ሪፖርተር – Ethiopian Reporter – #1 Best and reliable news source in Ethiopia
[ክቡር ሚኒስትሩ ወደ ቢሯቸው ሲገቡ አማካሪያቸው ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ በተመለከተው አንድ ጉዳይ ተገርሞ አገኙት]
- ምነው? ደህና አይደለህም?
- ኧረ ደህና ነኝ ክቡር ሚኒስትር።
- ፊትህ ላይ የማየው ግን እንደዚያ አይመስልም፡፡
- ማኅበራዊ ሚዲያ የተመለከትኩት አንድ መረጃ አስገርሞኝ ነው።
- ምን ዓይነት መረጃ ቢሆን ነው እንዲህ ያስገረመህ?
- ከሸዋ ስንዴ የማትጠብቅ አገር እናደርጋታለን የሚል መረጃ ነው።
- ማንን ነው እንደዚያ ያለ አገር እናደርጋለን የሚሉት?
- ክልሉን ነዋ።
- የትኛውን ክልል ነው?
- የሰሜኑን ክልል።
- ማን ናቸው እንዲህ ያለውን ቅዠት የተናገሩት?
- የቀድሞው ጄኔራል ናቸው።
- የትኛው?
- የፌዴራል መንግሥት ኮርፖሬሽን ይመሩ የነበሩ ጄኔራል ናቸው።
- እ… እሳቸው ናቸው እንዴ?
- አዎ ክቡር ሚኒስትር፣ አይገርሙም?
- እሳቸው እንኳን እንደዚያ ማለታቸው አይገርምም።
- እንዴት አይገርምም ክቡር ሚኒስትር?
- አይገርምማ፡፡
- ለምን?
- እሳቸው ከዚህም በላይ ሊሉ ስለሚችሉ አይገርምም።
- ያንን ሁሉ የሕዝብ ሀብት እጥብ አድርገው በልተው መፀፀት ሲገባቸው እንዴት እንደዚያ ይናገራሉ?
- ለዚህ እኮ ነው የማይገርመው።
- ለምን?
- ስለሚመስላቸው ነዋ።
- ምንድነው የሚመስላቸው?
- ሌላ አገር ማቋቋም የሚያስችላቸው ይመስላቸዋል።
- ምኑ?
- ከዚህ እጥብ አድርገው የበሉት።
[ክቡር ሚኒስትሩ ወደ ቤታቸው ሲገቡ ባለቤታቸው በሽብርተኝነት ተጠርጥረው ስለተከሰሱ ሰዎች የሚተላለፈውን ዜና በተመስጦ እየተከታተሉ አገኟቸው]
- ምንድነው እንዲህ ተመስጠሽ የምታደምጪው?
- ሰበር ዜና ነው።
- ስለምንድነው?
- በሽብርተኝነትና የክልሉን መንግሥት በኃይል ለመጣል ተጠረጥረው ስለተያዙና ስለሚፈለጉ ሰዎች ነው።
- እ… ስለእሱ ነው እንዴ?
- አዎ፣ ታውቅ ነበር?
- እንኳን እኔ እነሱ ራሳቸውም የሚያውቁ ይመስለኛል።
- ይደንቃል፡፡
- በአሸባሪነት መጠርጠር የለባቸውም ብለሽ ልትሟገቺ ነው?
- እኔ ምኑን አውቄ እሟገታለሁ?
- ታዲያ ምንድነው ያስደነቀሽ?
- ሰዎችን በሽብርተኝነት መክሰስ ገና እንደተጀመረ ያነጣጠረው በአዲስ አበባ ዙሪያ ነበር።
- በአዲስ አበባ ዙሪያ ማለት?
- አዲስ አበባ የሚገኙ ፖለቲከኞችና ጋዜጠኞች ላይ ትኩረት በማድረግ ነበር የተጀመረው ማለቴ ነው።
- ልክ ነሽ፣ ያኔ የሚያስቸግሩት እነሱ ነበሩ።
- ከዚያ ወደ ሰሜን ሄደ።
- ወደ ሰሜን ማለት?
- ወደ ሰሜኑ ክልል።
- እ…
- ተቀናቃኞቻቸውን በሽብርተኝነት መክሰስ የጀመሩት እነሱ ነበሩ፣ በኋላ ግን ወደ እነሱ ዞረ።
- አይገርምም፣ ለካ እነሱም አልቀረላቸውም?
- አሁን ደግሞ ሌላኛው ሰሜን ተረኛ ይመስላል።
- ካልሽማ ወደ ምዕራብም ዘልቆ ነበር።
- ይህ እኮ ነው ድንቅ የሚለኝ።
- ምኑ?
- የሚሽከረከረው ነገር፡፡
- ምኑ ነው የሚሽከረከረው?
- ክሱ ነዋ?
- የሽብርተኝነት ክሱን ነው?
- ታዲያስ፣ ልክ እንደ እንትን አዲስ አበባ ጀምሮ አገሩን ሙሉ ሊያዳርሰው እኮ ነው?
- እንደ ምን?
- የህዳሴ ዋንጫ!
[ክቡር ሚኒስትሩ ወደ ቢሯአቸው ሲገቡ ጸሐፊያቸው ኮምፒዩተሯ ላይ አቀርቅራ አላየቻቸውም]
- ዛሬ ደግሞ ምን ሆነሻል?
- ውይ መጡ እንዴ! ክቡር ሚኒስትር? በሶሻል ሚዲያ የተለቀቀ ውይይት ቀልቤን ስቦት ስትገቡ አልሰማሁም፡፡
- የምን ውይይት ነው የምታዳምጪው?
- ያው የሰሜኑ ጉዳይ ነዋ?
- ሰሜኑ ደግሞ ምን ሆነ?
- የአፋኝ ታፋኝ ድራማው ቀጥሏል፡፡
- ማነው የታፈነው? ማነው ያፈነው?
- ታፋኙማ ለጥቂት አምልጧል፡፡
- አፋኙ ሆን ብሎ ትቶት እንጂ አምልጦ አይመስለኝም፡፡
- ለምን ሆን ብሎ?
- እንዳይመለስ ለማድረግ!
The post [ክቡር ሚኒስትሩ ወደ ቢሯቸው ሲገቡ አማካሪያቸው ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ በተመለከተው አንድ ጉዳይ ተገርሞ አገኙት] first appear on ሪፖርተር – Ethiopian Reporter – #1 Best and reliable news source in Ethiopia and is written by በጋዜጣዉ ሪፓርተር