
ሶዞ ትሬዲንግ ካለፉት 15 ዓመታት ወዲህ የከበሩ ማዕድናትንና ሥጋን ወደ ውጭ በመላክ ሥራ ላይ ተሰማርቶ እየሠራ ይገኛል፡፡ ዘይትና ሌሎች ምግብ ነክ ነገሮችንም ወደ አገር በማስገባት ይታወቃል፡፡ ኩባንያው ስለሚልካቸው የከበሩ ማዕድናት፣ ዘርፉ ስለሚገኝበት ሁኔታ፣ ከሥጋ ምርት ጋር ተያይዘው ስለሚነሱ ችገሮች፣ ስለ ኦንላይን የሥጋ ግብይትና በሌሎችም ጉዳዮች ዙሪያ የሶዞ ትሬዲንግ ሥራ አስኪያጅ የሆኑትን አቶ ቶማስ መለሰን፣ የማነ ብርሃኑ አነጋግሯቸዋል፡፡
ሪፖርተር፡– ኤክስፖርት የምታደርጓቸው የከበሩ ማዕድናት የትኞቹ ናቸው? ወደ የትኞቹ አገሮችስ ትልካላችሁ?
አቶ ቶማስ፡- ኩባንያችን ከ15 ዓመታት በፊት የተመሠረተ ነው፡፡ በዋነኛነት የከበሩ ማዕድናትን ወደ ውጭ አገሮች ኤክስፖርት በማድረግ፣ በሥጋ ንግድና በቄራዎች አገልግሎት ላይ ተሰማርቶ እንቅስቃሴ ያደርጋል። የከበሩ ማዕድናት በቀላሉ የሚገኙ ዓይነት አይደሉም፡፡ የሚገኙበት ቦታም ውስን ነው፡፡ ከከበሩ ማዕድናት መካከል ደግሞ ኦፓል የምንለው በኢትዮጵያ ብቻ የሚገኝ ሲሆን፣ አብዛኛውን ጊዜ ሰሜን ሸዋ፣ መርሐቤቴና ደላንታ አካባቢዎች ይገኛል፡፡ ይህን ማዕድን በአካባቢው ካሉ ማዕድን በማውጣት ዘርፍ ከተደራጁ ማኅበራት በግዥ የምናገኘው ነው፡፡ ሳፋየርና ኤመራልድ የተባሉ የከበሩ ማዕድናትንም ከአፋርና ከትግራይ አካባቢዎች የምናገኛቸው ሲሆን፣ ሌሎች ኢንዱስትሪያል ማዕድን የሚባሉትን እንደ ሊቲየም፣ ታንታለምና ቤሪሊየም የመሳሰሉ ማዕድናትን ፈቃድ ካላቸውና በዘርፉ ከተደራጁ ማኅበራት በመቀበል ወደ ውጭ አገሮች እንልካለን፡፡ ኢትዮጵያ በማዕድን ሀብት የበለፀገች ነች፡፡ በጥናት እንደተረጋገጠው አብዛኛው ኦሮሚያ ክልል፣ በተለይ ቆላው አካባቢ፣ ሰሜን ሸዋ፣ ትግራይ፣ አፋርና ቤኒሻንጉል ጉሙዝ የማዕድን ሀብትና ክምችት አላቸው ተብለው የሚታወቁ ናቸው፡፡ አሁን ላይ ደግሞ ሀብቱ በብዛት እንዳላቸው የተረጋገጠና ግን ምንም ካልተሠራባቸው አካባቢዎች መካከል ባሌ ዞንን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ቻይና፣ ህንድ፣ አሜሪካና የአውሮፓ አገሮች የከበሩ ማዕድናትን ከምንልክባቸው አገሮች መካከል በቀዳሚነት የሚጠቀሱ ናቸው፡፡
ሪፖርተር፡– ኤክስፖርት ከምታደርጓቸው የከበሩ ማዕድናት የሚገኘው የውጭ ምንዛሪ ምን ይመስላል?
አቶ ቶማስ፡- ቀደም ባሉ ጊዜያት እንደ አገር ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ የሚገኘው ከቡና ምርት ነበር፡፡ አሁን የውጭ ምንዛሪ ከሚገኝባቸው ዘርፎች መካከል ማዕድን የቀዳሚነቱን ቦታ ይዟል፡፡ በዚህ ዘርፍ ድርጅታችን ይህ ነው ተብሎ የሚጋነን ባይሆንም በመጠኑም ቢሆን የውጭ ምንዛሪ እያስገኘ ይገኛል፡፡ በተለይ ኢንዱስትሪያል ማዕድናትን በብዛት ኤክስፖርት ባደረግን ጊዜ የሚገኘው የውጭ ምንዛሪ ከፍ ያለ ነው፡፡
ሪፖርተር፡– አሁን ላይ ወርቅ አምራች የሆኑ ክልሎች ለአብነት ቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልልን መጥቀስ እንችላለን፣ ለብሔራዊ ባንክ የሚያቀርቡት ወርቅ ቀደም ባሉት ጊዜያት ያቀርቡ ከነበረው ጨምሯል፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት ምንድነው?
አቶ ቶማስ፡- ይህን ያመጣው የኢኮኖሚ ሪፎርም መደረጉ ነው፡፡ ሪፎርሙ በማዕድን ብቻ ሳይሆን በሌሎችም ዘርፎች ከፍተኛ መነቃቃት እንዲኖር አድርጓል፡፡ የኢኮኖሚ ሪፎርሙ ከመካሄዱ በፊት በጥቁር ገበያና በብሔራዊ ባንክ መካከል ከፍተኛ ሊባል የሚችል የውጭ ምንዛሪ ልዩነት ነበር፡፡ ይህም ወርቅ በኮንትሮባንድ እንዲወጣ ምክንያት ሆኖ ቆይቷል፡፡ ሆኖም አሁን የውጭ ምንዛሪው ከጥቁር ገበያው ጋር ትይዩ መሆን በመቻሉ አብዛኛዎቹ ወርቅ አቅራቢዎች ምርቱን ለብሔራዊ ባንክ በማቅረብ ላይ ናቸው ብዬ አምናሁ፡፡ አንዳንድ ክልሎች ለብሔራዊ ባንክ የሚያስረክቡት የወርቅ መጠን የጨመረበትም ምክንያት ከዚሁ የተነሳ ነው ማለት ይቻላል፡፡
ሪፖርተር፡– በማዕድን ዘርፉ የሚታዩ ችግሮች ምንድናቸው?
አቶ ቶማስ፡- አሁን ላይ ለማዕድን ዘርፉ መንግሥት የተለየ ትኩረት ሰጥቶ በመሥራት ላይ ይገኛል፡፡ አበረታች የሚባሉ ለውጦችም እየታዩበት ነው፡፡ ሆኖም በሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ በኩል አንዳንድ ጥቃቅንና በቀጣይ ይስተካከላሉ ተብለው የሚታመኑ ነገሮች ከመኖራቸው በቀር የጎላ ችግር አለ የምለው የለኝም፡፡ ነገር ግን እንደ አገር ሰላም በሌለባቸው አካባቢዎች ሀብቱን አልምቶ ከመጠቀም አንፃር ውስንነቶች ስለሚታዩ ሰላምና ፀጥታን አረጋግጦ ሀብቱን መጠቀም ከተቻለ ከዘርፉ የሚገኘው የውጭ ምንዛሪ ኢኮኖሚውን በመደገፍ በኩል ትልቅ አበርክቶ ይኖረዋል ብዬ አምናለሁ፡፡
ሪፖርተር፡– ከማዕድን ዘርፍ በተጓዳኝ የሥጋ ምርት ወደ ውጭ ትልካላችሁ፣ ምርቱን የምትልኩባቸው አገሮች የትኞቹ ናቸው? ሥጋን ኤክስፖርት ከማድረግ አንፃር ያሉ ችግሮችስ ምንድናቸው?
አቶ ቶማስ፡- የሥጋ ምርት እየላክን የምንገኘው የመካከለኛው ምሥራቅ አገሮች ወደሆኑት ኦማን፣ ኳታር፣ ሳዑዲ ዓረቢያና ሌሎችም ነው፡፡ ሥጋን በመላክ ዘርፍ ከሌሎች አገሮች አኳያ እንደ አገር ተወዳዳሪነት ይጎድለናል፡፡ ከላቲን አሜሪካ እንደ ብራዚል፣ ከሩቅ ምሥራቅ እንደ ፓኪስታን ያሉ አገሮች ከእኛ በተሻለ ደረጃ ሥጋ የሚያቀርቡ ናቸው፡፡ ይህም የሆነበት እነዚህ አገሮች የእንስሳት መኖ ላይ በከፍተኛ ደረጃ በመሠራታቸው ነው፡፡ በኢትዮጵያ የእንስሳት መኖ ውድ ከመሆኑ አንፃር የሥጋ ዋጋ እንዲጨምር ምክንያት ሆኗል፡፡ በዚህም ምክንያት እንደ ብራዚልና ፓኪስታን ከመሳሰሉ አገሮች ለመወዳደር አልቻልንም፡፡ ለምሳሌ አንድ ኪሎ ሥጋ ወደ ውጭ አገሮች ሲላክ አምስትና ስድስት ዶላር አካባቢ ነው፡፡ ይህ አንድ ኪሎ ሥጋ አገር ውስጥ ቢሸጥ ግን ከዚያ በላይ ዋጋ ያወጣል፡፡ በዓለም ከፍተኛ የሥጋ ምርት አላቸው ከሚባሉት አገሮች መካከል ኢትዮጵያ አንዷ ሆና ብትቀመጥም፣ የመኖ ዋጋ ከፍተኛ በመሆኑ ምክንያት አቅርቦቱ አነስተኛ ሆኗል፡፡ ይህም ከሌሎች አገሮች ጋር በዘርፉ የሚደረገውን ውድድር ዝቅተኛ ሊያደርገው ችሏል፡፡
ሪፖርተር፡– በድንበር አካባቢ የቁም እንስሳት የኮንትሮባንድ ንግድ በሰፊው እንዳለ ይነገራል፡፡ የቁም እንስሳት በኮንትሮባንድ መውጣታቸው በእናንተ ሥጋ ላኪዎች ላይ ያመጣው ተፅዕኖ ይኖራል?
አቶ ቶማስ፡- እንደ ወርቅ ሁሉ፣ የቁም እንስሳት የኮንትሮባንድ ንግድም የኢኮኖሚ ሪፎርም ከመካሄዱ በፊት በስፋት ስለመኖሩ ሲነገር እንሰማለን፡፡ ከብቶች በድንበር አካባቢ ወደ ኬንያና ወደ ሌሎችም አገሮች ተነድተው የሚወጡበት አጋጣሚ ነበር፡፡ አሁን ላይ ይህ ችግር የመቀነስ አዝማሚያ እየታየበት ነው ይባላል፡፡ ሆኖም የቁም እንስሳት የኮንትሮባንድ ንግድን በድንበር አካባቢዎች ሙሉ በሙሉ ማስቆም የሚቻል ዓይነት አይመስለኝም፡፡ ነገር ግን ቁጥጥርና ክትትል ማድረግ ከተቻለ በኮንትሮባንድ የሚወጣውን የአገር ሀብት ወደ ሕጋዊ ማዕቀፍ ማምጣት ይቻላል የሚል እምነት አለኝ፡፡
ሪፖርተር፡– ወደ ውጭ የምትልኩት ሥጋ ጥራቱ፣ ንፅህናውና ጤናማነቱ የተጠበቀ መሆኑ የሚረጋገጠው እንዴት ነው?
አቶ ቶማስ፡- ኢትዮጵያ ውስጥ የኤክስፖርት ቄራዎች ተብለው የተቋቋሙ አሉ፡፡ እነዚህ ቄራዎች የላቦራቶሪም ሆነ ሌሎች አገልግሎቶች ተሟልቶባቸው ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎት የሚሰጡ ናቸው፡፡ ይህ ስለሆነም ከንፅህናና ከጥራት አንፃር የሚገጥሙ ችግሮች አሉ ብዬ አላምንም፡፡ በተጨማሪም ወደ ዓረብ አገሮች ሥጋ የሚልኩ ተቋማት ‹‹ሀላል›› ሰርተፍኬት የሚኖራቸው በመሆኑ በዚህ ዙሪያ ችግር የለም፡፡ ቀደም ሲል እንዳልኩት ትልቁ ችግር የዋጋ ጉዳይ ነው፡፡ እነ ብራዚልና ፓኪስታን የእንስሳት መኖን በርካሽ በማግኘታቸው ወደ መካከለኛው ምሥራቅ አገሮች የሚልኩት ሥጋም ከዋጋ አንፃር ዝቅተኛ ነው፡፡ ወደ እኛ አገር ስንመጣ መኖ ውድ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ የምናቀርበው ሥጋ በዚያው ልክ ዋጋው ከፍ እንዲል ሆኗል፡፡ በመሆኑም አሁን ላይ ያለብን ትልቁ ችግር በዋጋ ረገድ ከሌሎች አገሮች ጋር ተወዳዳሪ መሆን ያለመቻላችን ብቻ ነው፡፡
ሪፖርተር፡– ድርጅታችሁ ሥጋን ወደ ውጭ አገሮች ከመላክ ጎን ለጎን ‹‹ሁሌ ቅርጫ›› በሚል የኦንላይን ሥጋ ለተጠቃሚዎች ማድረስ ጀምሯል፡፡ ሥጋን በኦንላይን እያቀረባችሁ ያላችሁት በምን ዓይነት መልኩ ነው?
አቶ ቶማስ፡- ኢትዮጵያ የሥጋ ሀብት ያላት ሆና አንድ ኪሎ ሥጋ ሦስት ሺሕ ብር እየተሸጠባት ይገኛል፡፡ በእውነቱ ይህን ማየት ያማል፡፡ ሥጋ ለማኅበረሰቡ ቅንጦት ሳይሆን መሠረታዊ ምግብ መሆን ያለበት ነው፡፡ ከዚህ አኳያ አንድ ኪሎ ሥጋ አንድ ሺሕ ብርና ከዚያ በታች በሆነ ዋጋ መሸጥ ይኖርበታል በሚል ዕቅድ ይዘን በኦንላይን ሥጋ ማቅረብ ጀምረናል፡፡ አገራችን ከአፍሪካ በቀንድ ከብት ብዛት በቀዳሚነት ትጠቀሳለች፡፡ ይህ ማለት ሀብቱ አለ ማለት ነው፡፡ ስለሆነም ይህ ሀብት በአነስተኛ ዋጋ ተጠቃሚው ዘንድ መድረስ ይኖርበታል፡፡ ከዚህ አንፃር ሥጋ በውድ መሸጥ የለበትም በሚል የትንሳዔ በዓልን አስመልክተን በቴሌ ብር ዘመን ገበያ ቅርጫ ለማቅረብ ችለናል፡፡ በተጨማሪም ኅብረተሰቡ ጋር በቀላሉ ተደራሽ ለመሆን እንዲያስችለን በቅርብ ቀናት በየክፍለ ከተማው አንድና ሁለት የሥጋ መሸጫ መደብር ለመክፈት እንቅስቃሴ እያደረግን እንገኛለን፡፡
ሪፖርተር፡– የትንሳዔ በዓልን ምክንያት በማድረግ በኦላይን ያካሄዳችሁት ቅርጫ ምን ይመስላል?
አቶ ቶማስ፡- እጅግ ከጠበቅነው በላይ ሆኖ አግኝተነዋል፡፡ ወደ ገበያው የተቀላቀልነው በዓሉ የአንድ ሳምንት ጊዜ ሲቀረው የነበረ ቢሆንም፣ ግብይቱ ተጠቃሚ ያለው ስለመሆኑ ለማረጋገጥ የቻልንበትም ነው፡፡ ገበያውን በተቀላቀልንበት የአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ አሥር ያህል በሬዎችን አቃርጠን ለተጠቃሚዎች ለማድረስም ችለናል፡፡ ከተጠቃሚዎች ያገኘነውም ግብረ መልስ በሥራችን ደስ እንደተሰኙና በዋጋ ደረጃም ተመጣጣኝ በሚባል መልኩ ስለማቅረባችን ነግረውናል፡፡ ሁሌ ቅርጫ ለትንሳዔ በዓል አንድ መደብ ቅርጫ በ25 ሺሕ ብር ዋጋ ለተጠቃሚው እንዲደርስ አድርጓል፡፡ ይህ አንድ መደብ የምንለው ሥጋ እስከ 26 ኪሎ አካባቢ የሚመዝን ሲሆን፣ ፓኬጁ ኤክስፖርት ስታንዳርድ በሚባል ደረጃ የሆድ ዕቃው (ጨጓራው፣ ጉበቱና ኩላሊቱ) ለብቻው፣ አጥንቱና ሥጋውንም እንዲሁ ለየብቻ ታሽጎ ለተጠቃሚው የቀረበ ነው፡፡ በሥራችንም ደንበኞቻችን ደስተኞች ሆነው በማየታችን ድርጅታችን ኩራት እንዲሰማው ሆኗል፡፡
ሪፖርተር፡– በቀጣይ ምን ለመሥራት አቅዳችኋል?
አቶ ቶማስ፡- እስካሁን አገር ውስጥ ለሚቀርብ ሥጋ የዕርድ አገልግሎት እየሰጡ የሚገኙት የመንግሥት ቄራዎች ናቸው፡፡ ስለሆነም ድርጅታችን ይህን ክፍተት ለመሙላት ቄራዎችን በማቋቋም ለራሱ፣ ለተቋማትና ለግለሰቦች የዕርድ አገልግሎት ለመስጠት ወደ ሥራ ገብቷል፡፡ ጥቂት በሚባሉ ጊዜያትም አልግሎቱን የሚጀምር መሆኑን በዚህ አጋጣሚ ለመግለጽ እወዳለሁ፡፡