ከሐምሌ 8 ቀን 2018 ዓ.ም. ጀምሮ በመካሄድ ላይ ባለው አገራዊ ምክክር ጉባዔ፣ ከአንድ መቶ በላይ የዳያስፖራ አባላት እየተሳተፉ መሆናቸውን የዳያስፖራ አገልግሎት አስታወቀ፡፡
አገልግሎቱ ይህን ያስታወቀው ፒፕል ቱ ፒፕል (People to People) 25ኛ ዓመት የምሥረታ በዓሉን አስመልክቶ ሐምሌ 9 ቀን 2018 ዓ.ም. በስካይ ላይት ሆቴል ባዘጋጀው የዕውቅና መርሐ ግብር ላይ ነው፡፡
የዳያስፖራ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ፍፁም አረጋ (አምባሳደር) እንደተናገሩት፣ እየተካሄደ በሚገኘው አገራዊ የምክክር ጉባዔ በምርጫ የተወከሉ 91 የዳያስፖራ አባላት በመሳተፍ ላይ ናቸው፡፡
በተጨማሪም ከአሁን በፊት ወደ ኢትዮጵያ መጥተው በኢንቨስትመንትና በሌሎች የሥራ መስኮች ተሰማርተው የሚገኙ 12 ዳያስፖራዎችም፣ በምክክር ጉባዔው ተሳታፊ ሆነዋል ብለዋል፡፡
በአጠቃላይ ከአንድ መቶ በላይ የዳያስፖራ አባላት በውጭ አገር የሚኖረውን የዳያስፖራ ማኅበረሰብ በመወከል በአገራዊ የምክክር ጉባዔ እየተሳተፉ ናቸው ያሉት አረጋ (አምባሳደሩ)፣ ‹‹የምንገኝበት የክረምት ወቅት በርካታ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን የልጆቻቸው ትምህርት ቤት በመዘጋቱ የሥራ ጊዜያቸውን በማመቻቸት ወደ ኢትዮጵያ የሚመጡበት ነው፡፡ በኢትዮጵያ ቆይታቸውም ቤተሰብ ከመጠየቅና አገር ከመጎብኘት ባለፈ፣ በተለያዩ የበጎ አድራጎት ሥራዎች በመሳተፍ ማኅበረሰቡን የሚጠቅም ዘርፈ ብዙ አገልግሎት ይሰጣሉ፤›› በማለት አስረድተዋል፡፡
ፍፁም (አምባሳደር) እንደተናገሩት፣ ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ እንዲጠናቀቅ የዳያስፖራ አባላት ከፍ ያለ ሚና ተጫውተዋል፡፡ ስለሆነም በገንዘብ፣ በዕውቀትና በአድቮኬሲ (ውትወታ) ሲደግፉት የነበረውን ግድብ ለመጎብኘት እንዲችሉ ተቋማቸው የጉብኝት መርሐ ግብር በማዘጋጀት ላይ ነው ብለዋል፡፡
በተጨማሪም ባለፉት ዓመታት የተከናወኑና እየተከናወኑ የሚገኙ እንደ ኮሪደር ልማት፣ የወንዝ ዳርቻ ልማት፣ ገበታ ለአገር፣ ገበታ ለትውልድ፣ ገበታ ለሸገር፣ እንዲሁም የቱሪዝም መዳረሻ ሥፍራዎች የእንዲጎበኙ እንደሚደረግ ገልጸዋል፡፡ ቆይታቸው በቀጣይ በኢትዮጵያ ለመሥራት ላሰቧቸው ለመኖሪያ ቤቶች፣ ለንግድ ቤቶች፣ ለኢንቨስትመንትና ለመሳሰሉት መልካም አጋጣሚዎች የሚፈጥርላቸው መሆኑን ተናግረዋል፡፡
From The Reporter Magazine
የጤና ሚኒስትሯ መቅደስ ዳባ (ዶ/ር)፣ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ዳያስፖራዎች በዕውቀት፣ በሙያ፣ በቴክኖሎጂ፣ በሀብትና በበጎ ፈቃደኝነት ለአገራቸው በተለይም በጤናው ዘርፍ የሚያበረክቱት አስተዋጽኦ ከፍተኛ ነው ብለዋል፡፡
ፒፕል ቱ ፒፕልም ሆነ የዳያስፖራው አባላት በጤናው ዘርፍ በተለይም በስፔሻሊቲና ሰብ ስፔሻሊቲ የትምህርትና ሥልጠና መስኮች አበርክቷቸው የላቀ መሆኑን ሚኒስትሯ ገልጸዋል፡፡
ባለሙያዎችን በማስተማር፣ የሕክምና ትምህርት ተቋማትን በማዘመን፣ ከርቀት የሚሰጡ የሕክምና ትምህርቶች እንዲጠናከሩ በማድረግና በሌሎችም መስኮች በትብብር የተከናወኑ ሥራዎች ውጤት የተመዘገበባቸው ነበር ያሉት ሚኒስትሯ፣ በተለይ በቴክኖሎጂ፣ በፈጠራና የጤና ሥርዓቱን ዘላቂና የማይበገር አድርጎ በመገንባት ረገድ የዳያስፖራ ተቋማትና ባለሙያዎች ያበረከቱት ቴክኒካዊ ድጋፍ ለጤና ሚኒስቴር ትልቅ አቅም መሆኑን አክለዋል፡፡