እንደ ኢትዮጵያ ላሉ የባህር በር ለሌላቸው አገሮች የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ በትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ትስስር መዋዕለ ንዋይ በማፍሰስ የምትጫወተው ሚና ከፍተኛ መሆኑን፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የምሥራቅ አፍሪካ አማካሪ አቶ ጌታቸው ረዳ ተናገሩ፡፡
የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ከተባበሩት ዓረብ ኤምሬት ስትራቴጂ ጥናትና ምርምር ማዕከል፣ እንዲሁም አንዋር ጋርደስ የዲፕሎማቲክ አካዴሚ ከተሰኘ ተቋም ጋር በመሆን ‹ሂሊ ዲያሎግ የተሰኘ› የምክክር መድረክ ሰኔ 19 ቀን 2018 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ተካሂዷል፡፡
በውይይቱ የተገኙት የጠቅላይ ሚኒስትሩ የምሥራቅ አፍሪካ ጉዳዮች አማካሪ አቶ ጌታቸው ረዳ ባደረጉት ንግግር፣ ኢትዮጵያ ወደብ አልባ አገር በመሆኗ አሳሳቢ ችገሮች እያጋጠሟት መሆኗን ገልጸዋል፡፡ የወደብና የባቡር መስመሮች መተሳሰር ትልቅ ኢንቨስትመንት የሚፈልግ በመሆኑ፣ ይህንን ትስስር እንደ ተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ ያሉ የተሻለ አቅም ያላቸውን አጋሮች ሳያሳትፉ ማከናወን አይቻልም ብለዋል፡፡
በአፍሪካ በትራንስፖርት መተሳሰር፣ የወደቦችን አቅም ማሳደግ፣ የባቡር መስመሮችን መዘርጋት ጨምሮ በሎጂስቲክስ መሠረተ ልማቶች የተሻለ አቅም ያለው አጋር እንደሚያስፈልግ አስረድተዋል፡፡ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስን ጨምሮ ባልተነካው የአፍሪካ ሀብት ላይ መዋዕለ ንዋያቸውን በማፍሰስ ሊሰማሩና የሚታዩ ችግሮችን ሊፈቱ ያስፈልጋል ብለዋል፡፡ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ በወደብ ልማት ካላት ከፍተኛ ፍላጎትና ባላት ሚና አሁን አሳሳቢ የሆኑ የሎጂስቲክስ ችግሮችን ለመፍታት ብቻ ሳይሆን፣ የንግድ ስብጥርን በማሳደግ ጭምር አትራፊ እንደሚሆንላት አብራርተዋል፡፡
አቶ ጌታቸው በኢትዮጵያ ስላለው የቢዝነስ ምኅዳር ሲያብራሩ፣ ኢትዮጵያ ምኅዳሩን ምቹ ለማድረግ ከፍተኛ ፕሮጀክቶችን እያንቀሳቀሰች ነው ብለዋል፡፡ የከተማ ማስዋብ ሥራው (የኮሪደር ልማት) ለዜጎችና ለኢንቨስተሮች ዕድል የፈጠረ ነው ሲሉ ገልጸውታል፡፡ በተጨማሪም ወደ ኢትዮጵያ የሚመጡ ኢንቨስተሮች ኢትዮጵያ ያላትን የተደላደለ አቅም ለመጠቀም እየረዳቸው ነው ብለዋል፡፡ መንግሥት የዲጂታል ሥርዓቱን እያቀለለው መጥቷል ያሉት አቶ ጌታቸው፣ ለረዥም ጊዜ ይወስድ የነበረው የንግድ ምዝገባ አሁን ቀላል በመሆኑ፣ ኢትዮጵያን ለውጭ ባለሀብቶች ምቹ በማድረግ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ ጭምር የሚስብ መሆኑን አክለዋል፡፡
በውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ተመራማሪ ዳርእስከዳር ታዬ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ መንግሥት እያካሄደ ያለው ከፍተኛ ኢንቨስትመንት አዲስ አበባን ከዋና ዋና የክልል ከተሞች እያገናኘ ነው ብለዋል፡፡ መንግሥት በከተሞች እያካሄደ ያለውን የኮሪደር ልማት ሥራ ዜጎች ከጅምሩ የፕሮጀክቶቹን ውጤት ለመረዳት ተቸግረው የነበረ ቢሆንም፣ አሁን ግን ለውጡን ሲያዩ መንግሥት ለሚያከናውናቸው ሥራዎች አዎንታዊ አመለካከት እየያዙ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
አቶ ጌታቸው በበኩላቸው የመሠረተ ልማት ፕሮጀክት ሲጀመር ሥራው ለሕዝቡ ፍላጎት ቢሆንም የግል ቅሬታዎች መኖራቸው አይቀሬ ነው በማለት ገልጸው፣ ቤቶችን ማፍረስ የዜጎችን ሕይወት ከመቀየር አንፃር ታስቦ የሚሠራ ቢሆን እንኳ የሚቀርቡ የግል ቅሬታዎችን ሕጋዊ በሆነ መንገድ መፍታቱ የሕዝብ እርካታ እንደሚያመጣ ተናግረዋል፡፡ በከተሞች የኮሪደር ልማት ተብለው የሚጠሩ ፕሮጀክቶችን ጥቅም ዜጎች እየተረዱ ነው በማለት ተናግረዋል፡፡
From The Reporter Magazine
የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ ኢኮኖሚና ቱሪዝም ሚኒስቴር ተወካይ ታሪክ ሱዋደይ፣ ‹‹አፍሪካ ውስጥ ታማኝ ወዳጅ እንፈልጋለን፤›› ብለው፣ ለዚህም በኢትዮጵያና በተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ መካከል ያለው ግንኙነት ለአፍሪካ እንደ ሞዴል የሚወሰድ ነው ሲሉ ገልጸውታል፡፡ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ ፋይናንስ ብቻ ሳይሆን የተለያዩ ፓኬጆችን በማቅረብ ቀጣናዊ ትስስርን ትደግፋለች ብለዋል፡፡
የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ በኢትዮጵያ በኢንዱስትሪ፣ በግብርናና ሎጂስቲክስ ዘርፎች 2.9 ቢሊዮን ዶላር መዋዕለ ንዋይ በማፍሰስ በኢትዮጵያ ትልቋ የመካከለኛው ምሥራቅ ኢንቨስተር ስትሆን፣ ሁለቱ አገሮች ሦስት ቢሊዮን ዶላር የሚገመት ግብይት በራሳቸው ገንዘብ ለመገበያየት ስምምነት ማድረጋቸው ይታወሳል፡፡
