- ከ15 በላይ በሚሆኑ ድርጅቶች ላይ ሕጋዊ ዕርምጃ መወሰዱ ተገልጿል
በኢትዮጵያ የሚገኙ አብዛኛዎቹ የኦዲት ተቋማት ከስታንዳርድ በታች እየሠሩ መሆናቸው በኦዲት ጥራት ግምገማ ማረጋገጡን፣ የኢትዮጵያ ሒሳብ አያያዝና ኦዲት ቦርድ አስታወቀ፡፡
ቦርዱ ባለፉት አራት ዓመታት በ190 የኦዲት ድርጅቶች ላይ ያካሄደውን የጥራት የግምገማ ሪፖርት፣ ነሐሴ 4 ቀን 2018 ዓ.ም. የተለያዩ ኦዲት ድርጅቶችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ባሉበት ባካሄደው አገር አቀፍ ኮንፈረንስ ለመጀመሪያ ጊዜ ይፋ አድርጓል።
የኢትዮጵያ ሒሳብ አያያዝና ኦዲት ቦርድ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ፍቃዱ አጎናፍር፣ በቦርዱ ተመዝግበው አገልግሎት እየሰጡ ከሚገኙ 231 ከሚደርሱ የኦዲት ድርጅቶች ውስጥ፣ በ190 ድርጅቶች ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ ከ2014 ዓ.ም. አጋማሽ እስከ 2018 ዓ.ም. መጨረሻ የኦዲት ጥናት ግምገማ መደረጉን ለሪፖርተር ተናግረዋል።
በተደረገው የኦዲት ጥራት ምርመራ መሠረት ሁሉም ድርጅቶች ተመሳሳይ አቋም ላይ መሆናቸውን፣ በርካቶቹም የኦዲት ጥራት ስታንዳርዶችን ተከትለው የመሥራት ችግር እንደተገኘባቸው ገልጸዋል። የተጠናከረ የተቋም አደረጃጀት ክፍተት፣ የሰው ኃይል አቅርቦት፣ የአቅም ግንባታ ውስንነት በአብዛኞቹ ድርጅቶች ውስጥ መስተዋሉን ጨምረው አስረድተዋል።
የቦርዱ የኦዲት ጥራት ግምገማ ባለሙያ አቶ በርናባስ አያሌው በበኩላቸው፣ በ2014 ዓ.ም. በሦስት፣ በ2015 ዓ.ም. በ22፣ በ2016 ዓ.ም. በ18፣ በ2017 ዓ.ም. በ60 እና በ2018 ዓ.ም. በ87 ድርጅቶች ላይ ግምገማው መደረጉን ተናግረዋል። ግምገማው የተደረገባቸው ድርጅቶች በኦዲት ተደራጊ ተቋማትና በኦዲት አድራጊ ተቋማት መካከል ሙያን የተከተለ ግንኙነት አለመኖር፣ የሠለጠነ የሰው ኃይል አነስተኛ መሆን፣ ፖሊሲዎችንና አሠራሮችን የተከተለ የአደጋ ሥጋት ግምገማ ያለማድረግ ችግሮች መኖራቸው መረጋገጡን ገልጸዋል።
ነፃና ገለልተኛ ሆኖ በሥነ ምግባር መሠረት የመሥራት፣ የአስተዳደርና የአመራር፣ የሰው ሀብት፣ የድርጊት መርሐ ግብርና ዕቅድ አለማውጣት፣ የቴክኖሎጂና የሰው ሠራሽ አስተውሎት ችግሮች መሆናቸውን ጠቁመዋል።
የኦዲት ድርጅቶቹ ዓለም አቀፍ ስታንዳርዶችን ተከትለው ገለልተኛና ተዓማኒ የሆነ የኦዲት ሥራ መሥራት እንዳለባቸው፣ የአደጋ ሥጋትን መሠረት ያደረገ ግምገማ ማድረግ እንደሚኖርባቸውም አሳስበዋል።
From The Reporter Magazine
ትክክለኛውን የፖሊሲና የአሠራር ሥርዓት ተከትሎ አለመሥራት፣ የፋይናንስ ኦዲት ዕቅድ አለመኖር፣ የፋይናንስ ሪፖርት ሲሠራ የአደጋ ግምገማን አለማካተት መሠረታዊ ችግሮች መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ የቦርዱ የኦዲት ጥራት ምርመራ ባለሙያ አቶ አበራ ዘውዱ ናቸው።
የኦዲት ሥራዎች በዶክመንት የተሰነዱ አለመሆን በአብዛኛው የኦዲት ድርጅቶች ውስጥ መስተዋሉን፣ በዚህም ምክንያት አዳዲስ መመርያዎችና ስታንዳርዶቹን ተከትለው እንዲሠሩ ጠይቀዋል።
በግምገማው የተገኙ እነዚህና ሌሎች ግኝቶች በመጨረሻ በፋይናንስ ኦዲት ሪፖርት ጥራት የራሳቸውን ተፅዕኖ እንደሚያመጡ አቶ ፍቃዱ ገልጸዋል። ቦርዱ ግምገማ ሲያደርግ የታዩ ችግሮችን እንዲያስተካክሉና እንዲያርሙ ማሳወቁን፣ የድርጊት መርሐ ግብር አውጥተው እንዲሠሩና የአቅም ግንባታ ሥልጠና እንዲሰጡ እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል።
From The Reporter Magazine
ቦርዱ ከተያዘው ወር ጀምሮ በየበጀት ዓመቱ አዲስ የግምገማ ጥራት እንደሚያደርግ፣ ድርጅቶቹ ከመጀመሪያው ግምገማ የተገኙ ችግሮችን በግብዓትነት ወስደው እንዲያስተካክሉ፣ በቀጣይም የፋይናንስ ኦዲት ሪፖርት በተገቢው ጥንቃቄ እንዲያከናውን፣ በዚህ መሠረት የማይሠሩ ከሆነ ተጠያቂ እንደሚሆኑ ለማሳወቅ ኮንፈረንሱ መዘጋጀቱን ገልጸዋል።
ቦርዱ የሕዝብን ጥቅም የማስጠበቅ ኃላፊነት እንዳለበት፣ ይህንንም ፈቃድ ሰጥቶ በሚያስተዳድራቸው በእነዚህ የኦዲት ድርጅቶች አማካይነት እንደሚወጣ ተናግረዋል። እነዚህ ድርጅቶች ከተቋም አደረጃጀትና ከሰው ኃይል አንፃር የተሻለ አቅምና ቁመና ሊኖራቸው እንደሚገባ፣ የተቋም ቀጣይነት ሪፖርት ማዘጋጀት እንዳለባቸው፣ ለዚህም ኢንቨስት ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው፣ እነዚህና መሰል ችግሮች ሲፈቱ የፋይንናስ ኦዲት ጥራት ይጨምራል ተብሎ እንደሚጠበቅ፣ ይህ ካልሆነና የፋይናንስ ጥራት ካልጨመረ ግን ቦርዱ የሚወስደውን አስተዳደራዊ ዕርምጃ እንደሚያጠናክር አስታውቀዋል። ከዚህ በፊት ሕጉን የማለማመድና የማሳወቅ ሥራዎች በስፋት ሲሠሩ እንደነበር፣ ከዚህ በኋላ ግን ተገቢው ሕጋዊ ዕርምጃ በተጠናከረ መንገድ እንደሚወሰድ አስጠንቅቀዋል።
ቦርዱ እስካሁን ባደረገው ግምገማ ሕጋዊ ዕርምጃ የወሰደባቸው ተቋማት መኖራቸውን በተመለከተ ሪፖርተር ጥያቄ የቀረበላቸው አቶ ፍቃዱ ጫፍ የወጡ፣ ስታንዳርድ ያልጠበቁ፣ የሕዝብንና የኩባንያውን ጥቅም ያላስጠበቁ ከ15 በላይ ድርጅቶች ተጠያቂ መደረጋቸውን፣ ፈቃዱ የተቀማና ዕገዳ የተጣለበት መኖሩንም አስረድተዋል።
የቦርዱ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሙብሸት ታደሰ የተደረገው የኦዲት ጥራት ግምገማ የሕዝብ ተጠያቂነትንና ግልጽነትን ለማስፋት በሚያስችል መንገድ መከናወኑን፣ በቀጣይም ተጠናክሮ የሚቀጥል አገራዊ ጅምር መሆኑን ገልጸዋል። ቦርዱ በፋይናንስ ሪፖርቶች ላይ የተካሄዱ የጥራት ግምገማ ግኝቶችን ይፋ ለማድረግ ዝግጅት ማጠናቀቁንም አረጋግጠዋል።