የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ2016 የሒሳብ ዓመት ያሰባሰበው የውጭ ምንዛሪ ከቀዳሚው ዓመት በ300 ሚሊዮን ዶላር ዝቅ ያለ መሆኑ ተመላከተ፡፡
ባንኩ የ2016 የሒሳብ ዓመት የሥራ አፈጻጸሙን በተመለከተ እያካሄደ ባለው ግምገማ ላይ እንደተመለከተው በሒሳብ ዓመቱ 3.2 ቢሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሪ ማሰባሰብ ችሏል፡፡
ይህ ገቢ በቀዳሚው ዓመት አሰባስቦት ከነበረው 3.5 ቢሊዮን ዶላር አንፃር ሲታይ በ300 ሚሊዮን ዶላር ቅናሽ ያሳየ መሆኑን ለመገንዘብ ተችሏል፡፡
ከባንኩ ዓመታዊ ሪፖርት መረዳት እንደተቻለው በ2015 የሒሳብ ዓመት ባንኩ ያገኘው የውጭ ምንዛሪ መጠን ከ2014 አንፃር ሲታይ በ32 በመቶ አድጎ 3.5 ቢሊዮን ዶላር ደርሶ የነበረ ቢሆንም፣ ዘንድሮ ግን ያገኘው የውጭ ምንዛሪ ገቢ 3.2 ቢሊዮን ዶላር ዝቅ ማለቱን ነው፡፡
በ2016 ከተሰባሰበው አጠቃላይ የወጭ ምንዛሪ 878.5 ሚሊዮን ዶላር ከወጪ ንግድ የተገኘው ከፍተኛ መጠን ያለው የውጭ ምንዛሪ የተገኘው ከሐዋላ ሲሆን፣ በዚህም 2.7 ቢሊዮን ዶላር ተገኝቷል፡፡ ቀሪው 286.1 ሚሊዮን ዶላር ከውጭ ግዥ ማሰባሰብ የተቻለ መሆኑን ከባንኩ የተገኘው መረጃ ያስረዳል፡፡
በሒሳብ ዓመቱ ባንኩ ከፍተኛ ዕድገት ያሳየበት የውጭ ምንዛሪ የተገኘው ከወለድ ነፃ የባንክ አገልግሎት ሲሆን፣ በዚህ ዓመት ብቻ በሲቢኢ ኑር በኩል ባንኩ ያገኘው የውጭ ምንዛሪ 90 ሚሊዮን ዶላር ነው፡፡
በሲቢኢ ኑር በኩል የተገኘው የውጭ ምንዛሪ ገቢ ከቀዳሚው ዓመት ከሦስት እጥፍ በላይ ብልጫ ያለው ስለመሆኑ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡ እንደ ባንኩ መረጃ በ2016 የሒሳብ ዓመት ከውጭ ሐዋላ 2..18 ቢሊዮን ዶላር ለማግኘት ታቅዶ የነበረ ሲሆን፣ የተገኘው ደግሞ 2.07 ቢሊዮን ዶላር ነው፡፡
ሪፖርተር ባገኘው መረጃ የባንኩ የውጭ ምንዛሪ ገቢ በየዓመቱ ቅናሽ እያሳየ ለመምጣቱ ዋነኛ ምክንያት ከወጭ ንግድ የሚያገኘው የውጭ ምንዛሪ ዝቅ እያለ በመምጣቱ ነው፡፡
ከ2016 የሥራ አፈጻጸሙ ጋር በተያያዘ ባንኩ ይፋ ያደረጋቸው መረጃዎች እንደሚያመለክተው ባንኩ ከዕቅዱ በላይ ብድር ማቅረብ መቻሉ ነው፡፡ በሒሳብ ዓመቱ እሰጣለሁ ብሎ ያቀደው የብድር መጠን 208.8 ቢሊዮን ብር ቢሆንም የሰጠው ግን 218.2 ቢሊዮን ብር በመሆኑ የእቅዱን 104.5 በመቶ ማሳካቱን ጠቅሷል፡፡ ከሰጠው ብድር ውሰጥ 198.3 ቢሊዮን ለግል ዘርፍ የተሰጠ ሲሆን፣ 20 ቢሊዮን ብር ደግሞ ለመንግሥት ተቋማት የተሰጠ መሆኑን ገልጿል፡፡ በ2015 የሒሳብ ዓመት አዲስ የሰጠው የብድር መጠን 151.2 ቢሊዮን ብር እንደነበር ይታወሳል፡፡
በተቀማጭ ገንዘብ አሰባሰብም ባንኩ በሒሳብ ዓመቱ 120.7 ቢሊን ብር አዲስ ተቀማጭ ገንዘብ ማሰባሰብ በመቻሉ የአጠቃላይ የተቀማጭ ገንዘብ መጠኑን 1.2 ትሪሊዮን ብር መድረሱን ተገልጿል፡፡
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በዚህ የሥራ አፈጻጸሙ በበጀት ዓመቱ ከታክስ በፊት 25.6 ቢሊዮን ብር ማትረፍ ችሏል፡፡ ይህ የትርፍ ምጣኔ፣ በባንኩ ከፍተኛ የሚባል መሆኑን ተገልጿል፡፡ የተከታታይ ዓመታት የባንኩ የትርፍ ምጣኔን የተመለከቱ መረጃዎች እንደሚያሳዩት በ2014 ከታክስ በፊት 21.8 ቢሊዮን ብር ማትረፉን ሲሆን፣ በ2015 ደግሞ ከታክስ በፊት 22.1 ቢሊዮን ብር ማትረፍ መቻሉን ያሳያሉ፡፡ በ2015 ደግሞ ከታክስ በፊት 22.1 ቢሊዮን ብር ማትረፍ መቻሉን ያሳያሉ፡፡