በያሬድ ንጉሤ
በሲዳማ ክልል ምርጫ ጥቂት ቦታዎች ምርጫው እስከ እኩለ ሌሊት ስድስት ሰዓት ድረስ ሲሰጥ የነበረባቸው የምርጫ ጣቢያዎች ነበሩ፡፡ የምርጫ ጣቢያዎች በጊዜ ካለመከፈት ጋር ተያይዞ በተለያዩ የምርጫ ጣቢያዎች ሕዝቡ በሰዓቱ ድምፅ መስጠት እንዳልቻለም፣ የሲቪል ማኅበረሰብ ተወካዮች ገልጸዋል፡፡
የሲዳማ ክልል ሴቶች ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ገነት ማርቆስ፣ ‹‹እኔ በግሌ ከሐዋሳ ውጪ ባሉ ተንቀሳቅሼ እንደ መመልከቴ በሲዳማ ማዕከላዊ ዞን፣ በይርጋለምና በሐዋሳ ምርጫ ክልል መራጮች ቀደም ብለው የተሠለፉ ቢሆንም፣ ከማለዳ 12፡00 ሰዓት ሊጀመር የሚገባው ምርጫ ግን ዘግይቶ እንደጀመረ ታዝቤያለሁ›› ሲሉ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡


‹‹በምርጫው ወቅት የነበረው ችግር ከምሽቱ 12፡00 ሰዓት ከሆነም በኋላ ድምፅ ያልሰጡ መራጮች ስላሉ፣ ሠልፍ የሌለባቸው ምርጫ ጣቢያዎች እስከ ሌሊቱ 6፡00 ሰዓት ድረስ ክፍት ሆነው መቆየታቸውን ታዝበናል፤›› ሲሉም ገልጸዋል፡፡ ‹‹መራጮች ተጠቃለው ድምፅ ያልሰጡባቸው ሁለት የሐዋሳ ክልል ምርጫ ጣቢያዎች እስከ ሌሊቱ 6፡00 ሰዓት ድረስ ቆዩ ተብለን ከምርጫ ቦርድ ታዘናል ብለው የቆዩ የምርጫ አስፈጻሚዎች ነበሩ፤›› ሲሉ ገነት አክለው ገልጸዋል፡፡
በዲጂታል ለምርጫ የተመዘገቡ መራጮችም ምርጫ ጣቢያቸውን ያለማወቅና ሠልፍ ደርሷቸው መዝገባቸው ላይ ስማቸው ሲፈለግ በመታጣቱ፣ ስማቸው የሚገኝበት የምርጫ ጣቢያ ለመንከራተት መዳረጋቸውን ስለመታዘባቸው ገነት አስረድተዋል፡፡
ይሁንና ድምፅ የማጭበርበር ሙከራ እንደሚኖር ይገምቱ እንደሆነ ከሪፖርተር ለቀረበላቸው ጥያቄ ምላሽ የሰጡት የክልሉ ሴቶች ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ገነት፣ ‹‹ውጤቶች ተለጥፈው ገና አላለቁም፣ እስካሁን ድምፅ እየተቆጠሩ ያሉባቸው ጣቢያዎች አሉ፣ በእኛ ግምገማ ግን የማጭበርበር ሁኔታዎችን አላየንም፣ አላጋጠመንም፤›› ብለዋል፡፡
From The Reporter Magazine


ይህ በእንዲህ እንዳለ የሲዳማ ክልል ፖሊስ ኮሚሽነር ተስፋዬ ዴቢሶ ለሪፖርተር እንደተናገሩት ሞኖፖል፣ አዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ፊላደልፊያ መንደር፣ ወሎ ሠፈር፣ ታቦር፣ ቱላ፣ ዳጦ ምርጫ ጣቢያዎች እንዲሁም በገጠር አካባቢዎች ምሥራቅና ደቡብ ሲዳማ ዞኖች ምርጫ ጣቢያዎች ላይ በርካታ መራጮች ከመኖራቸውና ረጃጅም ሠልፎች የተነሳ ምርጫው እስከ እኩለ ሌሊት ስድስት ሰዓት ድረስ ተራዝሞ እንደነበር ተናግረዋል፡፡
በምርጫ ሰዓት አለመከበርና እስከ እኩለ ሌሊት ድረስ ድምፅ መስጠት ጉዳይ ላይ በሐዋሳ ምርጫ ክልል የምርጫ አስፈጻሚ የሆኑትን አቶ ከፊቱ ሥዩምን በተደጋጋሚ በስልክ ምላሽ እንዲሰጡን ብንጠይቅም፣ ‹‹አጣርቼ አሳውቃለሁ›› ከማለት ውጪ ተጨማሪ ማብራሪያ ማግኘት አልተቻለም፡፡
በሌላም በኩል በሐዋሳ ከተማ ከምርጫው ቀን በፊት እሑድ ግንቦት 23 ቀን እና የምርጫው ቀን ሰኞ ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም. የሦስት እግር ተሽከርካሪዎች (ባጃጆች) እና የሞተር ትራንስፖርት እንቅስቃሴ ተገቶና መንገዶች በአብዛኛው ጭር ብለው የታዩ ሲሆን፣ ይህ ክልከላ ለምን ተግባራዊ እንደተደረገ ከሪፖርተር ጥያቄ የቀረበላቸው ፖሊስ ኮሚሽነሩ ተስፋዬ ዴቢሶ፣ ‹‹መራጮች ድምፅ ለመስጠት ራቅ ያለ ቦታ መሄድ ስለማያስፈልጋቸውና በቅርበት ድምፅ የሚሰጡባቸው ጣቢያዎች ስላሉ ነው፤›› ብለዋል፡፡
From The Reporter Magazine
አክለውም በስም ያልጠቀሷቸው ምርጫን ለማበላሸት የሚሠሩ የውስጥና የውጭ ፀረ ሰላም ኃይሎች ሊኖሩ ስለሚችሉና የተሽከርካሪዎችን እንቅስቃሴ ስለሚጠቀሙበት፣ እንዲሁም ምርጫው ሰላማዊ እንዳይሆንና ሕዝቡ የፈለገውን በነፃነት መምረጥ እንዳይችል ለመቀስቀስና ለማደናቀፍ ይጠቀሙበታል ከሚል የመነጨ ነው ብለዋል፡፡
‹‹እነዚህ የጥፋት ኃይሎች ዕድል እንዳያገኙ ተፈልጎ ነው የትራንስፖርት መጠነኛ ዕገዳ የተደረገው፤›› ሲሉም አክለዋል፡፡
በሲዳማ ክልል በሐዋሳ ምርጫ ክልል የተካሄደው የ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ሰኞ ግንቦት 24 ቀን 2013 ዓ.ም. ሲካሄድ በ308 የምርጫ ጣቢያዎች መራጮች ድምፃቸውን ሲሰጡ ውለዋል፡፡
ሪፖርተር ቅኝት ካደረገባቸው የምርጫ ጣቢያዎች አንዱ በሆነው ልዩ ስሙ ወልደ አማኑኤል ጉዊ ቀበሌ ሰላም አደባባይ ቁጥር አንድ ምርጫ ጣቢያ ላይ መራጮች ከማለዳው 12:00 ሰዓት አንስቶ ድምፅ እንደሚሰጡ ቢጠበቅም ምርጫው የተጀመረው ግን 12:45 ሰዓት ሲሆን ነው፡፡
ሪፖርተር በዚህ ጣቢያ የተገኘው ከማለዳው 11፡25 ሲሆን የምርጫ አስፈጻሚዎች የምርጫ ቁሳቁሶችን የድምፅ መስጫ ሳጥንና የመራጮች መመዝገቢያ ቅፅ ለምርጫው ዝግጁ ሲያደርጉ ተመልክቷል፡፡
በዚሁ የምርጫ ክልል 16 ተፎካካሪ ፓርቲዎች ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት፣ እንዲሁም 126 ለክልል ምክር ቤት እንደሚወዳደሩ፣ በዚህ የምርጫ ጣቢያ አስፈጻሚ ቢንያም በላይነህ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ በምርጫ ጣቢያው 225 ድምፃቸውን ለመስጠት የተመዘገቡ መራጮች አሉ ብለዋል፡፡
ለክልል ምክር ቤት ምርጫ በዚሁ ጣቢያ ተገኝተው ድምፃቸውን ከሰጡት መካከል የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ ይገኙበታል፡፡
በሐዋሳ ምርጫ ክልል ሪፖርተር ቅኝት ያደረገባቸው ምርጫ ጣቢያዎች ከ225 እስከ 760 መራጮች ድረስ ማስመዝገባቸውን ማረጋገጥ ተችሏል፡፡ ይህም ለአብነት በአዲስ አበባ ካሉ የምርጫ ጣቢያዎች ጋር ሲነፃፀር በአንድ የምርጫ ጣቢያ ድምፅ የሚሰጡትን መራጮች ቁጥር አነስተኛ ያደርገዋል፡፡
በአዲስ አበባ የምርጫ ክልል በአንድ ጣቢያ እስከ 1‚500 መራጮች ድምፅ ሲሰጡ በአንፃሩ ደግሞ ሪፖርተር ባደረገው ቅኝት መሠረት በሐዋሳ የምርጫ ክልል ያሉ የምርጫ ጣቢያዎች ቢያንስ አንዱ ከሌላው ያላቸው ርቀት 100 ሜትር በመሆኑና ጣቢያዎቹ በቅርብ ርቀት በመገኘታቸው፣ የመራጩን ቁጥር አነስተኛ እንዳደረገው ተመልክቷል፣ የምርጫ ጣቢያዎች አስተባባሪዎችም ይህንን አረጋግጠውልናል፡፡
የምርጫ ጣቢያ ሒደት ቅኝት በተካሄደባቸው በርካታ ጣቢያዎች ምርጫው ከማለዳው 12፡00 ሰዓት ላይ እንደተጀመረ ሲያረጋግጥ ወልደ አማኑኤል ጉዊ ቀበሌ ሰላም አደባባይ ቁጥር 1 ምርጫ ጣቢያ ግን ምርጫው 45 ደቂቃ ዘግይቶ መጀመሩን መታዘብ ተችሏል፡፡
በሐዋሳ ምርጫ ክልል ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትና ለክልል ምክር ቤት መቀመጫዎች የተወዳደሩት የገዥው ፓርቲ ብልፅግናና የተለያዩ የተፎካካሪ ፓርቲዎች ዕጩዎች ታዛቢ ወኪሎቻቸውን በየጣቢያው አሰማርተው የነበረ ሲሆን፣ ሒደቱን በቅርበት ተከታትለዋል፡፡ ከተለያዩ የአገር ውስጥ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች የተውጣጡ ገለልተኛ ታዛቢዎችም በጣቢያዎች ተገኝተው ታዝበዋል፡፡
ይሁንና ወልደ አማኑኤል ጉዊ ቀበሌ ሰላም አደባባይ ቁጥር 1 ምርጫ ጣቢያ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ተወካዮች ምርጫውን ለመታዘብ ዘግይተው መድረሳቸውን ሪፖርተር አረጋግጧል፡፡
ሪፖርተር ቅኝት ባደረገባቸው ጣቢያዎች የውጭም ሆኑ የአገር ውስጥ ምርጫ ታዛቢዎች የምርጫው ጊዜ ሳይጠናቀቅ አስቀድመው ከጣቢያዎች መሄዳቸው ተገልጿል፡፡
የዚህ ማሳያ የሚሆነው በአዳሬ ቀበሌ አድማስ ምርጫ ጣቢያ ሲሆን የጣቢያው የምርጫ አስተባባሪ ኢያሱ አያሌው ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽንና የምሥራቅ አፍሪካ በየነ መንግሥታት ድርጅት (ኢጋድ) የምርጫ ታዛቢዎች ለሦስት ሰዓት ብቻ ምርጫውን ታዝበው ሄደዋል፡፡
በዚህ የምርጫ ጣቢያ 426 መራጮች የተመዘገቡ ሲሆን፣ አብዛኛው መራጭ ከጠዋቱ 12፡00 ሰዓት እስከ 10 ሰዓት ድረስ ድምፅ በመስጠቱ ምክንያት አድማስ ምርጫ ጣቢያና ሌሎችም በርካታ ጣቢያዎች ከ10፡30 በኋላ ጭር ብለው ታይተዋል፡፡
በአዳሬ ቀበሌ የብሩህ ተስፋ ምርጫ ጣቢያም በተመሳሳይ ሁኔታ ከ11፡00 ሰዓት በኋላ ድምፅ የሚሰጡ ሰዎች ጥቂት የነበሩ ሲሆን፣ በዚህና በሌሎችም ጣቢዎች ውስጥ ድምፅ ያልሰጡትን ለመጠበቅ እስከ 12፡20 ሰዓት ድረስ ምርጫ አስተባባሪዎች ሲጠብቁ እንደነበር መመልከት ተችሏል፡፡
በምርጫ ጣቢያዎች ውስጥ ለመራጮች ምቾት ሲባል የፕላስቲክና ረጃጅም አግዳሚ ወንበሮች ተዘጋጅተው ነበር፡፡ ይሁን እንጂ በአንዳንድ የሐዋሳ ዙሪያ ቀበሌዎችና በመሀል ከተማ በሚገኙ የድምፅ መስጫ ጣቢያዎች ጭምር ከቀኑ ስድስት ሰዓት በኋላ መራጮች በብዛት በመምጣታቸው ረጃጅም ሠልፎች ተስተውለዋል፡፡ መራጮች በጠራራ ፀሐይ ረጅም ሰዓታት ለመቆም መገደዳቸው የሒደቱ አንዱ ፈተና መሆኑን መራጮች ተናግረዋል፡፡
አብነት ወንድሙ በሐዋሳ ከተማ በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ፊላደልፊያ ቀበሌ ታጋይ መንደር ቁጥር ሁለት የምርጫ ጣቢያ ድምፅ ሲሰጡ ያገኘናቸው መራጭ ሲሆኑ፣ ከሰዓት 6፡30 ሰዓት አንስቶ ድምፃቸውን ሊሰጡ በጣቢያው ቢገኙም ረጅም ሠልፍ እንደነበርና ይህም አድካሚ እንደሆነባቸው ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡ ሌሎች የምርጫ ቀን ሁነቶች ግን ጥሩ የሚባሉ እንደሆኑም ገልጸዋል፡፡
ከዚህ በተጨማሪ ሪፖርተር ተዘዋውሮ ቅኝት ባደረገባቸው የምርጫ ጣቢያዎች ለመራጮች እንዴት መምረጥና የምርጫ ሰነዶች ላይ ምልክት ማድረግ እንዳለባቸው በምርጫ አስተባባሪዎች ማብራሪያ ሲሰጥ ቢታይም፣ ነገር ግን የገዥውም ሆነ የተፎካካሪ ፓርቲዎችን ስምና የተወዳዳሪዎች ምሥል የተለጠፈበት አንድም የምርጫ ጣቢያ አልተመለከተም፡፡
በተመሳሳይ ሁኔታም የኢትዮጵያ የሲቪል ማኅበራት ድርጅቶች ኅብረት ለምርጫ (ኅብረት ለምርጫ) ሰኞ ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም. ባወጣው የትዝብት ሪፖርቱ፣ ከ2,258 ጣቢያዎች መካከል፣ 2,171 ወይም 96 በመቶ ጣቢያዎች በምርጫ ጣቢያው ውስጥ ወይም በ200 ሜትር ርቀት ውስጥ የፖለቲ ፓርቲ ቅስቀሳ ምልክቶች (ፖስተር) ወይም ቅስቀሳዎች አለመከናወናቸውን ታዝቤያለሁ ብሏል፡፡
በተቃራኒው 87 ወይም አራት በመቶ ጣቢያዎች ውስጥ ወይም በ200 ሜትር ርቀት ክልል ውስጥ የፖለቲካ ፓርቲ ቅስቀሳ ምልክቶች፣ ቁሳቁሶች ወይም የቅስቀሳ እንቅስቃሴዎች መኖራቸውን ስለመታዘቡም ገልጿል፡፡
በሌላም በኩል በአብዛኞቹ ቅኝት ባደረገባቸው የምርጫ ጣቢያዎች ምርጫው ከማለዳው 12፡00 ላይ የተጀመረ ሲሆን፣ በርካታ መራጮችም ድምፃቸውን የሰጡት ከምሽቱ 12፡00 ሰዓት አስቀድሞ መሆኑ ከ10፡30 በኋላ ምርጫ ጣቢያዎች ጭር ብለው መታየታቸውን ተናግሯል፡፡
ሪፖርተር ቅኝት ባደረገባቸው እንደ ታጋይ ቁጥር ሁለትና ብሩህ ተስፋ የምርጫ ጣቢያዎች በአብዛኛው ወጣቶች ድምፅ ሲሰጡ የተመለከተ ሲሆን፣ በሌሎች ጣቢያዎች ደግሞ ጎልማሶችና አረጋውያን ድምፅ ሲሰጡ ለማየት ተችሏል፡፡
በአብዛኛዎቹ የምርጫ ጣቢያዎች ድምፅ የሚሰጡ ወጣት ሴቶች ቁጥር አነስተኛ ነበር፡፡ በሐዋሳ የምርጫ ክልል ብልፅግና ፓርቲና 17 ተፎካካሪ ፓርቲዎች ለምርጫ ቀርበዋል፡፡
የመላው ሲዳማ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ አንድነት ፓርቲ፣ የዎላይታ ሕዝቦች ነፃነት ንቅናቄ፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ አንድነት ፓርቲና ትብብር ለኢትዮጵያ አንድነት ከተፎካካሪ ፓርቲዎች ውስጥ ይገኙበታል፡፡
መብራት ደግፌ በሐዋሳ ምርጫ ክልል ባቤላ ቶላ ክፍለ ከተማ ጨፌ፣ ቆቱ፣ ጀቤሳ፣ ዘለቀ፣ መርሳሞ ምርጫ ጣቢያ የትብብር ለኢትዮጵያ አንድነት የተባለው የፖለቲካ ፓርቲዎች ጥምረት ምርጫ ታዛቢ ሲሆኑ፣ ምርጫው የምርጫ ጣቢያ አስተባባሪዎች በጣቢያው በአግባቡ እየሠሩ መሆናቸውንና ምርጫውም ጥሩ የሚባል እንደሆነ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡
በሌላም በኩል በተለያዩ የምርጫ ጣቢያዎችም የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶችን የሚወክሉ ሁለት ታዛቢዎች፣ እንዲሁም የብልፅግናና የኢዜማ ፓርቲዎችን የወከሉ ታዛቢዎች በቦታው ተገኝተው ሒደቱን ሲከታተሉ እንደነበር መመልከት ተችሏል፡፡
በ2013 ዓ.ም. ጠቅላላ ምርጫ በተለያዩ ቦታዎች እንደታየው ሪፖርተር ቅኝት ባደረገባቸውና የዘንድሮውን ጠቅላላ ምርጫ በተካሄደባቸው የምርጫ ጣቢያዎች ምንም ዓይነት የድምፅ መስጫ ቁሳቁስ ማለትም የምርጫ ወረቀት፣ ቀለም፣ ማኅተም እጥረት አላጋጠመም፡፡
መብራት አክለውም በተለይ ከሰዓት በኋላ በርካታ መራጮች ስለነበሩ የምርጫ አስፈጻሚዎች ከፍተኛ ጫና እንደነበረባቸውና የድካም ስሜት ተፈጥሮ ነበር ብለዋል፡፡
መብራቱ መርሳሞ ባቤላ ቶላ ክፍለ ከተማ ጨፌ፣ ቆቱ፣ ጀቤሳ፣ ዘለቀ፣ መርሳሞ ምርጫ ጣቢያ የምርጫ አስፈጻሚ ሲሆኑ፣ በምርጫ ጣቢያው 420 ወንዶችና 215 ሴቶች በድምሩ 635 መራጮች በጣቢያው ለመራጭነት መመዝገባቸውን ተናግረዋል፡፡ ይህ ጣቢያ ከሐዋሳ መሀል ከተማ አምስት ኪሎ ሜትር የሚርቅ ሲሆን ከከተማው መግቢያ ላይ የሚገኝ ጣቢያ ነው፡፡
የምርጫ አስፈጻሚው መብራቱ ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ በምርጫ ወቅት አስቸጋሪ ከሆኑ ሁኔታዎች መካከል አንዳንድ መራጮች በዲጂታል (ኦንላይን) ለመምረጥ ተመዝግበው የቀጥታ መልዕክት ተልኮላቸው የምርጫ ካርድ ያልወሰዱ፣ በሌሎች ጣቢያዎች ተመዝግበው ነገር ግን በዘለቀ መርሳሞ ምርጫ ጣቢያ ድምፅ ልስጥ ብለው መጠየቃቸውን፣ አንዳንዶች ባለማወቅ የመጡትን ወደ ተመዘገቡበት የምርጫ ጣቢያ ሄደው እንዲመርጡ ማግባባት መቻላቸውን ነግረውናል፡፡
በሐዋሳ ከተማ በመናኸሪያ ክፍለ ከተማ ሚሊኒየም ቀበሌ ክልል ትምህርት ቢሮ ምርጫ ጣቢያ ሌላው ድምፅ የተሰጠበት ምርጫ ጣቢያ ሲሆን፣ ምርጫው ማለዳ 12፡00 ሰዓት መጀመሩ ተረጋግጧል፡፡
ለሐዋሳ ምርጫ ክልል ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አንድ ዕጩ መቅረቡንና ለክልል ምክር ቤት እያንዳንዱ ተፎካካሪ ፓርቲ አሥር አሥር ዕጩ ተወዳዳሪዎችን አቅርቧል፡፡
ሚሊኒየም ቀበሌ ክልል ትምህርት ቢሮ ምርጫ ጣቢያ አስተባባሪ የሆኑት በኃይሉ ጌታቸው እንደነገሩን፣ በጣቢያው 436 መራጮች ድምፅ ለመስጠት ተመዝግበዋል፡፡ በሲዳማ ክልል 18 ፓርቲዎች 1‚338 ዕጩዎችን አቅርበው እየተወዳደሩ መሆናቸውንም የምርጫ ቦርድ መረጃ ያሳያል፡፡
ሚሊኒየም ቀበሌ ክልል ትምህርት ቢሮ ምርጫ ጣቢያ ድምፃቸውን የሰጡ ዜጎችም ለምርጫው ከማለዳው 12፡00 ሰዓት አንስተው ድምፅ እየሰጡ መሆናቸውንና ምርጫው በተረጋጋ ሁኔታ እየተከናወነ እንደነበር ገልጸዋል፡፡
ይሁንና በተለይም በአዲስ ክፍለ ከተማ ታጋይ ቁጥር ሁለት በተባለው የምርጫ ጣቢያ በዲጂታል ለመራጭነት የተመዘገቡ መራጮች የድፅ መስጫ ጣቢያቸውን አድራሻ በአግባቡ ባለመለየታቸው፣ ስማቸው ያልተመዘገበበት ጣቢያ በመሄድ ድምፅ ለመስጠት ሲሞክሩ እንደነበር የጣቢያው ምርጫ አስተባባሪ እርዳቸው እጅጉ ነግረውናል፡፡ በዚህ የምርጫ ጣቢያም 613 መራጮች ድምፅ ለመስጠት ተመዝግበዋል፡፡
ማክሰኞ ግንቦት 25 ቀን 2015 ዓ.ም. ጊዜያዊ የምርጫ ውጤቶች በተለያዩ አካባቢዎች ይፋ መደረጋቸውንም ሪፖርተር ተመልክቷል፡፡
