የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን የምሥራቅ አፍሪካ ቢሮ ባወጣው ሪፖርት፣ የኢትዮጵያ ማክሮ ኢኮኖሚ በጠንካራ ቁመና ላይ ቢሆንም እየጨመረ በመጣ ድህነትና የውጭ ዕዳ ጫና እየተፈተነ መሆኑን አስታወቀ፡፡
ድርጅቱ ይፋ ባደረገው ዓመታዊ ሪፖርቱ፣ ኢትዮጵያ ምንም እንኳ ጠንካራ የኢኮኖሚ አቋም ላይ ብትሆንም፣ በአብዛኛው ሕዝብ ውስጥ በማኅበራዊ ዘርፍ አመላካቾች ያልተመጣጠነ ዕድገት መኖሩን ገልጿል፡፡ ብሩንዲ፣ ማዳጋስካርና ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ከኢትዮጵያ እኩል አብዛኛው ሕዝባቸው ለፈርጀ ብዙ ችግር የተጋለጠ ነው ብሏል፡፡
ኢትዮጵያ ፈጣን ዕድገት እያስመዘገበች ያለች አገር ብትሆንም በቀጣናው ካሉ አገሮች ከፍተኛ የዕዳ ጫናና ከፍተኛ የድህነት ምጣኔ እንዳለባት፣ የዕድገትና የተጋላጭነት ተቃርኖ ውስጥ ያለች አገር ናት ሲልም ገልጿታል፡፡
መረጃዎች እንደሚያሳዩት የኢትዮጵያ አጠቃላይ የአገር ውስጥና የውጭ ብድር 52 ቢሊዮን ዶላር አካባቢ ደርሷል፡፡ መንግሥት ለ2019 ዓ.ም. ከያዘው አጠቃላይ 2.3 ትሪሊዮን ብር ዓመታዊ በጀት ውስጥ 542 ቢሊዮን ብር ለብድር ዕዳ መክፈያ የሚውል ነው መባሉ ይታወሳል፡፡
የኢትዮጵያ በጀት ከዓመት ወደ ዓመት ቢጨምርም አሁንም የጎረቤት ኬንያ ከምትመድበው ያነሰ መሆኑን፣ ኢትዮጵያ በውጭ ዕርዳታ ጥገኝነቷ በመካከለኛ ደረጃ እንደምትቀመጥ ገልጾ፣ እ.ኤ.አ. በ2026 9.2 በመቶ ዕድገት እንደምታስመዘግብ ሪፖርቱ አስታውቋል፡፡
የምሥራቅ አፍሪካ አገሮች በዓለም አቀፍ የነዳጅ ዋጋ ንረት ጉዳት በከፍተኛ ሁኔታ የተስተዋለባቸው አካባቢዎች ናቸው ይላል፡፡ የምሥራቅ አፍሪካ አገሮች ኢኮኖሚያቸው በበርካታ ጉዳዮች እየተፈተነ መሆኑን የሚገልጸው ሪፖርቱ፣ በጥሩ የማክሮ ኢኮኖሚ ዕድገት ላይ ትገኛለች ያላት ኢትዮጵያ የፖለቲካ አለመረጋጋት በ32 በመቶ፣ የፋይናንስ ዕጦት በ27 በመቶ፣ የታክስ ምጣኔ 12.7 በመቶ ኢኮኖሚውን እየፈተኑት ነው ብሏል፡፡
የኢትዮጵያ የውጭ ምንዛሪ በገበያ መመራት መጀመር በኋላ የክምችት ዕድገት ቢያሳይም፣ የምንዛሪ ተመኑን ማቀራረብ ግን ፈታኝ እንደሆነበት ያስረዳል፡፡ የውጭ ምንዛሪ ግብይቱ በንግድ ባንኮች አንድ የአሜሪካ ዶላር ከ160 ብር በላይ እየተገዛ ሲሆን፣ በውጭ ምንዛሪ ቢሮዎች አንድ ዶላር ከ178 እስከ 180 ብር ሲሸጥ፣ በጥቁር ገበያ ግን ከዚያ በላይ እንደሚመነዘር መረጃዎች ያመላክታሉ፡፡
From The Reporter Magazine
ኢትዮጵያ ከአሜሪካ ነፃ የንግድ ዕድል ተጠቃሚነት ብትሰረዝም ወደ አሜሪካ የምትልካቸው ወጪ ምርቶች ከፍተኛ ጭማሪ ማሳየታቸውን የሚጠቅሰው ሪፖርቱ፣ እ.ኤ.አ. በ2025/2026 ወደ አሜሪካ ከተላኩ ምርቶች 120 በመቶ ዕድገት መመዝገቡን ይገልጻል፡፡
ኢትዮጵያና ኡጋንዳ በወጪ ንግድ አፈጻጸም ፈጣን ዕድገት ያስመዘገቡ አገሮች መሆናቸውን፣ ሁለቱም አገሮች በቡናና በወርቅ ቀዳሚውን ደረጃ መያዛቸው ተጠቁሟል፡፡
ሥር የሰደደ የምግብ እጥረት እየተስተዋለባቸው ካሉ አገሮች መካከል ብሩንዲ 46 በመቶ፣ ማዳካስካር 45.8 በመቶ፣ ኢትዮጵያ 42 በመቶ ሲሆኑ፣ ይህም መሠረታዊ አቅርቦቶችና ምርታማነት ላይ የረዥም ጊዜ መዋቅራዊ ችግር መኖሩን ማሳያ መሆኑን ያስረዳል፡፡
From The Reporter Magazine
በኢትዮጵያ ሰፋ ያለ የማኅበራዊ ጥበቃ ፕሮግራም ሁሉን አቀፍ ድህነትን በመቀነስ ትልቅ ሚና መጫወቱን የሚገልጸው ሪፖርቱ፣ ሁሉን አቀፍ ድህነት አመላካች ከሆኑ ዘርፎች መካከል ትምህርት መሠረታዊ ጉዳይ ተብሎ ተመላክቷል፡፡ በድህነት አመላካች ትምህርት አንድ ሦስተኛውን ድርሻ ሲይዝ፣ ሲሼልስ 32 በመቶ፣ ማዳጋስካር 31.6 በመቶ፣ ኢትዮጵያ 31 በመቶ ናቸው ተብሏል፡፡ የተማሪዎች ቁጥር ቢጨምርም የመማር ማስተማር ውጤቱ በጣም ደካማና የትምህርት ማጠናቀቅ ምጣኔ ደግሞ ዝቅተኛ መሆኑ በሪፖርቱ ተካቷል፡፡
የሴቶች ውክልናን በተመለከተ የሚያብራራው ሪፖርቱ፣ በኢትዮጵያ በታችኛው ምክር ቤት 42 በመቶ፣ በላይኛው ምክር ቤት ደግሞ ወደ 30 በመቶ ውክልና እንዳላቸው ያብራራል፡፡