በአዲስ አበባ ከተማ እየተከናወነ ለሚገኘው የኮሪደር ልማት የወንዝ ዳር ፕሮጀክት ብቻ፣ በመንግሥትና በግል አጋርነት 1.3 ትሪሊየን ብር ፈሰስ መደረጉ ተገለጸ፡፡
ናሽናል ሚዲያ አክሲዮን ማኅበር ‹‹አዲሲቷ አዲስ›› በሚል ርዕስ የአዲስ አበባን የማደስና የማልማት ሥራዎች፣ መልካም ዕድሎችና ተግዳሮቶች ላይ ያተኮረ የውይይት መድረክ ትናንት ግንቦት 4 ቀን 2018 ዓ.ም. በዓድዋ ሙዚየም ውይይት አካሂዷል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርና የፌዴራል መንግሥት የሥራ ኃላፊዎች፣ የሚዲያ ባለሙያዎችና ከተለያዩ የማኅበረሰብ ክፍሎች የተውጣጡ ተሳታፊዎች በተገኙበት የውይይት መድረክ ላይ የተገኙት፣ የአዲስ አበባ ከተማ ውበትና አረንጓዴ ልማት ቢሮ ኃላፊና የኢዜማ ፓርቲ አባል አቶ ግርማ ሰይፉ፣ በከተማዋ ለተከናወነው የወንዝ ዳር ፕሮጀክት ብቻ በመንግሥትና በግል አጋርነት 1.3 ትሪሊየን ብር ፈሰስ መደረጉን ገልጸዋል፡፡


አቶ ግርማ ሰይፉ
ሁሉም ሥራ ከመንግሥት ካዝና በመንግሥት በጀት የተሠራ ተደርጎ የሚታሰበው ትክክል አለመሆኑን፣ አብዛኛው ሥራ የሚሠራው በግል ዘርፉ እንደሆነና የመንግሥት ኃላፊነት በዋናነት ማቀናጀት መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በጀት 350 ቢሊዮን ብር መሆኑን ያስታወሱት አቶ ግርማ፣ ለኮሪደር ልማት ለወንዝ ዳር ፕሮጀክት ብቻ 1.3 ትሪሊየን ብር ወጪ ሊደረግ የቻለው በመንግሥትና በግል አጋርነት ፕሮጀክት መሆኑንና ገንዘቡ ከየት መጣ የሚለው ሲታይም የኅብረተሰቡ በተለይም የባለሀብቶች ተሳትፎ ትልቅ ድርሻ እንዳለው ገልጸዋል፡፡
ለውይይት መነሻ የሚሆን ሁለት ጽሑፎች የቀረቡ ሲሆን፣ ‹‹የከተማ ትራንስፎርሜሽን ዕሳቤዎች፣ ትግበራና አንድምታዎች በአዲስ አበባ›› በሚል ርዕስ ጽሑፍ ያቀረቡት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ስትራቴጂካዊ ፕሮግራሞች ማኔጅመንት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ እሸትአየሁ ክንፉ (ዶ/ር)፣ 5‚414 ሔክታር መሬት በትራንስፖርት መር ኮሪደሮች የከተማ ማደስ ሥራ መከናወኑን ገልጸዋል፡፡
ይህም 205 ኪሎ ሜትር የአስፋልት መንገድ፣ 368 ኪሎ ሜትር የእግረኛ መንገድ፣ 250 ኪሎ ሜትር የብስክሌት መስመር፣ 180 ኪሎ ሜትር ፓርኪንግና ተርሚናል፣ 180 ኪሎ ሜትር የውኃ ፍስሻ መስመሮች መሠራታቸውን አብራርተዋል፡፡
From The Reporter Magazine
በወንዝ ዳርቻ ፕሮጀክት የተሠራን ሽፋን ሲገልጹ፣ 1‚160 ሔክታር መሬት መሆኑንና ይህም 50 ኪሎ ሜትር ርዝማኔ እንዳለው ተፈጥሮን መሠረት ባደረገ የወንዝ ዳርቻ ፕሮጀክት 456 ሔክታር መሬት ላይ መከናወኑን ተናግረዋል፡፡
በቀረቡት ጽሑፎች መነሻነት ከተሳታፊዎች ጥያቄዎች ቀርበዋል፡፡ በአዲስ አበባ እየተከናወኑ የሚገኙ ሥራዎች ለልጆች ምቹ ሁኔታ መፍጠራቸውን፣ እንግዶችንም ለማስተናገድ አመቺ መሆኑን የኔክስት ፋሽን ዲዛይን መሥራችና ሥራ አስኪያጅ ዲዛይነር ሳራ መሐመድ ገልጸው፣ ይህን ሥራ ያከናወኑ አመራሮች ምሥጋና ይገባቸዋል ብለዋል፡፡
የልማት ተነሺዎችን በሚመለከትም በሕግ የተቀመጠ የካሳ ክፍያ እንዳለ ተገልጾ አንደነበር በመግለጽ፣ ተነሺዎች የተሰጣቸው ካሳ ጊዜውንና ንብረቱን ታሳቢ ያደረገ ስለመሆኑ ጥያቄ አቅርበዋል፡፡
From The Reporter Magazine
በከተማዋ እየተከናወኑ የሚገኙ ሥራዎችን አለማድነቅ አይቻልም ያሉት ጸሐፊ ተውኔት ኃይሉ ፀጋዬ፣ ሥራዎችን ዜጎች ሳይገፋ ልማቱ እንዲቀጥል ጠይቀዋል፡፡ እየተሠራ ያለው ሥራ በርካታ ሰዎችን ዋጋ አስከፍሎ እዚህ የደረሰ መሆኑ መረሳት እንደሌለበት ጠቁመው፣ ከተማዋ ወደፊት ምን ያህል ሕዝብ እንድምትይዝ የታቀደ ነገር ስለመኖሩ ማብራያ ቢሰጥ ብለዋል፡፡
ሌላው ተሳታፊ አቶ ደበሽ ተመስገን (አርቲስት) በበኩላቸው የተሠራውን ሥራ በማድነቅ ጥያቄያቸውን ጀምረው፣ ስለከተማዋ ዕድገት ሲገለጽ መልካም ጎኖቹ ብቻ እንደሚነገር፣ ነገር ግን ከተሞች ሲስፋፉ የፖለቲካ፣ የማኅበራዊና የኢኮኖሚ ጉዳት ስለሌላቸው ነው ወይ ሲሉ ጠይቀዋል፡፡
በተነሱት ጥያቄዎች ላይ ምላሽ የሰጡት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ስትራቴጂካዊ ፕሮግራሞች ማኔጅመንት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ እሸትአየሁ (ዶ/ር)፣ አዲስ አበባ ምን ያሀል ሰው መሸከም አለባት የሚለው ጠቃሚ አጀንዳ መሆኑንና እስካሁን ግን የተቀመጠ ገደብ አለመኖሩን ገልጸዋል፡፡
የከተማዋን ሥፋት በሚመለከት ግን ተሠርቶ ማለቁንና የሚታይ በመሬት ላይ የተከለለ ድንበር መኖሩን ተናግረዋል፡፡
የኮሪደር ሥራውን በሚመለከት ሲያብራሩም፣ ለሥራው የወጣው አብዛኛው ገንዘብ ከግሉ ሴክተር የመጣ መሆኑንና መንግሥት የማመቻቸት ሥራውን በዋናነት ማከናወኑን ጠቁመዋል፡፡ ‹‹የወንዝ ዳር ልማት በትሪሊየን ብር ኢንቨሰት ተደርጎበታል፤›› ያሉት ኃላፊው፣ ፕሮጀክቱ ሁሉንም ነገር መንግሥት ከያዘው ይበላሸል የሚለው አመለካከት የተሳሳተ መሆኑ የተረጋገጠበት ነው ብለዋል፡፡
ካሳን በሚመለከት ለቀረበው ጥያቄ ሲያብራሩም የካሳ ሳይንስ የሕግና የኢኮኖሚ ውህደት መሆኑን፣ ሁለቱም የሚስማሙት ደግሞ ተመጣጣኝ የካሳ ክፍያ መሆኑንና ይህም የሆነው የትኛውም የካሳ ክፍያ በገበያው ዋጋ ሲተመን እኩል መካስ ስለማይቻል እንደሆነ አስረድተዋል፡፡
በዚህም በሕጉ መሠረት በልካቸው ተጠቅመዋል ወይ የሚለውን ለመመልከት መጀመሪያ ሕጉን ማወቅ እንደሚገባ፣ ሕጉ የሚደነግገው በቁጥር ሳይሆን የማኅበራዊ፣ የኢኮኖሚዊ፣ የቁሳቁስ፣ የትራንስፖርትና የሥነ ልቦና ካሳ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ይህ የሚወሰነውም በዕለቱ ምንዛሪ መሆኑንና በዚህ አግባብ ሲታይ ተመጣጣኝ ካሳ ነው ብለው እንደሚያምኑ ገልጸዋል፡፡
በተቃራኒው ግን ከዚህ በፊት በነበረው በልማት መስፋፋት የተጎዱ ሰዎች ተክሰዋል ወይ ለሚለው ጥያቄ ተክሰዋል ብለው እንደማያምኑ፣ ለዚህም ሕጉ በራሱ የነበረበት ክፍተትና ሕጉን ያስፈጸሙ ሰዎች የነበራቸው ፍላጎት ያመጣው አደጋ ነው ብለዋል፡፡
