- አምስት ኤርፖርቶች የደኅንነት አስተዳደር ሥርዓት ሙሉ በሙሉ አልተገበሩም ብሏል
የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት ኢትዮ ቴሌኮም የሚያከናውናቸው አንዳንድ ግዥዎች በፖሊሲዎችና በመመርያዎች መሥፈርት መሠረት እንዳልሆኑ አስታወቀ፡፡
ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት የኢትዮ ቴሌኮም የግዥና ንብረት አስተዳደር ኢኮኖሚያዊ፣ ቀልጣፋና ውጤታማ መሆኑን በተመለከተ ባካሄደውና በመጋቢት ወር አጠናቆ ሰሞኑን ይፋ ባደረገው ከ2015 እስከ 2018 ዓ.ም. ሁለተኛ ሩብ ዓመት ድረስ ያሉትን የሥራ አፈጻጸም የክዋኔ ኦዲት ሪፖርት፣ ኩባንያው የሚያከናውናቸው የተሽከርካሪ፣ የኮንክሪት ፖል ግዥና በራስ ኃይል ያከናወናቸው የሕንፃ ዕድሳት ሥራዎች መሥፈርቱን አለማሟላታቸውን ጠቁሟል፡፡
ኩባንያው መጠናቸው ሰባት፣ ስምንትና ዘጠኝ ሜትር የሆነ ኮንክሪት ፖሎች ለመግዛት ጨረታ አውጥቶ እንደነበርና እ.ኤ.አ. ጥቅምት 3 ቀን 2020 ፋይናንሽያል ፕሮፖዛል የተከፈተ መሆኑን፣ ውጤቱን በማየት አሸናፊውን የመለየት ሥራ በማከናወን የአሸናፊነት ሰርተፊኬት መስጠት ቢገባም አለመስጠቱ ተገልጿል፡፡
ከጨረታ ተሳታፊዎች ውስጥ ኤዚቲ ኤሌክትሮኒክና ሕንፃ መሣሪያ አምራች የተባለ ድርጅት የአሸናፊነት ደብዳቤ እንዲሰጠው መጠየቁን፣ ነገር ግን ምላሽ ሳይሰጠው የሶርሲንግ ኮሚቴ ስብሰባ በማካሄድና ውጤቱን በመሰረዝ አዲስ ጨረታ እንዲካሄድ ውሳኔ መሰጠቱን የዋና ኦዲተር ግኝት ያስረዳል፡፡
ኩባንያው ጨረታውን በድጋሚ በውስን ጨረታ ማውጣቱንና በጨረታው የተጋበዙ ድርጅቶች ማንነትና የተጋበዙበት ደብዳቤ በጨረታ ሰነዱ ውስጥ ማግኘት እንዳልተቻለ፣ ነገር ግን በቴክኒክ ግምገማው ሰሚክና ጋቲ የተባሉ ድርጅቶች እንደቀረቡና እንደተገመገሙ በግምገማ ሪፖርቱ መመልከቱን ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት አስታውቋል፡፡
በዚህም ቀድሞ የተሰረዘው ጨረታ አሸናፊ ከነበረው ኤዚቲ ድርጅት ጋር በማወዳደርና የእሱን ዋጋ በመውሰድ፣ ሰሚክ የተባለው ድርጅት አሸናፊ እንዲሆን መደረጉ ተገልጿል፡፡ በተጨማሪም በመጀመሪያው ጨረታ ዝቅተኛ ዋጋ ያስገባው ኤዚቲ ድርጅት በሁለተኛው ጨረታ ሳይወዳደር እንደተሳተፈ ተደርጎ ለድርድር እንዲቀርብ የተደረገ መሆኑን የኦዲት ግኝቱ ያመላክታል፡፡
ኢትዮ ቴሌኮም ባወጣው የባለ ሰባት፣ ስምንትና ዘጠኝ ሜትር ኮንክሪት ፖሎች ጨረታ ባዘቶ፣ ጋቲና ሳንሻንግ የተባሉ ድርጅቶችን በውስን ጨረታ የጋበዘ መሆኑን፣ ነገር ግን ለጨረታ የጋበዘበት መሥፈርት የሚያሳይ ማስረጃ አለመቅረቡን፣ ተጫራቾች የተመዘገቡበትን ሰነድ፣ የቴክኒክና የፋይናንሽያል ፕሮፖዛል በሚከፈትበት ወቅት ተጫራቾች ፊርማቸውን ያላሠፈሩ መሆኑን የዋና ኦዲተር ግኝት ያመላክታል፡፡
From The Reporter Magazine
የኢትዮ ቴሌኮም የበላይ ኃላፊዎች በበኩላቸው የመጀመሪያውን ግልጽ ጨረታ መሥፈርት ያሟሉ ድርጅቶች ከአምራች ተረክበው የሚያቀርቡ በመሆናቸው፣ የጨረታ ውጤቱ ባለበት እንዲቆይና ጥናት በማድረግ በጥናቱ መሠረት ውስን ጨረታ እንዲከናወን የሶርሲንግ ኮሚቴው መወሰኑን ገልጸዋል ተብሏል፡፡
ሆኖም ማንኛውም ግልጽ ጨረታ ከወጣ በኋላ የቀረበው የጨረታ ውጤት፣ ለጨረታ አውጭው ድርጅት ጉዳት የሚያስከትል ከሆነ ወይም ተቋሙ ልዩ ጥቅም የሚያገኝ ከሆነ የመሰረዝ መብት ቢኖረውም፣ የሰረዘበትን ምክንያት ለተጫራቹ የማሳወቅ ግዴታ እንዳለበት በኦዲት ሪፖርቱ ተገልጿል፡፡
በመሆኑም ይህ ባልተካሄደበትና የግልጽ ጨረታ ውጤቱን በመያዝ በድጋሚ ውስን ጨረታ ማውጣት የጨረታ ሕግን የሚቃረን ነው ተብሏል፡፡
From The Reporter Magazine
ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት የኦዲት አካባቢውን ለመገምገም፣ ኩባንያው ለሚያከናውናቸው ሥራዎች ግብዓቶችን ለማሟላት የሚያካሂደውን ግዥ ግልጽነት ያለው፣ ፍትሐዊና ወጪ ለተደረገው ገንዘብ ተመጣጣኝ የሆነ አቅርቦት መገኘቱን ለማረጋገጥ የሚያስችል ኢኮኖሚያዊ፣ ቀልጣፋና ውጤታማ የአሠራር ሥርዓት የዘረጋ መሆኑን፣ የሀብት ብክነት አጠቃቀምና ብክነትን ለመቀነስ ኢኮኖሚያዊ፣ ቀልጣፋና ውጤታማ የንብረት አያያዝና አስተዳደር ሥርዓት መዘርጋቱን መገምገም የሚሉ ሁለት የኦዲት ትኩረት አቅጣጫዎች የለየ መሆኑን አብራርቷል፡፡
እነዚህ የትኩረት አቅጣጫዎችን ለመመዘን የሚረዱ 26 የኦዲት መመዘኛ መሥፈርቶች መዘጋጀታቸውንና ኩባንያውን ለማቋቋም የወጡ አዋጆችና ደንቦች፣ መመሥረቻ ሰነዶች፣ የሦስት ዓመት ስትራቴጂ ዕቅድና አገሪቱ በዓለም አቀፍ ደረጃ የተቀበለቻቸው ስታንዳርዶች መሆናቸው ለኩባንያው ተልኮ አስተያየት እንዲሰጥበት መደረጉ ተገልጿል፡፡
ይህ በዚህ እንዳለ ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት የኢትዮጵያ አየር መንገድን በሚመለከት በተመሳሳይ፣ የኤርፖርት የመሠረተ ልማት ሥራዎች አፈጻጸምና ኤሮናቲካል ያልሆኑ ገቢዎች አስተዳደር ውጤታማነት መሠረት የክዋኔ ኦዲት ማካሄዱን ይፋ ባደረገው የኦዲት ሪፖርት አስታውቋል፡፡
ሪፖርቱ የአየር መንገዱ ኤርፖርቶች የተቀመጠላቸውን ስታንዳርድ ያሟሉ መሆናቸውን፣ በዕቅድ የተያዙ የመሠረተ ልማት ሥራዎች አፈጻጸም ቀልጣፋ፣ ኢኮኖሚያዊና ውጤታማ በሆነ መንገድ መከናወናቸውንና አየር መንገዱ ኤሮናቲካል ያልሆኑ ገቢዎቹን ኢኮኖሚያዊና ውጤታማ በሆነ መንገድ ማስተዳደሩን መገምገም የኦዲቱ የትኩረት አቅጣጫዎች መሆናቸውን ያሳያል፡፡
የአውሮፕላን ማረፊያዎች በተለያየ ደረጃ የሚገለጽ የብቃት ማረጋገጫ ሰርተፊኬት ከኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን አግኝተው እንደሚሠሩ ተገልጿል፡፡
ሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን ኤርፖርች የተቀመጠላቸውን ዝቅተኛ መሥፈርት ማሟላታቸውን በማረጋገጥ የማስተካከያ ዕርምጃ እንዲወስዱ በሚሰጠው አቅጣጫ መሠረት፣ በአየር መንገዱ በዕቅድ ተይዘው የሚተገበሩ መሆናቸው ተመላክቷል፡፡
ሆኖም በድሬዳዋ፣ በመቀሌ፣ በባህር ዳር፣ በጎንደርና በቀብሪደሃር ኤርፖርቶች የኤርፖርት ደኅንነት አስተዳደር ሥርዓት ሙሉ በሙሉ ያልተተገበረና በሒደት ላይ መሆኑ የኦዲት ግኝቱ አመላክቷል፡፡
በቀብሪደሃር ኤርፖርት የአውሮፕላን መንደርደሪያ የጥገና ሥራ ያልተጀመረ መሆኑ፣ የላሊበላና የነቀምት ጉዲና ቶምሳ ኤርፖርት ሙሉ ግቢው ባለመታጠሩ እንስሳትና ሰዎች ወደ ግቢው እንደሚገቡ በኦዲት ግኝቱ ማረጋገጡን ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት ገልጿል፡፡
የአዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት በሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን የተቀመጠውን ዝቅተኛ መሥፈርት የሚያሟላ መሆኑን፣ በተቀሩት 22 ኤርፖርቶች ግን የኤርፖርት ደኅንነት ሥርዓት ተግባራዊ አልተደረገም ብሏል፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ የበላይ የሥራ ኃላፊዎች ለሪፖርቱ በሰጡት ምላሽ፣ የቀብሪደሃር ኤርፖርት የአውሮፕላን መንደርደሪያ ሜዳ የመልሶ ግንባታ ሥራ ለማከናወን ከታኅሳስ 14 ቀን 2018 ዓ.ም. ጀምሮ ኤርፖርቱ ተዘግቶ የማሻሻያ ሥራ በመከናወን ላይ እንደሚገኝ መግለጻቸው ተመላክቷል፡፡
ያልተሟሉ መሣሪያዎችን የማሟላትና የመትከል ኃላፊነት የሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን በመሆኑ አየር መንገዱ እንዲሟሉ ፍላጎት እንዳለው፣ የድሬዳዋ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት የመሠረተ ልማት ማሻሻያ ሥራ ለማከናወንም ዕቅድ የተያዘ መሆኑ ኃላፊዎቹ መግለጻቸውን የኦዲት ሪፖርቱ ያስረዳል፡፡
ሆኖም የኤርፖርቶች ደኅንነት አስተዳደር ሥርዓት ጋር የተያያዙ ሥራዎችና የደኅንነት አጥር ግንባታ ሥራዎች ቅድሚያ ሊሰጣቸው እንደሚገባ፣ በሲቪል አቪዬሽን በኩል መሟላት ያለባቸው መሣሪያዎች እንዲሟሉ የተጠየቀበት ማስረጃ ባለመቅረቡ የቀረበውን ምላሽ ለመቀበል እንደሚቸገር ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት አስታውቋል፡፡