በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል እየጨመረ በመጣው የነዋሪዎች ቁጥር ምክንያት የንፁህ መጠጥ ውኃ አቅርቦት ችግር ሆኖ መቀጠሉ ተገለጸ።
ከፍተኛ የማዕድን በተለይም የወርቅ ሀብት እንዳላት በሚነገርላት የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል፣ የንፁህ መጠጥ ውኃ አቅርቦት ችግር አሁንም ድረስ መቀጠሉን፣ በክልሉ የውኃና ኢነርጂ ቢሮ የዕቅድ ክትትልና ግምገማ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ፈንታሁን ባንቴ ለሪፖርተር ገልጸዋል።
ከ3‚500 በላይ የሚሆኑ የውኃ ተቋማት መኖራቸውንና ከእነዚህ ውስጥ በፀጥታ ችግር ምክንያት ከ500 በላይ የሚሆኑት ጉዳት እንደደረሰባቸው፣ አሁንም ድረስ ያልታደሱና አገልግሎት መስጠት ያልጀመሩ የውኃ ተቋማት መኖራቸውን ተናግረዋል።
በፀጥታ ችግሩ ወቅት ከ1‚500 በላይ የውኃ ተቋማት ጉዳት ደርሶባቸው እንደነበር የገለጹት አቶ ፈንታሁን፣ አክሽን አጌንስት ሃንገር ኢትዮጵያ (Action Against Hunger) የተሰኘውን የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅትን ጨምሮ፣ ሌሎች ድርጅቶችም ተረባርበው አብዛኞቹ የውኃ ተቋማት የማደስ ሥራ እያከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል።
ሆኖም ከ35 እስከ 40 በመቶ የሚሆነው የክልሉ ሕዝብ አሁንም ድረስ ንፅህናውን ያልጠበቀ የወንዝና የኩሬ ውኃ እንደሚጠቀም አስረድተዋል።
የክልሉ የሕዝብ ቁጥር በየጊዜው እየጨመረ መሆኑንና በተለይም በአሁኑ ወቅት ከሌሎች አጎራባች ከተሞች የተሻለ አንፃራዊ ሰላም በመኖሩ ከአራትና አምስት ዓመታት ወዲህ የሕዝብ ቁጥሩ ከፍተኛ በመሆኑ፣ የነባሩ ሕዝብ የውልደት መጠንም በመጨመሩ የውኃ አቅርቦት ፍላጎቱ ከፍተኛ መሆኑን ጠቁመዋል።
የአገር ውስጥ ተፈናቃዮች የሚያርፉበትን ቦታ የከተማ አስተዳደሩ እንደሚሰጥ፣ በካምፖች ውስጥ የሚኖሩ ተፈናቃዮች የሚጠቀሙባቸው የውኃና የጤና ተቋማት ለነዋሪው ማኅበረሰብ የተሠሩትን በመሆኑ ከፍተኛ ጫና መፍጠራቸውን አመላክተዋል።
From The Reporter Magazine
የተሠሩ የውኃ ተቋማትን በአግባቡ የመያዝ ችግር መኖሩን፣ በተለይም ከነበረው የፀጥታ ችግር አኳያ በማኅበረሰቡ ዘንድ የተሠሩትን የውኃ ተቋማት በአግባቡ የመያዝ ችግር እንደነበር አስረድተዋል። ሆኖም አሁን በአያያዝ ላይ የነበሩ ችግሮች መሻሻል ማሳየታቸውን ገልጸዋል።
ከካምፕ ውጪ በእርሻም ሆነ በጉልበት ሥራ ተሰማርተው የሚገኙ የአገር ውስጥ ተፈናቃዮች መኖራቸው፣ ይህም ለአካባቢው ነዋሪዎች ከፍተኛ ጫና የሚፈጥር መሆኑን አስረድተዋል።
የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች በክልሉ መኖራቸው ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው፣ በተለይም በውኃ ልማት ያላቸውን ድጋፍ አወድሰዋል።
From The Reporter Magazine
እንደ ክልል የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅት መረጃዎችን የሚከታተሉት እሳቸው በመሆናቸው፣ አክሽን አጌንስት ሃንገር እንደ አንድ አጋር በርካታ ሥራዎችን ፕሮጀክቶቹ ባሉበት ዞኖችና ወረዳዎች ሲያከናውን መቆየቱን ገልፀዋል።
ንፁህ ውኃ ለኅብረተሰቡ እንዲደርስ ከማድረግ አኳያ የተበላሹና አገልግሎት የማይሰጡ የውኃ ቧንቧዎችን በማደስና የውኃ ማከሚያ ኬሚካሎችን በማቅረብ፣ እንዲሁም የአቅም ግንባታ ሥልጠናዎችን እንደሚሰጥ ተናግረዋል። ከፍተኛ የፀጥታ ችግር ባሉባቸው አካባቢዎች ሳይቀር ሥራዎችን እንደሚያከናውኑ ገልጸዋል።
እስካሁን የሚሠራው የወደሙትንና አገልግሎት መስጠት ያቆሙት የማደስ ሥራ መሆኑን፣ ነገር ግን የውኃ ፍላጎት በክልል ደረጃ ከፍተኛ በመሆኑ ይህን ማሟላት ስላልተቻለ በአዳዲስ የውኃ ፕሮጀክቶች ላይ ትኩረት እንዲደረግ አሳስበዋል።
