ሰሞኑን ከወደ አሜሪካ የተሰማው ዜና ለኢትዮጵያ መልካም ነው፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ/ር) ከአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጋር በሁለቱ አገሮች ግንኙነት፣ በንግድ፣ በኢንቨስትመንትና በቀጣናዊ ደኅንነት ጉዳዮች ላይ መወያየታቸው ተሰምቷል፡፡ በተጨማሪም ከአሜሪካ ጋር የመከላከያ ትብብርን ጨምሮ የተለያዩ ስምምነቶች መደረጋቸው ታውቋል፡፡ ሁለቱ አገሮች የሁለትዮሽ ግንኙነታቸውን በማጠናከር በቀጣናዊና ዓለም አቀፍ ጉዳዮች ላይ አብረው ለመሥራት መስማማታቸው ትልቅ ነገር ነው፡፡ እንደሚታወቀው በአሁኑ ጊዜ የፖለቲካ፣ የዲፕሎማሲ፣ የኢኮኖሚና የሌሎች ተዛማጅ ግንኙነቶች ቅርፅና ይዘት እየተለወጠ ነው፡፡ አሜሪካም ወዳጅና ጠላት እያለች የምትፈርጀው በዚህ ለውጥ ላይ ተመርኩዛ ስለሆነ፣ ከኢትዮጵያ ጋር በዚህ ደረጃ ለመቀራረብ ፍላጎቷን ስታይ እንደ መልካም አጋጣሚ መቆጠር አለበት፡፡ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ ለአሜሪካ ከማንም በተሻለ ተመራጭና ተፈላጊ አገር እንድትሆን የበለጠ መሥራትም ያስፈልጋል፡፡ ሰሞነኛውን የዲፕሎማሲ ዕድል በማጠናከር ኢትዮጵያ የከፍታው ማማ ላይ ትገኝ፡፡
ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ ቀጣና ውስጥ ካሉ አገሮች በተሻለ የምዕራቡንም ሆነ የምሥራቁን ጎራ ኃያላን ቀልብ መሳብ የምትችል አገር ናት፡፡ በብልኃትና በስክነት የሚመራ ዲፕሎማሲ ይዛ ወደ ዓለም አቀፍ አደባባይ ስትወጣ ፈላጊዋ ብዙ እንደሆነም የታወቀ ነው፡፡ ከዚህ ቀደም የነበሩ መልካም ልምዶችን በማከል ዘመኑ በደረሰበት አስተሳሰብ በሚመራ ዲፕሎማሲያዊ ጥበብ በመታገዝ፣ ከአፍሪካ ቀንድ አልፋ በአፍሪካ ጭምር ተመራጭ መዳረሻ እንድትሆን ወገብን ጠበቅ አድርጎ መሥራት የግድ ይላል፡፡ ሰሞነኛውን ከአሜሪካ ጋር የተደረገ ቅርርብ በማጠናከር ኢትዮጵያን መልካም አጋሮች እንድታገኝ ጥረቱ ይቀጥል፡፡ ዲፕሎማሲው ይበልጥ ተጠናክሮ መቀራረቡ ስፋትና ጥልቀት ሲያገኝ በአገር ውስጥ ላሉ ችግሮች ጭምር መፍትሔ ለማግኘት መንገዱ ይመቻቻል፡፡ ኢትዮጵያ በቀጣናው ተፈላጊነቷ በጨመረ ቁጥር ማሳካት ለምትፈልጋቸው ጂኦ ፖለቲካዊ መሻቶች አጋዥ ታገኛለች፡፡ በፖለቲካም ሆነ በዲፕሎማሲ የበላይነቱን ትጎናፀፋለች፡፡
በምዕራቡ ዓለም እየተለወጠ ካለው የፖለቲካና የኢኮኖሚ አስተሳሰብ በተጨማሪ፣ ከጎረቤት አገሮች ጀምሮ ኢትዮጵያ ያለችበት ቀጣና አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ነው የሚገኘው፡፡ በታላቁ የህዳሴ ግድብ ሳቢያ ግብፅና ሱዳን እየተናበቡ የሚፈጽሙትን አሻጥር መግታት የሚቻለው፣ በአኅጉርም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ የዲፕሎማሲ የበላይነት ሲኖር ነው፡፡ ግብፅ በኢትዮጵያ ዙሪያ ያሉ ጎረቤት አገሮችን ከጎኗ ለማሠለፍ በትጋት እየሠራች መቆየቷ አይዘነጋም፡፡ ሰሞኑን ደቡብ ሱዳን በኢትዮጵያ ድንበር አካባቢ የነበረውን የግብፅ ወታደራዊ ሠፈር የመዝጋቷ ዜና ተሰምቷል፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ዜና መሰማቱ ለኢትዮጵያ እንደ ትልቅ ድል ይቆጠራል፡፡ ግብፅ ሌሎች ጎረቤት አገሮችን አግባብታ ተጨማሪ እውክታ እንዳትፈጥር ነቅቶ መጠበቅም ይገባል፡፡ ከጎረቤት አገሮች ጋር ግንኙነትን ማጠናቀር አስፈላጊ ነው፡፡ ሁሉንም እንደ አመጣጡ ማስተናገድ የሚቻለው በፖለቲካውም ሆነ በዲፕሎማሲው ግንባር በቂ ዝግጅት ሲደረግ ብቻ ነው፡፡
መንግሥትን ጨምሮ በተለያዩ መስኮች የተሰማሩ ምሁራንና ልሂቃን የአገር ብሔራዊ ደኅንነትና ጥቅም የሚከበረው፣ በአንድነት በመቆም ብቻ እንደሆነ ሊረዱ ይገባል፡፡ አሁን ከአገር በፊት የሚቀድም ምንም ነገር እንደሌለ በመረዳት፣ ሙሉ ጊዜያቸውን ለኢትዮጵያ ደኅንነትና ጥቅም ብቻ ማዋል ይጠበቅባቸዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከድህነት አዘቅት ውስጥ ካልወጣች ማንም አያከብራትም፡፡ በዓለም አደባባይ ተደማጭነት የሚገኘው በተባበረ ክንድ ከድህነት በመውጣት ብቻ ነው፡፡ ውስጣዊ ችግሮችን በሰላማዊና በዴሞክራሲያዊ መንገድ በመፍታት ኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተፈላጊ ለማድረግ መረባረብ የግድ ነው፡፡ ይህ ክቡር ዓላማ በፀረ ኢትዮጵያ ኃይሎች ተንኮል ተደናቀፈ ማለት ለኢትዮጵያውያን ውርደት ነው፡፡ ከዚህ ቀደም ግብፅ በኢትዮጵያ ላይ የጠላትነት ስሜት በማጠናከር ከውጭም ከውስጥም የምትወጥረው፣ ከአሜሪካ ጋር ያላትን የጠበቀ ቁርኝት በመመካት እንደሆነ በይፋ የሚታወቅ ነው፡፡ ለዚህም ማስረጃው በታላቁ የህዳሴ ግድብ ላይ የከፈተችው ዘመቻ ያስገኘላት ድጋፍ ነው፡፡
አሜሪካ በመካከለኛው ምሥራቅ ከኢራን ጋር የገጠመችበት ጦርነት በሆርሙዝ ሰርጥ ላይ የደቀነው አደጋ ይታወቃል፡፡ በሆርሙዝ ሰርጥ በአሜሪካና በኢራን ፍጥጫ ምክንያት የመርከቦች እንቅስቃሴ መታወኩ፣ በዓለም ላይ ከባድ የሚባል የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ አስከትሏል፡፡ የዓለም አንድ-አምስተኛ ነዳጅ የሚተላለፍበት የውኃ መስመር በዓለም ኢኮኖሚ ላይ ከፍተኛ ኪሳራ እያስከተለ ነው፡፡ ችግሩ አድማሱን አስፍቶ ወደ ቀይ ባህርና ህንድ ውቅያኖስ እንዳይዳረስ፣ አሜሪካ በዚህ አካባቢ ስትራቴጂካዊ አጋሮችን እያማተረች መሆኑ ከተሰማ ሰነባብቷል፡፡ ይህ መልካም አጋጣሚ ደግሞ ኢትዮጵያና አሜሪካን የረጅሙን ዘመን ወዳጅነታቸውን እንዲያጠናክሩ ሲጋብዝ፣ የተገኘውን ዕድል በሰፊ ዕይታ ላይ በመመሥረት የባህር በር ተጋሪነትን ጭምር ሊያስገኙ የሚያስችሉ ሥራዎችን ይዞ ብቅ ማለትም ጠቃሚ ነው፡፡ በተጨማሪም ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቱ የበለጠ ሲጠናከር በኢትዮጵያ ኢንቨስት ሊያደርጉ የሚያስቡትንም ሆነ ሌሎችን እንደሚያበረታታ ይጠበቃል፡፡
በአፍሪካ ቀንድ ውስጥ ማለትም በሱዳን፣ በደቡብ ሱዳን፣ በሶማሊያና በመሳሰሉት የሚካሄዱ ጦርነቶችም ሆኑ ግጭቶች በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ለኢትዮጵያ ጉዳት እንደሚያስከትሉ ይታወቃል፡፡ ቀጣናው ከግጭት ፀድቶ ሰላምና መረጋጋት እንዲፈጠር ኢትዮጵያ እንደተለመደው ሚናዋ ከፍተኛ መሆን ይኖርበታል፡፡ በኢትዮጵያ ዙሪያ ባሉ አገሮች ግጭቶች ሲኖሩ ተረጋግቶ ልማት ለማከናወን አይቻልም፡፡ አሜሪካም በመካከለኛው ምሥራቅ የተፈጠረው ቀውስ እንዳይባባስ ለአፍሪካ ቀንድ ትኩረት ስትሰጥ፣ ከሰላም ማስፈን ባሻገር አጋጣሚው ይዟቸው የሚመጡ በርካታ ዕድሎችን ለመጠቀም ዝግጅትን ማጠናቀቅ ይገባል፡፡ ውስጣዊ ሰላምን በማረጋገጥ አካባቢያዊ መረጋጋት መፍጠር ለኢኮኖሚያዊ ዕድገት ቁልፍ ጉዳይ ነው፡፡ ከድህነት ማጥ ውስጥ በፍጥነት በመውጣት በልማትና በዕድገት ጎዳና ለመረማመድ ዲፕሎማሲው ይጠናከር፡፡ ኢትዮጵያ ሰላምና መረጋጋት እንዲኖራት አስፈላጊዎቹ ሥራዎች እየተከናወኑ፣ በዲፕሎማሲው መስክ ደግሞ ተፈላጊነቷ የላቀ እንዲሆን ከፍተኛ ጥረት ይደረግ!
