የመረጃ ነፃነት አዋጅን የሚያስፈጽው የኢትዮጵያ ሕዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም ፓርላማ ገብተው እንዳይዘግቡ የተከለከሉ ሚዲያዎችን በሚመለከት፣ ተጠሪነቱ ለፓርላማው በመሆኑ ፓርላማውን የመቆጣጠር ሥልጣን እንደሌለው ገለጸ፡፡
የኢትዮጵያ ሕዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም የመረጃ ነፃነት አዋጅ ቁጥር 1427/2018ን በሚመለከት ዓርብ ሐምሌ 10 ቀን 2018 ዓ.ም. ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል፡፡
ዋና ዕንባ ጠባቂዋ ወ/ሮ ስመኝ ውቤ መግለጫውን በጽሑፍ ባነበቡበት ወቅት፣ አዋጁ በፓርላማ የፀደቀበትን ዕለት ጨምሮ የግል መገናኛ ብዙኃን በፓርላማ ተገኝተው እንዳይዘግቡ መከልከሉን አስመልክቶ ዕንባ ጠባቂ ተቋም ምን እየሠራ እንደሆነ ጥያቄ ቀርቦላቸዋል፡፡
ለጥያቄው ምላሽ የሰጡት ዋና ዕንባ ጠባቂ ወ/ሮ ስመኝ፣ የአዋጁን መፅደቅና ተቋሙ ለፓርላማ ያቀረበውን የ11 ወራት ሪፖርት በርካታ ሚዲያዎች ሲዘግቡ መመልከታቸውን ገልጸው፣ ‹‹ተጠሪነታችን ለፓርላማ ስለሆነ ፓርላማውን ወደ ላይ መቆጣጠር ሥልጣን የለንም፤›› ብለዋል፡፡
‹‹ክፍተቱ የት ጋ እንደሆነ እርግጠኛ አይደለንም፤›› ያሉት ዋና ዕንባ ጠባቂዋ፣ ችግር ካለም ምላሽ የሚሰጠው ፓርላማው እንጂ ዕንባ ጠባቂ ተቋም ምላሽ ለመስጠት እንደሚቸገር ገልጸዋል፡፡
የተሻሻለውን የመረጃ ነፃነት አዋጅ ለማስፈጸም ዕንባ ጠባቂ ሙሉ ሥልጣን የተሰጠው ሲሆን፣ መረጃ በማይሰጡ ኃላፊዎች ላይ አስተዳደራዊ ዕርምጃ የመውሰድና ሥልታዊ ምርመራ የማድረግ መብት እንዳለው ተደንግጓል፡፡
ለ17 ዓመታት ሥራ ላይ የነበረው የመገናኛ ብዙኃንና የመረጃ ነፃነት አዋጅ ቁጥር 590/2000 በርካታ ችግሮች ነበሩበት ያሉት ወ/ሮ ስመኝ፣ ድንጋጌዎችን የማስፈጸምና የመቆጣጠር ኃላፊነት ለዕንባ ጠባቂ ተሰጥቶ የነበረ ቢሆንም፣ የተሰጠው ኃላፊነት ግን የተሟላ ባለመሆኑ ለመረጃ ነፃነት ተፈጻሚነት እንቅፋት መሆኑን በተለያዩ ጥናቶች መመላከቱን አብራርተዋል፡፡
From The Reporter Magazine
የበፊቱ አዋጅ ሁለት የተለያዩ መሠረታዊ ነፃነቶች የሚመሩበትን ድንጋጌዎች በአንድ አጣምሮ በመያዙ፣ በተለይም የመረጃ ነፃነት ድንጋጌዎች በተሟላ የአስተዳደር ሥርዓትና የአፈጻጸም ግልጽነት እንዳይቀርብ ማድረጉን ተናግረዋል፡፡
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የማሻሻያ ረቂቅ አዋጅን ለዝርዝር ዕይታ፣ ለዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ከመራ በኋላ ለሁለት ወራት ውይይት ሲደረግበት ከቆየ በኋላ ምክር ቤቱ ሰኔ 17 ቀን 2018 ዓ.ም. ማፅደቁ ይታወሳል፡፡
የተሻሻለውን አዋጅ የተፈጻሚነት ወሰን ሲገልጹም እስከ ታችኛው የመንግሥት መዋቅር ድረስ ባለ በማንኛውም የመንግሥት ተቋም፣ በመንግሥት የልማት ድርጅት፣ በመንግሥታዊ ሥራ ላይ በተሰማራ የግል ማኅበር ወይም የመንግሥት አካል የአክሲዮን ድርሻ ባለው የንግድ ማኅበር፣ በማንኛውም ጊዜና ቅርፅ ተዘጋጅቶ በእነዚህ አካላት እጅ በሚገኝ በማንኛውም መረጃ ወይም ሰነድ ላይ እንደሚሆን አስረድተዋል፡፡
From The Reporter Magazine
የተጠየቀው መረጃ ስለሚሰጥበት የጊዜ ገደብ የያዘውን የአዋጁን ድንጋጌ ክፍል ያስረዱት ዋና ዕንባ ጠባቂዋ፣ መደበኛ የመረጃ ጥያቄን የተቀበለ የመረጃ ኃላፊ በበፊቱ አዋጅ 30 ቀናት የነበረውን በ21 የሥራ ቀናት ውስጥ ምላሽ መስጠት እንዳለበት መደንገጉን ገልጸዋል፡፡
በእነዚህ ቀናት መረጃውን መስጠት ካልተቻለ የጊዜ ገደቡን ለአንድ ጊዜ ብቻ ለተጨማሪ 14 ተከታታይ ቀናት ላልበለጠ ጊዜ ማራዘም እንደሚቻል መደንገጉን ወ/ሮ ስመኝ ተናግረዋል፡፡
ነገር ግን የቀረበው ጥያቄ አስቸኳይ የመረጃ ጥያቄ ከሆነ በ48 ሰዓታት ውስጥ ምላሽ መሰጠት እንዳለበት፣ ይህም በበፊቱ አዋጅ አሥር ቀናት እንደነበር አስታውሰው፣ የተደረገው ማሻሻያ ተገቢ ነው ብለዋል፡፡
የተጠየቀው መረጃ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ወይም የመንግሥት አካል ተጠሪ ለሆነለት ወይም ለሌላ የመንግሥት አካል ለማቅረብ የተዘጋጀ ሪፖርት ከሆነ ግን ለሚመለከተው አካል እስኪቀርብ ድረስ 21 የሥራ ቀናት ቢያልፍም፣ የመረጃ ጥያቄውን ለተወሰነ ጊዜ ማዘግየት ወይም ለሌላ ጊዜ ማስተላለፍ እንደሚቻል መደንገጉን ዋና ዕንባ ጠባቂዋ አስረድተዋል፡፡
የመረጃ ነፃነትን ለመጣስ ወይም መረጃ ጠያቂን ለመጉዳት በማሰብ ሆን ብሎ በተንኮል መረጃ የከለከለ ወይም ሰነድ የደለዘ፣ ያበላሸ፣ የደበቀ ወይም ግዴታውን ያልተወጣ መሆኑን መረጃ ጠያቂ በበቂ ሁኔታ ማስረዳት የማይችልበት አጋጣሚ ሰፊ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
በመሆኑም በመንግሥት አካል ወይም በግል ድርጅት የተሰጠን ውሳኔ ወይም የተፈጸመን ድርጊት ሕጋዊነትና ተገቢነት የማስረዳት ግዴታ የመንግሥት አካልና የግል ድርጅት እንደሆነ፣ በአዲሱ አዋጅ በግልጽ መደንገጉን ገልጸዋል፡፡