- የመገንጠል መብት ከሕገ መንግሥቱ ሊሰረዝ ይገባል ተብሏል
የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ (ኢዜማ) የአገሪቷ ከፍተኛ ባለሥልጣን ፕሬዚዳንት እንዲሆን በሚያስችልና ፕሬዚዳንቱ በቀጥታ በአብላጫ ድምፅ (50+1) የሚመረጥበት ፕሬዚዳንታዊ የፖለቲካ ሥርዓት መተካት እንዳለበት፣ ከአብላጫ ድምፅ በተጨማሪ ፕሬዚዳንቱ በአብዛኛው ክልሎችም ተመራጭ የሚሆንበት ሥርዓትም መዘርጋት አለበት የሚል አጀንዳ ለአገራዊ ምክክር ኮሚሽን አቀረበ፡፡
በሕገ መንግሥቱ በአንቀጽ 45 የተዘረጋው የፓርላሜንታሪ ሥርዓት መሪው በቀጥታ የማይመረጥበት፣ ቋንቋን መሠረት ባደረገ መልኩ የተመረጡ ተወካዮች ተሰብስበው የሚመርጡት መሪ በመሆኑ፣ የመሪው ወይም የጠቅላይ ሚኒስትሩ ቅቡልነት ጥያቄ ውስጥ ሲገባና የአንድ ብሔር ተወካይ እንጂ የአገር መሪ እንዳልሆነ ሲቆጠር በመስተዋሉ የፖለቲካ ሥርዓቱ ሊቀየር ይገባል ብሏል፡፡
ፓርቲው በአገር ህልውናና ቀጣይነት ላይ የተደቀነውን አደጋ የማስወገድና አገርን በጠንካራ መሠረት ላይ የማቆምንም ጉዳይ የምክክር አጀንዳ አድርጎ አቅርቧል፡፡
ኢዜማ ኅዳር 26 ቀን 2018 ዓ.ም. በ73 ገጽ አገራዊ የምክክር አጀንዳዎች መነሻ ሰነድ ለአገራዊ የምክክር ኮሚሽን አስረክቧል።
ፓርቲው አጀንዳዎችን በአምስት ርዕሶች ማለትም፣ የአገር ህልውናና ቀጣይነት አደጋ፣ የዜጎች ሰብዓዊና ደኅንነት መከበር አለመቻል፣ ከድህነትና ከኋላቀርነት መላቀቅ አለመቻል፣ የጋራ ማንነት፣ ጥቅም ፍላጎትና ስሜት አለመዳበርና የሕገ መንግሥት ማሻሻያዎች በሚል ማቅረቡን ሪፖርተር ካገኘው ሰነድ መመልከት ችሏል።
በአገር ህልውናና ቀጣይነት ላይ የተደቀነውን አደጋ የማስወገድና አገርን በጠንካራ መሠረት ላይ የማቆም ጉዳይ፣ አገራዊ ምክክሩ ከሌሎች ማናቸውም ጉዳዮች በላይ ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባ መሠረታዊ ጉዳይ ነው። ኢዜማ ለአገር ህልውና ከምንም ነገር በላይ ቅድሚያ የሚሰጠው፣ የአገር ህልውና ችግር ውስጥ በሚወድቅበት ጊዜ የሚፈጠረው እጅግ አስከፊ ሁኔታ፣ ማንኛውንም የማኅበረሰብ ክፍል፣ ቡድንና ግለሰብ፣ ለህልውና አደጋ መጋለጡ የማይቀር በመሆኑ እንደሆነ በሰነዱ ላይ አሥፍሯል።
በአግባቡ ባለመስተናገዳቸው የበርካታ ቅራኔና ግጭት መፈልፈያ በመሆን፣ የአገርን ህልውናና ቀጣይነት አደጋ ውስጥ በመጣል፣ የማናቸውም ባለድርሻዎች ደኅንነት ለከፍተኛ አደጋ ያጋለጡትን፣ ከዘርና ከሃይማኖት ብዝኃነት የሚነሱ የፍትሐዊ ጥያቄዎችን፣ ለአገር ህልውናና ቀጣይነት አደጋ በማይሆኑበት ሁኔታ ማስተናገድ የሚችል አገራዊ የፖለቲካ ሥርዓት፣ መሠረት የሚጣልበትንና ተጠናክሮ የሚቀጥልበትን ሁኔታ ማመቻቸት በሚችሉ የመፍትሔ ሐሳቦች ላይ የጋራ ስምምነት ላይ መድረስ እንደሚገባ በሰነዱ ላይ ተገልጿል። በአገራዊ ምክክሩ ላይ መነሳት ያለበት ሌላው ጉዳይ የዜጎች ሰብዓዊና ዜግነታዊ ደኅንነት ማስጠበቅ ያለመቻሉ ጉዳይ መሆኑ በሰነዱ ላይ ሠፍሯል።
From The Reporter Magazine
በመሆኑም በዜጎች ላይ የሚደርሰውን ሰብዓዊ ጥቃት ለማስቆምና አገርን ከህልውና አደጋ ለመታደግ፣ ብሎም ሰላማዊና የተረጋጋ አገራዊ ሁኔታ እንዲኖር፣ የፌዴራል መንግሥት የደኅንነት አካላት ሰብዓዊና ዜጋዊ መብቶችን አለማስከበርና አለማክበር፣ ከፌዴራል መንግሥት በታች ያሉት የክልል የደኅንነት አካላት ሰብዓዊና ዜጋዊ መብቶችን አለማክበር፣ አለማስከበር፣ የፌዴራልና ከፌዴራል በታች ያሉ የሕግ አካላት ሰብዓዊና ዜጋዊ መብቶችን አለማስከበር፣ የሰብዓዊ መብት ተከራካሪ አካላት፣ መገናኛ ብዙኃንና የሲቪል ማኅበራት ሰብዓዊና ዜጋዊ መብቶችን ለማስከበር ያላቸው ዝግጁነት ዝቅተኛ መሆን፣ ጨርሶ አለመኖር፣ በአንዳንድ ሁኔታ ለመብቶቹ ጥሰት የመተባበር ችግር፣ የሕግ ሰውነት የሌላቸው ኢመደበኛ የሆኑና የዘውግ መሠረት ያላቸው ነፍጥ ያነገቡ ፖለቲካ ነክ ወይም የውንብድና አደረጃጀቶች በብዛት መኖርና ይህንን ማስቆም አለመቻል ዓይነት ችግሮች፣ በአገራዊ ምክክር መሠረታዊ መፍትሔ ሊገኝላቸው እንደሚገባ ኢዜማ በሰነዱ አካቷል።
‹‹ከመቼውም ዘመን ይልቅ ድህነትና ኋላቀርነት በአሁኑ ወቅት እንዳለንበት ዘመን የበርካታ አገራዊ አደጋዎች መፈልፈያና ተጠናክሮ መቀጠያ ምክንያት ሆነው አያውቁም፤›› ያለው ፓርቲው፣ በዚህም ሊደረግ በታሰበው አገራዊ ምክክር፣ ድህነትና ኋላቀርነት እንደ አንድ ጉዳይ መቅረብ አለበት ብሏል።
በመሆኑም ከሥርዓት አገርን ከድህነትና ኋላቀርነት የማላቀቁን ሒደት በማስጀመር፣ በተጓዳኝ የእኩልነትና የፍትሕ ጥያቄዎችን በየደረጃው ለመመለስ መደረግ ያለበትን ጥረት፣ የዘር ማንነትን መሠረታዊ መመዘኛ ያደረገው የኢሕአዴግ የአገዛዝ ሥርዓት እጅግ አስቸጋሪ እንዲሆን በማድረጉ፣ ድህነቱና ኋላቀርነቱ ከቁጥጥር ውጪ ወጥቶ፣ ለአገር አለመረጋጋት ብሎም መበተን ምክንያት ከመሆኑ በፊት፣ አገራዊ ምክክሩ ሊያያቸው ከሚገቡ ጉዳዮች መካከል አንዱ መሠረታዊ ጉዳይ ሊሆን እንደሚገባ በሰነዱ አመላክቷል።
From The Reporter Magazine
በኢትዮጵያ ከፍተኛውን የሉዓላዊነት ሥልጣን ለዘር ማንነት ቡድኖች የሰጠው ሕገ መንግሥት፣ በዘርና በሃይማኖት የማንነት ቡድኖች መሀል ግጭት የሚቀሰቅሱ ትርክቶች፣ የጋራ ፍላጎትን፣ ጥቅምንና የጋራ ማንነትን ሊያጎለብቱ የሚችሉ ምልከታዎች ተግባራዊ አለመደረግ፣ የጋራ ፍላጎትና ጥቅም፣ የጋራ ማንነት እንዳይኖር እያደረጉ ያሉ ሁኔታዎች መሆናቸውን የገለጸው ኢዜማ፣ የአገርን መሠረት የዘር ቡድኖች ያደረገው፣ በፈለጉ ጊዜ በዘር የተሰባሰቡ ቡድኖች የራሳቸውን ክልልና አገር መመሥረት ይችላሉ የሚል መብት፣ በተግባር ግን የአገር ህልውና ብቻ ሳይሆን በዘር የተሰባሰቡትን ቡድኖች ህልውና ለከፍተኛ አደጋ ያጋለጠውን ሁኔታ፣ የሕግ ድጋፍ የሚሰጠው ሕገ መንግሥት፣ አገራዊ ምክክሩ ሊመክርባቸውና መፍትሔ ሊሰጥባቸው ከሚገቡ ጊዜ የማይሰጡ ችግሮች መሀል አንዱ መሆኑን አጽንኦት ሰጥቷል።
ኢዜማ እንደገለጸው፣ ሕገ መንግሥቱ በአንድ በኩል መሠረታዊ ማስተካከያ የሚያስፈልጋቸውና ለአገር ስብራት ምክንያት የሆኑ ድንጋጌዎችን የያዘ፣ በሌላ በኩል ደግሞ እንዳሉ ጥቅም ላይ ሊውሉ የሚችሉ አንቀጾችም ያሉበት ሰነድ ነው። ስለሆነም በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ ካለችበት ሁኔታ፣ ከዓለም አቀፍ ሁኔታዎች፣ እንዲሁም እስካሁን ከሕገ መንግሥቱ ካገኘነው ተሞክሮ አንፃር ሊሻሻልና ዘመኑን በዋጀ መልኩ መሠረታዊ የሆነ ዕርማት ሊደረግለት እንደሚገባ ፓርቲው በሰነዱ ገልጿል።
በዚህም የሕገ መንግሥቱ መግቢያ በሚከፋፍሉና በሚያለያዩ ጉዳዮች ላይ ከማተኮርና ከማጠንጠን ይልቅ፣ አንድ በሚያደርጉ እንደ አንድ የፖለቲካ ማኅበረሰብ የጋራ በሆነው መሠረታዊ የዜግነት ጉዳይ ላይ ሊያተኩር እንደሚገባ አሳስቧል።
በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 39 መሠረት ማንኛውም ብሔር ብሔረሰብና ሕዝብ እስከ መገንጠል የሚደርስ መብት እንዳለው ተደንግጓል። ይህ አንቀጽ ኢትዮጵያ አንድ አገር ሆና የመቀጠል መብቷን የሚያመነምንና በማንኛውም ሰዓት በጥቂቶች ፍላጎት ላይ በመመሥረት ብቻ አገርን የሚያፈርስ ከመሆኑም በላይ፣ በሕዝብ መካከል መተማመንን የሚሸረሽር፣ የጋራ ፍላጎትንና ጥቅምን ብሎም የጋራ ማንነትን፣ የሚያቀጭጭ አንቀጽ በመሆኑ፣ ሙሉ በሙሉ ሊሰረዝ እንደሚገባ ምክረ ሐሳብ አቅርቧል።
ሕገ መንግሥቱ የተሻለ የጋራ መግባቢያ ሰነድ እንዲሆንና ቅቡልነት እንዲኖረው፣ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 62/1/ የተጠቀሰው ሕገ መንግሥቱን የመተርጎም ሥልጣን ከፌዴሬሽን ምክር ቤት ወጥቶ ለሕገ መንግሥት ተርጓሚ ፍርድ ቤት እንዲሰጥ መደረግ እንደሚኖርበት፣ የሕገ መንግሥት ተርጓሚ ፍርድ ቤት ራሱን ችሎ እንዲቋቋም ወይም በልዩ ችሎት ሊተገበር ይገባል ብሏል፡፡ አንቀፅ 3 – ሰንደቅ ዓላማ፣ አንቀጽ 8 ሉዓላዊነት፣ አንቀጽ 40 የመሬት ባለቤትነት፣ አንቀጽ 46 እና 47 የክልል አደረጃጀት፣ አንቀጽ 52 የክልሎች ሥልጣን፣ አንቀጽ 104 እና 105 ሕገ መንግሥቱን ማሻሻል ሌሎች እንዲሻሻሉ በሰነዱ የተካተቱ አንቀጾች ናቸው።
በርክክብ ሥነ ሥርዓቱ ላይ ንግግር ያደረጉት የኢትዮጵያ አገራዊ ምክክር ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር መስፍን አርዓያ (ፕሮፌሰር)፣ ፓርቲው ያቀረባቸውን አጀንዳዎች ለአገራዊ ጉባዔው በአግባቡ ጥቅም ላይ እንደሚውሉ ገልጸዋል፡፡
የኢዜማ መሪ ብርሃኑ ነጋ (ፕሮፌሰር) በበኩላቸው፣ አገራዊ ምክክሩ የኢትዮጵያን መሠረታዊ ችግሮች ለመፍታት ቁልፍ ጉዳይ መሆኑን ጠቅሰው፣ ኢዜማ ኮሚሽኑ የሚያከናውናቸውን ተግባራት ለማገዝ ቁርጠኛ ነው ማለታቸውን የኮሚሽኑ መረጃ ያሳያል፡፡