
በጊዜያዊ አስተዳደርም ሆነ በጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዚዳንት መቀጠል አያስፈልግም የሚል ውሳኔ ላይ የደረሰው ሕወሓት፣ በመጨረሻ ከጦርነቱ በፊት በተደረገው ምርጫ ተመሥርቶ የነበረው መንግሥት በትግራይ እንዲመለስ ውሳኔ አሳልፏል፡፡ ምርጫው በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ዕውቅና የተነፈገውና ሕገወጥ የተባለ መሆኑ ይታወሳል፡፡ ምርጫው ለትግራይ ጦርነት መጀመር አንዱ መነሻ ምክንያት መሆኑም ይታወቃል፡፡ ፌዴራል መንግሥት ምርጫውን ‹‹የጨረባ ምርጫ›› ብሎ ቢያወግዘውም፣ ሕወሓት ግን ወደ 2.8 ሚሊዮን የትግራይ ሕዝብ ድምፁን የሰጠበት፣ በሰፊ ብልጫ ሕወሓት አሸንፎ ክልላዊ መንግሥት የመሠረተበትና የድርጅቱ መሪ ደብረ ጽዮን ገብረ ሚካኤል (ዶ/ር) የክልሉ ፕሬዚዳንት የሆኑበት ‹‹ሕጋዊ ምርጫ›› መሆኑን ሲሟገት ቆይቷል፡፡


የሕወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ ውሳኔ የፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነትን ያፈርሳል ብለዋል
ጦርነቱን ባስቆመው የፕሪቶሪያ ሰላም ስምምነት መሠረት ከጦርነቱ በፊት ተመሥርቶ የነበረው መንግሥት እንዲፈርስና ጊዜያዊ አስተዳደር በትግራይ ክልል እንዲመሠረት፣ የስምምነቱ ፈራሚዎች ሕወሓትና ፌዴራል መንግሥቱ መግባባት ላይ መድረሳቸው ይታወሳል፡፡ ይሁን እንጂ በክልሉ ለሁለት ዓመታት ከቆየው ከአቶ ጌታቸው ረዳ ጊዜያዊ አስተዳደር መፍረስ ወዲህ የፕሪቶሪያ ስምምነት መፍረሱን የሚጠቁሙ መግለጫዎች ከሕወሓት አመራሮች ሲሰጡ የቆዩ ሲሆን፣ ከጦርነቱ በፊት የነበረውና በደብረ ጽዮን (ዶ/ር) የሚመራው መንግሥት በትግራይ ይመለስ የሚል ሙግት ሲነሳም ቆይቷል፡፡
እሑድ ሚያዝያ 11 ቀን 2018 ዓ.ም. ይፋ የሆነው የሕወሓት መግለጫ በክልሉ ከጦርነቱ በፊት የነበረው ክልላዊ አስተዳደር ምክር ቤት ወደ ሥራ እንዲመለስ የድርጅቱ ማዕከላዊ ኮሚቴ መወሰኑን አረጋግጧል፡፡ ‹‹መከተ ምክር ቤት›› የሚባለው የሕወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ አባላትንና ወታደራዊ አመራሮችን ያሰባሰበውን ምክር ቤት ጨምሮ፣ ሁሉንም የትግራይ የፖለቲካ ኃይሎችን ያቀፈ መንግሥት በክልሉ እንዲመሠረት ሕወሓት መወሰኑን መግለጫው ጠቁሟል፡፡ ከፌዴራል መንግሥቱት ጋር ያሉ አለመግባባቶችን በንግግር ለመፍታት ሕወሓት ዝግጁ መሆኑን የጠቀሰው መግለጫው፣ ከሌሎች ወንድም ሕዝቦችና ክልሎች እንዲሁም ከጎረቤት አገሮች ጋር መልካም ግንኙነቶችን ለማጠናከር እንደሚፈልግም ይገልጻል፡፡
ይህ የሕወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ ውሳኔ በትግራይ ክልል ባለፉት ሦስት ዓመታት በሥራ ላይ የቆየውን የጊዜያዊ አስተዳደር ብቻ ሳይሆን የፕሪቶሪያ ስምምነትንም የሚያፈርስ ውሳኔ ነው እየተባለ ነው፡፡ በክልሉ ምርጫ ተደርጎ በሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ መንገድ መደበኛ መንግሥት እስኪመሠረት ተብሎ ከፕሪቶሪያ ስምምነት በኋላ የተመሠረተው ጊዜያዊ አስተዳደር፣ በቅርቡ በፌዴራል መንግሥት ለአንድ ዓመት ቆይታው እንዲራዘም መወሰኑ ይታወሳል፡፡ ይህንን የፌዴራል መንግሥቱን ውሳኔ የተቃወመው ሕወሓትም ከሰሞኑ ተከታታይ ስብሰባዎችን ሲያደርግ የቆየ ሲሆን፣ በስተመጨረሻም ጊዜያዊ አስተዳደሩን ወደ ጎን በመተው ከጦርነቱ በፊት የነበረው አስተዳደር በክልሉ እንዲመለስ መግባባት ላይ መደረሱን የሚጠቁም መግለጫ ይፋ አድርጓል፡፡
ለዚህ የሕወሓት ውሳኔ የፌዴራል መንግሥቱ ምን ዓይነት ምላሽ ይሰጣል የሚለው ጉዳይ ደግሞ በሰፊው እያነጋገረ ነው፡፡ የፌዴራል መንግሥቱ በዚህ ጉዳይ ዝም ማለትና አያገባኝም ብሎ ማለፍ ይችላል ወይ የሚል ሙግትም እየተነሳ ነው፡፡ ሕወሓት ከስድስት ዓመት በፊት በተደረገ ምርጫ ክልላዊ መንግሥት የመመሥረት ሥልጣን አለው ወይ ከሚለው ጀምሮ ሕወሓት የወሰደው ዕርምጃ፣ ለሌሎች ክልሎች የሚኖረው አርዓያና ልምምድ ምን ሊሆን ይችላል የሚለው ጉዳይም ክርክር እያስነሳ ነው፡፡
የትግራይ ፖለቲካን በተመለከቱ ጉዳዮች በቅርበት የሚከታተሉትና ትንተናዎችን በመስጠት የሚታወቁት የሕግ ባለሙያና የፖለቲካ ተንታኙ አቶ ዳንኤል ብርሃኔ፣ ጊዜያዊ አስተዳደሩ ሲራዘም ጀምሮ ይህን ዓይነት ውዝግብ ሊፈጠር እንደሚችል እንደሚታወቅ ይገልጻሉ፡፡
‹‹ጊዜያዊ አስተዳደሩን ፌዴራል መንግሥቱ ያለ ሕወሓት ዕውቅናና ተሳትፎ የአንድ ዓመት ቆይታው እንዲራዘም የወሰነው ከዚያ ውሳኔ የሚገኝ የፖለቲካ ትርፍን አሥልቶ ነው፡፡ ይህ እንደሚመጣ ሳያውቀው ቀርቶ አይደለም፡፡ ሕወሓት መግለጫ ሲያወጣ ፌዴራሉ እስካሁን ምንም ምላሽ ያልሰጠውም ለዚያ ነው፡፡ በሁለተኝነት ሕወሓት የቀደመው አስተዳደር እንዲመለስ ከመግባባት ላይ መደረሱን ተናገረ እንጂ በተጨባጭ አላደረገውም፡፡ በመርህ ደረጃ የወሰነው እንጂ በተግባር እንዴት እንደሚተረጎም ያደረገው ነገር የለም፡፡ ፌዴራል መንግሥቱም ቢሆን በተጨባጭ እንቅስቃሴ በሌለበት ለምን ብሎ የአፀፋ ዕርምጃ ሊወስድ ይችላል? በኮሙዩኒኬሽን ተቋሙ መግለጫ ሊያወጣ ይችላል፣ ከዚያ ውጪ ግን ወደ ዕርምጃ ለመግባት ይቸኩላል ብዬ አልገምትም፡፡ የጊዜያዊ አስተዳደሩ ወደ ጽሕፈት ቤት እንዳይገባ ሲደረግ፣ የጊዜያዊ አስተዳደሩ ተሿሚዎች ከሥራ ሲሰናበቱ፣ ወይም አዲስ ምክር ቤት ሲደራጅና ሌላም ተጨባጭ ዕርምጃ ሲወሰድ ፌዴራሉ ጠብቆ በተግባር አፀፋ ሊሰጥ ይችላል፡፡ ከዚያ ውጪ ግን በመግለጫ ተመጣጣኝ አፀፋ ከመስጠት በዘለለ ወደ ሌላ ጉዳይ አይገባም ብዬ እገምታለሁ፤›› በማለት ተናግረዋል፡፡
From The Reporter Magazine
ይሁን እንጂ እሳቸው ከሚሉት በተቃራኒ ፌዴራል መንግሥቱ ይህን የሕወሓትን ውሳኔ በዝምታ ማለፍ የማይችልበት ሕጋዊ ግዴታ እንዳለበት የሚጠቅሱ አሉ፡፡ በአንድ ክልል ከፍተኛ የበላይነት ያለው አንድ የፖለቲካ ኃይል በፌደሬሽኑ ሕጎችና በፌዴራል መንግሥቱ ውሳኔ አልገዛም በሚልበት ወቅት ችግሮች የሚፈቱት በምን መንገድ ነው? ከሚለው ጉዳይ ጀምሮ ሕወሓት ይህን ውሳኔ የመወሰን ሥልጣን አለው ወይ? ክልሉን ወደ ቀደመ አስተዳደር የመመለስ መብት አለው ወይ? ፌዴራሉ ይህ ሲሆን ዝም እንዲል ሕጉና የተጣለበት አገር የመምራት ኃላፊነት ያስችለዋል ወይ? የሚሉ ጠንካራ ጥያቄዎችን ጭምር ጉዳዩ እያስነሳ ነው የሚገኘው፡፡
ይህን በሚመለከት አቶ ዳንኤል ሲናገሩ፣ ‹‹ፌዴራል መንግሥቱ ማድረግ ያለበትንና እያደረገው ያለውን ነገር ለያይተን ማየት አለብን፤›› በማለት ይገልጻሉ፡፡ ‹‹ፌዴራል መንግሥቱ እስካሁን ማድረግ እያለበት ያላደረጋቸው ብዙ ነገሮች አሉ፡፡ አሁንም ቢሆን ማድረግ ያለበትን እንንጋገር ከተባለ ተጨባጭ እንቅስቃሴ በሌለበት ለተሰጠ አንድ ፖለቲካዊ መግለጫ የምትሰጠው አፀፋ ፖለቲካዊ መግለጫ ብቻ ነው መሆን ያለበት፡፡ ሕወሓት በመግለጫው የጠቀሰውን ነገር በተግባር ወደ መተርጎም ልግባ ካለ ያን ጊዜ ምን ምላሽ ሊሰጥ እንደሚችል መነጋገር ይቻላል፡፡ በሌላ በኩል ፌዴራል መንግሥቱ ሊያደርግ የሚገባውንና ሳያደርግ የቀረውን ነገር እናውራ ከተባለም ብዙ ነጥቦችን ማንሳት ይቻላል፡፡ ከሕወሓት ጋር ምንም ግንኙነትና ንግግር ሳያደርግ ከፕሪቶሪያ በፊት የነበሩ ሕጎችን ጠቅሶ ለብቻው የጊዜያዊ አስተዳደሩን ሥልጣን ማራዘሙ ሲያሳውቅ፣ ከሕወሓት ሊመጣ የሚችለውን አፀፋ ገምቶ ነው ያደረገው፡፡ ፌዴራል መንግሥቱ የራሱን ሥሌት መሠረት አድርጎ እንጂ ማድረግ የሚጠበቅበትን ነገር ለማድረግ ብሎ አይደለም ጊዜያዊ አስተዳደሩን በተናጠል ውሳኔ ያራዘመው፡፡ በሕወሓት መግለጫ ፕሪቶሪያ ፈርሷል ብሎ ለማወጅ ፌዴራል መንግሥቱ ምክንያት እየፈለገ ከሆነ አሁን ያንን ግብ አሳካሁ ሊል ይችላል፡፡ ከዚያ ውጪ ግን ነገሩ ወደ ወታደራዊ እንቅስቃሴ ሊያስገባ ይችላል የሚለውም አያስኬድም፡፡ ምክንያቱም ሕወሓትና ፌዴራል መንግሥቱ ከፕሪቶሪያ ማግሥት ጀምሮ እርስ በእርስ ከሚያሰሙት መካሰስ አንፃር እስካሁን ወደ ጦርነት ለመግባት በቂ መነሻዎች ነበሯቸው፡፡ ለጦርነት ምክንያት እስካሁን አጥተው የአሁኑ ሁኔታ ወደ ጦርነት ይወስዳቸዋል የሚል ግምት የለኝም፡፡ ለጦርነት ምቹ የሆኑ ዓለም አቀፍ ሁኔታዎች ስላጡ ወይም በራሳቸው ግል ምክንያት ነው እስካሁን ጦርነት ሳይከፍቱ የቆዩት፡፡ ጊዚያዊ አስተዳደሩ አሁን ሥራውን ቢያቆም ፌዴራል መንግሥቱ በዚህ ብቻ ወደ ኃይል ዕርምጃ ይገባል ብዬ አላስብም፤›› በማለት ሐሳባቸውን አካፍለዋል፡፡
በእሳቸው ግምት ቲፒኤፍ ወይም ሀራ መሬት የሚባለው የፌዴራል መንግሥቱ ይደግፈዋል የሚባለው ኃይልም ቢሆን በዚህ መነሻነት ዕርምጃ ለመውሰድ የሚያስችል የራሱ አቅም ያለው ኃይል ነው፡፡ ሀራ መሬት ተብለው የተደራጁ ሰዎች በፌዴራል ዕገዛም ሆነ በራሳቸው ሕወሓትን ለመውጋት ምቹ ነው ብለው የሚያስቡት ሁኔታ የመሟላቱን አጋጣሚ እንደሚጠብቁ ነው የሚጠቅሱት፡፡
From The Reporter Magazine
‹‹ያለፈው ጦርነትም ቢሆን በምርጫ ብቻ አይደለም የተጀመረው፡፡ ምርጫው እንደ አንድ ተደማሪ ግብዓት ወይ ምክንያት ሆኖ ነበር ያገለገለው፡፡ አሁንም ቢሆን ሕወሓት በ2012 ዓ.ም. ምርጫ የተመሠረተው መንግሥት ይመለስ የሚል መግለጫ ስላወጣ ብቻ ተነስተህ ወደ ጦርነት አትገባም፡፡ ሌሎች የምትከፍተውን ጦርነት ቅቡልነት እንዲኖረው የሚያደርጉልህ ነገሮች እስኪሟሉ ትጠብቃለህ፡፡ ፌዴራል መንግሥቱ ይህ ነገር እንደሚመጣ እያወቀ ነው የጊዜያዊ አስተዳደሩን ቆይታ ያራዘመው፡፡ ሕወሓቶች ያን ውሳኔ ዕውቅና የመንፈግና ከጨዋታ ውጪ የመደረግ ውሳኔ ነው ብለው እንደሚወስዱትና የራሳቸውን አፀፋ እንደሚሰጡም ያውቃል፡፡ እንኳን እነሱ እኛም በርቀት ፖለቲካ ምንተነትነው ይህ እንደሚሆን ገምተናል፡፡ አሁንም ቢሆን ከዚያ ስሌታቸው አንፃር ነው ሁለቱም የሚንቀሳቀሱት፡፡ ከዚህ ግምት ውጪ ውሳኔው በትግራይ ፖለቲካ ኃይሎች መካከል ልዩነት ፈጥሮ ወደ እርስ በእርስ ግጭት ከተገባ፣ ይህ ደግሞ በፌዴራል መንግሥቱ ዘንድ ዕርምጃ ለመውሰድ አመቺ አጋጣሚ ነው ተብሎ ከታመነበት ወደ ጦርነት ሊገባ ይችላል፤›› በማለት ነው ጉዳዩ የአዲስ ጦርነት መነሻ በቀላሉ እንደማይሆን ያስረዱት፡፡
ፌዴራል መንግሥቱና ሕወሓት ይህን አዲስ ውዝግብ የፈጠረ ጉዳይ ከጦርነት ውጪ በሆኑ አማራጮች ለመፍታት የሚችሉባቸው ሥልቶች አሉ ወይ? የሚለው ጥያቄም ብዙ እያነጋገረ ነው፡፡ የጊዜያዊ አስተዳደሩን ሕወሓትን ባሳተፈ መንገድ ዳግም እንዲዋቀር ማድረግ ይቻላል ወይ? የፕሪቶሪያ ስምምነትን መተግበር ካልሆነም መከለስና ዳግም ድርድር ከማድረግ ጀምሮ ሕወሓትን ሕጋዊ ሰውነት እስከ መመለስ ያሉ አማራጮች ሊተገበሩ ይችላሉ ወይ? የሚሉ ነጥቦች ሁሉ እየተነሱ ነው፡፡
ከጦርነት በመለስም ቢሆን በዚህ ውሳኔ የተነሳ ትግራይ ክልል ከፌዴራል መንግሥት ጋር የነበረው የሳሳ ግንኙነት ጨርሶ ወደ መቋረጥ ሊገባ እንደሚችል አንዳንዶች እየሠጉ ነው፡፡ ከዚህ ከፍ ያለ ሥጋት የሚያነሱ ወገኖች ደግሞ ትግራይ እንደ ሶማሌላንድ ሆና መገንጠልም ሆነ ፌዴሬሽኑን ሙሉ ለሙሉ ተቀላቅሎ መኖር ሳትችል በውዝግብ ልትቀጥል ትችላለች የሚል ግምት ሲሰጡም ይሰማል፡፡
አቶ ዳንኤል ግን ወደ እዚህ ነገር መገባት የለበትም የሚል ሐሳብ ነው የሚሰጡት፡፡ የሶማሊያን ንፅፅር እንውሰድ ከተባለም ለንፅፅር ቅርብ የምትሆነው ሶማሌላንድ ሳትሆን የፑንትላንድ ከፊል ራስ ገዝ ግዛት ጉዳይ የተሻለ እንደሆነ ነው የተናገሩት፡፡
‹‹ፑንትላንድ አገር ነኝ ብላ አላወጀችም፡፡ ቀጥታ ቁጥጥር ባይደረግባትም በሶማሊያ ውስጥ መሆኗን ዕውቅና ነፍጋ አታውቅም፡፡ መጠርጠር ቢቻልም ነገር ግን ለመገንጠል መፈለጓንና አለመፈለጓን በእርግጠኝነት መናገር አንችልም፡፡ ለረዥም ዓመታት በዚህ መንገድ ነው ስትመራ የቀጠለችው፡፡ ራሷን እያስተዳደረች ከሶማሊያ ጋር ሆና ስትቀጥል ነው ያየነው፡፡ ይህ ለሕወሓት ንፅፅር ሊሆን ቢችልም ሕወሓት እንደ ሶማሌላንድ ትግራይን ገንጥሎ አገር ለማወጅ ዓላማ ፍላጎት ኖሮት አያውቅምም፣ አሁንም የለውም፡፡ ይህ ግምት የመሀል አገር ፖለቲከኞች ሰፊ ግምት እንደሆነ ቢገባኝም፣ ነገር ግን ስለሕወሓት ፖለቲካ ልሂቃን ካለ የተሳሳተ ግምት የመነጨ ግምት ነው፡፡ ሕወሓት የራስን ዕድል በራስ የመወሰን መብትን የሚጠቀምበት እስከ ራስን በራስ እስከ ማስተዳደር ድረስ ብቻ ነው፡፡ ከፑንትላንድ ጋር ሊነፃፀር ቢችልም ነገር ግን መገንጠልን ግቡ ካደረገው ሶማሌላንድ ጋር ለማነፃፀር መለፋት የለበትም፤›› በማለት ነው በዚህ ዙሪያ የሚሰጠውን ግምት ውድቅ ያደረጉት፡፡
አቶ ዳንኤል ሐሳባቸውን ሲያክሉም፣ ‹‹ፌዴራል መንግሥቱ ከአንድ ዓመት ተኩል በፊት ጀምሮ ነው የፌዴራል ሠራዊቱን ከኤርትራ ድንበሮች አካባቢ ያስወጣው፡፡ ፌዴራል መንግሥቱ በራሱ ፍላጎትም ይሁን በሌላ መነሻ በትግራይ ውስጥ ያለውን መዋቅራዊ ትስስሮሽ እየቀነሰ ነው የመጣው፡፡ የፌዴራል ፖሊሶች አውሮፕላን ማረፊያዎች አካባቢ አሉ፣ ነገር ግን መከላከያ የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ከሚያስተዳድራቸው አካባቢዎች ወጥቷል፡፡ አሁን በተሰጠው የሕወሓት መግለጫ ፌዴራሉ ከትግራይ ጋር የነበረው ግንኙነት ይበጠሳል ብሎ መደምደም አስቸጋሪ ነው፡፡ ከዚያ በፊት ከፕሪቶሪያ መፈረም ጀምሮ በትግራይ የነበረውን ሚና ቀስ በቀስ እየቀነሰ ነው የመጣው፡፡ ስለዚህ የአሁኑ መግለጫ ለዚህ መነሻ ይሆናል ከሚለው ይልቅ፣ ፌዴራሉ ይህ እንደሚሆን እያወቀ በወሰዳቸው ዕርምጃዎች የተፈጠረ ነው ብዬ አስባለሁ፡፡ ይህን ያደረገው ደግሞ ፕሪቶሪያን አፈረሱት ብሎ ለመክሰስ ምቹ ሁኔታ ስለሚፈጥርለት ሊሆን ይችላል፡፡ ፌዴራል መንግሥቱ ሕወሓትን አማክሮ ጊዜያዊ አስተዳደሩን ቢያራዝም ምን ምላሽ ይኖር ነበር የሚለውን በእርግጥ መገመት ይከብደኛል፡፡ ይሁን እንጂ አሁን የተፈጠረው ችግር ሁለቱም ወገኖች ፈልገው የገቡበት ምዕራፍ ይመስለኛል፡፡ አንዱ ሌላው ምን እንደሚያደርግ ጠብቀዋል፡፡ በይፋ ባይናገሩም ከሚያደርጉት ነገር በቀላሉ መገመት ይቻል ነበር፡፡ ሳያውቁት በድንገት የተፈጠረ ነገር ያለ አይመስለኝም፡፡ ሕወሓት እንደ ድርጅት አትታወቅም ተብሏል፡፡ ስለዚህ ሕጋዊ ሰውነቱን የማስመለስና ህልውናውን የማስጠበቅ ጉዳይ አድርጎ ነው የሚወስደው፡፡ ሕወሓት በተጨባጭ ጠንካራ ድርጅታዊ ቁመና አለው፡፡ በሕግ ዓይን ግን ዕውቅናና ጥንካሬ ያለው ጊዜያዊ አስተዳደሩ ነው፡፡ ፌዴራል መንግሥቱ ደግሞ ከፕሪቶሪያ ሰላም ስምምነት መፋታት ይፈልጋል፡፡ ፕሪቶሪያ በራሱ ሳይሆን በሕወሓት ጥፋት ፈርሷል ተብሎ የሚታወጅበትን አጋጣሚ ይፈልገዋል፡፡ ሁለቱ ወገኖች ከዚህ ቀደም ተታኩሰዋል፡፡ ድሮን ጭምር ያሳተፈ ውጊያ በጠለምትና በራያ በቅርብ ጊዜ ተካሂዷል፡፡ ነገር ግን አላራዘሙትም በዚያው ቆሟል፡፡ ሀራ መሬት የሚባለው ኃይልና ቲዲኤፍም ከአራት ላላነሱ ጊዜያት ተፋጠዋል፣ ወይም ተታኩሰዋል ሲባል ታዝበናል፡፡ ሁለቱ ወገኖች ለመዋጋት መጠቀም ስላልፈለጉ እንጂ በተለያየ ጊዜ በቂ አጋጣሚዎች ነበሯቸው፡፡ አሁንም ቢሆን የጊዜያዊ አስተዳደሩ ፕሬዚዳንት በሥልጣን መቆየት አለመቆየታቸው ምክንያት ሊሆናቸው አይችልም፡፡ ሕወሓት ጊዜያዊ አስተዳደሩን ሲያፈርስ ፕሪቶሪያን እንዳፈረሰ ይቆጠራል፡፡ ስለዚህ ይህን መነሻ አድርጌ አመቺ ዕድል ሲፈጠር የሕግ ማስከበር ዘመቻ ብዬ ጦርነት ለማወጅ ይጠቅመኛል ብሎ ፌዴራል መንግሥቱ ሊያስብ ይችላል፡፡ ሕወሓት ደግሞ የእኔ ተሳትፎና ዕውቅና ሲፋቅ ማየት አልችልም የሚል የህልውና ጥያቄ በማንሳት አጋጣሚውን ሊጠቀምበት ይችላል፤›› በማለት ነው የነገሩ ማጠንጠኛ የሁለቱም የፖለቲካ ፍላጎት መሆኑን ለማብራራት ሞክረዋል፡፡
ኤርሚያስ አማረ የተባሉ አንድ የኪነ ሕንፃ ባለሙያና በትግራይ ፖለቲካ ጉዳዮች ላይ ትንተና በማቅረብ የሚታወቁ ሰው ብዙ ተከታይ ባፈራው የፌስቡክ ገጻቸው ላይ፣ ከሰሞኑ የተፈጠረው ጉዳይ ምን ያህል አሳሳቢ እንደሆነ የሚጠቁም ተነባቢ ጽሑፍ አጋርተው ነበር፡፡
‹‹ሕወሓት የሰሞኑን ዕርምጃ የወሰደበት መንገድ ልክ ከጦርነቱ በፊት ያደረገውን ምርጫ ያደረገበትን አጋጣሚ የሚያስታውስ ነው፡፡ ሕወሓት በአሁኑ ሰዓት ብልፅግና ተዳክሟል፣ ፋኖ እየተጠናከረ ሲሆን ከፋኖ በተጨማሪ ሻዕቢያም ከጎኔ ሊሠለፍ ይችላል፣ በዚህ ላይ እንደ ግብፅና ሱዳን ያሉ አገሮች ፀረ ኢትዮጵያ ፖሊሲ ነው የሚከተሉት፡፡ ስለሆነም በዚህ አጋጣሚ ልንጠቀም እንችላለን በሚል ሥሌት ነው ዕርምጃውን የወሰደው፡፡ በተቃራኒው እንደምናየው ደግሞ የብልፅግና መንግሥት ትዕግሥት የለሽ ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ አንድ ቴድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ) የተባለ ሙዚቀኛ በለቀቀው ሙዚቃም ከሰሞኑ ሲበሰጫጭ ታዝበናል፡፡ ብልፅግና ነገሮችን ንቆ ወይም ታግሶ የማለፍ ጠባይን አለመታደሉን ለቴዲ አፍሮ አልበም ከሰጠው ምላሽ ብቻ ሳይሆን፣ ከቀደመው ጦርነት ጀምሮ በወሰዳቸው ዕርምጃዎች መታዘብ እንችላለን፡፡ ስለሆነም ሕወሓት በዚህ ዕርምጃው የብልፅግናን ትዕግሥት መፈታተኑ የማይቀር ነው፡፡ ይሁን እንጂ ምንም ነገር ቢፈጠር ግን ፌዴራል መንግሥት ወደ ጦርነት እንዳይገባ እመክራለሁ፡፡ አንደ ሕወሓት ያሉ ኃይሎች ይጎነትሉህና ወይም ይመቱህና ወደ ግጭት ውስጥ ካስገቡህ በኋላ ግን ዘመተብን ብለው በማስወንጀል የተካኑ ናቸው፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ዲፕሎማሲያዊ ጫና ማድረጉ ነው ብቸኛው አዋጭ መንገድ፤›› በማለት አንዴ ወደ ጦርነት ከተገባ የሚነካካው ጉዳይም ሆነ ይዞት የሚመጣው ቀውስ ሰፊ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዚዳንት ሌተና ጄኔራል ታደሰ ወረደ ማክሰኞ ምሽት በሰጡት መግለጫ፣ የሕወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ ውሳኔ የፕሪቶሪያን ስምምነት እንደሚያፈርስ አስታውቀዋል፡፡
የቀድሞው የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዚዳንትና አሁን የጠቅላይ ሚኒስትሩ የምሥራቅ አፍሪካ ጉዳዮች አማካሪ አቶ ጌታቸው ረዳ የሕወሓትን ውሳኔ ፕሪቶሪያን የማፍረስና ጦርነት የማወጅ ዕርምጃ መሆኑን በመጥቀስ ተችተውታል፡፡ ሀራ መሬት የሚባለው ኃይልም ሕወሓትን ለጦርነት እየተጋበዘ ነው ሲል ወንጅሎታል፡፡ ለሪፖርተር አስተያየታቸውን የሰጡ ትግራይ ፖለቲካ ፓርቲዎች አመራሮችም የሕወሓትን ውሳኔ በጊዜያዊ አስተዳደሩ ላይ እንደተፈጸመ መፈንቅለ መንግሥት አድርገው እንደሚቆጥሩት ተናግረዋል፡፡ ከዚሁ ጋር በተገናኘ ሐሳባቸውን ያጋሩ አንዳንድ የሕግ ባለሙያዎችም ቢሆኑ ፕሪቶሪያንና ጊዜያዊ አስተዳደሩ የተመሠረተባቸውን ሕጎች የጣሰ ዕርምጃ ሕወሓት መውሰዱን የሚጠቁም ሐሳብ ነው ያጋሩት፡፡ ከዚህ ተቃራኒ የሆነ አስተያየት የሰጡ አንዳንድ ወገኖች በበኩላቸው ፌዴራል መንግሥቱ በጀት፣ ነዳጅ፣ ደመወዝና ሌላም ነገር ከትግራይ ክልል በማቋረጥ ፕሪቶሪያ እንዳይፈጸም እንቅፋት ሲሆን መቆየቱ አሁን ለተፈጠረው ችግር ራሱን የቻለ ምክንያት እንደሆነ ሲናገሩ ተደምጠዋል፡፡ ምንም ተባለ ምንም ግን በዚህ መነሻነት ሊመጣ የሚችለው ግጭት ወይም ዳግም ጦርነት ብዙዎችን እያሠጋ ነው፡፡