦች ሊደርስባቸው የሚችል የበቀል ዕርምጃና የማስፈራራት ሥጋት በመኖሩ፣ አስተማማኝ የጠቋሚዎች ጥበቃ ሥርዓት ማነስ፣ እንዲሁም የጥቆማ አሰጣጥ ሒደቱ ረዥምና ውስብስብ መሆን ኅብረተሰቡ ሙስና ለመጠቆም ሥጋት እንዳለበት በጥናቱ መገለጹ ተነግሯል፡፡
በጥናቱ እንደተገለጸው 75 በመቶ የሚሆኑት ተሳታፊዎች በሙስና ጥፋተኞች ላይ ጠንካራ፣ ፈጣንና አስተማሪ የሆነ የሕግ ቅጣት መጣል፣ የተመዘበረ ሀብት እንዲመለስ ማድረግ ሙስናን ለመቀነስ ውጤታማ ዕርምጃ ናቸው፡፡
ኮሚሽኑ የሙስና ወንጀል ሕግ የማስከበር የአሠራር ሥርዓት ግልጽነት በተመለከተ አካሄድኩት ባለው ጥናት የሙስና ወንጀል ሕግ ማስከበር ግልጽ፣ ተገማችና ውጤታማ እንዲሆን ተጨማሪ የአሠራር ማሻሻያዎች እንደሚስፈልጉት ገልጿል፡፡ አክሎም የሙስና ወንጀል የሕግ ማስከበር አሠራር ግልፅ፣ ተጠያቂነት ያለው፣ ተገማችና ውጤታማ እንዲሆን ቀጣይነት ያለው ማሻሻያ ማከናወን ያስፈልጋል ብሏል፡፡
From The Reporter Magazine
የሙስና ወንጀል የሕግ ማስከበር ሒደት ውስጥ የሚሳተፉ ተቋማት በመረጃ ልውውጥና በውሳኔ አፈጻጸም ላይ መዘግየቶች በምርመራ፣ በክስ አቀራረብና በፍርድ ሒደቶች ላይ አሉታዊ ጫና ማድረሳቸው ተጠቁሟል፡፡ የምርመራ ሒደት የማስረጃ አሰባሰብ ውስንነት፣ የዲጂታልና የፎረንሲክ ምርመራ አቅም ውስንነት፣ እንዲሁም የሠለጠነ የሰው ኃይል እጥረት ለሙስና ወንጀል ምርመራዎች መሰናክል መሆናቸውን በጥናቱ ተመላክቷል፡፡