ህዳሴ ቴሌኮም አክሲዮን ማኅበር ያለበትን 741.1 ሚሊዮን ብር ዕዳ ሳይከፍል ተጨማሪ አገልግሎት እንዳያገኝ፣ ኢትዮ ቴሌኮም መወሰኑ ተሰማ።
በዋናነት ከኢትዮ ቴሌኮም አገልግሎቶችን በመረከብ ሽያጭ በማካሄድ ከሚገኝ ትርፍ ሕልውናው የመሠረተው ህዳሴ ቴሌኮም ከሰሞኑ ኢትዮ ቴሌኮም ያሳለፈበት ውሳኔ የኩባንያውን ሠራተኞችና ባለአክሲዮኖች ሥጋት ላይ መጣሉን ያነጋገርናቸው ሠራተኞች ገልጸዋል፡፡
ህዳሴ ቴሌኮም እስካሁን የኢትዮ ቴሌኮም አገልግሎቶችን ተረክቦ ሲሠራ የቆየው በአብዛኛው በዱቤ ሲሆን፣ ክፍያው ወቅቱን ጠብቆ እየተከፈለ ስላልነበረ የህዳሴ ቴሌኮም ዕዳ 741.1 ሚሊዮን ብር ደርሷል። ይህንንም ተከትሎ ኢትዮ ቴሌኮም መፍትሔ ይሆናል ያለውን ውሳኔ ማሳለፉ ታወቋል።
ውሳኔው የተላለፈው በኢትዮ ቴሌኮም የተዋቀረ አንድ ኮሚቴ፣ ህዳሴ ቴሌኮም አሁን ያለበት ተቋማዊ የፋይናንስ አቅም ደረጃ ያለበትን ዕዳ ከፍሎ ሥራውን ማስቀጠል እንደማያስችለው አጣርቶ ባቀረበው ሪፖርት መሠረት መሆኑ ታውቋል፡፡


ይህ ኮሚቴ በኢትዮ ቴሌኮም ሥር ያሉ ከሸያጭ፣ ከሕግና ከፋይናንስ ክፍሎች የተውጣጣ የዳይሬክተሮች የጋራ ኮሚቴ ሲሆን፣ አጋር ባላቸው እንደ ህዳሴ ቴሌኮም ያሉ ተቋማት ላይ ምርመራ በማድረግ የውሳኔ ሐሳብ ማስተላለፉ ታውቋል። ኮሚቴው የአጋር ድርጅቶችን የብድር ችግር በማጥናትና በመመርመር የመፍትሔ አቅጣጫ እንዲያቀርብ ጭምር በኢትዮ ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ትዕዛዝ ተሰጥቶት ሥራውን ሲያከናውን ከቆየ በኋላ፣ መውሰድ አለበት ያለውን ዕርምጃ በሪፖርቱ አቅርቧል፡፡ በምርመራው መሠረት ኮሚቴው አካፋፋዮቹ ያቀረቡትን ዝርዝር ጥቄያዎችና ወቅታዊ ሁኔታቸውን በጥልቀት በመገምገም የኢትዮ ቴሌኮምን መሠረታዊ ጥቅም በሚያስጠብቅ መልኩ የውሳኔ ሐሳቡን አቅርቧል።
ከህዳሴ ቴሌኮም በተጨማሪ፣ ተመሳሳይ ችግር ገጥሞት ምርመራ የተደረገበት ሳራ መሐመድ ዑስማን የተባለ ኩባንያም ይገኝበታል። እነዚህ ሁለት ድርጅቶች የገጠሟቸው ችግሮች መነሻቸው ይለያይ እንጂ፣ ያስከተሉት ውጤትና ተፅዕኖ ተመሳሳይ መሆኑን የሚያመላክተው የኮሚቴው ሪፖርት፣ ይህንንም መሠረት በማድረግ ሊወሰዱ ይገባሉ ያላቸውን ዕርምጃዎች ዝርዝር አቅርቧል፡፡ የኮሚቴው ሪፖርት፣ ሁለቱም ድርጅቶች በከፍተኛ የጥሬ ገንዘብ ፍሰት እጥረት ውስጥ በመሆናቸው፣ ለፈጸሙት የብድር ግዥ ክፍያ መፈጸም የማይችሉበት ደረጃ ላይ መድረሳቸውን ያመለክታል።
From The Reporter Magazine
በተለይ አጠቃላይ ውዝፍ ዕዳው 741.1 ሚሊዮን ብር የደረሰው ህዳሴ ቴሌኮም አክሲዮን ማኅበር፣ ባለበት ውዝፍ ዕዳና በገጠመው የፋይናንስ እጥረት ሳቢያ ዕለታዊ የሥርጭት ሥራውን መቀጠል እንደማይችል በመግለጽ ኢትዮ ቴሌኮም ድጋፍ ሊያደርግልኝ ይገባል ያላቸውን ጥያቄዎች አቅርቦ እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡ ህዳሴ ቴሌኮም ካቀረባቸው ጥያቄዎች መካከል፣ ያለ ባንክ ዋስትና እስከ 500 ሚሊዮን ብር የሚደርስ የብድር ግዥ ለአራት ወራት እንዲፈቀድት፣ ለወቅታዊ የብድር ግዥዎችና ለደረሱ ክፍያዎች የጊዜ ገደብ እንደራዘምለት፣ ዕዳውን በወቅቱ ባለመክፈሉ ምክንያት የተጣሉበት ድርብርብ ቅጣቶች እንዲነሱለት የሚሉት ይገኙባቸዋል፡፡
ኩባንያው እንዲህ ያሉ ጥያቄዎችን ቢያቀርም፣ ኮሚቴው ያደረጋቸው ማጣሪያዎች እንዲህ ያለውን ጥያቄ ለመመለስ አስቻይ ሁኔታ ያለመኖሩን የሚጠቁም ሆኗል፡፡ በዋስትና ብድር ለማግኘት የሚያስችል ሁኔታ ውስጥ አለመሆኑንም ኮሚቴው በምርመራ ሪፖርቱ አቅርቧል፡፡ በሪፖርቱ እንደጠቀሰውም ህዳሴ ቴሌኮም ለፋይናንስ እጥረት የተጋለጠውና የችግሩ መንስዔዎች ከግዥ መጠን በላይ የተፈጸሙ ክፍያዎች፣ ለባንክ ዋስትና የተቀመጠው 25 በመቶ ማስያዣ፣ ለፍራንቻይዝ፣ ለተሽከርካሪ ጥገና ማዕከላት ማስፋፊያ ከፍተኛ ወጪ መደረጉ፣ የውስጥ አሠራርና በሎጂስቲክስ ድክመት ሽያጭ በወቅቱ ወደ ዋና የሒሳብ ቋት ገቢ አለመደረጉ ናቸው።
በመሆኑም ለኩባንያው ያለ ባንክ ዋስትና ከኢትዮ ቴሌኮም ምርት እንዲወስድ መፍቀድ፣ ኢትዮ ቴሌኮም ላይ ተፅዕኖ ያሳድራል የሚል መደምደሚያ ላይ የደረሰው ኮሚቴው፣ ይህም በኢትዮ ቴሌኮም የጥሬ ገንዘብ ፍሰት ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ የሚያሳድር መሆኑንም አስታውቋል፡፡ ለሌሎች አከፋፋዮችም መጥፎ ተሞክሮ በመሆኑና ከማከፋፈል ውሉ ሐሳብና ዓላማ ውጪ በመሆኑ ተቀባይነት እንደማይኖር በሪፖርቱ አሥፍሯል፡፡ በሌላ በኩል ግን በዚህ ሪፖርት ውስጥ የተጠቀሱት ሁለቱ አጋሮች ሚዛናዊ ድጋፍ ካልተደረላቸው ሊከተሉ የሚችሉ አደጋዎችንም በዚህ ሪፖርቱ አካቷል፡፡ ሊከተሉ ይችላሉ ብሎ የገለጻቸው አደጋዎች፣ ‹‹አከፋፋዮቹ በገበያ ላይ የፈጠሩት ክፍተት ተፎካካሪዎች ይቆማሉ፣ የማከፋፈልና የችርቻሮ ሰንሰለቱ ወደ ተፎካካሪዎች የመሸጋገር ዝንባሌ ሊያሳይ ይችላል›› በሚል ተገልጿል፡፡
From The Reporter Magazine
አያይዞም፣ ድርጅቶቹ ቢፈርሱ ውዝፍ ዕዳውን ለማስመለስ የሚደረገው የሕግ ክርክር ረዥም ጊዜና ከፍተኛ ወጪ የሚጠይቅ መሆኑ፣ ጉዳዩን ግራና ቀኝ በማየትና የኩባንያውን ጥቅም በማስቀደም ኮሚቴው የደረሰበትን የውሳኔ ሐሳቦች እንዲፀድቁ ጠይቋል፡፡
በኮሚቴ ውሳኔ መሠረት ‹‹ለማንኛውም ዓይነት የአየር ሰዓትና ሲም ካርድ ግዥ በአከፋፋይ በውሉ መሠረት ተገቢና በቂ የሆነ፣ በሁኔታዎች ላይ ያልተመሠረተ የባንክ ዋስትና በማቅረብ ብቻ ግዥ እንዲፈጽሙ›› የሚለው ውሳኔ አንዱ ነው፡፡ ማንኛውም በብድር ግዥ ተከናውኖ ክፍያቸው ያለፉ ዕዳዎች ይህ ውሳኔ ከፀደቀበት ቀን ጀምሮ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ሙሉ በሙሉ ክፍያ እንዲፈጸምባቸው ድርጅቶቹ እንዲያገግሙና የምርት ሥርጭቱ እንዲቀጥል ለማገዝ ከውዝፍ ዕዳው ጋር ተያይዘው የተከማቹ ቅጣቶች በሙሉ እንዲነሱ የሚለው ውሳኔ ተፈጻሚ እንዲሆን ኮሚቴው ውሳኔ አሳልፏል፡፡ ይህ ውሳኔ እንደተጠበቀ ሆኖ ከኢትዮ ቴሌኮም የሚሰጠው ድጋፍም ተግባራዊ ከመደረጉ በፊት ህዳሴ ቴሌኮምና ሌላው አጋር ኩባንያ እንደ ግዴታ የተቀመጡትን የመፍትሔ ሐሳቦች በጽሑፍ ሊያረጋግጥ እንደሚገባ ግን አስታውቋል፡፡
በጽሑፍ ሊያረጋግጠው ይገባል ተብሎ የተጠቀሰው ደግሞ ‹‹ወደፊት በማንኛውም ምክንያት ተመሳሳይ የፋይናንስ እጥረት ቢከሰት ከኢትዮ ቴሌኮም ተመሳሳይ ድጋፍ እንደማይጠይቁ የሚገልጹ የዋስትና ደብዳቤ ማቅረብ›› የሚል ይገኝበታል፡፡ ከዚህም ሌላ ለወደፊቱ የሚከናወኑ የብድር ግዥዎች በተቀመጠው የጊዜ ገደብ ውስጥ በጥብቅ ለመክፈል መደበኛ የጽሑፍ ግዴታ መግባት እንደሚኖርባቸውም ይገልጻል፡፡ ይህ ከተደረገ በኋላም ቢሆን የአፈጻጸም ሁኔታው በየሳምንቱ የሚገመገም ሆኖ የተቀመጠውን የክፍያ መርሐ ግብር ባላከበረ አጋር ላይ የብድር አገልግሎቱ ድጋፍ ወዲያው እንዲቋረጥ የሚደረግ ስለመሆኑም ኮሚቴው አስገዳጅ ሁኔታ አሥፍራል፡፡ እንዲህ ያለው ድምዳሜ ላይ የደረሰበትን ሁኔታም ሲያብራራ፣ የኢትዮ ቴሌኮምን የገበያ ድርሻ ለመጠበቅ ውዝፍ ዕዳዎችን በሥርዓት ለመሰብሰብ ሲባል ተዋቅሮ ተግባሩን ለማከናወን እንዲያስችለው ነው፡፡ ኮሚቴው በአጋር አከፋፋዮች በሆኑት የህዳሴ ቴሌኮም ኩባንያና ሳራ መሐመድ ዑስማን ላይ የተከሰቱን የፋይናንስ ችግሮች በጥልቀት በመመርመርና መንስዔዎችን በመለየት ሚና የሆነ የውሳኔ ሐሳብ ለማቅረብ እንዲቻል አጋሮቹ ካቀረቡ ጥያቄ ባለፈ የተመለከታቸው ነገሮች እንዳሉም ሪፖርቱ አመልክቷል፡፡
በተለይ የኢትዮ ቴሌኮም የፋይናንስ ደኅንነት የሽያጭ አስተዋጽኦና የገበያ መረጋጋትን ማረጋገጥ፣ እንዲሁም የአጋሮቹን የጥሬ ገንዘብ ፍሰትና የማገገም አቅምን ማጠናከር ላይ ያተኮረ ትንታኔ መስጠቱንም አስታውቋል፡፡ በዚህም መሠረት ኮሚቴው በዋናነት በሚከተሉት ሦስት ነጥቦች ላይ ትኩረት በማድረግ ወደ ውሳኔ ስለመግባቱ በመጥቀስ የህዳሴ ቴሌኮም ኩባንያና የሳራ መሐመድ ዑስማን የጥሬ ገንዘብ እጥረት መንስዔዎችን መለየት፣ አጋር አከፋፋዮች ከሥራ ውጪ ከሆኑ ያላቸው የምርት፣ አገልግሎት ሰንሰለት ወደ ተፎካካሪዎች ሊሸጋገር የሚችልበትን መገምገም፣ የሚቀርቡት የውሳኔ ሐሳቦች የኢትዮ ቴሌኮምን ጥቅም የሚያስከብር አኳኃን ተፈጻሚ መሆን እንዳለበትም ጠቁመዋል፡፡
በእነዚህም የአሠራር እንቅፋቶችን በማስወገድ የዕለት ተዕለት የማከፋፈል ሥራውን ቀጣይነትን ለማረጋገጥ የታለመ ሲሆን፣ የምርት የሽያጭ የሥርጭት ሰንሰለቱን በማስጠበቅ ውዝፍ ዕዳዎችን በሥርዓት ለመሰብሰብ ያስችላል ተብሎ እንደሚጠበቅ አስታውቋል፡፡
ኢትዮ ቴሌኮም ያዋቀረው ኮሚቴ የአጋር ድርጅቶቹን ሥራ የማስቀጠል ዓላማም ያለው በመሆኑ፣ ይህንን ለማድረግ ያስችላል ያላቸውንም የመፍትሔ ሐሳቦችም አካቶ አቅርቧል።
ኮሚቴው አጋሮቹ ካቀረቡት ደብዳቤ፣ ከተደረጉ ውይይቶች፣ ከውል ስምምነቶችና ከሽያጭ ፖሊሲዎች በመነሳት የወሰናቸው ውሳኔዎችና ዕርምጃዎች የፋይናንስ ዲሲፕሊንን በጠበቀ መልኩ የአጋሮችን ማገገም ለመደገፍ የታለሙ ስለመሆናቸው አስታውቋል፡፡
በዚህም መሠረት ለህዳሴ ቴሌኮም ኩባንያ የቀረበ ውሳኔ ሐሳብ ለሁሉም ዓይነት የአየር ሰዓትና ለሲም ካርድ የክሬዲት ግዥ በማከፋፈል ውሉ መሠረት ተገቢና በቂ ሁኔታዎች ላይ ያልተመሠረተ የባንክ ዋስትና በማቅረብ ብቻ ግዥ እንዲፈጽም የሚለው በዋናነት ተቀምጧል፡፡ ማንኛውም በክሬዲት ግዥ ተከናውኖ ጊዜው ያለፈ ውዝፍ ዕዳ፣ ይህ ውሳኔ ከፀደቀበት ቀን ጀምሮ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ክፍያ እንዲፈጸም የኮሚቴው ውሳኔ ሪፖርት ውስጥ ተካትቷል፡፡ ድርጅቱ እንዲያገግምና የምርትና አገልግሎት ሥርጭት ሥራው ቀጣይነት እንዲረጋገጥ፣ ከውዝፍ ዕዳው ጋር ተያይዘው የተከማቹ ቅጣቶች በሙሉ እንዲነሱ፣ በገበያ መረጋጋትን በማይነካ መልኩ፣ እንዲሁም ድርጅቱ ባቀረበው በሁኔታዎች ላይ ያልተመሠረተ የባንክ ዋስትናን ታሳቢ በማድረግ የቫውቸር ካርድ፣ የቪዲ (አየር ሰዓት) ወርኃዊ የሽያጭ ዕቅዱ ተመጣጥኖ እንዲመደብ የሚል ውሳኔ በአማራጭነት ቀርቧል፡፡
ኩባንያቸው የገባበት ችግር እጅግ ያሳሰባቸው መሆኑን የሚገልጹ ሠራተኞች ግን ኢትዮ ቴሌኮም አሁን ደርሼበታለሁ ባለው ውሳኔ መሠረት በአንድ ወር ውስጥ 741 ሚሊዮን ብሩን ለመክፈል ይችላል ወይ? የሚለውን ነው፡፡ የኩባንያው ህልውና የተመሠረተው ኢትዮ ቴሌኮም በሚሰጣቸው አገልግሎቶች ላይ የተመሠረተ በመሆኑ፣ ይህ አገልግሎት ከተቋረጠ የሚያካሂደው ሽያጭ አይኖርም፡፡ ባለፉት ሦስት ወራትም አገልግሎቱ ተቋርጦ ስለነበር ገቢው ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ማሳደሩን ይገልጻሉ፡፡ ሽያጭ ከሌለ ደግሞ የሚገኝ ገቢ ስለማይኖር ኩባንያው አደጋ ውስጥ ሊገባ ስለሚችል ይህ እንዳይሆን የኩባንያው የሥራ ኃላፊዎች የተለያዩ አማራጮችን መፈለግ አለባቸው፡፡
እንደ ሠራተኞቹ ገለጻ፣ ኢትዮ ቴሌኮም በአንድ ወር ውስጥ ይክፈል ያለውን ዕዳ ህዳሴ ቴሌኮም መክፈል የሚችልበት አቅም ላይ ባይሆንም፣ ጊዜ ቢሰጠው ግን ይህንን መክፈል የሚችልበት አማራጮች እንዳሉ የሚገልጹት እነዚሁ ተቆርቋሪ ሠራተኞች ይገልጻሉ፡፡ አንዱ አማራጭ ኩባንያው ባለፉት 14 ዓመታት ያፈራቸው ሀብቶችን አስይዞ ብድር የሚያገኝበትን ሁኔታ ማመቻቸት ነው፡፡
ኩባንያው በአዲስ አበባና በአራት የክልል ከተሞች የአምስት ሕንፃዎች ባለቤት በመሆኑ፣ ይህ አሴት ተጨማሪ ብድር ለማግኘት የሚያስችል በመሆኑ፣ ይህንን አማራጭ በመጠቀም ዕዳውን ማቃለል የሚችልበትን መንገድ ማመቻቸት እንዳለበትም ይጠቁማሉ፡፡
የህዳሴ ቴሌኮም ለዚህ ሁሉ ችግር መዳረግ በኩባንያው ውስጥ ያለ ችግር ነው የሚሉ ወገኖች የሒሳብ ሪፖርቶቹ ሳይቀር መመሰቃቀል የሚታይባቸው ሆነው መገኘታቸውን ይገልጻሉ፡፡ ኮሚቴው ባቀረበው ሪፖርት ውስጥ አማራጭ መፍትሔ ለመስጠት እንኳን ህዳሴ ቴሌኮም በአሁኑ ወቅት ኦዲት እያካሄደ በመሆኑና ባንኮች ተጨማሪ የባንክ ዋስትና ለመስጠት ኦዲት የተደረገ የፋይንስ መግለጫ ስለሚጠይቁ ይህንን ማቅረብ ያልተቻለ መሆኑን በሪፖርቱ ማካተቱ ደግሞ ኩባንያውን አጣብቂኝ ውስጥ ከቶታል ይላሉ፡፡
በ2017 የሒሳብ ዓመት ሪፖርት ሲቀርብም በቦርዱና በማኔጅመንቱ የቀረቡት የሒሳብ ሪፖርቶች የተለያዩ መሆናቸው፣ የሒሳብ ሪፖርቱ በገለልተኛ ኦዲተር እንዲታይ እስከመወሰን አድርሷል፡፡
በዚሁ ውሳኔ መሠረትም ይህንን የሒሳብ ሪፖርት ለማጣራት የተመረጠ ኦዲተር የምርመራ ሥራውን እያከናወነ ሲሆን፣ ነገር ግን ምርመራውን ከጀመረ አራት ወራት ቢሆኑትም እስካሁን የደረሰበትን ውጤት አለመታወቁ ከነበረበት አጣብቂኝ ለማውጣት ሌላ እንቅፋት እንደሆነበት እነኚሁ ሠራተኞች ይገልጻሉ፡፡
በኢትዮ ቴሌኮም የተዋቀረው ኮሚቴ ሪፖርት የሳራ መሐመድ ዑስማን ኩባንያ ላይም ማንኛውም በክሬዲት ግዥ ተከናውኖ ጊዜው ያለፈ ውዝፍ ዕዳ ይህ ውሳኔ ከፀደቀበት ቀን ጀምሮ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ክፍያ እንዲፈጽም፣ ድርጅቱ በራሱ ሠራተኞች የደረሱበትን ያልታሰበ የወንጀል ድርጊት ከግምት ውስጥ በማስገባትና የንግድ አጋርነታችንን ለማጠናከር ሲባል፣ የተከማቹ ቅጣቶች በሙሉ እንዲነሱ የሚል ውሳኔ ያሳለፈው መሆኑ ታውቋል፡፡ እንዲህ ያሉ ድጋፎችን ለማድረግ ግን ሁለቱም አጋር ድርጅቶች ሊያሟሉ ይገባል ያላቸውን ተጨማሪ ግዴታዎች ወደፊት በማንኛውም ምክንያት በውል መሠረት ተግባራቸውን ማከናወንና ተመሳሳይ የፋይናንስ እጥረት ቢከሰት፣ ከኢትዮ ቴሌኮም ተመሳሳይ ድጋፍ እንደማይጠይቁ የጽሑፍ ዋስትና እንዲያቀርቡ፡፡ ለወደፊቱ የሚከናወኑ የብድር ግዥዎች በሙሉ በተቀመጠው የጊዜ ገደብ ውስጥ በጥብቅ ለመክፈል የጽሑፍ ግዴታ እንዲገቡ አስገዳጅ ሁኔታ አስቀምጧል፡፡
የሳራ መሐመድ ዑስማን የተጠራቀመ ቅጣት ሳይጨምር አጠቃላይ አለበት ተብሎ የተጠቀሰው ዕዳ 41.9 ሚሊዮን ብር ነው፡፡ የዚህ አጋር ድርጅት ችግር መነሻው የንግድ ሥራ ውድቀት ሳይሆን፣ በውስጥ ሠራተኞች የተፈጸመ የኢቪዲ/ኢ ገንዘብ ኃላፊና የፋይናንስ ሥራ አስኪያጅ ያለ ፈቃድ ቼኮችን በመቁረጥና ሕገወጥ የአየር በአየር ንግድ በማካሄድ የድርጅቱን ገንዘብ መመዝበራቸው ለቀውሱ መንስዔ መሆኑን ኮሚቴው ማረጋገጡንም ጠቅሷል፡፡
ህዳሴ ቴሌኮም ገብቶበታል የተባለውን አጣብቂኝና የኢትዮ ቴሌኮም የውሳኔ ሐሳብ በተመለከተ አንድ ያነጋገርናቸው የህዳሴ ቴሌኮም የሥራ ኃላፊ ተፈጠረ የተባለውን ችግር እየፈቱ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
ከዚህም ቀደም ተመሳሳይ ዕዳዎች ሲኖሩ ሲከፍል የነበረ በመሆኑ፣ አሁንም ያለበትን ዕዳ የሚከፍልና ድርጅቱን ሥጋት ላይ የሚከት ነገር አለመኖሩን ጠቁመዋል፡፡ በዚህ ሐሳብ የማይስማሙ ተቆርቋሪ ሠራተኞች ግን ኩባንያው ከዚህ በፊት እንዲህ ያለ ነገር አጋጥሞት የማያውቅ መሆኑንና አሁን በኢትዮ ቴሌኮም ሊወሰድ የታሰበው ዕርምጃ የሚተገበር ከሆነ አገልግሎቱ ውስን ስለሚሆን ድርጅቱ ህልውናውን ጥያቄ ውስጥ ይከታል የሚል ሥጋት አላቸው፡፡
ኩባንያው አሁን ላጋጠመው የገንዘብ እጥረት ኩባንያው ውስጥ ያሉ አንዳንድ ችግሮች ሁኔታውን እንዲባባሱ ማድረጋቸውን የሚገልጹት እነዚሁ ሠራተኞች፣ ድርጅቱን ለማስቀጠል ባለአክሲዮኖቹ አፋጣኝ ዕርምጃ ሊወስዱ እንደሚገባም ሳያመለክቱ አላለፉም፡፡
ህዳሴ ቴሌኮም በ2,508 ባለአክሲዮኖች የተቋቋመ ሲሆን፣ ከአንድ ሺሕ በላይ የሽያጭ ማዕከላትን ያሉትና 90 በመቶው በገጠራማ ከአባቢዎች ያሉ ናቸው፡፡ የኢትዮ ቴሌኮም ሪፖርት ውስጥ ህዳሴ ቴሌኮም አጠቃላይ ያለው የሀብት መጠን ከሦስት ቢሊዮን ብር በላይ መሆኑን ይጠቅሳል፡፡
