- ኢንቨስትመንትን ለመሳብ ጠቀሜታ ይኖረዋል ተብሏል
ብሔራዊ የዲጂታል መታወቂያ ፕሮግራም (ፋይዳ) አገራዊ የዲጂታል ሕዝባዊ መሠረተ ልማትን ለማጠናከር ‹‹ፋይዳቨርስ ዲጂታል ሶሉሽንስ ኢንተርፕራይዝ›› በሚል ስያሜ የመንግሥት የልማት ድርጅት ሆኖ እንደገና መቋቋሙን፣ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ አስታወቀ፡፡
በፕሮጀክት ደረጃ ሲንቀሳቀስ የነበረው ፋይዳ ይፋዊ አገራዊ ግልጋሎት በሚሰጥ ፋይዳቨርስ (Faydaverse) በተሰኘ የመንግሥት የልማት ድርጅት ደረጃ ተደራጅቶ በይፋ መቋቋሙ፣ ትናንት ማክሰኞ ሐምሌ 28 ቀን 2018 ዓ.ም. ይፋ ተደርጓል።
ፋይዳቨርስ ዜጎችን፣ ንግዶችንና ተቋማትን የሚደግፍ አስተማማኝ የዲጂታል ሕዝባዊ መሠረተ ልማት (DPI) መፍትሔዎችን የመገንባት፣ የማንቀሳቀስና የማስፋፋት ኃላፊነት እንደተሰጠው የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ በሰጠው መግለጫ አስታውቋል።
ተቋሙ የአገሪቱን ስትራቴጂካዊ የኢንቨስትመንት ሀብቶች የሚያስተዳድረው የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ (EIH) አካል ሆኖ መቀላቀሉም ተገልጿል። ይህ ሞዴል ተቋሙ አቅሙን እንዲያሰፋ፣ አጋርነቶችን እንዲያጠናክር፣ ኢንቨስትመንትን እንዲስብና ከኢትዮጵያ አገራዊ የልማት ግቦች ጋር የተጣጣሙ የዲጂታል መፍትሔዎችን ማልማቱን እንዲቀጥል እንደሚያስችለው በመግለጫው ተነግሯል፡፡
ፋይዳቨርስ ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን መስክ ያላትን ሚና እንደሚያጠናክር፣ አገሪቱ በትልቅ ደረጃ የዲጂታል ማንነት መሠረተ ልማትን በመተግበር ረገድ ያላትን ልምድ በመጠቀም በመላው አፍሪካ የዕውቀት ልውውጥን፣ የቴክኒክ አጋርነቶችንና የዲጂታል ሕዝባዊ መሠረተ ልማት እንዲደግፍ ተብሎ መዘጋጀቱ ተነግሯል።
ከመንግሥታት፣ ከተቋማትና ከቴክኖሎጂ አጋሮች ጋር በመተባበር ፋይዳቨርስ ከአኅጉራዊ አጋርነቶች ጋር በተጣጣመ መንገድ ዘመናዊ አፍሪካን፣ እንዲሁም የአፍሪካ ነፃ ንግድ ቀጣናን (AfCFTA) ጨምሮ) የተጣጣሙ ሉዓላዊ፣ ደኅንነታቸው የተጠበቁና አካታች ዲጂታል ሥርዓቶችን ለማልማት አልሞ እንደሚሠራ ተገልጿል።
ይህ ውሳኔ ኢትዮጵያ ደኅንነቱ የተጠበቀ የዲጂታል ተሳትፎ እንዲኖራት የሚያስችል፣ የአገልግሎት ተዳራሽነትን የሚያሻሽል፣ የኢኮኖሚ አካታችነትን የሚደግፍና የዘመናዊ ዲጂታል ኢኮኖሚ መሠረትን የሚያጠናክር ዘላቂ የዲጂታል ሕዝባዊ መሠረተ ልማት ለመገንባት ያላትን ቁርጠኝነት እንደሚያሳይ ተጠቁሟል።
From The Reporter Magazine
ውሳኔው የፋይዳቨርስን ተቋማዊ መሠረት፣ የአመራር ሥርዓትና የረዥም ጊዜ ዘላቂነት በከፍተኛ ደረጃ እንደሚያጠናክረው ተገልጿል። ፋይዳቨርስ በባዶ መሬት ላይ የተመሠረተ ሳይሆን፣ ባለፉት ዓመታት ያስመዘገባቸውን አስደናቂ ተግባራዊ ውጤቶች መሠረት ያደረገ መሆኑ ተጠቅሷል።
ይህ አዲስ ተቋማዊ መዋቅር ፋይዳቨርስ ‹‹አንድ ሰው፣ አንድ ማንነት›› በሚለው መሠረታዊ መርህ ላይ ያተኮሩ የባዮሜትሪክ ዲጂታል ማንነት ሥርዓቶችን፣ የኤሌክትሮኒክ ደንበኛን ማወቅ (Electronic Know Your Customer-eKYC)፣ የተጠቃሚዎችን ግላዊነት የሚጠብቁ የዲጂታል መታወቂያና ሌሎች አገልግሎቶችን በሰፊው እንዲያቀርብ እንደሚያስችለው ተገልጿል። በተጨማሪም ክፍያዎችንና በፈቃደኝነት ላይ የተመሠረተ የመረጃ ልውውጥን የሚያቀናጁ የዲጂታል ሕዝባዊ መሠረተ ልማት መፍትሔዎችን በተመለከተ የምክር አገልግሎቶችን ለተቋማት ለመስጠት ማቀዱ ተገልጿል።
የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ብሩክ ታዬ (ዶ/ር)፣ ፋይዳቨርስ የመንግሥት የልማት ድርጅት ሆኖ መቋቋሙና በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ሥር መካተቱ፣ ከኢትዮጵያ ስትራቴጂካዊ የዲጂታል ሀብቶች አንዱን ለማጠናከር የተወሰደ ትልቅ ዕርምጃ ነው ብለዋል።
From The Reporter Magazine
ፋይዳቨርስ የመንግሥት የልማት ድርጅት ሆኖ መቋቋሙ፣ በኢትዮጵያ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ጉዞ ውስጥ ወሳኝ ምዕራፍ መሆኑንና የቴክኖሎጂ ፈጠራን፣ ተቋማዊ ጥንካሬንና ስትራቴጂካዊ የኢንቨስትመንት ድጋፍን በማጣመር አካታች ዕድገትን፣ የኢኮኖሚ ዕድልንና አስተማማኝ የዲጂታል መሠረተ ልማት ግንባታ ቀጣይነት እንዲኖረው እንደሚያስችል ተናግረዋል።
ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ሥርዓት 50 ሚሊዮን ነዋሪዎችን መድረሱንና ከ150 በላይ ከተቋማት ጋር ቅንጅቶች መፍጠሩን፣ 190 ሚሊዮን ደኅንነታቸው የተጠበቁ ማረጋገጫዎችን ማከናወኑን፣ 12 ሺሕ የሕዝብ መመዝገቢያ መሣሪያዎችን ማሰማራቱን፣ እንዲሁም ከ15 ሚሊዮን በላይ የማንነት ማረጋገጫዎችን መስጠቱ ተነግሯል።
ፋይዳቨርስ ለፈጠራ፣ ለዕድገትና ለዘላቂ ተፅዕኖ የተዘጋጀ ራሱን የቻለ ተቋም ሆኖ መሸጋገሩን በተበሰረበት መድረክ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ የልማት አጋሮች፣ የቴክኖሎጂ መሪዎች፣ የግሉ ዘርፍ ተወካዮችና ዓለም አቀፍ ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።