
በኢትዮጵያ የተለያዩ ሞዴል ያላቸው ከ115 ሺሕ በላይ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች በሥራ ላይ እንደሚገኙ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር መረጃ ያመላክታል፡፡ እነዚህ ከአነስተኛ የቤት አውቶሞቢሎች እስከ የሕዝብ ማመላለሻ አውቶቡሶች ድረስ ያሉ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች በአምስት ዓመታት ውስጥ ወደ ግማሽ ሚሊዮን ለማድረስ ዕቅድ ተይዞ እየተሠራ እንደሆነም ይሄው የመሥሪያ ቤቱ መረጃ ያመለክታል፡፡፡
በመንግሥት ውጥን መሠረት በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ቁጥር 500 ሺሕ ለማድረስ በቀጥታ ከውጭ ከሚገቡት የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ባሻገር በአገር ውስጥ የሚገጣጠሙ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ታሳቢ ተደርገዋል፡፡


በኤሌክትሪክ የሚሠሩ ተሽከርካሪዎችን ቁጥር ያሳድጋል ተብሎ ተስፋ የተደረገበት ሌላው ውጥን ደግሞ፣ በነዳጅ የሚሠሩ ተሽከርካሪዎችን ወደ ኤሌክትሪክና በተፈጥሮ ጋዝ ወደሚሠሩ ተሽከርካሪዎች መቀየር ነው፡፡ ይህንን ሥራ ለመሥራት የተዘጋጁ ኩባንያዎች ወደ ሥራ ለመግባት የሚኒስቴሩን ይሁንታ እየተጠባበቁ ናቸው፡፡ ከዚህ አንፃር አሥራ ሰባት የሚሆኑ የኤሌክትሪክ መገጣጠሚያ ፋብሪካዎች ፈቃድ ወስደዋል፡፡
ከውጭ ከሚመጡት የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ባሻገር፣ የአገር ውስጥ መገጣጠሚያ ፋብሪካዎች ጉልህ ድርሻ እንዲኖራቸው ታሳቢ ተደርጓል፡፡ አሁን ያሉትን 17 መገጣጠሚዎች ወደ 60 ለማድረስ በሥራ ላይ የነበሩ ሁሉም የመኪና መገጣጠሚያዎች ወደ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች እንዲገጣጠሙ መመርያ እስከማውረድ ተደርሷል፡፡
አዲስ አስገዳጅ መሥፈርት በመውጣት የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ለማስገባት ፈቃድ ያገኙ ኩባንያዎች ቁጥር 32 መድረሱ ታውቋል፡፡
እንዲህ ያለው ለዘርፉ የተሰጠው ትኩረት በአሁኑ ወቅት ከፍተኛ ቁጥርና ካላቸው የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች የአፍሪካ አገሮች ኢትዮጵያ አንዷ እንድትሆን ማስቻሉን መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ ይሁን እንጂ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ከዓለም አቀፍ ወቅታዊ ዋጋ ጋር ሲነፃፀር በኢትዮጵያ እየተሰጠ ያለው ዋጋ ከፍተኛ መሆን አነጋጋሪ መሆኑ አልቀረም፡፡
From The Reporter Magazine
በተለይ ባለፉት ወራት እንደ ቢዋይዲ ያሉ ትልልቅ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ አምራቾች የዋጋ ቅናሽ እያደረጉ ከመሆናቸው አንፃር፣ ቅናሹ በአገር ውስጥ ገበያም ሊንፀባረቅ ቢገባም ጭራሽ ዋጋቸው ጨምሮ እየተሸጡ ናቸው፡፡
ቢዋይዲ በቅርቡ ይፋ እንዳደረገው የሽያጭ ዋጋው ላይ ቅናሽ አድርጓል፡፡ እንደ ቢዋይዲ ሴጉል ያሉ የ2025 ሞዴል ተሽከርካሪዎችን ዋጋ ከ7,800 ዶላር ጀምሮ በመሸጥ ላይ እንደሆነም አስታውቋል፡፡


ይህ ዋጋ በዚህ ሳምንት ባለ አማካይ የምንዛሪ ዋጋ (165 ብር) ሲታስብ በኢትዮጵያ ብር 1.28 ሚሊዮን ብር መሆኑን ያሳያል፡፡ አዲስ አበባ ላይ ግን ይሄው ተሽከርካሪ በአማካይ እየተሸጠበት ያለው ዋጋ 3.8 ሚሊዮን ብር በላይ ደርሷል፡፡ ይህ ማለት በቻይና ከሚሸጥበት ዋጋ ጋር ሲነፃፀር በሦስት እጥፍ ይበልጣል፡፡ ወይም ከ2.6 ሚሊዮን ብር በላይ ልዩነት አለው፡፡ ከአንድ ወር በፊት ይኼው የተሽከርካሪ ሞዴል ዋጋው ቢበዛ ከ2.8 ሚሊዮን ብር ያልበለጠ እንደነበረው የሚጠቀስ ሲሆን፣ ባለፈው በአንድ ወር ውስጥ ከ400 እስከ 600 ብር የዋጋ ጭማሪ አሳይቷል፡፡ ሌሎች የኤሌክትሪክ መኪና ሞዴሎች እስከ አንድ ሚሊዮን ብር የዋጋ ለውጥ እየታየባቸውም እንደሆነ እየተገለጸ ነው፡፡ የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት በተፈጠረው የነዳጅ እጥረት የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ፍላጎት ከፍ በማለቱ የተደረገ ጭማሪ መሆኑ ቢነገርም፣ ዋጋው በዚህን ያህል ደረጃ መጨመሩ ተገቢ እንዳልሆነም እየተገለጸ ነው፡፡ በኢትዮጵያ የነዳጅ ተሽከርካሪዎችን ወደ ኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ለመቀየር ከበላይ አብ ሞተርስ ጋር ጥምረት በመፍጠር ሥራ ለመጀመር ዝግጅት እያደረገ ያለው የዩኒቨርሳል ኢንጂነሪንግ ኩባንያ መሥራችና በማርቼዲስ ቤንዝ ኩባንያ በከፍተኛ ኤክስፖርትርነት እያገለገሉ ያሉት አቶ እሸቱ መኮንን፣ እነዚህ ተሽከርካሪዎች ዋጋ በዚህን ያህል ዋጋ ለሽያጭ መቅረባቸው አግባብ አለመሆኑን ከሚሞግቱ መካከል አንዱ ናቸው፡፡
From The Reporter Magazine
በእርግጥም የቻይና ኩባንያዎች ዋጋ እየቀነሱ ስለመሆኑ የገለጹት አቶ እሸቱ፣ በኢትዮጵያ ግን በሰሞኑ ብቻ በተለያዩ ሞዴል ባላቸው የቻይና የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ላይ እስከ አንድ ሚሊዮን ብር ዋጋ በመጨመራቸው መታዘባቸውን ገልጸዋል፡፡ ይህም አግባብ ነው ብለው እንደማያምኑ ገልጸዋል፡፡ በኢትዮጵያ የተሽከርካሪዎች ገበያ ፍፁም ከሌላው ዓለም የሚለይ መሆኑን ጭምር የገለጹት አቶ እሸቱ፣ ሌላው ቀርቶ አሮጌ ተሽከርካሪዎች ዋጋ ጨምረው የሚሸጡበት አገር ስለመሆኑም አስታውሰዋል፡፡
የኢትዮጵያ የመኪና ዋጋ የተለየ የሚያደርገው እንዲህ ያለው ባህሪው ነው ይላሉ፡፡ ከማምረቻው ቦታ ሲቀንስ እነዚም መቀነስ ነበረበት፡፡ በሌሎች አገሮች የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ግብይት የሚፈጸመው የዕርጅና ታሳቢ ተደርጎ ስለመሆኑም ዋጋቸው መጀመሪያ ከሚሸጡበት ዋጋ በእጅጉ ቀንሶ ነው፡፡ የኢትዮጵያ የተሽከርካሪ ገበያ ከሌላው የዓለም ክፍል የተለየ ሊሆን የቻለበት የተለያዩ ምክንያቶች እንደሚኖሩም ጠቁመዋል፡፡
አንዱ የመኪና ነጋዴዎች እጅግ የተጋነነ ትርፍ ለማግኘት ያላቸው መሻት ነው፡፡ የዓለም ገበያን በማገናዘብ የተመጠነ ትርፍ ይዞ ለመሸጥ ፍላጎት ማጣት የመኪና ገበያውን አስወድዶታል፡፡
በተለይ ለኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች የሚከፍሉት ታክስ ከአምስት እስከ 15 በመቶ ሆኖ ሳለ፣ በዚህን ያህል መጨምር አልነበረበትም፡፡ በሌላ በኩል ግን በኢትዮጵያ ያለው የተሽከርካሪዎች ዋጋ በእጅጉ ለመጨመሩ እንደ ምክንያት የሚጠቀሰው ኢትዮጵያ የምታስገባው የተሽከርካሪዎች ቁጥር ውስን መሆኑ ነው፡፡ ይህ ፍላጎቱ አቅርቦቱን የሚመጥን አለመሆን ለዋጋው መወደድ ምክንያት መሆኑ አይቀርም፡፡ በቁጥ ቁጥ የሚገቡ የተሽከርካሪዎች የትራንስፖርትና የሎጂስቲክ ዋጋቸውን ስለሚጨምር ይህ ተሽከርካሪዎቹ ዋጋ ላይ እንዲጨምር ሊያደርግ እንደሚችልም አብራርተዋል፡፡ ከቻይና ወይም ከዱባይ 7,800 ዶላር የተገዛ የተሽከርካሪ እዚህ አሥርና አሥራ አንድ ሺሕ ዶላር ሊሸጥ የሚችልበት አንዱ ምክንያት በቁጥ ቁጥ ወደ መሃል አገር ለምሳሌ የተሽከርካሪዎቹን በአንዴ በባቡር ጭኖ ማስገባት ቢቻል የትራንስፖርት ሎጂስቲክስ ዋጋው ስለሚቀንስ የተሽከርካሪዎቹ ዋጋም ሊቀንስ ይችላል፡፡ ‹‹ወደብ አልባ መሆናችን የወደብ አገልግሎት ዋጋውም የራሱ ተፅዕኖ አለው›› የሚሉት አቶ እሸቱ፣ የኤሌክትሪክ የተሽከርካሪዎችን ዋጋ ለመቀነስና ተጠቃሚዎችን ለማብዛት አነስተኛ ቁጥር ያላቸውን ተሽከርካሪዎች በብዛት ማምጣት ወሳኝ ጉዳይ ነው፡፡ እንዲህ ማድረግ ከተቻለ የተሽከርካሪዎችን ዋጋ መቀነስ ይቻላል ይላሉ፡፡ ምክንያቱም በብዛት ከመጣ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዋጋው በከፍተኛ ደረጃ ይቀንሳል፡፡ ይህንን ማድረግም የውጭ ምንዛሪ እጥረት ሊኖር እንደሚችል ቢታመንም፣ መንግሥት ለነዳጅ እያወጣና ወደፊት ሊያወጣ ከሚችለው ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ አንፃር፣ የኤሌክትሪክ የተሽከርካሪዎች በብዛት እንዲገቡ በማድረግ የኤሌክትሪክ የተሽከርካሪዎችን ዋጋ በእጅጉ እንዲቀንሱ ማድረግ በብዙ የሚያተርፍበት ይሆናል ብለው ይመክራሉ፡፡
ይህ ማለት ደግሞ በቀጥታም የነዳጅ ወጪን በእጅጉ መቀነስ ማለት ስለሆነ፣ መንግሥት ከብዙ አገሮች ቀድሞ የኤሌክትሪክ የተሽከርካሪዎችን መጠቀም አዋጭ መሆኑን ተገንዝቦ ወደ ሥራ እንደገባ ሁሉ፣ እንዲህ ያሉ አሠራሮችን መተግበር ወደሚፈለገው ግብ እንደሚያደርሰው ሳይገልጹ አላለፉም፡፡
እርግጥ ነው የመንግሥት የተሽከርካሪ ግዥዎች በሙሉ በኤሌክትሪክ የሚሠሩ የተሽከርካሪዎች ላይ የተመሠረቱ እንዲሆኑ መወሰኑ፣ በነዳጅ የሚሠሩ ከባድ የተሽከርካሪዎችን መከልከሉና ለኤሌክትሪክ የተሽከርካሪዎች የተለያዩ ማበረታቻዎች መሰጠቱን ለግሪን ኢነርጂ ያለውን ጠንካራ አቋም የሚያመለክት ቢሆንም ተሽከርካሪዎቹ በተመጣጠነ ዋጋ መሸጥ ይኖርባቸዋል፡፡
የሚያመጣውን ጠቀሜታ ተገንዝቦ የተሽከርካሪዎችን በብዛት እንዲገቡ በፖሊሲ ደረጃ ባንኮችም ለዚህ አገልግሎት በቂ ፋይናንስ ሊያቀርቡ ይገባል፡፡
የትራንስፖርና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር ደኤታው አቶ በርኦ ሐሰን የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ዓለም አቀፍ ዋጋ እየቀነሰ ከመሆኑ አንፃር፣ የአገር ውስጥ የመሸጫ ዋጋቸው እንዲቀንስ ምን የታሰበ ነገር አለ ለሚለው ጥያቄ የሰጡት ምላሽ፣ ‹‹በአገር ውስጥ መገጣጠሚያዎችን፣ ማምረቻዎችንና አቨለቢሊቲን ማሳደግ ነው›› የሚል ነው፡፡ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ዋጋ ለመቀነስ ዋናው ጉዳይ ይህ መሆኑን የጠቀሱት ሚኒስትር ደኤታው፣ ለዚህም ትልልቅ ዓለም አቀፍ ኢንቨስተሮችን ለመሳብ በዘርፉ ኢትዮጵያ የፈጠረችውን ዕድል በማስተዋወቅ በኢትዮጵያ ውስጥ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ፋብሪካዎችን እንዲከፈቱ የመሳብ ሥራ በከፍተኛ ሁኔታ እየተሠራበት ነው፡፡
በአሁኑ ወቅትም በዓለም ላይ ትልልቅ የሚባሉ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ አምራቾች እየገቡ ሲሆን፣ ለመግባትም ዝግጀት እያደረጉ ያሉ መኖራቸውንም ጠቅሰዋል፡፡ በቀጣይ የሚደረጉ ትልልቅ ዓለም አቀፍ የንግድ ትርዒቶች ላይ የምናደርገው የማስተዋወቅ ሥራም ሌሎች ኩባንያዎችን ይስባል፡፡ ተብሎ ስለሚታሰብ የእነዚህ ኩባንያዎች ሥራ መጀመር ደግሞ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን በቀላሉ ገበያ ላይ ለማግኘት የሚያስችል ዕድል ይፈጥራል ተብሎ እንደታመነበት አመልክተዋል፡፡ ይህ ደግሞ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ዋጋ እንዲቀንስ ያግዛል በሚል ዕሳቤ እየተሠራ መሆኑን በመግለጽ ዋጋውን ለመቀነስ ምርት ማብዛት ወሳኝ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
የኤሌክተሪክ ተሽከርካሪዎችን ከማስገባት ጎን ለጎን በነዳጅ የሚሠሩ ተሽከርካሪዎችን በኤሌክተትሪክ ወደ ተፈጥሮ ጋዝ እንዲሠሩ ማስቻል ከነዳጅ ጥገኝነት እንደሚላቅቅ ታሳቢ ተደርጓል፡፡ መንግሥትም የነዳጅ ተሽከርካሪዎችን ወደ ኤሌክትሪክ የተፈጥሮ ጋዝ ተሽከርካሪዎች የመቀየር ሥራ ተጀምሯል፡፡ እንዲህ ያሉ ሥራዎችን የሚሠሩ የውጭና የአገር ውስጥ ኩባንያዎች ሥራውን ለመሥራት አስፈለጊውን ዝግጅት በማድረግ ፈቃድ እንዲሰጣቸው ጥያቄ አቅርበዋል፡፡ ይሁን እንጂ ኩባንያዎቹ ከሚኒስቴሩ ሊሰጣቸው የሚገባውን ፈቃድ ባለማግኘታቸው ወደ ሥራ ሊገቡ አለመቻላቸው ግን ጥያቄ ማስነሳቱ አልቀረም፡፡ እንዲህ ያለ ጥያቄ ካላቸው መካከል አንዱ የአቶ እሸቱ ኩባንያ አንዱ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ በነዳጅ የሚሠሩ ተሽከርካሪዎችን በተመጣጠነ ዋጋ ወደ ኤሌክትሪክ መቀየር ሊያስገኝ የሚችለው ጠቀሜታ ግምት ውስጥ ገብቶ ፈቃዱ ሊሰጥ ይገባ ነበር ይላሉ፡፡ ነገር ግን እስካሁን ፈቃድ ሊያገኙ ባለመቻላቸው ወደ ሥራ ሊገቡ አልቻሉም፡፡
አቶ በርኦ በዚህ ጉዳይ ላይ በሰጡት ማብራሪያ ግን ፈቃድ ለመስጠት ወደማይቻልበት ደረጃ ላይ እየተደረሰ መሆኑ ነው፡፡ የነዳጅ ተሽከርካሪዎችን ወደ ኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ለመቀየር ፍላጎት ያላቸው ኩባንያዎችን ወደ ሥራ ለማስገባት የሚያስችል ራሱን የቻለ ስታንዳርድ ያስፈልግ ነበር፡፡ አሁን እየተጠበቀ ያለው መመርያው ነው፡፡ ይህም መመርያ ቢሆን የመጨረሻው ምዕራፍ ላይ የደረሰ በመሆኑ በቅርቡ ይፀድቃል ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልጸዋል፡፡
አውቶቡሶችን ወደ ኤሌክትሪክ የመቀየሩ ሥራ ግን እንደተጀመረ የገለጹት ሚኒስትር ደኤታው፣ ከነዳጅ ወደ ኤሌክትሪክና ከነዳጅ ወደ ተፈጥሮ ጋዝ ወደሚሠሩ ተሽከርካሪዎች ለመቀየር እንዴት እንደሚቻልና ማሟላት ያለበትን ሁኔታ የሚያሳይ መመርያ እንደወጣ ፈቃድ መስጠት ይጀመራል፡፡ እስከዚያው ግን ፈቃ እንዲሰጣቸው ካመለከቱ ኩባንያዎች ውስጥ አንዳንዶቹ እየተመዘኑ ነው፡፡ በሚደረገው ምዘና ሊያልፉ ለሚችሉ መመርያው እስኪፀድቅ ድረስ ማኑዋል ቢዝድ ፈቃድ መውሰድ የሚችሉበት ሁኔታ ስለመመቻቸቱ ገልጸዋል፡፡
እንደ አቶ እሸቱ ገለጻ፣ እንደ ኢትዮጵያ ያሉ አገሮች በሁሉም የግሪን ኢነርጂ አማራጮች ሲሠሩ ይገባል፡፡ በዓለም ላይም የኤሌክትሪክ የተሽከርካሪ አምራቾችም ፍላጎት እየጨመረ ነው፡፡ የኤሌክትሪክ የተሽከርካሪዎች ምርት እየጨመሩ ነው፡፡ ቻይና ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ነች፡፡ እንደ ቢዋይዲ ያሉ ኩባንያዎች ምርቶቻቸውን በዕጥፍ አሳድገዋል፡፡ ቀጣይ በዕቅዳቸውም የሚያሳየው የምርት መጠኑን በመጨመር መቀጠል ነው፡፡
የተሽከርካሪዎቹ ብቻ ሳይሆን ባቡሮችም እየሠሩ ያሉት በኤሌክትሪክ ብቻ ነው፡፡ በኤሌክትሪክ መሥራታቸው አስፈላጊና አዋጭ በመሆኑ ነው፡፡ በኢትዮጵያም የተሽከርካሪዎችም ሆነ የባቡር ትራንስፖርትን ወደ ኤሌክትሪክ የመቀየሩ ሥራ ዛሬ ካልጀመረች የምትችለው አይሆንም፡፡ አሁን መንግሥት በዚህ ዘርፍ እየወሰደ ያለው ዕርምጃ እንደ ምሳሌ የሚታይ መሆኑን የለጹት አቶ እሸቱ፣ በአውሮፓም ቢሆን አብዛኛው የተሽከርካሪዎች በኤሌክትሪክ የሚሠሩ ይሁኑ የሚል ውሳኔ እስከማስተላለፍ ደርሰዋል፡፡ ኢትዮጵያን እየተገዳደራት ያለውን የነዳጅ ወጪ ለመቀነስ እነዚህ የኤሌክትሪክ የተሽከርካሪዎችን ማብዛትና ከነዳጅ ወደ ኤሌክትሪክ እንዲቀየሩ ማድረግ በጣም ወሳኝ ጉዳይ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት ወደ 1.6 ሚሊዮን ተሽከርካሪዎች በኢትዮጵያ እንዳሉ የጠቀሱት አቶ እሸቱ፣ ከዚህ ውስጥ 500 ሺዎቹን ወደ ኤሌክትሪክ መቀየር ቢቻል እንደ አገር ትልቅ ጠቀሜታ ይኖረዋል፡፡ ተጠቃሚዎችም የነዳጅ ወጪያቸውን የሚያስቀርላቸው ሲሆን፣ በነዳጅ መወደድ ምክንያት ተሽከርካሪዎቻቸውን ሳያሽከረክሩ እንዳይቀሩ ታደጋቸዋል፡፡ ስለዚህ እሳቸው ኩባንያ ከበላይ አብ ጋር በመሆን የጀመረውን ፕሮጀክት ዳር ለማድረስ መንግሥት ትልቅ ድጋፍ ማድረግ የሚገባው መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
ከዚህም በኋላም ቢሆን የነዳጅ ዋጋ እየጨመረ ስለሚሄድ የነዳጅ መወደድ ሊያስከትል የሚችለውን ትልቅ ችግር ግንዛቤ ውስጥ በማስገባት ወደ ኤሌክትሪክ የመቀየሩ ሥራ ጊዜው የሚጠይቀው መሆኑንም አመልክተዋል፡፡ አንዳንድ የአውሮፓ አገሮችም ወደ እዚህ መስመር እየገቡ መሆናቸውንም የጠቀሱት ባለሙያው፣ እንደ ሰሪላንካ ያሉ አገሮችም 500 ሺሕ የሚሆኑ በነዳጅ የሚሠሩ የተሽከርካሪዎችን ወደ ኤሌክተሪክ እንዲቀየሩ በመወሰን ይህንን እያደረጉ ነው፡፡
በርካታ የተሽከርካሪዎች ያላቸው እንደ ፊሊፒንስ ያሉ አገሮችም በነዳጅ እጥረቱ የትራንስፖርት አገልግሎት ስለተስተጓጎለባቸው የነዳጅ ተሽከርካሪዎችን ወደ ኤሌክትሪክ እንዲቀየሩ እያደረጉ ነው፡፡ በአፍሪካ ደረጃ እንደ ናይጄሪያ ያሉ አገሮችም ይህንኑ በመተግበር ውጤታማ ስለመሆናቸው በመግለጽ ኢትዮጵያም በዚሁ መንገድ መጓዝ እንዳለበት ይመክራሉ፡፡
ወደ ኤሌክትሪክ የመቀየሩ ሥራ በአብዛኛው አነስተኛ የተሽከርካሪዎች ላይ የሚተገበር ቢሆንም፣ ትልልቅ የተሽከርካሪዎችንም ወደ ኤሌክትሪክ መቀየር እንደሚቻልም ገልጸዋል፡፡ በተለይ በናፍጣ የሚሠሩ የጭነት የተሽከርካሪዎችን የነዳጅ እጥረት ወደፊትም ሊገጥማቸው የሚችለውን ችግር ለመቅረፍ ከተፈለገ አሁንም በኤሌክትሪክ እንዲሠሩ ማስቻል ‹‹ያሉትን መቀየር አዲስ የሚገቡትም በኤሌክትሪክና በጋዝ የሚሠሩ ከሆነ ከነዳጅ ጥገኝነት መውጣት ያስችላል፤›› ብለዋል፡፡
ሰሞኑን የተፈጠረው የነዳጅ እጥረት በትራንስፖርቱ እንቅስቃሴው ላይ ያሳረፈው ተፅዕኖ በአንፃራዊነት እንዲቀንስ አሁን ሥራ ላይ ያሉት ወደ 115 ሺሕ የሚጠጉ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች የሰጡት ጠቀሜታ በቀላል መታየት እንደሌለበት አቶ እሸቱ ሳይገልጹ አላለፉም፡፡
ይህ ቁጥር በርከት ብሎ ቢሆን ኖሮ ጫናው ሊቀንስ ይችል እንደነበር ገልጸዋል፡፡ ሚኒስቴር ደኤታውም ይህንን ሐሳብ ይጋራሉ፡፡ ያለ ነዳጅ የሚንቀሳቀሱ የትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ፣ ተሽከርካሪዎች የትራንስፖርት አማራጭ እንዲኖር ዕድል ሰጥቷል፡፡ ስለዚህ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች የትራንስፖርት አገልግሎት እንደ አንድ አማራጭ የምንጠቅሰው ዘርፍ ሆኗል ማለት ነው ይላሉ፡፡
በሁሉም ካታጎሪ ከ115 ሺሕ በላይ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች አሉ ማለት ጥቂት የሚባል አይደለም፡፡ ከዚህ ውስጥ ከ128 በላይ የሕዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ አውቶብሶች መሆናቸውን የገለጹት አቶ በርኦ፣ አዲስ አበባን ለይተን ካየን 100 አውቶብሶች ከአንድ ዓመት በላይ የአገልግሎት ጊዜያቸው ከ40 ሚሊዮን በላይ ተገልጋዮችን አጓጉዘዋና በቀላል የሚታይ አበርክቶ አይደለም ብለዋል፡፡ በዚህ ሰዓት ይህ የአገልግሎት ዘርፍ እጃችን ላይ መኖሩ ትልቅ አቅም ፈጥሯል፡፡ በግልጽ ማስተዋል እንደሚቻለውም የሕዝብ ትራንስፖርት የሚሰጡ ተሽከርካሪዎች ነዳጅ ለማግኘት ሲሠለፉ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎቹ ለሰከንድ እንኳን ሳይቆሙ ፍሪኮንሲያቸው ጨምረው ኅብረተሰቡን ማገልገል መቻላቸው በዚህ ቀውስ ወቅት ቀላል የማይባል ድጋፍ ማድረጋቸውን አመላክቷል፡፡ አውቶብሶቹ ብቻ ሳይሆኑ 15 እና ከዚያም በላይ የመጫን አቅም ያላቸው ቢኒባሶች ሰሞናዊውን የትራንስፖርት አገልግሎት እየደገፉ መሆናቸው በራሱ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ማብዛት አገራዊ ጠቀሜታው ከፍተኛ ነው ብለዋል፡፡
አቶ እሸቱ በበኩላቸው፣ ከትራክተር ጀምሮ በኤሌክትሪክ የሚሠሩ የጭነት የተሽከርካሪዎች ተሠርተዋል፡፡ ብዙዎቹ በእነዚህ ለመጠቀም አለመድፈራቸው ነው እንጂ፣ በሁሉም የተሽከርካሪዎች እየተሠሩ ነው፡፡ ለትልልቅ ፕሮጀክቶች የሚያገለግሉ እንደ ዶዘርና መለስተኛ ተሽከርካሪዎችም በባትሪ እንዲሠሩ እየተደረጉ ነው፡፡
ከሁሉም በቀላሉ እየተሠሩ ያሉት አውቶብሶች ናቸው፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ባትሪ የሚጫነው አናቱ ላይ ስለሆነ ነው፡፡ ሌሎች የራሳቸው የባትሪ ቦታ የሚልጉ ካልሆነ በቀር ሁሉም ወደ ኤሌክትሪክ እየተቀየሩ ነው፡፡
‹‹ኢትዮጵያን ወደ ግሪን ኢነርጂ መግባት ይኖርባታል›› ሲባል በዚህ ዘርፍ የተሻሉ ዕድሎችም ስላሏት ነው፡፡ የኤሌክትሪክ ብቻ ሳይሆን በሶላር አነርጂም ባትሪዎችን መሙላት የሚቻልበት ተፈጥሮ ስላላትም መሆኑ ነው፡፡ ቻርጀሮቹ ራሳቸው በሦላር የሚሠሩም እየሆኑ በመምጣታቸው፣ እንዲሁም የተፈጥሮ ጋዝ መገኘቱ፣ ግሪን አነርጂን በትኩረትም የሚሠራበት መሆን ከነዳጅ ጥገኝነት እያላቀቀን ይሄዳል የሚል እምነት እንዳላቸውም አመልክተዋል፡፡