ስድስተኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሥራ ዘመኑን ሲጠናቀቅ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ከምክር ቤቱ አባላት ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ሰፊ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ስብሰባ በ2013 ዓ.ም. ስድስተኛው አገራዊ ምርጫ ተመርጠው ወደ ምክር ቤቱ የገቡ እንደራሴዎች ሽኝት በተቃረበበት ወቅት የተካሄደ በመሆኑ ትኩረት የሳበ ነበር፡፡ ስብሰባው ከዚህ በላይ ደግሞ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጭምር የሚገኙበት የበጀት ዓመቱ የመዝጊያ ስብሰባ በመሆኑ ጭምር ምን ይስተናገድበታል የሚለው ጉዳይ ተጠባቂ ነበር፡፡ ልክ እንደ ቀደሙ የፓርላማ ዙሮች ሁሉ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትሮች በዓመቱ መጀመሪያ፣ አጋማሽና መዝጊያዎች ለስብሰባው በተገኙ ቁጥር የምክር ቤት አባላት የሚቀርቡላቸው ጥያቄዎችና የሚሰጡት ምላሽ ሁሌም ተጠባቂ ነው፡፡


ጥያቄ አቅራቢ ከነበሩ የምክር ቤቱ አባላት መካከል የዜጎች አንገብጋቢ ጥያቄዎች ናቸው የሚሏቸውን የተለያዩ ጥያቄዎችና አስተያየቶች ሲያነሱ ተደምጠዋል፡፡ ከእነዚህ ጥያቄዎች መካከል ደግሞ በበርካታ ጠያቂዎች በተለያየ ይዘትና አገላለጽ የቀረበው የሰላምና መረጋጋት ጉዳይ ጎልቶ ይጠቀሳል፡፡ በርካቶች በተለያየ መንገድ ላነሱት ሰላምን ለተመለከቱ ጥያቄዎች ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ (ዶ/ር) የሰጡት ምላሽና ማብራሪያ ትኩረት የሚስብ ነበር፡፡
ቀድመው የመጠየቅ ዕድል ያገኙ ሁለት የምክር ቤቱ ተወካዮች ዘላቂ ሰላም ለአገሪቱ ያስገኛል ተብሎ የተጀመረው አገራዊ ምክክሩ የበለጠ የተሳካ እንዲሆን ምን ይደረግ? እንዲሁም በትግራይ ክልል ዘላቂ ሰላም ለማረጋገጥ ምን እየተደረገ ነው? የሚሉ ይዘት ያላቸው ጥያቄዎችን አንስተዋል፡፡
የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ (ኢዜማ) ፓርቲ ተወካዩ አቶ ባርጠማ ፈቃዱ፣ የመልካም አስተዳደር ችግርና ፍትሕ ማጣት ዜጎችን ተስፋ አስቆርጦ ለሰላምና አለመረጋጋት ዕጦት እንደሚዳርግ፣ እንዲሁም ከፀጥታ አኳያ መሻሻል ቢኖርም ነገር ግን አሁንም ችግር መኖሩን በማስታወስ፣ መንግሥት ለዘላቂ ሰላምና መረጋጋት ለመፍጠር ምን ዓይነት ዕቅድ እንዳለው ጠይቀዋል፡፡
በብዙ ቦታዎች ዕገታና አስገድዶ ገንዘብ መቀበል በዜጎች ላይ እንደሚፈጸምና ታጣቂዎች በሚንቀሳቀሱበት አካባቢ ግድያ መቀጠሉን የጠቆሙት አቶ ባርጠማ፣ ታጣቂዎችም ሆኑ መንግሥት ለሰላም ትኩረት እንዲሰጡ ጠይቀዋል፡፡ ጦርነት፣ ሥርዓት አልበኝነት፣ መፈናቀልና ግድያ እንዲቆሙ ለሰላም ቅድሚያ መሰጠት እንዳለበት የገለጹ ሲሆን፣ ከዚህ ደግሞ መንግሥትም ሆነ ታጣቂዎች በአጠቃላይ ደግሞ አገሪቱ እንደሚያተርፉ ነበር የጠቆሙት፡፡
From The Reporter Magazine
ሌላው የምክር ቤት አባልና የአዳማ ዩኒቨርሲቲ የኬሚስትሪ ባለሙያ ዓለሙ ጎንፋ (ዶ/ር)፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ሃይማኖትን ተገን በማድረግ የሚነሱ ግጭቶችና አለመረጋጋቶችን በተመለከተ ጠይቀዋል፡፡ የፌዴራል የሕግና ፍትሕ ኢንስቲትዩት ምክትል ዳይሬክተሩ ዘካሪያስ ኤርቆላ (ዶ/ር)፣ የሆርሙዝ ሰርጥ ቀውስ እንደ ኢትዮጵያ ላሉ አገሮች በአንድ የባህር በር መስመር ላይ ጥገኛ መሆን ብቻ አደገኛ እንደሆነ ማረጋገጡን ጠቅሰው፣ እንዲሁም የባህር በር ጥያቄውን ፍትሐዊነት አመልክተው ባንዳና ባንዳዎች ያሏቸው ኃይሎች የሚያነሱትን ተቃውሞ ለመቀልበስ ምን ዕቅድ እንዳለ ጠይቀዋል፡፡ ሌላው ተወካይ ቶፊቅ አብዱላሂ (ዶ/ር)፣ ከዚሁ ጋር የተያያዘ ጥያቄ ያነሱ ሲሆን፣ በዋናነት ቀጣናዊ የሰላምን ፀጥታ ሥጋት የሆኑ ችግሮችና የውጭ ተጋላጭነቶች ላይ መንግሥት ምን እየሠራ እንደሆነ ጥያቄ አቅርበዋል፡፡
የቦሮ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ ተወካዩ መብራቱ ዓለሙ (ዶ/ር) አራት ጥያቄዎች እንዳሏቸው ገልጸው ከእነዚህ መካከልም ዘላቂ ሰላም፣ ብሔራዊ መግባባትና የሕግ የበላይነትን የተመለከተው አንዱና ዋናው መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ የልማት ውጤቶች መሠረት ዘላቂ ሰላም መሆኑን ያሰመሩበት ጠያቂው፣ በኢትዮጵያ በየአካባቢው ዜጎች ተረጋግቶ መኖር፣ በነፃነት መንቀሳቀስ፣ ሀብታቸውን ማልማትና ልጆቻቸውን ማስተማር እንደሚፈልጉ በማስታወስ ዘላቂ ሰላምና መረጋጋትን በሁሉም የአገሪቱ አካባቢዎች በእኩልነት ለማረጋገጥ መንግሥት ምን እያደረገ እንደሆነ ጠይቀዋል፡፡
የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ፓርቲ የቀድሞ ተወካይ ደሳለኝ ጫኔ (ዶ/ር) ባነሱት ጥያቄ፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ (ዶ/ር) መንግሥት የሥልጣን ዘመን መዋቅራዊ ድክመት የሚታይበት የታሪክ አጋጣሚ ሆኖ እንደሚታይ ጠንከር ባለ አገላለጽ ተችተዋል፡፡ ባለፉት አምስት ዓመታት የኢትዮጵያ ሕዝብ ከባድ ዋጋ ሲከፍል መቆየቱን በማስታወስ፣ እንዲሁም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወደ ሥልጣን ሲመጡ የገቡት የሰላምና የብልፅግና ተስፋ አለመፈጸሙን ጠቅሰው፣ ‹‹የአምስት ዓመት ቆይታዬ የመጨረሻ ጥያቄዎች›› ያሏቸውን ጥያቄዎች አከታትለው ጠይቀው ነበር፡፡
From The Reporter Magazine
የሰሜን ኢትዮጵያው ጦርነት አስከፊ ጠባሳ ሳይሽር በአማራ፣ በኦሮሚያ፣ በጋምቤላ፣ በቤኒሻንጉል ጉሙዝና በሌሎችም ክልሎች ያላባሩ ግጭቶች እንደሚታዩ፣ ብሔርና ሃይማኖት ተኮር ጥቃቶች እንደቀጠሉ፣ ዕገታዎችና አለመረጋጋቶች የዜጎችን ሕይወት አደጋ ላይ መጣላቸውን አስረድተዋል፡፡ አገራዊ አለመግባባቶች መስፋታቸውንና መካረሮች እንደሚታዩ፣ የፖለቲካ ምኅዳሩ ብቻ ሳይሆን የሚዲያና የሲቪክ ምኅዳሮች መጥበባቸውን፣ የፖለቲካ እስረኞች የፍትሕና ሕገ መንግሥታዊ መብት መነፈግ፣ በአጠቃላይ የሚታየው የፖለቲካ፣ የሰላምና የፀጥታ ውድቀት የመንግሥት መዋቅራዊ ውድቀት መሆኑንም አውስተዋል፡፡
የመንግሥት ብድርና ዕዳ ጭማሪ፣ የኢኮኖሚ ዕድገት አኃዝ ቅሸባ፣ የትምህርት ዘርፍ መውደቅና የሥራ ዕድል ማጣት፣ የሰብዓዊ ረድኤት አቅርቦት ሥርዓት ችግር፣ የኑሮ ልዩነት መስፋት፣ የዋጋ ንረት ማሻቀብ የመሳሰሉ ጉዳዮችን የተመለከቱ ያሏቸውን ጥያቄዎች ያስከተሉት ደሳለኝ (ዶ/ር) በመደምደሚያቸው የሰላም ጉዳይን በድጋሚ አንስተው ነበር፡፡
ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት፣ ብሔራዊ ደኅንነትና ልማት በአገሪቱ ለመፍጠር እውነተኛ ብሔራዊ ውይይትና ፖለቲካዊ መፍትሔ መፈለግ እንደሚጠይቅ ጠቁመዋል፡፡ በብሔራዊ ምክክር አጀንዳ ማሰባሰብ ከ200 ሺሕ በላይ ዜጎች መሳተፋቸውን ኮሚሽኑ አሁን ላይ ለዋናው የብሔራዊ ምክክር ስብሰባ መዘጋጀት መጀመሩን ጠቅሰው፣ ነገር ግን ውጤታማ እንዲሆን ከተፈለገ ሒደቱን ከመንግሥት ፖለቲካዊ ተፅዕኖ ሙሉ ለሙሉ ነፃ ማድረግ እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል፡፡ በተጨማሪም ሁሉንም የታጠቁና ያልታጠቁ ኃይሎች ያሳተፈ እንዲሆን ማድረግ ጠቃሚ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ ይህ ባልሆነበት ከታጠቁ ኃይሎች ጋር ግጭት ሳይቆም የሚደረግ የምክክር ሒደት ጊዜና ገንዘብ የባከነበት ብቻ ይሆናልም ብለዋል፡፡ ልክ እንደማንነትና ወሰን ኮሚሽን እንዲሁም እንደ ብሔራዊ ዕርቀ ሰላም ኮሚሽን ሁሉ መንገድ ላይ እንደሚቀርም በንፅፅር አቅርበዋል፡፡
በሌላ በኩል ነፃና ፍትሐዊ የሽግግር ፍትሕ ሒደት፣ ሁሉን አቀፍ አገራዊ ዕርቅ ማድረግ፣ ሁሉን አሳታፊ ሕገ መንግሥታዊ ማሻሻያ ማድረግ፣ የክልሎችን ራስን በራስ የማስተዳደር መብት የሚያረጋገጥ ሥርዓት መፍጠር፣ የፖለቲካ ችግሮችን ከኃይል ይልቅ በሰላም መፍታት ለሰላም አስፈላጊ መሆናቸውን ደሳለኝ (ዶ/ር) ጠቃሰዋል፡፡ ዘላቂ ሰላም በኢትዮጵያ ለመገንባት ግልጽ የሰላም ዕቅድና የጊዜ ሰሌዳ ካለው መንግሥት እንዲያብራራም አያይዘው ጠይቀዋል፡፡
ለእነዚህና ለሌሎችም ጥያቄዎች ሰፊ ጊዜ ወስደው ማብራሪያ የሰጡት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ (ዶ/ር)፣ ስለሰላም ጉዳዮች ትኩረት ሰጥተው ምላሽ ያሏቸውን ሐሳቦች አንስተው ነበር፡፡
‹‹የአጋጪና ገጪ›› ሚናን የሚጫወቱ ወገኖች የሰላም መደፍረስ ምንጭ መሆናቸውን የጠቆሙት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ሰባተኛው አገራዊ ምርጫ ራሱ የፀረ ሰላም ኃይሎች የጥቃት ዒላማ የነበረ ቢሆንም በስኬት መጠናቀቁን አውስተዋል፡፡ የፕሪቶሪያ ሰላም ስምምነትን ‹‹አሸናፊና ተሸናፊ እኩል ተቀምጠው በመደራደር የተገኘ ውጤት›› መሆኑን አስምረውበታል፡፡ የጀርመኖችን ‹‹አመክንዮ ሲሞት ጉልበት ቦታውን ይይዛል›› የሚል አባባል ተውሰው የሰላምና ፀጥታ ጉዳዮችን በሰፊው ወደ ማብራራት የገቡት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ በዘንድሮው ምርጫ ‹‹ጽንፈኝነት፣ ባንዳነትን አንፈልግም›› ማለታቸውን ጠቅሰዋል፡፡
ፓርቲያቸው ብልፅግና 85 በመቶ የፓርላማ ወንበሮች በሚመረጡባቸው አካባቢዎች ብቻ ተወዳድሮ 15 በመቶውን ለተፎካካሪ ፓርቲዎች መተውን ለሰላምና ለዴሞክራሲ የተከፈለ ዋጋ፣ እንዲሁም በአፍሪካ ያልታየ ዕርምጃ ሲበማለት የጥይት ድምፅ ሳያሸብረው የመረጠውን ሕዝብ አደራም አቅልሎ እንደማያይ ጠቁመዋል፡፡
ለ30 ዓመታት ታፍነው የቆዩ ብሶቶች በለውጡ ማግሥት ፈንድተው መውጣታቸው፣ የተዛባ ትርክት ሰፍኖ መቆየቱ ሁሉ ተደማምረው የግጭትና አለመረጋጋት ችግር መፍጠራቸውን ዓብይ (ዶ/ር) ገልጸዋል፡፡
እሳቸው ከመጡ ጀምሮ ከ225 ባላነሱ መድረኮች ከሕዝብና ከኅብረተሰብ ተወካዮች ጋር ስብሰባ ማድረጋቸውን፣ ፓርቲያቸው ብልፅግና ደግሞ ከ4,000 በላይ መድረኮች ፈጥሮ ውይይት መደረጉን፣ እንዲሁም ዳያስፖራውን ጨምሮ በመቶ ሺሒ የሚቆጠሩ ሰዎችን ያሳተፉ መድረኮችን በብሔራዊ ምክክር ኮሚሽኑ በኩል ማካሄድ መቻሉን ትልቅ ቦታ የሚሰጠው መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ እነዚህ ሁሉ ውይይቶች ደግሞ በማኅበረሰቦች መካከል ግጭት መቀነሳቸውን፣ ሃይማኖትን ከሃይማኖት የሚደረጉ ግጭቶችን መቀነሳቸውን አውስተዋል፡፡ እነዚህን ማኅበረሰባዊ ልዩነቶች ተጠቅመው ሕዝብ ሲያጋጩ የነበሩ ወገኖች አሁን ላይ ታክቲካቸውን ለውጠው ‹አጋጪ የነበሩት ራሳቸው ኅብረተሰቡን ገጭ› መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡
ዓብይ (ዶ/ር) ሲቀጥሉም ኢትዮጵያ ተረጋግታና ፀንታ እንዳትኖር የሚፈልጉ ኃይሎች ያሏቸው ወገኖች ባንዳ በማሰማራት ችግር እየፈጠሩ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ እነዚህ ባንዳዎች ደግሞ ያልሠለጠነና ያልተገራ ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ በማድረግ አገርና ተቋማትን እስከማፍረስ ይሠራሉ ብለው፣ በአፍሪካ አገሮች ከሚታዩ ሸማቂዎች እንቅስቃሴ ጋር ተመሳሳይ አካሄድ እንዳላቸው ጠቁመዋል፡፡ የናይጄሪያውን አክራሪ የሃይማኖት ሸማቂ ቡድን ቦኮ ሀራምን ሁኔታ በምሳሌነት ያነሱ ሲሆን በቅርቡ 13 ሺሕ ተዋጊዎቹን የናይጄሪያ መንግሥት ደምስሶበትም ቡድነ አለመጥፋቱንና ለረዥም ጊዜ ሳይጠፋ መዝለቁን ጠቁመዋል፡፡ በናይጄሪያ ብዙ መንግሥታት ቢፈራረቁም ቦኮ ሀራም ግን ተዳክሞም ቢሆን መንቀሳቀስ መቀጠሉን አስታውሰዋል፡፡ በኢትዮጵያ ያሉ የሰላምና የግጭት ምንጭ ናቸው ያሏቸውን ሸማቂ ቡድኖችን በየጊዜው የማዳከምና እንዲጠፉ የማድረግ ሥራ መሥራት ያስፈልጋል የሚል ሐሳብ ያነሱት ዓብይ (ዶ/ር)፣ ለዚህ አስፈላጊው ሥራ እየተሠራ መሆኑንም አስረድተዋል፡፡
ሕግ ማበጀት፣ የበለጠ ውይይትና መግባባት መፍጠር፣ ጠንካራ የፀጥታ ተቋማትን መፍጠር የሚሉ የመፍትሔ አማራጮችን ያቀረቡት ዓብይ (ዶ/ር)፣ ‹‹በአንፃራዊ መልኩ የኢትዮጵያ ሰላም በቅርብ ዓመታት ተሸሽሏል›› ሲሉም ገልጸዋል፡፡
በሌላ በኩል በፕሪቶሪያ ስምምነት መፈረም ያኮረፉ ኃይሎች ተሰባስበው መንግሥትን ለመውጋት እየተባበሩ መሆኑን፣ የመጥረቢያ ስለት፣ የመጥረቢያ እጀታ፣ የመጥረቢያ ሰንዛሪ እጅ ሆነው የተሰለፉ ሕወሓት፣ ሻዕቢያና ከበስተጀርባቸው ያሉ ኃይሎች መኖራቸውን ተናግረዋል፡፡ ‹‹እንኳን ሻዕቢያ፣ ወያኔና ሱዳን ቀርቶ ሌላም ቢጨመር የኢትዮጵያ ሉዓላዊነት ጥያቄ ውስጥ አይገባም፤›› የሚል ንግግር ያሰሙት ዓብይ (ዶ/ር)፣ ጦርነት ለመቀስቀስ እየተዘጋጀ ነው ያሉት፣ ‹‹ሀብት እየተመኘ ለመዋጋት መዘጋጀት ይቃረናሉ›› በማለት አዲስ አበባ ሕንፃ ገንብተው የሰላም መደፍረስ ምንጭ እንሁን የሚሉት ላይ ዕርምጃ እንደሚወሰድ አሳስበዋል፡፡ በማሳረጊያቸውም የኢትዮጵያ ሰላምና መረጋጋት ዕጦት ምንጭ ከየት እንደሆነ መንግሥታቸው እንደሚያውቅና ለዚያም መክሸፍ እየተዘጋጀ መሆኑን አስምረውበታል፡፡
ስለማክሰኞው የጠቅላይ ሚኒስትሩ የፓርላማ ውሎ በተመለከተ በዋናነት አንገብጋቢ አጀንዳ በሚባለው በሰላም ጉዳይ ላይ ከምክር ቤቱ አባላት የቀረቡ ጥያቄዎችንና የተሰጣቸው ምላሽን በሚመለከት አስተያየት እንዲሰጡ ሪፖርተር ያነጋገራቸው የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ሐሳባቸውን ሰጥተዋል፡፡
የመጀመሪያዋ አስተያየት ሰጪ አንጋፋዋ ፖለቲከኛና የሶሻል ዴሞክራቲክ ፓርቲ አመራር ራሔል ባፌ (ዶ/ር)፣ ሲሆኑ ከቤቱ የቀረቡ ጥያቄዎች ጥሩ እንደነበሩ ጠቅሰው፣ ነገር ግን በቂ የሚባል ጥያቄዎቹ ምላሽ አለማግኘታቸውን ጠቁመዋል፡፡ ‹‹በእኔ ግምት ለቀረቡ ጥያቄዎች ምላሽ አልተሰጠም፡፡ ስለሰላም ለተነሱ ጥያቄዎች የተሰጠው ምላሽም ቢሆን ችግሮችን በመደራደርና በውይይት የመፍታት መፍትሔን ሳይሆን፣ ማንም ተባብሮ ቢመጣ አቅም አለን በዚያ እንፈታዋለን የሚል ሐሳብ ነው ጎልቶ የተስተጋባበት፡፡ ሥር ለሰደዱ የሰላም ችግሮች መፍትሔ ቢጠየቅም፣ መፍትሔ ከመስጠት ይልቅ ‹‹ቢሆን ጥሩ ነው፣ ወይም ቢፈታ መልካም ነው የሚሉ ይዘት ያላቸው ምላሾችን ነው ያደመጥነው፡፡
የብሔራዊ ምክክሩ አቃፊ እንዲሆን ስለማድረግም ሆነ ታጣቂዎችን አሳታፊ ማድረጉን በሚመለከት አልሰማሁም፡፡ እኔ የጠበቅሁት በዚህ ደረጃ መልስ ይሰጣል ብዬ ስለነበር አዝኛለሁ፡፡ የውጭ አደራዳሪዎችንም አሳትፈንም ሆነ ማንኛውንም መንገድ ሄደን ለአገሪቱ መሠረታዊ የሰላም ችግር መፍትሔ እናፈላልጋለን የሚል ሐሳብ ይንፀባረቃል ብዬ ገምቼም ነበር፤›› በማለት የፓርላማውን ውሎ በጠበቁት ልክ እንዳላገኙት ፖለቲከኛዋ ተናግረዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በምላሽና ማብራሪያቸው ማሳረጊያ ላይ የታሰሩ ሰዎችን የመፍታት ሐሳብ፣ ወደ ውጭ የተሰደዱ ሰዎችን ለውይይት የመጋበዝ፣ የታጠቁም ሆነ ሌሎች ያልተካተቱ አካላትን የማቅረብ ፍላጎት መንግሥታቸው ያለው መሆኑን በጥቂቱ ጠቆም ማድረጋቸውን በማስታወስ፣ ይህ የመንግሥትን የሰላም መፍጠር ሰፊ ፍላጎት አያመለክትም ወይ? የሚል ጥያቄ የቀረበላቸው ራሔል (ዶ/ር)፣ ይህን አለመታዘባቸውን ነው የተናገሩት፡፡
‹‹በፓርላማው የነበረውን ድባብ ካየነው እንዲሁም የተጠየቁ ጥያቄዎችና የተሰጡ ምላሾችን አንድምታ ከመዘንነው ይህን አናገኝም፡፡ በቋንቋና በንግግር እንደምላሽ ከቀረበው ተነስተን ብቻ ሳይሆን ከአካላዊ እንቅስቃሴ (ጀስቸር) ጀምሮ አጠቃላይ ውሎውን መታዘብ አለብን፡፡ ንግግር በቋንቋ ወይም ቃላት ብቻ ሳይሆን በስሜት አገላለጽና በአካል እንቅስቃሴያችንም ነው የሚመዘነው፡፡ እኔ እንዳስተዋልኩት በንግግር ብቻ ሳይሆን በጀስቸር (በሰውነት እንቅስቃሴ) ጭምር ለሰላም ዘላቂ መፍትሔ የመፈለግ ፍላጎትን ከስብሰባው አልታዘብኩም፡፡ እንደዚያ ዓይነት መፍትሔ የመፈለግ ነገር አላነበብኩም፡፡ ብሔራዊ ምክክር ውስጥ የሚነሱ ጉዳዮችን ጭምር ሲያነሱ የነበሩ የታሰሩ ሰዎችና የተገለሉ ሰዎች አሉ፡፡ ሁሉም ኃይሎች ወደ ጠረጴዛ ዙሪያ ሐሳባቸውን እንዲያመጡ ዕድሉ ቢከፈት ጥሩ ነው ብዬ አስባለሁ፡፡
አሁን ላይ የአገርን አሳሳቢ የሰላም ችግሮች ለመፍታት እየተነሳን ነው፡፡ ስለዚህ ከተደበቅንበት ሳጥኖች ሁላችንም መውጣት አለብን፡፡ እባብ ጆሮ የለውም አይሰማም ይባላል፡፡ ልክ እንደ እባብ ሳይደማመጡ ሌላውን ለማጥፋት ከመንቀሳቀስ ሁላችንም ወጥተን መደማመጥ መቻል አለብን፡፡ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት የሚያነሷቸው ጥያቄዎች ከገዥውም ሆነ ከተቃዋሚ ፓርቲ ወገን ቢመጡ እዚያ የተገኙት ሕዝብን ወክለው እስከሆነ ድረስ ከእከሌ ፓርቲ የመጣችሁ ሳይባል ጥያቄያቸውን በወጉ አድምጦ በአግባቡ መልስ መስጠት አስፈላጊ ነው፡፡ አሁን የብሔራዊ ምክክር ወቅት ነው፡፡ ዛሬ ወደ አዲስ አበባ ተወያዮቹ እየገቡ ነው፡፡ ስለዚህ ይህን የበለጠ የሚያግዝ ምላሽ በፓርላማው ጠብቄ ነበር፤›› በማለት ለተነሱ ጥያቄዎች፣ አጥጋቢ መልስ የተሰጠበትን ሁኔታ አለማየታቸውን አብራርተዋል፡፡
ራሔል (ዶ/ር) ሐሳባቸውን ሲቀጥሉ፣ አምባሳደሮችና ዲፕሎማቶች እንዲሁም ሌሎች ታዛቢዎችን ጨምሮ በተቀመጡበት ቦታ ሆነው ፓርላማውን ሲከታተሉ መዋላቸውን ጠቁመዋል፡፡ ታዛቢዎች በሚቀመጡበት ወንበር የነበሩ ሁሉ በንቃት ሒደቱን ሲከታተሉ መመልከታቸውንም ጠቅሰዋል፡፡ ‹‹ዛሬ የመዝጊያ ስብሰባ ፓርላማው እንደማድረጉ መጠን በተስፋ ነበር ብዙዎቻችን የሄድነው፡፡ ስላሳለፍናቸው ብቻ ሳይሆን ለሚቀጥሉት አምስት ዓመታት አገሪቱ የምትሄድበትን መንገድ የሚወስን በጎ ነገር ከዛሬው ፓርላማ ጠብቄ ነበር የሄድኩት፡፡ ይሁን እንጂ እንደጠበቁት ሆኖ አላገኘሁትም፡፡ መጀመሪያ ለችግሮቻችን ዕውቅና መስጠት አለብን፡፡
በእጃችን ላለው አገራዊ ምክክር አካታች ሆኖ እንዲካሄድ ፈቃድ ማሳየት አለብን፡፡ የሚካሄደውም ውይይት ቢሆን ሀቀኛና ከልብ መሆን አለበት፤›› ሲሉ ተናግረዋል፡፡ ራሔል (ዶ/ር) በፓርላማው የቀረበውን ለ85 በመቶ ወንበሮች ብቻ በመወዳደር ቀሪውን 15 በመቶ ለተፎካካሪ ፓርቲዎች የመልቀቅ ዕርምጃን አጥብቀው እንደሚቃወሙ አያይዘው ጠቅሰዋል፡፡ ጉዳዩ የፖለቲካ ምኅዳር መጥበብ ካልሆነም የምርጫ ሥርዓቱ አለመቃናትና የተፎካካሪ ፓርቲዎችን አቅም ማጣት ከመጠቆም ባለፈ ለአገሪቱ ሰላምም ሆነ ፖለቲካ መረጋጋት እንደማይጠቅም ተናግረዋል፡፡ ይህን መሰሉ ዕርምጃ የሕዝቡን አማራጭ የማግኘትና የመምረጥ መብት የሚነፍግ ከመሆኑ በላይ፣ የዴሞክራሲ ተሳትፎና ውክልና የማግኘት ጉዳይን የዕርዳታና ችሮታ ጉዳይ ወደ መሆን እንደሚያወርደው ነው የተናገሩት፡፡
ሌላኛው አስተያየት ሰጪና ፖለቲከኛ አቶ ደስታ ዲንቃም የትናንቱን የፓርላማ ውሎ አጥጋቢ መልስ ያልተሰጠበት ስብሰባ ሆኖ እንዳገኙት ነው የተናገሩት፡፡ በፓርላማው የብልፅግና አባላት በአገሪቱ መሻሻልና ለውጥ እንዳለ መሆኑን ሲናገሩ መዋላቸውን የጠቆሙት አቶ ደስታ፣ ነገር ግን በእሳቸው እምነት የአገሪቱ ተጨባጭ ችግሮች አለመፈታታቸውን ነው የገለጹት፡፡ ‹‹የአገሪቱ የሰላም ችግሮች በስፋትም በጥልቀትም ጨምረዋል እንጂ የተሻሻሉ ሁኔታዎችን አናይም፡፡ ከዚህ ቀደም ትግራይ፣ አማራና ኦሮሚያ ብቻ ነበሩ በሰላምና በግጭት ስማቸው ሲጠራ የነበረው፡፡ አሁን ግን ቤንሻንጉልና ጋምቤላን የመሳሰሉ ክልሎችም በዚህ ችግር ስማቸው እየተጠራ ነው፡፡ በትግራይ ጦርነት ቢቆምም ነገር ግን አሁን ያለው ውጥረት ከፍተኛ ሥጋት ፈጥሯል፡፡ ጊዜያዊ አስተዳደሩ ፈርሶና አመራሮቹ ተነስተው ከጦርነቱ በፊት ወደነበረው ሁኔታ ክልሉ የተመለሰ ሲሆን፣ አሁን የጦርነት ነጋሪት እየተጎሰመ ነው፡፡ በአማራ ክልል በአሁኑ ወቅት መከላከያ መጠነ ሰፊ ዘመቻ በፋኖ ኃይሎች ላይ እያካሄደ መሆኑንና የክልሉ ግጭት ተጠናክሮ መቀጠሉን እየታዘብን ነው፡፡ ከፋኖ ጋር የተያያዘው ግጭት ወደ ኦሮሚያ ወለጋም ተዛምቶ እናያለን፡፡ በኦሮሚያ በሌሎች አካባቢዎች ከኦላ ጋር የሚደረገው ግጭትም አልቆመም፡፡ በቤኒሻንጉል አዲስ ታጣቂ ኃይሎች መፈጠራቸውን እየሰማን ሲሆን፣ ከዚያ አልፎ በጋምቤላ የሚንቀሳቀሱ ታጣቂ ኃይሎች ጭምር ከሕወሓትና ከሻዕቢያ ጋር ግንኙነት ፈጠሩ የሚል ነገር እንሰማለን፡፡ ኤርትራና ሱዳን ከመሳሰሉ ጎረቤት አገሮች ጋር የነበረው ውጥረትም ጨምሯል፡፡ መሬት ላይ በተጨባጭ እነዚህን የመሳሰሉ ችግሮች እየታዘብን የኢትዮጵያ ሰላም ሁኔታ ተሻሽሏል የሚል ነገር ማንሳት ለብዙዎች የሚዋጥ አይሆንም፤›› በማለት የሰላም ችግሮችንና መፍትሔዎቻቸውን በተመለከተ ተጨባጩን የአገሪቱን ሁኔታ የሚያሳይ ውይይት ከፓርላማው አለማግኘታቸውን አብራርተዋል፡፡
አቶ ደስታ እንደተናገሩት፣ ጥያቄዎች ሲቀርቡም ሆነ መልስና ማብራሪያዎች ሲሰጡ በአገሪቱ ከሚታዩ ነባራዊ ሀቆች ጋር የሚጣጣሙ ሆነው በፓርላማው ውሎ ላይ እንዳልተመለከቱ ገልጸዋል፡፡ ‹‹ለምሳሌ ምርጫው በሰላምና በስኬት መጠናቀቁን በሰፊው ተነግሯል፡፡ ነገር ግን በምርጫው ቀን በኦሮሚያ ክልል ብቻ በ30 ቦታዎች መለስተኛና ከባድ የሚባሉ ግጭቶች በተለያዩ ቦታዎች መካሄዳቸውን ራሱ መንግሥት ጭምር አረጋግጧል፡፡
ምርጫ ይካሄድባቸዋል በተባሉ በርካታ የምርጫ ጣቢያዎች ውስጥ ጥቂት በማይባሉት ውስጥ ምርጫውን በአግባቡ ማካሄድ አለመቻሉንም እኔ በቅርበት በምከታተለው በኦሮሚያ ክልል እንደነበረ አረጋግጫለሁ፡፡ ከእነዚህ ሁሉ ተጨባጭ እውነታዎች ተነስተን ምርጫው ሰላማዊና ስኬታማ ነበር ማለት ያስቸግራል፤›› የሚሉት አቶ ደስታ በፓርላማው ውሎ ላይ ስለ ሰላም ጉዳይ የቀረቡ ሐሳቦች፣ በአገሪቱ ከሚታዩ ተጨባጭ ሀቆች ጋር የሚጋጩ ሆነው እንዳገኙዋቸው ነው ያብራሩት፡፡