
ሶማሊያን ይጎበኛሉ ተብለው ሲጠበቁ የነበሩት የቻይናው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋንግ ዪ ባልታወቀ ምክንያት ጉዟቸውን በመሰረዝ ወደ ሌላ የጉብኝታቸው መዳረሻ አገር ማቅናታቸው እያነጋገረ ነው።
እስራኤል ከሶማሊያ ለተገነጠለችው ሶማሌላንድ የመጀመሪያውን የሉዓላዊ አገርነት ዕውቅና ከሰጠች ከሁለት ሳምንታት በኋላ የቻይናው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሶማሊያ፣ መቋዲሾን ለመጉብኝት ማቀዳቸው በሶማሊያ መንግሥት በኩል ከፍተኛ ጉጉት ፈጥሮ ነበር።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ዋንግ ዪ፣ ኢትዮጵያን፣ ሶማሊያን፣ ታንዛኒያን ለመጎብኘት በያዙት ፕሮግራም መሠረት ሐሙስ ታኅሳስ 30 ቀን 2018 ዓ.ም. አዲስ አበባ የገቡ ሲሆን፣ በነጋታው ጥር 1 ቀን 2018 ዓ.ም. ደግሞ ወደ ሶማሊያ የመጓዝ ፕሮግራም ነበራቸው።
ሆኖም በሶማሊያ ዋና ከተማ ሞቃዲሾ ተገኝተው እስራኤል ለሶማሌላንድ የሰጠችውን ዕውቅና በማውገዝ፣ ለሶማሊያ ፌዴራል መንግሥት ዲፕሎማሲያዊ ድጋፍ ይሰጣሉ ተብለው በጉጉት ሲጠበቁ የነበሩት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ፣ ይገባሉ ተብለው በሚጠበቁበት ሰዓት አለመድረሳቸው ታውቋል።
ከሰዓታት ቆይታ በኋላም በሞቃዲሾ ሊያደርጉት የነበረው ጉብኝት ይፋ ባልተደረገ ምክንያት መታጠፉን የሶማሊያ ባለሥልጣናት አስታውቀዋል። ከጥቂት ሰዓታት በኋላም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ፣ በታንዛኒያ መግባታቸው ታውቋል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ በኢትዮጵያ በነበራቸው የአንድ ቀን ቆይታ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) እና ከኢትዮጵያ አቻቸው ጌድዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) ጋር ተገናኝተው በሁለትዮሽ ግንኙነትና በቀጣናዊ ጉዳዮች ላይ ተወያይተዋል።
ውይይታቸውን አስመልክቶ ባወጡት የጋራ መግለጫም፣ በልማት ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች ዙሪያ የሚያደርጉትን ቅንጅት የበለጠ ለማሳደግ መስማማታቸውን ገልጸዋል።
From The Reporter Magazine
ኢትዮጵያ ለአንድ ቻይና መርህ ያላትን ፅኑ ቁርጠኝነት፣ እንዲሁም ታይዋን የቻይና የማይገሰስ ግዛት አካል መሆኗንና የቻይና ሕዝባዊ ሪፐብሊክ መንግሥት መላውን ቻይና የሚወክል ብቸኛ ሕጋዊ መንግሥት መሆኑን ማረጋገጧ በጋራ መግለጫው ላይ ይፋ ተደርጓል።
ቻይና በበኩሏ የአፍሪካ አገሮች በተለያዩ ዘርፎች ግንኙነትና ትብብራቸውን በማጠናከር ቀጣናዊ ውህደት በተለይም በውይይትና በዲፕሎማሲያዊ መንገዶች የባህር በር ተደራሽነትን በማረጋገጥ ሎጂስቲክስ መስፋፋትን እንዲያረጋግጡ እንደምታበረታታ አስታውቃለች።
ኢትዮጵያ ታይዋንን በተመለከተ ያራመደችው አቋም፣ በሰዓታት ውስጥ ከታይዋን መንግሥት ተቃውሞ ገጥሞታል።