
ጉዞ ከጦር ኃይሎች ወደ ጀሞ ነው፡፡ ተጠጋግተው የታክሲ ወረፋ ሠልፍ ከያዙት ሰዎች መሀል አንዱ ከፊቱ ለተሠለፈው፣ ‹‹እዚህ አገር ድህነቱ አልበቃ ብሎን በላዩ ላይ ንትርክ፣ ከንትርክ አልፈን ወደ ግጭት፣ ከዚያም ወደ ለየለት ጦርነት እየገባን መተላለቅ፣ አቅማችን ዝሎ ትንፋሽ ለመውሰድ ደግሞ የማስመሰል ፀፀት ውስጥ መግባት ክፉ አመል ሆነብን እኮ…›› እያለ ሲነግረው ያኛው በበኩሉ፣ ‹‹ሰሞኑን እያገረሸበት ያለው ነገር በጊዜ ማቆሚያ ካልተበጀለት እንጃ ብቻ በጣም ያስፈራል…›› እያለ መለሰለት፡፡ ‹‹እንዴት ነው ነገሩ፣ ዓለም ቅጥ አንባሩ እየጠፋ ባለበት በዚህ ጊዜ ለሰላም በጋራ መቆም እንጂ ይህንን ምን ይሉታል…›› ከማለቱ የላፕቶፕ ቦርሳ ያነገበ ቀይ ጎልማሳ ድንገት፣ ‹‹ከግጭት ካልሆነ ከሰላም የማያተርፉ፣ ለዘመኑ አስተሳሰብ ፈፅሞ የማይመጥኑ ናቸው ቁምስቅላችንን የሚያሳዩት…›› ትላለች ከኋላው የተሠለፈች ከሲታ ሴት፡፡ ‹‹እውነትሽን ነው፣ በዚህ በሠለጠነ ዘመን ጠመንጃ ማንገብ ጌጥ የሚመስላቸው እንኩቶዎች ናቸው ሰላም የሚነሱን…›› ብለው ከፊታቸው የቆሙ አዛውንት ሲናገሩ፣ ‹‹እነሱ ግን መቼ ይሆን ከቆሞ ቀርነት የሚገላገሉት…›› ብላ አንዲት ጠይም ወጣት አከለችበች፡፡ ሊጀመር ነው!
‹‹እነሱም አደብ የሚገዙበት ጊዜ መምጣቱ አይቀርም፡፡ ነገር ግን እስኪያልፍ ያለፋል እንደሚባለው በጋራ ለአገራችን ሰላም፣ ልማትና ዕድገት የሚበጀውን ዘዴ ለመቀየስ ከመተባበር ውጪ አማራጭ አይኖረንም፡፡ የፖለቲካ ቁማሩን በሠለጠነ መንገድ ማሸነፍ ሲያቅታቸው ጠመንጃ ውልወላ ውስጥ መግባት ልማድ ያደረጉትን ሁሉ አንድ ቀን መስመር ማስያዛችን አይቀርም…›› ብላ ጠይሟ በራሷ ንግግር ላይ ስታክልበት፣ ‹‹ልጄ እንደ አፍሽ ያድርግልን…›› ያሉት አንዲት እናት ናቸው፡፡ በዚህ መሀል አንዲት ጎስቆል ያለች ሚኒባስ ታክሲ ደርሳ፣ በወያላው አጋፋሪነት ከፊት ያለነው ቦታ ቦታችንን ከመያዛችን የተለመደው ‹‹ሳበው!›› ሲባል ጉዞ ተጀመረ፡፡ ‹‹ማነሽ ልጄ የሰላምን ነገር ስታነሺ ምን ትዝ አለኝ መሰለሽ፣ አገርን ከግጭት ውስጥ ለማውጣ የተባበረ ክንድና ልብ ሲኖር ምንም ነገር ማድረግ እንደሚቻል ነው፡፡ ሳንተባበር ስንቀር ግን እርስ በርስ መባላት፣ መጨካከን፣ በንፁኃን ደም መነገድ፣ መዋሸት፣ መስረቅና ወገንን ማሰቃየት መደበኛ ሥራ ይሆናሉ፡፡ እናንተ ወጣቶች ግን ካለፈው የውድቀት ታሪካችን በመማር የተሻለች አገር ለመገንባት ተባበሩ፡፡ ዓለም እየሄደችበት ያለው አደገኛ መንገድ ውስጥ ለመግባት ሳይሆን፣ አዋጭ የሆነውን ለመያዝ አንድ ሁኑ…›› ያሉት እኚያ እናት ናቸው፡፡ ልክ ናቸው!
ታክሲ ጥበቃው ሠልፍ ላይ የተጀመረው የታክሲ ወጋችን በድንገት በሌላ ወሬ ተጠመደ፡፡ መሀል ወንበር ላይ የተሰየመ ጎልማሳ አጠገቡ ለተቀመጠችው፣ ‹‹በቀደም ዕለት ማኪያቶ ለመጠጣት እዚያ ካፌ በረንዳ ላይ ወንበር ስቤ ከመቀመጤ ያ ወዳጄ ይደውልልኛል፡፡ ለአንድ ደቂቃ ያህል አውርተን ከመሰነባበታችን አንድ ጎረምሳ ቀጥሎ ካለው ጠረጴዛ ተንደርድሮ መጥቶ፣ ‹ጋሼ የተደወለልህ ቁጥር ሙሉ ነው ጎደሎ…› ሲለኝ ደነገጥኩ፡፡ በድንገተኛው ሁኔታ ተደናግጬ አፍጥጬ ሳየው፣ ‹ጋሼ ምን መሰለህ ሞላ ጎደለ እየተጫወትን ነው› ሲለኝ ከራስ ፀጉሬ እስከ እግር ጥፍሬ ድረስ ንዴት አርገፈገፈኝ…›› ሲላት ሰማነው፡፡ ‹‹አይ አንተ፣ አንዳንዴ አለመስማትን የመሰለ መልካም ነገር ያለ አይመስለኝም…›› ስትል አጠገቡ ያለችው፣ ‹‹ጉዳችንማ በደንብ ይሰማ እንጂ…›› ብላ አንዲት ወይዘሮ ጥልቅ አለች፡፡ ‹‹ሥራ ጠል የሆኑ የማይረቡ ጉዶች ከየት አምጥተው እንደሚበሉ፣ እንደሚቅሙ፣ እንደሚጠጡ፣ እንደሚቆምሩ የማይታወቅባት ኢትዮጵያ ውስጥ ቁማሩ እኮ መንገድ ላይ ጭምር እያስቆሙ የጫማ ቁጥር ማስጠየቅ ጀምሯል፡፡ ባለቤቴ ከወዳጆቹ ጋር ቢራ ሲጠጣ አንድ ቁማርተኛ መጥቶ እስካሁን የጠጣችሁት ቢራ ስንት ነው ብሎ ይጠይቀዋል፡፡ ለምን ብሎ ሲጠይቀው ቁጥሩ ሙሉ ወይም ጎደሎ መሆኑን ለማወቅ ነው ብሎ መለሰለት…›› ስትለን ግራ ተጋብተን ተያየን፡፡ ወቸ ጉድ!
ከብዙ ፀጥታ በኋላ ድንገት የእጅ ስልክ ጥሪ ተሰማ፡፡ የስልክ ጥሪው ባለቤት የላፕቶፕ ቦርሳ የያዘው ጎልማሳ ነበር፡፡ ‹‹ሃሎ ወዳጄ እንዴት ነህ፣ አንተ ሶሻል ሚዲያ ላይ በጣም በዝተሃል፡፡ የአክቲቪዝም ኑሮ እንዲህ እሳት የላሰ አነብናቢ ያደርጋል እንዴ…›› እያለ ከወዲያኛው ጋር መነጋገር ሲጀምር፣ ‹‹ሶሻል ሚዲያው ለስንትና ስንት ቁምነገር መዋል ሲገባው፣ እኛ አገር ግን ጥራዝ ነጠቁ ሁሉ ዋና ተንታኝና አስተንታኝ ሆኖ ብዙ ዕውቀት ያቆሩ ግን ሰሚም ሆነ አዳማጭ የላቸውም…›› የሚለው መሀል ወንበር ላይ የተቀመጠ ቀይ ወጣት ነው፡፡ ‹‹እኔ ግን እጅግ በጣም የማደንቃቸው ጥቂት ሰዎች በዓለም ወቅታዊ ሁኔታ ላይ የሰጧቸው ትንታኔዎች አንጀቴን ስላራሱት በጣም ደስ ብሎኛል፣ ያላሰብኩትንም ዕውቀት ገብይቻለሁ፡፡ እነዚህን ዕንቁ የሆኑ ሰዎች ጥቂቶች እየተከተሏቸው ዕውቀት ሲጨልፉ፣ ብዙኃኑ ግን ጥራዝ ነጠቆች ሠፈር ከትመው ድንቁርና ይጋታሉ…›› ብላ ጠይሟ ስትናገር አዛውንቱ አጨበጨቡላት፡፡ ‹‹ልጄ ተባረኪ፣ እኔ በዚህ ዕድሜዬ በጣም የማውቃቸው ጥቂት ልሂቃን እየመገቡን ያለውን ዕውቀት የመንግሥት ሰዎች ቢቋደሱ አገራችን የት በደረሰች ነበር…›› ብለው ሲያክሉበት፣ ‹‹መንግሥት ብቻ ሳይሆን እኛም ማዳመጥ አለብን…›› የሚለው ወጣቱ ነበር፡፡ ግሩም ድንቅ ዕይታ!
የታክሲያች ጉዞ ቀጥሏል፣ ወጉም ደርቷል፡፡ ሾፌሩ ከአሮጌዋ ታክሲ ሬዲዮ፣ ‹‹አሜሪካ አብረሃም ሊንከን የተባለችውን የጦር መርከብ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ አስጠጋች…›› የሚል ድምፅ ከመሰማቱ፣ ‹‹ሾፌር በሕግ አምላክ ይህንን ዜና እንዳታሰማኝ…›› የሚል ድምፅ ሰማን፡፡ ከኋላ ወንበር ከተቀመጠ ፀጉሩን እንደ ራስታዎች የጎነጎነ ጠይም ጎልማሳ ነው፡፡ ‹‹…ይቅርታ ካጠፋሁ ወገኖቼ፣ ነገር ግን ባቢሎን የምትባለው አሜሪካ ስም ሲነሳ ስለሚያመኝ ነው፡፡ ይህች የምድራችን ጭራቅ ዓለምን በአራቱም ማዕዘናት ማባላቷ ሳያንሳት፣ አሁን ደግሞ ለይቶላት አገሮችን መውረርና ማስፈራራት ሥራዬ ብላ ይዛለች፡፡ ትራምፕ የሚሉት ሰውዬ ፈላጭ ቆራጭ የሆነበት የዓለም ሥርዓት ለመገንባት ተብሎ ከፊታችን መከራ ተደቅኗል፡፡ ያቺ ስሟ ከዴሞክራሲ ጋር ተጣብቆ የኖረች አገር ሲኦል ልትሆን ነው፡፡ አሜሪካውያን በገዛ አገራቸው ሲገደሉ ፍትሕ እየጠፋ ነው፡፡ የዓለም ሕዝብ ደግሞ የከፋ ነገር ነው የሚጠብቀው…›› ብሎ ሲንገፈገፍ ሁኔታው ያስፈራ ነበር፡፡ ‹‹እኛ በየት በኩል ዲቪ ደርሶን ከችጋር ውስጥ በወጣን ስንል ትራምፕ የሚሉት ክፉ ዘጋጋው…›› ያለችው ከሾፌሩ ጀርባ የተቀመጠች ቀይ ወጣት ስትሆን፣ ‹‹አይ አንቺ፣ ሰውዬው ስለምን እየተናገረ እንደሆነ ቢገባሽ እንዲህ አትይም ነበር…›› የሚላት ወያላው ነው፡፡ አልተግባብቶም!
‹‹ሾፌር ዜናው ቀርቶብን እስኪ ሙዚቃ ክፈትልን…›› ብሎ አንድ ጎረምሳ ከወደኋላ ማሳሰቢያ ሲሰጥ፣ ‹‹ሙዚቃ በደፈናው ክፈት አይባልም፡፡ ለምሳሌ ከአገራችን ቅኝቶች አንቺ ሆዬ፣ ትዝታ፣ አምባሰል፣ ባቲ፣ እንዲሁም ከውጭ ደግሞ ጃዝ፣ ብሉዝ፣ ሬጌ፣ ሮክ፣ ወዘተ ትመርጥና ነው ሙዚቃ ክፈት የሚባለው…›› ብሎ አጠገቡ የተቀመጠው ቢጤው ሲራቀቅ፣ ‹‹ተው እንጂ፣ እሱን ለባለሙያዎቹ ትተህ የምትፈልገውን ሙዚቃ ወይም ድምፃዊ ስም ነው መጥቀስ ያለብህ…›› ብሎ ሾፌሩ በማጮንቆሪያ መስታወቱ እያየ ሲናገር ሰማነው፡፡ ወያላው እየሳቀ፣ ‹‹አንተ ደግሞ ታክሲያችንን የምሽት ጭፈራ ቤት ልታስመስላት ነው እንዴ የዘፈንና የዘፋኝ ቡፌ የምትደረድርለት…›› በማለት ሌላ ዘውግ ውስጥ ሲከተን፣ ‹‹ሸማ የሚለበሰው በየፈርጁ ነው እንደሚባለው፣ ሙያን ለባለሙያ ብንተው እኮ የማያገባን ውስጥ ጥልቅ እያልን አንዘባርቅም ነበር…›› የሚሉት እናታችን ናቸው፡፡ እሳቸው አንዳንዴ ጣል ከሚያደርጉት በስተቀር ዘንቢላቸውን እያዩ ሐሳባቸው ጭልጥ የሚያደርጋቸው ኑሮ እየደቆሳቸው እንደሆኑ ያስታውቃሉ፡፡ አልሞላ ያለ ኑሮ ስንቱን እያመሰው ይሆን!
ወደ መዳረሻችን እየተጠጋን ነው፡፡ ‹‹ሰሞነኛው ጉንፋን ሦስት ቀን ሥራ አስፈትቶኝ ዛሬ ነው ወደ እንጀራዬ የምሄደው…›› ከሲታዋ ሴት አጠገቧ ለተቀመጠችው እየነገረቻት ነው፡፡ ያችም ጎርነን በሚል ድምፅ፣ ‹‹እኔስ ብትይ ደቁሶኝ ነው የከረመው…›› ብላ ስትመልስላት፣ ‹‹ውጭ ያሉ ዘመዶቻችንም ሲመረመሩ ለክፉ የማይሰጥ ኮቪድ እንደሆነ ተነግሯቸዋል፡፡ እኛ ግን ምርመራ ማድረግ ስለማንወድ እንደ ተራ ጉንፋን ንቀነው ያድፈጠፍጠናል…›› ጠይሟ ወሬውን ስትቀላቀል፣ ‹‹ልጄ ምርመራ ስትይ፣ እኛ እኮ እንደ ምርመራ የምንጠላው ነገር የለም፡፡ የሠለጠኑት በዓመት አንዴ ወይም ሁለቴ ሁለመናቸውን ተመርምረው ጤናቸውን ሲንከባከቡ፣ እኛ ግን ፍርኃት ይሁን ወይም የገንዘብ ዕጦት አላውቅም ምርመራ ለማድረግ እንቸገራለን…›› ብለው አዛውንቱ ሲያክሉበት፣ ‹‹አባቴ የቫይረስ ምርመራ ብቻ ሳይሆን፣ እስቲ የአዕምሮ ጤንነታችንም በሚገባ ይመርመር፡፡ የፖለቲከኞች የዕልቂትና የውድመት ቁማር አልበቃ ብሎ የሞላ ጎደለ ቁማር ቤታችን ድረስ ሰተት ብሎ ሲገባ ምርመራ ያስፈልገናል…›› ብሎ ባለላፕቶፑ ሲያብራራው ጀሞ ደርሰን ‹‹መጨረሻ!›› ተብለን ስንብት ተደረገልን፡፡ መልካም ጉዞ!