በተሾመ ብርሃኑ ከማል
(ክፍል አንድ)
ከሚያዚያ 2 ቀን 2016 ዓ.ም. ጀምሮ በአክሱም ሙስሊሞች ላይ ሕገወጥ ድርጊት እየተፈጸባቸው መሆኑን አክሱማውያን ሙስሊሞች፣ የትግራይ ክልል እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ጉባዔ (መጅሊስ)፣ የትግራይ ወጣቶችና አንዳንድ የዳያስፖራ እስላማዊ ድርጅቶች ለዓለም ድምፃቸውን እያስተጋቡ ነው፡፡ ለምሳሌ ሚያዝያ 18 ቀን 2018 ዓ.ም. በመቐለ ከተማ ከሚገኙ ከ15 በላይ መስጊዶች የተወከሉ የከተማዋ ሙስሊም ነዋሪዎች፣ በአክሱም ሙስሊም ወንድሞቻቸውና እህቶቻቸው ላይ እየደረሰ ያለውን በደል አስመልክቶ ሰፊ የውይይት መድረክ አካሂደዋል። በውይይቱ ላይ በአክሱም ከተማ አስተዳደርና በሃይማኖት መሪዎች የተላለፉት ውሳኔዎች በኢትዮጵያና በትግራይ ክልል ሕገ መንግሥታት የፀደቂ መሠረታዊ መብቶችን የሚጥሱ መሆናቸው በዝርዝር ተገምግሟል። ማኅበረሰቡም በአክሱም ሙስሊሞች ላይ እየደረሰ ያለው ግፍ እጅግ እንዳሳዘነውና ድርጊቱንም በፅኑ እንደሚኮንን በቁጣ ገልጿል። በትግራይ የእስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት የተጀመረው ይህ የተቃውሞና የውይይት መድረክ በሁሉም የትግራይ ዞኖችና አካባቢዎች ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አቅጣጫ ተቀምጧል።
መረጃዎች እንደሚያመለክቱት በሕግ አካላትና በግለሰቦች ማን አለብኝነት ጥቃት እየደረሰባቸው ቢሆንም በመንግሥት በኩል የተሰጠ ምላሽ ወይም የተወሰደ የመፍትሔ ዕርምጃ የለም፡፡ ለምን? ለዚህ ጥያቄ አጥጋቢ መልስ ባይገኝም በሁለቱም ወገን ‹‹በአክሱም ውስጥ የሙስሊሞች መብት ይከበር›› በሚሉና ‹‹አክሱም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ክርስቲያን ቅድስት ከተማ ስለሆነች የሙስሊሞች መስጊድ ሊሠራባትም፣ የአዛን ድምፅ ሊሰማባትም፣ ኢስላማዊ ተግባራት ሊከናወኑባትም›› በሚሉ (በሙስሊሙና በክርስቲያኑ ኤሊት) ጉዳዩን ዓለም አቀፍ ትኩረት እንዲያገኝ እየተሞከረ ነው፡፡ በመሠረቱ፣ እንደዚህ ዓይነቱ ክስተት በአማካይ በየ አሥር ዓመቱ የሚከሰት ሲሆን ይህም ክስተት በ1970ዎቹ፣ በ1980ዎቹ፣ በ1990ዎቹ፣ በ2000 ብለን ከፍለን ልንመለከተው እንችላለን፡፡ በዚህም መሠረት በ1970ዎቹ ሙስሊሞች ያለባቸውን ችግር ለማሳወቅ ሰፊ ሠላማዊ ሠልፍ አድርገው ደርግን የጠየቁበት፣ በ1980ዎቹ የኢሕአዴግ መንግሥት የሙስሊሞችን እንዲያስከብር የጠየቁበት፣ በ1990ዎቹ የኢሕአዴግ መንግሥት በኢስላም ላይ ጣልቃ መግባቱን እንዲያቆም የጠየቁበት፣ በ2000 መንግሥት በሙስሊሞች የአስተምህሮት ልዩነት ጣልቃ እንዳይገባ በተናጠል የጠየቁበት፣ በ2010ቹ የአክሱም ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ሴት ተማሪዎች ሒጃብ ለብሰው ትምህርት ቤት እንዳይገቡ የተደረገባቸው ክልከላ የሚመለከት ነው፡፡ ነገሩ ከኢትዮጵያ ታሪክ አኳያ ጠቃሚ ስለሆነ ካለፈው ዓመት ጀምሮ እንመልከተው፡፡
የአክሱም ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ሴት ተማሪዎች ሒጃብ
ባለፈው ዓመት ከታኅሳስ 9 እስከ ጥር 13 ቀን 2017 ዓ.ም. የአክሱም ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ሴት ተማሪዎች ሒጃብ አድርገው እንዳይገቡና እናዳይማሩ በመከልከሉ ምክንያት ልዩ ልዩ እንቅስቃሴዎች በማኅበራዊ ሚዲያዎች ብቻ ሳይሆን በፕሬስና በኤሌክትሮኒክስ ሚዲያዎች የተቃውሞ እንቅስቃሴ ሲደረግ ቆየቷል፡፡ በዚህ እንቅስቃሴ የታወቁ አክቲቪስቶችና የዜና አውታሮች ተሳታፊ ሆነዋል፡፡ ይህ የአክሱም ሴት ተማሪዎች ሒጃብ ለብሰው እንዳይገቡ ክልከላ ክልላዊ ብቻ ሳይሆን ብሔራዊ መልክ ይዟል፡፡ በዚህ ጽሑፍ ትኩረት የሚደረገው በርዕሱ እንደተጠቀሰው የአክሱም ሴት ተማሪዎች ሒጃብ እንዳይለብሱ ክልከላ፣ ሕመሙ ራሱ ወይስ የሕመሙ ምልክት ነው? የሚለው በአጭር በአጭሩ ይቀርብና ስለሕመሙ፣ ስለሕመሙ ምልክቶችና ሕመሙን ለማዳን ምን መደረግ እንዳለበት ይቀርባል፡፡
ታኅሳስ 9 ቀን 2017 ዓ.ም. ሀሩን ሚዲያ የአክሱም ተምሪዎች ሒጃብ አድርገው እንዳይገቡ መከልከላቸውን ዘገበ፣ ታኅሳስ 15 ቀን 2017 ዓ.ም. ‹‹ተደራራቢ በደል በአክሱም ሙሰሊሞች›› በሚል ርዕስ በማሜ ሙሳ የተባለ አክቲቪስት ተጻፈ፡፡ ታኅሳስ 16 ቀን 2017 ‹‹ተክቢራ ሚዲያ›› የሙስሊም ሴቶች ከትምህርት ማባረር ለትግራይ ትልቅ ውድቀት ነው በሚል ርዕስ አስተላልፏል፡፡ ይህንን 4.1 ሺሕ ተመልካቾች ተመልክተውታል፡፡ ታኅሳስ 16 ቀን 2017 ዓ.ም. RN05 የተባለ የውጭ አገር ሚዲያ ‹‹አክሱም መስጂድ ብቻ ሳይሆን ሒጃብንም ማየት ተጠይፋለች›› በሚል ርዕስ ጽፏል፡፡
From The Reporter Magazine
ከፖለቲካ ድርጅቶች መካከል ‹‹ብሔራዊ ባይቶና ፓሪቲ›› ታኅሳስ 16 ቀን 2017 ዓ.ም. ሙስሊም ሴት ተማሪዎች ሃይማታዊ ክብራቸው ተጠብቆና መብታቸው ተከብሮላቸው የመማር ነፃነታቸው ሊሰጣቸው እንደሚገባ ገልጿል፡፡ ሐሩን ሚዲያ ታኅሳስ 16 ቀን 2017 ዓ.ም. ባይቶና ያስተላለፈውን መግለጫ አድንቆ አውጥቷል፡፡ የነፃነትና እኩልነት ፓርቲ (የትግራይ ቅርንጫፍ) ታኅሳስ 17 ቀን 2017 ዓ.ም. የአክሱም ከተማ ሙስሊም ተማሪዎች በሒጃባቸው ምክንያት ከትምህርት ገበታ መታገዳቸውን የሚያወግዝ መግለጫ አውጥቷል፡፡
ከሲቪል ማኅበራት መካከል ታኅሳስ 18 ቀን 2017 ዓ.ም. መቀመጫውን አሜሪካ አገር ያደረጉት ሂጅራና በድር የአክሱም ከተማ ሙስሊም ተማሪዎች በሒጃባቸው ምክንያት ከትምህርት ገበታ መታገዳቸውን የሚያወግዝ መግለጫ አውጥተዋል፡፡ የትግራይ አስልምና ጉዳዮች ምክር ቤትም ታኅሳስ 16 ቀን 2017 ዓ.ም. ሙስሊም ሴት ተማሪዎች ከሒጃብ መልበስ ጋር በተያያዘ ውዝግብ ከትምህርት ገበታ ውጭ ሆነው እንደሚገኙ ማስታወቁ ተነገረ፡፡
የትግራይ መጅሊስ ከትምህርት ገበታቸው የታገቱ የአክሱም ከተማ ሴት ሙስሊም ተማሪዎችና ወላጆቻቸውን ለስብሰባ መጥራቱን ታኅሳስ 22 ቀን 2017 ዓ.ም. ሀሩን ሚዲያ አስታውቆ ችግሩ በሦስት ቀናት ካልተፈታ ከሕዝብ ጋር በመነጋገር ሰላማዊ ትግል የሚደረግ መሆኑን አሳወቀ፡፡
From The Reporter Magazine
ጥር 6 ቀን 2017 ዓ.ም. የአክሱም ወረዳ ፍርድ ቤት የአክሱም ከተማ ሴት ሙስሊም ተማሪዎች ሒጃብ ለብሰው ትምህርት ቤት መከልከላቸውን አስመልክቶ ተማሪዎቹ ሒጃብ ለብሰው እንዳይገቡ ያደረገውን ክልከላ የክስ ሒደቱ ውሳኔ እስኪያገኝ ወይም ተለዋጭ ትዕዛዝ እስኪሰጥ ድረስ የተላለፈው አስተዳደራዊ ውሳኔ እንዲታገድ አዟል። በተጨማሪም ተከሳሾች ጥር 16 ቀን 2017 ዓ.ም. በአካል ችሎት ተገኝተው በቃል ሐሳባቸውን እንዲያቀርቡ ፍርድ ቤቱ አዟል::
የትግራይ ክልል ትምህርት ቢሮ የአክሱም ከተማ ሴት ተማሪዎች በሒጃብ ምክንያት ከትምህርት ገበታ ውጪ የተደረጉ ተማሪዎች ቀድሞ ለብሰው ይማሩበት በነበረው ሥርዓት ማለትም ሒጃብ ለብሰው ወደ ትምህርት ገበታ እንዲመለሱ ለአክሱም ከተማ ትምህርት ጽሕፈት ቤት በጻፈው ደብዳቤ ገልጿል። ቢሮው በጻፈው ደብዳቤውም ‹‹በከተማችሁ ከሴት ሙስሊም ተማሪዎች የአለባበስ ሥርዓት ጋር ተያይዞ የተፈጠረው ችግር በአጠቃላይ የመማር ማስተማር ሒደት ላይ ያሳደረውንና ለቀጣይ ሊፈጥረው የሚችለው አሉታዊ ተፅዕኖ ግምት ውስጥ በማስገባት መንግሥት ችግሩን በስምምነት ለመፍታት የተለያዩ ጥረቶችን እያደረገ ነው፤›› ብሏል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የትግራይ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት በሒጃብ ምክንያት ከትምህርታቸው የተገፉ ተማሪዎችን አስመልክቶ በመጪው ማክሰኞ በመላው ትግራይ ሠላማዊ ሠልፍ ያካሂዳል።
ጥር 20 ቀን 2017 ዓ.ም. የትግራይ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት የሃይማኖት ተቋማት ጉባዔ፣ የትግራይ ሕዝብ ግንኙነት፣ የትግራይ ሲቪክ ማኅበራት፣ የትግራይ ሴቶች ቢሮ፣ የሕወሓት ጽሕፈት ቤት በክልሉ የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች በአክሱም ከተማ ሴት ተማሪዎች ላይ የተደረገውን የሒጃብ ክልከላ በሚመለከት አቋማቸውን እንዲያሳውቁ ጠየቀ፡፡ ጥር 13-14 ቀን 2025 ሒጃቧን ትለብሳለች ትምህርቷንም ትማራለች የሚል መፈክር መስተጋባት ጀመረ፡፡ የክልሉ መጅሊስ መር ሠላማዊ ሠልፈኞቹ አቤቱታቸውን ለማሰማት ወደ ክልሉ ጊዜያዊ መስተዳድሩ ሄዱ፡፡ አስተዳዳሪውም ሁኔታው አሳዛኝ ክስተት መሆኑን አውስተው እንደሚታረም ቃል ገቡ፡፡
ጉዳዩ በርካታ መደበኛ ሚዲያዎችንና ማኅበራዊ ሚዲያዎችን የሳበ ስለነበር እንደዬ አመለካከታቸው አስተያየታቸውን የሰጡ ሲሆን ጥር ርዕዮት ሚዲያ 15 ቀን 2025 ሙስሊም ምሁራንን በመጋበዝ አስተያየት እንዲሰጡና በሰፊው እንዲተነትኑ ዕድል ሰጥቷዋል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ኦሪያ ሚዲያ የተባለ ዮናስ ገብረሚካል የተባለ ለረዥም ጊዜ ኖርዌይ የነበረና ሕወሓት ከመንግሥት ጋር ያደረገውን ፍልሚያ ለመቀላቀል የመጣ ዲያስፖራ ችግሩ አገራዊ ሳይሆን የውጭ እጅ እንዳለበት ለማሳየት ሞክሯል፡፡ ነጃሺን ለመጎብኘት የሄዱ የውጭ ዜጎችንም እንደ ምክንያት ለመጥቀስ ሞክሯል፡፡ ዮናስ ገብረሚካል ‹‹ያንን ሠላማዊ ሠልፍ ለማዘጋጀት መቀሌ ውስጥ ሆቴል ተከራይተው ለአንድ ወር የተቀመጡ ነበሩ፡፡ እነዚህ ሰዎች ከእነማን ጋር እንደተገናኙ ተገናኝተውም ምን እንደተነጋገሩና ሠልፉ ከመደረጉ በፊት አንድ ቀን ቀደም ብለው ወደ አዲስ አበባ እንደተመለሱ እናውቃለን፡፡ የአሁኑ የሒጃብ ጥያቄ ትግራይ ባለችበት ሁኔታ ኢምንትም ቅጦትም ነው፡፡ ከእነሱ ጋፈክር ሥር ተሠልፎ ለሦስት ተከታታይ ቀናት ሠላማዊ ሠልፍ ሲደረግ ፊታቸው ያልታየ ሙስሊም አመራሮች በዚህ መታየታቸው የጥያቄያቸው ዴሞክራሲያዊነት አጠያያቂ ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ ትልቅ ብሔራዊ ጉዳዮች እያሉ ሒጃብ ካላደረግን ብሎ ማወክ ተገቢ አይደለም፡፡ ለመሆኑ እነዚህ ልጆች በቤታቸው መብታቸው ይከበራል ወይ? 12ኛ ክፍል ብትጨርስ እኮ አሳሪ የሆነ የሸሪዓ ሕግ ስላለ ትምህርቷን እንድትቀጥል አያደርጋትም፡፡ ሸሪዓ የሴትን ልጅ አንቆ የሚያዝ ስለሆነ መብቷን አያስከብርላትም፡፡ ለምሳሌ አንድ ሙስሊም ሁለት ሦስት ሚስት እንዲያገቡ ያዛል፡፡ ሆኖም ብትፋታ አንዲት ዕቃ ይዛ እንድትወጣ አይፈቅድላት፡፡ እኔ ነኝ የሷን መብት የምከላከልላት እኔ ነኝ፡፡›› ያለው ዮናስ ገሚካኤል ‹‹ይህ ሠልፍ በሒጃብ ከለላ የቀረበ እንጂ የሒጃብ ጉዳይ አደለም፡፡ ‹‹የሒጃብ ጥያቄ አንስተው ሆ የሚሉት ሰዎች ራሳቸው በቤታቸው ሴቶችን ጨቋኞች ናቸው፡፡ ሴቶቻቸውን እየጨቆኑ በአደባባይ ሆ ማለት እኔ አላምንበትም፡፡›› ይላል፡፡ ዮናስ አክቲቪስት ሲሆን ለብዙ ዓመታት ኖርዌይ የኖረ ነው፡፡ ዮናስ ‹‹ሙስሊሞች ከእኛ ጋር ብዙ ኖረዋል፡፡ አሁንም እየኖሩ ነው፡፡ አብረውን መኖር ይቀጥሉ›› ባይ ነው፡፡ ለመሆኑ አብረውን ኖረዋል ማለት ምን ማለት ነው?
ዮናስ ገብረሚካኤል የተባሉት ግለሰብ ኢስላምን ባልተረዱበትና ባላወቁት መንገድ ገብተው ሸሪዓውን ሲያንቋሽሱ እናገኛቸዋለን፡፡ የትግራይን ወቅታዊ ሁኔታ ሽፋን ለማድረግ ክርስቲያኖች ለትግራይ ሲዋደቁ ሙስሊሞች አሁን ደርሰው መብት ጠያቂ ሆነው ቀረቡ በማለት ያላቸውን ንቀት በደም ፍላት ይገልጻሉ፡፡ ሙስሊሞች እኛ ጋር ኖረዋል ሲሉ የገለጡት የእሳቸውን አስተሳሰብ ብቻ አይደለም የራሳቸውን አቋም አይደለም፡፡ አባቶቻቸውም ‹‹እስላም አገሩ መካ፣ አሞራ ማደሪያው ዋርካ›› ብቻ ሳይሆን ‹‹እስላም አገር የለውም ሰማይ አምድ የለውም›› ይሉ ከነበረው በቀጥታ ተቀብለው ነው፡፡ ይህን በሚመለከት በራሱ ርዕስ ሥር በዚህ ጽሑፍ አቀርበዋለሁ፡፡
አቡነ ሰላማ (ኣባ ሰረቀብርሃን) ሒጃብ ክልከላን በተመለከተ የሰጡት አስተያየት
አቡነ ሰላማ (ኣባ ሰረቀብርሃን) በትግራይ ቴሌቪዥን የአክሱም ሴት ተማሪዎች ሒጃብ መከልከላቸውን በሰጡት ተግሳጽ የተመላበት አስተያየት ‹‹(የኢትዮጵያ እስልምና ምክር ቤት) የትግራይ ሕዝብ ከዓረብ አገሮች በመጡ፣ ከኤምሬትስ በመጡ፣ ከቱርክዬ በመጡ ዱሮኖች ሲጨፈጨፍ የት ነበር? ትግራይ ውሰጥ ያላችሁ የእስልምና ተከታዮች የሆናችሁ የወንድሞቻችን ልጆችስ? ምክር ቤት ያላችሁ ሙስሊሞችስ መከራ አልጠገባችሁም እንዴ? ትናንት እስልምና ምክር ቤት ክዶናልና አይወክለንም ብላችሁ ከእኛ ጋር አልነበራችሁ? ምክር ቤታችን የለም ተሳስተሃል እኛ እንነጋገርበታለን ብሎ መግለጽ ነው የሚቀድመው ወይስ ግፍ እየደረሰብን ነው እያላችሁ መግለጽ? ለመሆኑ እናንተ የበላይ የምትሉት ምክር ቤት በትግራይ ሕዝብ ላይ፣ በሙስሊሙ ላይ፣ በኦርቶዶክሱ ላይ ያ ግፍ ሲፈጽም ከእኛ ጋር እያለቀሳችሁ ለእሱ ሳይቀር ግፍ ነው ስትሉ አልነበረም? ለመሆኑ ሒጃብ ይልበሱ ነው የሚቀድመው ወይስ ሕዝብ ሲጠፋ?›› በማለት የፌዴራሉን የእስልምና ምክር ቤት ወቅሰዋል፡፡
አቡነ ሰላማ (ኣባ ሰረቀብርሃን) ከዚህም በተጨማሪ፣ ‹‹የአልነጋሺ መስጊድ በዓለም፣ ከአፍሪካ ከዚያ ከምትመኩበት ከመካ ቀጥሎ ትልቅ የሆነ፣ ታሪካዊ መስጊድ በመድፍ ሲፈርስ፣ ደብረዳሞ እንደዚያ ሲሆን፣ ይህ ሁሉ ሲሆን ትንፍስ ያላለ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳይ ምክር ቤት አሁን ተነስቶ መብታቸው ተገፏል፣ የኢትዮጵያ መንግሥት፣ የዓለም አቀፍ መንግሥታት እርዱን፣ ድረሱልን ማለት ምን አመጣው? ምክር ቤቱኮ (የፌዴራል እስልምና ጉዳዮች) በሒጃብ ሽፋን መቃብር የላቸውም፣ መስጊድ የላቸውም፣ ነፃነት የላቸውም ወደሚል ቀይሮ ይፋ አድርጎታል።›› ካሉ በኋላ ይፋ ባደረጉት ዕቅድ ‹‹አክሱም እንደ ቫቲካ ራሷን የቻለች እንድትሆን የሚደረገው ጥረት ደግሞ ለሙስሊም፣ ለካቶሊኩም ለሌላውም ነው እንጂ ለኦርቶደክሱ ብቻ አይደለም። አክሱም ውስጥ የካቶሊክም፣ የሙስሊምም፣ የሌላም (የፕሮቴስታንትም) የለም። ይህም ማለት በአክሱም ከተማ የለም ለማለት እንጂ ዳርዳሩ ማለትም ከአየር መንገዱ አልፎ፣ ዓድዋ የለም ማለት አይደለም። ይህም ለሕዝቡ፣ ለመላው ኢትዮጵያ የሚጠቅም እንጂ አክሱም ልዩ ጥቅም የምታገኝበት አይደለም። የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን (እምነቱን አልከለከለም) እንዳይሠራ የተከለከለው መስጊድ ብቻ ነው?›› ብለዋል፡፡
አቡነ ሰላማ በስም ባይጠሩትም አክሱም በተለያየ ጊዜ ጥቃት እንደደረሰባት ጠቅሰው ይህም ሙስሊሙ ኅብረተሰብ እንደሚያውቅ አስገንዝበዋል፡፡ አባ ሰላማ ንግሥተ ነገሥታት ዮዲትን ወይም ኢማም አሕመድ ኢብራሂም አልቓዚን በስም ሳይጠቅሱ አልፈውታል፡፡
አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች ግን አቡነ ሰላማ (ኣባ ሰረቀብርሃን) አክሱም እንደ ቫቲካን ነፅ ለማድረግ በሚደረገው ጥረት እንደ ቫቲካን በራሷ ሕገ መንግሥትና በንቡረዕድ የምትተዳር ነፃ አገር ለማድረግ ከሆነ የኢትዮጵያና የትግራይ ሕገ መንግሥቶች መቀየር ሲኖርባቸው ራሷም በራሷ ሕገ መንግሥት የምትመራና በራሷ በጀት የምትተዳደር መሆን ይኖርባታል፡፡ በአክሱም መንግሥትና በኢትዮጵያ መንግሥት መካከልም ልዩ ስምምነት መኖር አለበት፡፡ ይህ በሌለበት ሁኔታ ምናልባት በአፈርሜቲቭ አክሽን ልዩ ክልል ሆና ብትተታደር ነገሩ አስቸጋሪ መሆኑን ያስገነዝባሉ፡፡
- እንዲህ ያለ ችግር ከመቼ ጀምሮ ተከሰተ?
የክርሲቲያን ኢትዮጵያውያንና የሙስሊም ኢትዮጵያውያን ልሂቃን ግጭት የተጀመረው በአፄ ቴዎድሮስ ዘመን ሲሆን ለዚህ እንደ ምሳሌ የሚጠቀሱት አባ ሰላማ ናቸው፡፡ እኒህ ጳጳስ ለዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ መከሩ የሚባሉት አገርህን በሰላም አስተባብረህ ለመግዛት የምትፈልግ ከሆነ ሁሉንም በአንድ ሃይማኖት ግዛ ብለው ይመክራሉ፡፡ ቴዎድሮስ በጅምር ላይ እያሉ ሲሞቱ አፄ ዮሐንስ አራተኛ ሥልጣን ላይ ይወጣሉ፡፡ እሳቸውንም ተመሳሳይ ምክር ሰጧቸው፡፡ አፄ ዮሐንስም ምክሩን ሰምተው ‹‹ይህች አገር የክርስቲያን አገር ናት፡፡ ክርስቲያን ያልሆንክ ከአገሬ ውጣልኝ›› ከዚያ ጊዜ ጀምሮ የክርስቲያን አገርም የክርስቲያን ደሴትም ሆነች፡፡ የአክሱም ቫቲካንን የመሆን ምኞት የሚመነጨውም ከዚሁ ነው፡፡
- የመስጊድ ዕገዳ በአክሱም በተመለከተ ቢቢሲ እንደዘገበው
ቢቢሲ የተሰኘው የዜና ወኪል እ.ኤ.አ. ሰኔ 24 ሰኔ 2019 ‹‹የመስጊድ ዕገዳ፡ የተቀደሰች ከተማችን አክሱም ልትጠበቅ ይገባል›› በሚል ርዕስ በሃና ዘራፅዮን ዘጋቢነት ባጠናከረው ዜና መዋዕል ‹‹ታቦቱ ለሙሴ ከእግዚአብሔር የተሰጣቸውን አሥር ትዕዛዛት እንደ ያዘ የሚታመን ሲሆን በከተማው ውስጥ ባሉ መነኮሳት ጥበቃ ሥር ይገኛል። ይህም ሆኖ አንዳንድ የሙስሊም ቡድኖች ‹‹ፍትሕ ለአክሱም ሙስሊሞች›› በሚል ባንዲራ በመሰባሰብ በከተማዋ መስጊድ የመሥራት መብት እንዲከበርላቸው በመጠየቅና የፀሎት ጥሪያቸውን በማሰማት ላይ ይገኛሉ – ‹‹አላህ ታላቅ ነው›› በማለት በከተማዋ መስጊድ ለመገንባት ዘመቻ እያካሄዱ ነው – ይህ ሐሳብ በክርስቲያን መሪዎች ተቀባይነት የለውም በአክሱም ከተማ መስጊድ ተገንብቶ ከምናይ መሞትን እንመርጣለን፡፡ መስጊድ ለመሥራት የሚመጣ ካለ እንሞታለን። ከዚህ በፊትም ፈጽሞ አልተፈቀደም፡፡ በእኛ ዘመን እንዲከሰት አንፈቅድም›› ማለታቸውን አቅርባለች፡፡ ሃና ዘርዓጽዮን ‹‹አክሱም መካችን ናት ያሉት ከፍተኛ የሃይማኖት አባት አቶ ጎደፋ መርሐ፣ በእስልምና ቅድስና ቦታ ላይ አብያተ ክርስቲያናት እንደታገዱ ሁሉ በአክሱም መስጊዶች ሊኖሩ አይችሉም ብለው ያምናሉ። ጎደፋ መርሐ የተባሉ የአክሱም ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ምክትል ኃላፊ ደግሞ ‹‹አክሱም ቅዱስ ቦታ ነው ይህች ከተማ ገዳም ናት›› ሲሉ ተናግረዋል።
- አንዳንድ ጸሐፍት
በሃይማኖቶች መካከል ለሚፈጠረው ልዩነት አንደኛው ምክንያት ሆን ብሎ ልዩነት ለመፍጠር ሲባል የሃይማኖት መጻሕፍት አጣምሞ በመተርጎም ነው፡፡ በዚህም መሠረት በቁርዓን ላይ (በዓለም ደረጃ) ተጣሞ የተጻፈውን ብንመለከት ብዙ ነው፡፡ የፈረንጆቹን ትተን በአገራችን ከ2000 ወዲህ የተጻፉትን አራት መጻሕፍት ለአብነት ብንጠቅስ፣ አባ ዘሐቅሌ ዋሊ «ታሪክህንና ሃይማኖትህን እወቅ» (ኅዳር 2001)፣ አባ ሳሙኤል «በኢትዮጵያ የሃይማኖት መቻቻል አለን?» (ሚያዝያ 2000)፣ ኤፍሬም እሸቴ «አክራሪ እስልምና በኢትዮጵያ» (2000)፣ ዲያቆን አይቸው ወርቅነህ «አዬ ጉድ ቁርአኑን አይተውታልን?» የሚሉትን ማቅረብ ይቻላል፡፡ ከእነዚህ መጻሕፍት መካከል ምንም እንኳን ቁርዓኑን ያለምሕረት አጣሞ የተረጎመ ቢሆንም መቻቻልን ከራሱ አኳያ የተቀበለ የሚመስለው የመጀመሪያው ሲሆን የመጨረሻው ደግሞ ስም አጥፊ ብቻ ሳይሆን በጭፍን ጥላቻ ክርስቲያኑ ጦሩን ሰብቆ በሙስሊም ወንድሙ ላይ እንዲነሳ የሚቀሰቅስ ነው፡፡ ከቀረቡት መካከል በጣም የሚያሳዝነው ደግሞ በአባ ሳሙኤል በታላቁ የሃይማነኖት አባት የተጻፈው ነው፡፡ በዚህ መጽሐፍ አንዱን የበላይ ሌላውን የበታች ማድረጋቸውን ሁሉንም እኩል ለሚያይ ፈጣሪ እንተውና አንድ አዲስ አበባ ውስጥ የሚገኝ ቤተ ክርስቲያን በተለይም እሳቸው አዘውትረው የሚገኙበት የቅድስት ማሪያም ቤተ ክርስቲያን ብቻ ምን ያህል ሔክታር መሬት እንደ ያዘ ሲያወሳ ከ1983 ዓ.ም. ወዲህ የተሠሩት መስጊዶች ብዛት ቁጭት በተመላበት ሁኔታ ተጽፎ መገኘቱ ነው፡፡ ይህ መጽሐፍ ከትልቅ የሃይማኖት አባት የቀረበ በመሆኑ፣ አብያተ ክርስቲያናት የተሠሩበት ቦታ መንግሥት ወይም የሁሉም ሕዝብ መሬት ላይ መሆኑን ከግምት ውስጥ ማስገባት አይፈልግም፡፡ ለስንት ዓመታት ከሌላው ሃይማኖት የላቀ ሰፊ ቦታ እንደያዘም ጉዳዩ አይደለም፡፡ ነገር ግን የያዝኩት በቂ አይደለምና ይጨመርልኝ ባይ ብቻ ሳይሆን ሌሎቹ ለምን በአገራቸው የአምልኮ ቤት የሚሠሩበትን ቦታ ያገኛሉ? ሥጋቶቼ ናቸውና መንግሥት ያስብበት፣ በማለት ራሱን ብቻ ዋና የመንግሥት ሕልውና ተቆርቋሪ አድርጎ ያቀርባል፡፡ ለመሆኑ ለሰው ምን ያህል መሬት ይበቃዋል?
በመሠረቱ መስጊድ ስለበዛ ወይም የቤተ ክርስቲያን ቁጥር በከፍተኛ ደረጃ ስለጨመረ ወይም ሰፊ ቦታ ስለያዘ እምነቱ ያንን ያህል ጠንካራ ይሆናል ብሎ ማሰብ የዋህነት ነው፡፡ የቤተ እምነት ውበትም አማኝን እንደማይፈጥር በአውሮፓ፣ በአሜሪካና በካናዳ ከሚገኙትና አፋቸውን ከፍተው ከሚውሉት እጅግ ውብ ቤተ መቅደሶች መመልከት ይቻላል፡፡ ለመሆኑ የመስጊድ ወይም የቤተ ክርስቲያን መብዛት ወይም ማማር አማኞችን በማብዛት በዕውቀት ላይ የተመሠረተ መቻቻል ሊፈጠር ይችላል? ስለዚህ መቻቻል ከምን ይጀምራል? ማንስ ይጀምረዋል? እንዴትስ ይጀምራል? የሚሉ ጥያቄችን በጋራ ለመመለስ ጥረት ማድረግ ይጠበቅብናል፡፡
- አቡነ ጳውሎስ ‹‹ጥገኝነት ብንሰጣቸው መግዛት አማራቸው››
በ2013 ዓ.ም ወጣት ኢትዮጵየውያን ሙስሊሞች በ‹‹ድምፃችን ይሰማ›› መፈክር የእኩልነት መብት እንዲከበር በጠየቁበት ጊዜ የሰጡት አባታዊ መግለጫ ‹‹(ሙስሊሞች) ጥገኝነት ብንሰጣቸው መግዛት አማራቸው›› የሚል ነበር፡፡ እኚህ በስደት አሜሪካ የኖሩ አባት በኖሩበት አገር ዜግነት ያለው ሰው የመንግሥት የሥልጣን ተካፋይ፣ በሚመጥነው ደረጅ የአሜሪካ ምክር ቤት አባል፣ በሕግ መወሰኛ ምክር ቤትና በአስፈጻሚው ምክር ቤት የሕዝብ ወኪል ሆኖ እንደሚኖር በሚገባ ያውቃሉ፡፡ ሆኖም እንደ እሳቸው በኢትዮጵያ አፈር የተሠራውን ፈጣሪ ለኢትዮጵያ የሰጣትን የተፈጥሮ ፀጋ ተካፍሎ የሚኖረውን፣ እንደ እሳቸው አገሬ ወገኔ የሚለውን ሙስሊም ‹‹ጥገኝነት ብንሰጣቸው መግዛት አማራቸው›› በማለት የቤተ ክርስቲያኗን አቋም ገለጹ፡፡ አገላለጽ ጅምላ እንኳን ቢሆን የተቃወመው ስላልነበረ እንደ ጋራ አቋም የሚታይ ነው፡፡
- የአቶ ተክለ ፃድቅ መኩሪያ ማስጠንቀቂያ
አቶ ተክለ ፃድቅ መኩሪያ ብዙ የታሪክ መጻሕፍትን ያበረከቱ ታላቅ ኢትዮጵያዊ ናቸው፡፡ እኚህ ሰው ካበረከቱልን መጻሕፍት አንዱ ‹‹የግራኝ አሕመድ ወረራ›› በሚል ይታወቃል፡፡ መጽሐፉ በፈረንሣይ ቤተ መጻሕፍት ቁጭ ብለው የጻፉት ከመሆናቸውም በላይ እነሬኔ ባሴ ፉቱሑል ሐበሽንና የፖርቱጋል ጸሐፍትን ሥራዎች በመቀላቀል ያዘጋጁትን የራሳቸውን አስተያየታቸውን በሰፊው ጨምረው ለንባብ አብቅተውታል፡፡ ከጨመሩት አስተያየትም ብዙ መረጃዎችን እናገኛለን፡፡ በዚህ ጽሑፍ ለማቅረብ የተፈለገው ግን መጽሐፉን የጻፉትና ለንባብ ያቀረቡት ሰለሞናዊው ክርስቲያን መንግሥት (እንደ ግራኝ) ያለው ጠላት መናቅ እንደማይገባውና በንቃት መጠበቅ እንደሚገባቸው ለማስጠንቀቅ መሆኑን በመግቢያው ላይ ደጋግመው ያስጠነቅቃሉ፡፡ አቶ ተክለ ፃድቅ መኩሪያ የወላስማ መንግሥትም ከዓረብ የመጣ (መጤ) መሆኑና እስኪያንሰራራ ድረስ መጠበቅ እንዳልነበረበት አስተያየታቸውን ይሰጣሉ፡፡ አቶ ተክለ ፃድቅ መኩሪያ በጻፉት ትልቅ መጽሐፍ የነገሥታቱን ድክመት በማውሳት መጪው ትውልድ ንጉሠ ነገሥቱንና የክርስቲያን አገር የሆነችውን ኢትዮጵያን እንዲጠብቅ ያሳስባሉ፡፡
- ችግሩ ሥር የሰደደ ስለ መሆኑ ሐጅ በሽር ዳውድ አገላለጽ፣ ‹‹በሕይወቴ ሒደት ዙሪያ›› ከገጽ 37-38፣ በ2002፡፡
ሐጅ በሽር ዳውድ ‹‹በሕይወቴ ሒደት ዙሪያ›› በሚል ርዕስ በ2002 ለኅትመት ባበቁት ሥራቸው (ከገጽ 37-38) እንደሚከተለው ይገልጹታል፡፡
‹‹በማስታወቂያ ሚኒስቴር ተቀጥሬ ከ12 ዓመታት በላይ ስሠራ፣ ‹እስላም ነው፣ እስላም ተበድሏል ይላል፣ የኢትዮጵያ ጠላት ነው›› በማለት በዲግሪዬ መሠረትም ሆነ በአገልግሎቴ ሳይከፈለኝ ቆየሁ፡፡ በዚህም እጅግ ተበሳጨሁና ከአፋር ባላባቶች ጋር እርሻ አርሳለሁ ብዬ ገጠር ለመግባት ወሰንኩ፡፡ ሐረርጌ ውስጥ በምትገኝ ‹‹ኤረር›› በምትባል ትንሽ ከተማ ደረስን፡፡ እዚያም ለሦስት ቀናት ስንቆይ የአፋርና የዒሳ ብሔረሰቦች በመሣሪያ ብቻ ሳይሆን በዓይናቸው፣ በጨለማ ብቻ ሳይሆን በቀን ጭምር የሚጋደሉ ይመስላሉ፡፡ ሁኔታቸውም እጅግ አስከፊና አስፈሪ ሆኖ ታየኝ፡፡ እኔም በጊዜው ወጣት ጋዜጠኛ ነበርኩኝ፡፡ ሱፌን ለብሼ፣ ክራባት ሸብ አድርጌና ጎፈሬዬን ነቅሼ ነበር፡፡ ሙስሊም መሆኔ አያስታውቅም፡፡ የአውራጃው ገዥ ኮሎኔል ነው፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ላናግራቸው ብዬ ወደ ቢሮዋቸው ብቅ አልኩ፡፡ ኮሎኔሉ ሙስሊም መሆኔን አላወቁም፡፡ ተቀብለውኝ ከፊታቸው በነበረው ወንበር ላይ አስቀምጠው በአክብሮት ቡና ጋበዘኝ፡፡ ‹‹ጉዳይህ ምንድነው?›› አሉኝ፡፡ ጋዜጠኛ መሆኔን አሳወቅኩ፡፡ በእነዚህ ሁለት ብሔሮች በአፋርና በዒሳ መካከል የተመለከትኩትን አስከፊ ሁኔታ ዘርዝሬ ያለውን አስረዳሁ፡፡ ‹‹ለምን እንደዚህ ይሆናል? በሁለቱም በኩል ነፍሰ ገዳይ ለቅማችሁ 100 ና 200 ያህሉን በሕግ እያስወሰናችሁ ከድሬድዋ እስከ ናዝሬት ባለው ግንድ ላይ ብታንጠለጥሉት ሰላም ይሰፍናል፡፡ ከዚያም ሕዝቡን ወደ ትምህርትና ሥራ ለማሰማራት ይቻላል፤›› አልኩ፡፡ ኮሎኔሉ ደነገጡ፡፡ ፊታቸውን ጥቁር ጭምድድ አደረጉና ሌባ ጣታቸውን በአፋቸውና በአፍንጫቸው ላይ አድርገው ‹‹እስ! ኡስ!›› አሉኝ፡፡ ‹‹ከእኔ በቀር ሌላ ሰው አደራ እንዳይሰማህ፣ አደጋ ላይ ትወድቃለህ፤›› አሉኝ፡፡ እኔም እንደመደንገጥ ብዬ ‹‹ምነው ኮሎኔል›› ብላቸው ‹‹ከሰሜን ቀይ ባህር ከምዕራብ በሱዳን ድንበር አድርጎ በመንዝ ተራራ ሥር አልፎ እስከ ኬንያ በሚደርሰው ረባዳና ቆላማ ምድር ላይ ሠፍሮ የሚኖረው በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠረው ሕዝብ በሙሉ እስላም ነው፡፡ ይህ ሕዝብ መጋደሉ ቀርቶ ሰላም ቢሆን፣ ቢማርና ዘላን መሆኑ ቢቀር እርስ በእርሱ አንድነትን እየፈጠረ በዙሪያው ካሉት እስላም አገሮች ጋር ግንኙነት ያደርጋል። ክርስቲያን ለሆኑት ነገሥታትና የክርስቲያን ደሴት ለሆነችው ኢትዮጵያም እጅግ አደገኛ ይሆናል፡፡ እንዲሁ እየተጋደሉ፣ ሳይማሩና ተከፋፍለው በዘላልነት ብቻ ግብር እየከፈሉ እንዲኖሩ ከነገሥታትና ከበላይ ባለሥልጣኖች ተጠንቶ የተሰጠ መመርያ አለ፡፡ ጋዜጠኛ ነኝ እያልህ ይህን እንዴት አታውቅም?›› አሉኝ፡፡ ‹‹ሰውነቴ በድንጋጤ ራደ፡፡ ቡናዬን በፍጥነት ፉት ብዬ አመሠግናለሁ፤›› በማለት ወጣሁ፡፡ ይህም ‹‹አገር የጋራ ሃይማኖት የግል›› በሚለው መፈክር ጥላ ወይም ሽፋን ሥር በኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ላይ የሚፈጸም ሥውር ማዕቀብ ወይም ተንኮል መገለጫ ነው፡፡
ከአዘጋጁ፡- ጸሐፊው አንጋፋ ጋዜጠኛ፣ ደራሲ፣ የእስልምና ጉዳዮች ተመራማሪ፣ እንዲሁም የታሪክ አጥኚ ሲሆኑ፣ ጽሑፉ የእሳቸውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እየገለጽን፣ በኢሜይል አድራሻቸው [email protected] ማግኘት ይቻላል፡፡
