መሰንበቻውን በኦሮሚያ ክልል በምሥራቅ አርሲ ዞን በኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ምዕመናን ላይ በተፈጸመው ግድያ፣ ማፈናቀል፣ የንብረት ውድመትና የቤተ ክርስቲያን መቃጠል ምክንያት በብዙዎች ላይ ከፍተኛ ቁጣ መቀስቀሱ ይታወቃል፡፡ ለሟች ወገኖች ሐዘንን ከመግለጽ ጀምሮ ከጥቃቱ ተርፈው በየተገኘበት ቦታ ለተጠለሉ ወገኖች ድጋፍ ማድረግ እንዳለ ሆኖ፣ በቀጣይ ምን መደረግ እንዳለበት በስክነት ተነጋግሮ የጋራ አቋም መያዝ የግድ መሆን አለበት፡፡ ከማዘን፣ ከመቆጨት፣ ጎራ ለይቶ ከመወነጃጀልና ለነገ የበለጠ ጥፋት ከሚያመቻቹ አሉታዊ ድርጊቶች በመታቀብ ተመሳሳይ ጥፋቶች እንዳይከሰቱ በአንክሮ መነጋገር ተገቢ ነው፡፡ ይህ ዓይነቱ ነውረኛ ጥቃት ለመጀመሪያ ጊዜ የተፈጸመ ሳይሆን፣ ከዚህ ቀደም በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች በዘግናኝ ጥቃቶች በርካታ ወገኖች ለሕልፈት መዳረጋቸው ይታወሳል፡፡ እንዲህ ዓይነት ድርጊቶችን ተባብሮ ለማስቆም ካልተቻለ፣ ነገ ተነገ ወዲያ የባሱ ጥፋቶች በተከታታይ እንደማይፈጸሙ አስተማማኝ ነገር የለም፡፡
እንደሚታወቀው በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ያለው የፀጥታ ሁኔታ በብሔርም ሆነ በሃይማኖት ሰበብ ሊነሱ ለሚችሉ ጥቃቶች የተመቻቸ ነው፡፡ የፀጥታ ሁኔታው አስተማማኝ ባልሆነባቸው አካባቢዎች በቂምና በበቀል ሊከሰቱ የሚችሉ ተጨማሪ ጥፋቶችን ለማስቆም፣ ኢትዮጵያውያን በመተባበር መፍትሔ ማዋጣት ይጠበቅባቸዋል፡፡ መንግሥት ሕግ እያስከበረ የሕዝቡን ሰላምና ደኅንነት የማስከበር ኃላፊነት እንዳለበት የታወቀ ቢሆንም፣ በመኖሪያ አካባቢዎችም ሆነ በሥራ ቦታዎች ለዜጎች ሰላምና ደኅንነት ጠንቅ የሆኑ ሐሳቦችንም ሆነ ድርጊቶችን ለማስቆም የጋራ አቋም ሊኖር ይገባል፡፡ ብሔርና እምነትን እየታከኩ ለሰላምና መረጋጋት መጥፋት ጥርጊያ የሚያመቻቹ ግለሰቦችንም ሆነ ቡድኖችን በቃችሁ መባል አለበት፡፡ ልዩነቶች ወይም አለመግባባቶች ሲፈጠሩ በንግግር እንጂ በኃይል እንዳይፈቱ ማኅበረሰቡ ማገዝ ይጠበቅበታል፡፡ ለአገር ልማትና ዕድገት ፋይዳ የሌላቸው ትርክቶችን በመዝጋት ለጥፋት የሚንቀሳቀሱ ወገኖችን ማስቆም ሊታለፍ የማይገባ ተግባር ይሁን፡፡
በመንግሥት በኩል ዋነኛ ኃላፊነቱ የሚያስተዳድረውን ሕዝብ ሰላምና ደኅንነት ማስከበር እንደሆነ የሚታወቅ ነው፡፡ መንግሥት ሁሉንም አስተዳደራዊ መዋቅሮቹንና የፀጥታ አስከባሪ ተቋማቱን አቀናጅቶ ከሕዝብ ጋር ከተባበረ፣ በኢትዮጵያ ምድር ማኅበረሰቦች እየተለዩ ጥቃት አይደርስባቸውም፡፡ በአስተዳደርም ሆነ በፀጥታ መዋቅሮች ውስጥ ችግሮች ሲያጋጥሙ እየፈታ በጥናት መንቀሳቀስ ከቻለ፣ እንኳንስ በዕልቂትና በውድመት የታጀቡ ጥቃቶች ተራ ወንጀሎች ሳይቀሩ በከፊልም ሆነ ሙሉ ለሙሉ የሚወገዱበት ዕድል አለ፡፡ በፌዴራልም ሆነ በክልል ደረጃ መንግሥታዊ ቁጥጥሩ ሲጠብቅና ሕግ የማስከበር ብቃቱ ሲጎለብት በየቦታው የሚፈጸሙ ጥቃቶች፣ ዕገታዎችና ዘረፋዎች በአጭር ጊዜ ውስጥ ይመክናሉ፡፡ መንግሥት ሕዝቡ ውስጥ መሽገው በብሔርና በሃይማኖት ተደራጅተው አገርን ጤና የሚነሱ ኃይሎችን ማንበርከክ ካቀተው ግን፣ የአገር ህልውና ጉዳይ አደጋ ውስጥ እንደሚወድቅ ነጋሪ አያስፈልግም፡፡ ስለዚህም ከሕዝብ ጋር ተባብሮ በአገር ላይ ያንዣበበውን አደጋ ያስወግድ፡፡
በተለይ በክልሎች ውስጥ ሰላምን ለማስከበር አለመቻል የዜጎችን ከቦታ ወደ ቦታ መንቀሳቀስ መገታት ብቻ ሳይሆን፣ በሚኖሩበትና በሚሠሩበት ጭምር ግድያና መፈናቀል እየገጠማቸው ነው፡፡ ይህንን ችግር በዘላቂነት ለመቅረፍ የሚያስችሉ ሕጋዊ ማዕቀፎች አስፈላጊ ናቸው፡፡ አንደኛውና ዋነኛው ሕገ መንግሥታዊ ማሻሻያ ሲሆን፣ በዚህ መሠረት አሁን ያለውን አገር አፍራሽ እንቅስቃሴ በሙሉ ለማስወገድ የአዕምሮ ዝግጅት ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ክልሎች አሁን በደረሱበት ደረጃ ላይ ሆነው ውስጣዊ ሰላማቸውን ማስጠበቅ ካልቻሉ፣ ከዜጎች ሰላምና ደኅንነት የሚበልጥ አንዳችም ጉዳይ ስለሌለ የሕገ መንግሥት ማሻሻያው የግድ መሆን አለበት፡፡ በራሱ ኃይል ዜጎችን ከጥቃት መከላከል የማይችል ክልል፣ የፌዴራል ኃይልን ዕገዛ ለማግኘት ፈቃጅና ከልካይ ሆኖ ሊቀጥል አይችልም፡፡ ይህ ጉዳይ በአገሪቱ የሕግ ምሁራንና ልሂቃን አማካይነት ጠንከር ያለ ውይይት ቢደረግበት መልካም ነው፡፡
በመንግሥትና በሕዝብ መካከል እንደ ድልድይ ሆነው የሚያገለግሉ ተቋማት ያስፈልጋሉ፡፡ እነዚህም የሙያ ማኅበራት፣ የሲቪክ ማኅበራት፣ የእምነት ተቋማት፣ የዴሞክራሲ ተቋማትና የመሳሰሉት ናቸው፡፡ ዜጎች በተለያዩ ማኅበራት ሲደራጁ ጥቅሞቻቸውን ከማስከበር ጎን ለጎን፣ ግዴታቸውን አውቀው የሚፈለግባቸውን አገራዊ ግዴታ ለመወጣት ይችላሉ፡፡ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች እንዲከበሩ፣ የሕግ የበላይነት እንዲኖር፣ ዜጎች በፍትሐዊነት አገልግሎቶችን እንዲያገኙና እንዲዳኙ የማኅበራቱና የተቋማቱ ሚና ትልቅ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ከመንግሥት መዋቅር ጀምሮ በሁሉም ሥፍራ ተቌማት ሲያብቡና ሲጠናከሩ፣ ፍላጎትን በኃይል ከማስፈጸም ይልቅ በጠረጴዛ ዙሪያ መነጋገር ባህል ይሆናል፡፡ ማንም እየተነሳ በጉልበት እንዳሻው ለመሆን አይደፍርም፣ በፍርኃት የሚሸበቡ ዜጎችም አይኖሩም፡፡ በእንዲህ ዓይነቱ ዓውድ ውስጥ ሕገወጥነትና ሥርዓተ አልበኝነት ቦታ አይኖራቸውም፡፡ ከዚህ ውጪ ያለው ግን ጽንፈኞች እንደፈለጉ የሚገድሉበትና የሚያፈናቅሉበት ምቹ ሁኔታ እንደሆነ ይታወቅ፡፡
አሁንም እዚህ ላይ ሳናነሳ ማለፍ የማንፈልገው ነጥብ የግልጽነት፣ የተጠያቂነትና የኃላፊነት መርህ ነው፡፡ ግልጽነትና ተጠያቂነት ከሌለ በተናጠልም ሆነ በቡድን የሚፈጸሙ ወንጀሎች ጠያቂ የለባቸውም፡፡ መንግሥት በአርሲም ሆነ በሌሎች ሥፍራዎች የተፈጸሙትንም ሆነ እየተፈጸሙ ያሉ ወንጀሎች በአስቸኳይ አጣርቶ ለሕዝብ በግልጽ ይፋ በማድረግ ሕጋዊ ዕርምጃ ማስወሰድ አለበት፡፡ በንፁኃን ላይ የሚፈጸሙ የጅምላ ግድያዎች ከአንድ ሰሞን የሐዘን መግለጫና እርስ በርስ መካሰስ በላይ፣ የሕግ ተጠያቂነት መኖሩን ማሳያ መሆን ካልቻሉ ችግሩ ተስፋፍቶ መመለሻው ይቸግራል፡፡ በመንግሥት መዋቅር ውስጥ ሆነው ድርጊቱን የሚፈጽሙም ሆነ ተጠያቂነት እንዳይኖር የሚያደርጉ ሳይቀሩ፣ ተራ በተራ ተጋልጠው መቀጣጫ መሆን አለባቸው፡፡ ወንጀልን እያድበሰበሱ ችግሩ እንዲቀጥል የሚያደርጉ ከጥቅማቸው ይልቅ ጉዳታቸው ስለሚብስ፣ ሕግ ፊት ቀርበው በመዳኘት ቅጣታቸውን ያግኙ፡፡ እስከዚያው ድረስ ግን ለአሳሳቢው የፀጥታ ችግር የጋራ መፍትሔ ይፈለግ!
