ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ መሠረተ ልማትን በመጋራት ረገድ ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር ተፈጥሮ የነበረው አለመግባባት መፈታቱን፣ ነገር ግን ከሞባይል ፋይናንስ አገልግሎት ጋር በተገናኘ አሁንም መፍትሔ የሚሻ ጉዳይ መኖሩን አስታወቀ፡፡
ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ. መጋቢት 31 የተጠናቀቀውን የ2026 በጀት ዓመት አፈጻጸም አስመልክቶ፣ ግንቦት 3 ቀን 2018 ዓ.ም. ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል፡፡
ኩባንያው በበጀት ዓመቱ ያከናወናቸውን ሥራዎች፣ ያጋጠሙትን ተግዳሮቶችና የቴሌኮም ዘርፉን በሚመለከት ማብራሪያ የሰጡት የሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዊም ቫንሄሌፑቴ፣ ከዚህ ቀደም የኢትዮጵያ የቴሌኮም ዘርፍ ለሁሉም ኦፕሬተሮች እኩል የመጫወቻ ሜዳ እንዲፈጠር ሲጠይቃቸው የነበሩ ጉዳዮች መፍትሔ እያገኙ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
የቴሌኮም ዘርፍ ከፍተኛ ቁጥጥር የሚደረግበት መሆኑንና ሁለት ተቆጣጣሪ አካላት መኖራቸውን፣ የመጀመሪያው የቴሌኮም ዘርፉ የሚቆጣጠረው የኢትዮጵያ ኮሙዩኒኬሽን ባለሥልጣን መሆኑንና ኤምፔሳን የሚቆጣጠረው ደግሞ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ እንደሆነ በመግለጽ፣ በኤምፔሳ በኩል አሁንም መፍትሔ የሚፈልጉ ጉዳዮች መኖራቸውን አስረድተዋል፡፡
ባለፉት ጥቂት ወራት ከተደረጉ ለውጦች መካከል የመሠረተ ልማት መጋራትን በሚመለከት የኮሙዩኒኬሽን ባለሥልጣን የዋጋ ተመን መመርያ ማውጣቱን፣ ይህም ማለት ከዚህ በኋላ የዋጋ ተመን ቁጥጥር እንደሚደረግበት ያግዛል ብለዋል፡፡ በባለሥልጣኑ የተላለፈው ሌላው ውሳኔ ማንኛውም የቴሌኮም ኦፕሬተር አገልግሎቶቹን ከዋጋ በታች መሸጥን የከለከለበት መሆኑንና ይህም ዘርፉን ይበልጥ እንደሚያሳድገው አክለዋል፡፡
‹‹በቴሌኮም አገልግሎት ላይ የተደረጉ ለውጦች መልካም ቢሆኑም፣ የመንግሥት አገልግሎት የክፍያ ሥርዓት ለሁሉም ተደራሽ እንዲሆንና ሁሉም የክፍያ አገልግሎት ሰጪዎች እኩል የመጫወቻ ሜዳ እንዲፈጠርላቸው በማድረግ ረገድ፣ ከመንግሥት በኩል በጎ ምላሽ እንጠብቃለን፤›› ብለዋል፡፡
ኤምፔሳ የፋይናንስ አገልግሎቶችን ለማቅረብ እንዲችል አሁንም በሒደት ላይ የሚገኙ ሥራዎች እንዳሉና ፖሊሲዎችም መኖራቸውን፣ ነገር ግን አተገባበሩ የተወሰነ ጊዜ እንደሚወስድና በመጪዎቹ ከስድስት እስከ 12 ወራት በአተገባበሩ ላይ እውነተኛ ለውጥ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል፡፡
From The Reporter Magazine
ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ በአጠቃላይ 3‚500 ማማዎች እንዳሉት የገለጹት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፣ ከእነዚህ ውስጥ 1‚500 ወይም 40 በመቶ ያህሉን ከኢትዮ ቴሌኮም በኪራይ እንዳገኛቸው ጠቁመዋል፡፡ በኪራይ ለሚያገኛቸው ማማዎች የሚከፈለው ገንዘብ ቁጥጥር ሊደረግበት እንደሚገባ የኮሙዩኒኬሽን ባለሥልጣን መወሰኑን በመግለጽ፣ በዓመት ለኪራይ የሚከፈለው ከአምስት እስከ ስድስት ቢሊዮን ብር ይደርሳል ብለዋል፡፡
ባለፉት 12 ወራት በተለይም ባለፈው ሩብ ዓመት የቴሌኮም ኢንዱስትሪው ትርፋማ መሆን እንዲችል የዋጋ ጭማሪ መደረጉን አስታውሰው፣ ይህም ዘርፉን ጤናማ እንዳደረገው ገልጸዋል፡፡
የኮሙዩኒኬሽን ባለሥልጣን በአገሪቱ የሚገኝ የቴሌኮም ኦፕሬተር ማንኛውንም ምርት ወይም አገልግሎት ከዋጋ በታች እንዲሸጥ እንደማይፈቀድ በመመርያው ባሳወቀው መሠረት፣ በሚቀጥሉት ከ12 እስከ 18 ወራት ጊዜ ውስጥ ከመመርያው ጋር የሚጣጣም የዋጋ ጭማሪ እንደሚኖር ተናግረዋል፡፡
From The Reporter Magazine
የዋጋ ጭማሪ ይኖራል ሲባል ‹‹ደንበኞች በበጎ ላይመለከቱት ይችላሉ›› ያሉት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፣ ነገር ግን አገሪቱ ለቴሌኮም መሠረተ ልማት አምስት ቢሊዮን ዶላር ኢንቨስትመንት እንደሚያስፈልግ በመረዳት፣ ተጨማሪ ኢንቨስትመንትን መሳብ ካስፈለገ ምርትና አገልግሎቶች ከዋጋ በታች መሸጥ እንደሌለባቸው አሳስበዋል፡፡
ኩባንያው በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 15.9 ቢሊዮን ብር ዓመታዊ ገቢ ማግኘቱን፣ ይህም ካለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀር የ130.9 በመቶ ዕድገት ማስመዝገቡን እንደሚያሳይ አስረድተዋል፡፡
