አሁንም መልሰን መላልሰን መገንዘብ ያለብን፣ ለአገር ህልውና ከሰላም ውጪ አማራጭም አቋራጭም አለመኖሩን ነው፡፡ ሰላም እንዲሰፍን ደግሞ ለእኩልነት፣ ለነፃነትና ለማኅበራዊ ፍትሕ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ትኩረት መስጠት ያስፈልጋል፡፡ ፋይዳ ቢስ የሆኑ ሰበቦችን በመደርደር የጉልበት መንገድ ከመምረጥ ይልቅ፣ በእርጋታ ተቀምጦ የመነጋገር ባህልን ማዳበር ይገባል፡፡ ሊያጋጥሙ የሚችሉ ማናቸውም ችግሮች መፈታት ያለባቸው በእኩልነትና በሰጥቶ መቀበል መርህ በመነጋገር እንጂ፣ የአንድን ወገን ፍላጎት በሌላው ላይ በጉልበት ለመጫን በመሞከር አይደለም፡፡ ኢትዮጵያ ለዓመታት ከመከራ አዘቅት ውስጥ መውጣት አቅቷት የድህነት መጫወቻ የሆነችው፣ በሠለጠነ መንገድ ተነጋግሮ ልዩነትን ለመፍታት በጎ ፈቃድ በመታጣቱ ነው፡፡ እስካሁን የሚደረጉ አውዳሚ ጦርነቶችም ሆኑ ግጭቶች እንኳን ሊካሄዱ ቀርቶ ሊታሰብም አይገባም ነበር፡፡ የጉልበት መንገድ ዕልቂትና ውድመት እንጂ ልማትም ሆነ ዕድገት እንደማያመጣ በተደጋጋሚ ታይቷል፡፡ የጉልበት መንገድ ተዘግቶ የሐሳብ ልዕልና ይንሰራፋ፡፡
በኢትዮጵያ ከተፋላሚ ጎራዎች ውጪ ሌሎች አማራጭ ያላቸው መኖራቸው እየተዘነጋ ወይም ሆን ተብሎ እየታለፈ፣ ኢትዮጵያውያን ሳይወዱ በግድ የመከራ ገፈት ቀማሽ እየሆኑ በርካታ ዓመታት ነጉደዋል፡፡ አገራቸውም ነዳጅ አልቆበት ዳገት ላይ እንደ ቆመ ተሽከርካሪ ቁልቁል እየተንሸራተተች፣ የሲኦል ምድር ሆና ትውልዶች በችግር እየተጠበሱ ተፈራርቀዋል፡፡ ጥንታዊ ኢትዮጵያውያን ከማንም በፊት የሥልጣኔ አሻራ ያሳረፉባቸውን በርካታ ቅርሶች ትተው ቢያልፉም፣ ተከታታይ ትውልዶች ግን ከሥልጣኔ ተራርቀው የኋላቀርነትና የድህነት መጫወቻ ሆነው መዘባበቻ ሆነዋል፡፡ ለፖለቲካ ሥልጣን የሚደረገው ትንቅንቅ ሕግ የማይዳኘው፣ ምራቃቸውን የዋጡ የአገር ሽማግሌዎች ምክር የማይገታው፣ እንደ ዘመኑ የዕድገት ደረጃ በሙያና በልምድ የዳበሩ ልሂቃን ሐሳብ የማያካፍሉበት፣ በአጠቃላይ የኢትዮጵያ ሕዝብ ገለል እየተደረገ የአሸናፊና የተሸናፊ ድርሳናት እየተከተቡበት ድንቁርና የሰፈነበት የቅርብ ጊዜ ሁነት እንደነበርም መቼም አይዘነጋም፡፡
ከዕልቂትና ከውደመት አባዜ ለመላቀቅና በሕግ ማዕቀፍ ውስጥ መኖርን ለመለማመድ እንዲቻል፣ ሕገወጥነትና ሥርዓተ አልበኝነት መክሰም ይኖርባቸዋል፡፡ አገር አስቸጋሪ ሁኔታ ሲያጋጥማት የተለያየ አተያይና የልምድ ተሞክሮ ያላቸው ልሂቃን፣ ምን ቢደረግ ጥሩ ነው ብለው ለመፍትሔ የሚረባረቡበት ምኅዳር ያስፈልጋል፡፡ ኢትዮጵያ የበደልና የግፍ መፈጸሚያ ሆና ልጆቿ አሳራቸውን ሲበሉ ዘመናት ነጉደዋል፡፡ በ21ኛው ክፍለ ዘመን ጭምር ነውረኛ ድርጊቶች እየተፈጸሙ ጉልበተኝነት የሁሉም ነገር የበላይነት ማሳያ ሆኖ ቀጥሏል፡፡ እንዲህ ዓይነት አስነዋሪ ድርጊቶች አሁንም ተባብሰው እንዲቀጥሉ እንቅልፍ አጥተው የሚያድሩ አሉ፡፡ የሰላም ተስፋ ብልጭ ከማለቱ ለማዳፈን የሚሯሯጡ ሊበቃቸው ይገባል፡፡ ኢትዮጵያን አዘቅት ውስጥ የከተታት በግልና በቡድን ፍላጎት የታጠረ ነውጠኝነት ነው፡፡ በሕግና በሥርዓት መኖርን መልመድ ከጥፋት ስለሚያድን፣ ጠመንጃ ከኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ይውጣ፡፡ ለሐሳብ ጥራት እንጂ ለጉልበት ቦታ አይሰጥ፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ የሕግ የበላይነት መስፈን ያለበት ሕጋዊም ሆነ ፖለቲካዊ መፍትሔ የሚያሻቸው ጉዳዮች ሲያጋጥሙ፣ ይዋጣልን እየተባለ እጅጌ የሚሰበስቡበት የጉልበተኞች ፍልሚያ ቀርቶ የተለያዩ ሐሳቦች በነፃነት እንዲንሸራሸሩ ነው፡፡ ሁሉም ነገር በሥርዓት ሲመራ ሕግ የበላይ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ሰዎች በሕግ ፊት እኩል መሆናቸው በቃል ሳይሆን በተግባር ይረጋገጣል፡፡ ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች እየታፈኑ መሰቃየት ወይም ማሰቃየት አይቻልም፡፡ የመንግሥት ሥልጣን የሚያዘው በጉልበት ሳይሆን፣ ወቅቱን ጠብቆ በሚካሄድ ምርጫ ብቻ ይሆናል፡፡ ልዩነት ተፈጥሮ ችግር ሲያጋጥም የሕግና ተያያዥነት ያላቸው ባለሙያዎች ምክረ ሐሳቦች ያቀርባሉ፡፡ ንግግሩም በስሜት ሳይሆን በምክንያታዊነት ላይ የተመሠረተ ሆኖ፣ አሻሚና አወዛጋቢ ምልከታዎች ሊቀርቡ ይችላሉ፡፡ ሐሳቦቹ ለውሳኔ የሚረዱ ግብዓቶች በመሆናቸው ከተለያዩ ማዕዘናት በመቅረባቸው፣ ለውሳኔ ጥራት ይረዳሉ እንጂ ጉዳት አይኖራቸውም፡፡ በዚህ መንገድ የመነጋገር፣ የመከራከርና የመደራደር ባህል እንዲዳብር ጥርጊያውን ማመቻቸት ይገባል፡፡
ለሰላም መስፈን ብዙኃን አዎንታዊ ምላሽ ሲሰጡ መደመጣቸው በአንድ በኩል ሥልጡን የሆነ የዳበረ ውይይት እንደሚያስፈልግ፣ በሌላ በኩል ለአገር ከማይጠቅሙ ድርጊቶች በመላቀቅ አዲስ ምዕራፍ ለመክፈት መልካም ጅምር እንዲኖር ይረዳል፡፡ ከአገር ውስጥም ሆነ ከውጭ በተለያዩ መስኮች የዳበረ ልምድ ያላቸው ልሂቃን ለዘለቄታ ሰላም መስፈን ትኩረት ሰጥተው አስተዋጽኦ ሲያበረክቱ፣ በሌሎች መስኮች አገራቸውን ማገዝ ለሚፈልጉ ልሂቃን ትልቅ ብርታት ይሰጣል፡፡ እዚህ ላይ እየተነጋገርን ያለነው የሰላም ተስፋው ክፋታቸውን ስላመከነባቸው ከንቱ ፕሮፓጋንዲስቶች ሳይሆን፣ ከእነሱ በተሻለ ጥልቅና ሰፊ ሐሳብ ስላላቸው አርቆ አሳቢ ኢትዮጵያውያን ነው፡፡ ጦርነት አውዳሚና ትውልድ ገዳይ መሆኑን የተረዱ ወገኖች፣ አገራቸው ኢትዮጵያ የነፃነትና የእኩልነት እንድትሆን ሲሉ ነው ለሰላም መስፈን ይታገሉ፡፡ ምክንያቱም ኢትዮጵያ የበርካታ ፍላጎቶች፣ ሐሳቦችና የጋራ እሴቶች ኅብር ስለሆነች የጥቂቶች መጫወቻ እንዳትሆን መደረግ አለበትና፡፡
የኢትዮጵያ ፖለቲካ ለውይይትና ለድርድር ባዕድ የሆነው የፖለቲካ ምኅዳሩ ምሁር ጠል፣ ለመካሪና ለዘካሪ ያስቸገረ፣ ለማኅበረሰቦች ተሳትፎ ቦታ ያልነበረው፣ የአስመሳዮችና የአድርባዮች መፈልፈያና መራቢያ ስለነበር ነው፡፡ ክፋት፣ ሴራ፣ አሻጥርና ኋላቀርነት የተፀናወቱት ከመሆኑም በላይ አርቆ አስተዋይነት ያልፈጠረባቸው ደካሞችና ሰነፎች ስለሚተውኑበት፣ ለአገር ሰቆቃ እንጂ ብሥራት አልነበረውም፡፡ እርስ በርስ መጋደል፣ መሳደድ፣ ስም መጠፋፋት፣ ወጣቱን ትውልድ መበከልና የአገርን ሚስጥር ለባዕዳን ማቀበል አሳፋሪ ልማዶች የሰፈነበት በመሆኑ፣ ኢትዮጵያና ሕዝቧ ያለ ኃጢያታቸው ፍዳቸውን አይተዋል፡፡ ያንን የወደቀ አስተሳሰብ አንለቅም ብለው የሚንገታገቱ ኃይሎች እስቲ እንነጋገር፣ እንደራደር፣ የጎደለ ካለ አብረን እንሙላ ሲባሉ እዚያው አረንቋ ውስጥ ካልተገኘን ማለታቸው ያሳፍራል፡፡ ከዚያ አሳፋሪ የታሪክ ትርክት ተላቆ በብሔራዊ ጉዳዮች ላይ ሁሉን አሳታፊ ንግግር መጀመር የግድ ይላል፡፡ በኢትዮጵያ የጉልበት አባዜ ተወግዶ የሐሳብ ልዕልና የሚናኘው ለንግግር በር ሲከፈት ብቻ ነው!