በይበቃል ጌታሁን
በአዲስ አበባ ከተማ በምርጫ ክልል 28 ውስጥ በሚገኙት ጣቢያዎች በሰሚት ኮንዶሚኒየም ምርጫ ጣቢያ ለንደን ፓርክ፣ ጤና ጣቢያ፣ ብሩህ ተስፋ ብርሃን አንድና ንዑስ ጣቢያ፣ ማርያም መሄጃ መንገድ፣ 12 ዕጩዎች ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት፣ 101 ለክልል ምክር ቤት በተለያዩ ፓርቲዎች ቀርበዋል፡፡ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ብልፅግና፣ ሕዳሴ፣ ትብብር ለኢትዮጵያ፣ የወሎ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ፣ ነፃነትና እኩልነት ፓርቲ፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ አንድነት ፓርቲ፣ ኢዜማ፣ የኢትዮጵያ ዴሞክራቲክ ፓርቲ፣ ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ፣ አዲስ ትውልድ፣ አንድ ኢትዮጵያ ዴሞክራሲ ፓርቲና ሰላም ለኢትዮጵያ ጥምረት ይገኙበታል፡፡
በሰሚት የጋራ መኖሪያ ቤቶች ከሚገኙት ምርጫ ጣቢያዎች ሪፖርተር ቅኝት ባደረገባቸው ጣቢያዎች በአራቱ በለንደን ፓርክ፣ በሰሚት ጤና ጣቢያ፣ በብሩህ ተስፋ ዋናና በንዑስ ምርጫ ጣቢያዎች ድምፅ አሰጣጥ ሒደት ዘግይቶ ተጀምሯል፡፡
በአዲስ አበባ ምርጫ ክልል 28 ቦሌ ክፍለ ከተማ (የአሁኑ ለሚ ኩራ) ወረዳ 10 ሰሚት ኮንዶሚንየም ለንደን ፓርክ የምርጫ ጣቢያ 1,280 መራጮች በታብሌት የተመዘገቡ ሲሆን፣ ከሌሊቱ 10፡00 ሰዓት ጀምሮ ድምፅ ለመስጠት ተገኝተዋል፡፡
ድምፅ የመስጠት ሒደቱ ከንጋቱ 12፡12 ሰዓት ላይ ተጀምሮ ሦስት መራጮች ድምፅ ከሰጡ በኋላ፣ 12፡29 ሰዓት ላይ የድምፅ መስጠት ሒደቱ ለአንድ ሰዓት ተቋርጦ ተጀምሯል፡፡
በዕለቱ በምርጫ ጣቢያው የመጣው የክልል ምክር ቤት ድምፅ መስጫ ወረቀት የተሳሳተ ነው በሚል ተቋርጦ ቢቆይም፣ 1፡36 ሰዓት ላይ የፓርቲና የሲቪክ ማኅበራት ታዛቢዎች ቃለ ጉባዔ በመያዝ እንዲጀመር አድርገዋል፡፡
በአጠቃላይ አምስት ታዛቢዎች የተገኙ ሲሆን ከብልፅግና አንድ፣ ከአዲስ አበባ ወጣቶች ማኅበር ሁለት፣ ከሰኔ 16 ሰላምና ለውጥ የበጐ አድራጎት ማኅበር ሁለትና አንድ ከመስጠት በጎ አድራጎት ማኅበር ናቸው፡፡
From The Reporter Magazine
የምርጫ ጣቢያው ኃላፊ ወ/ሪት ትዕግሥት አለኸኝ በጣቢያው 1,280 በታብሌት መመዝገባቸውን በኦንላይን የተመዘገቡትን ቁጥር ማወቅ እንዳልቻሉ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
የድምፅ አሰጣጡ ሒደት ለማስጀመር የብልፅግና ፓርቲ ተወካይ የሆኑት አቶ ዘሪሁን ጌታቸው የክልል ተወካዮች ዕጩ ድምፅ መስጫ ወረቀት የዚህ ምርጫ ጣቢያ አለመሆኑን ገልጸው፣ በቅሬታ እንዲያዝላቸው በጽሑፍ ለጣቢያው አሳውቀዋል፡፡
የጣቢያው ኃላፊና ምርጫ አስፈጻሚዎች መራጩ መጉላላት ስለሌለበትና ከምርጫ ቦርድ ድምፅ መስጠት ሒደቱ እንዲጀምሩ በተነገራቸው መሠረት እንዲጀመር አድርገዋል፡፡
From The Reporter Magazine
በተመሳሳይ በምርጫ ክልል 28 ወረዳ 10 የሰሚት ጤና ጣቢያ ምርጫ ጣቢያ ኃላፊ ወ/ሮ በሀርልን አወል ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በጣቢያው በድምፅ መስጫ ወረቀት ላይ በተነሳው ግርታ ምክንያት ድምፅ መስጠት ሒደቱ ዘግይቶ ተጀምሯል፡፡
በጣቢያው 1,526 መራጮች በታብሌት የተመዘገቡ መሆናቸውን፣ ምንም ዓይነት ቅሬታ እንዳልቀረበና ከታዛቢዎች ጋር ቃለ ጉባዔ በመፈራረም ድምፅ የመስጠት ሒደቱ እንደተጀመረ ተናግረዋል፡፡
የምርጫ ጣቢያው ሰሚት ጤና አጠገብ በሚገኘው የጋራ መኖሪያ ቤቶች ግቢ ውስጥ የሚገኝ ሲሆን፣ በርካታ መራጮች ድምፅ ለመስጠት ተራቸውን ሲጠብቁ ለመመልከት ችለናል፡፡ በጣቢያው የደንብ ልብስ የለበሱ የፀጥታ አካላት አልነበሩም፣ በግቢው የጥበቃ ሠራተኞች ነው ፍተሻ የተከናወነው፡፡ በምርጫ ጣቢያው በተገኘንበት ወቅት በርካታ መራጮች ረዥም ሠልፍ ይዘው ተራቸውን ሲጠብቁ ተመልክተናል፡፡ ሒደቱም ሰላማዊና የተቀላጠፈ ነበር፡፡
የአዲስ አበባ ወጣቶች፣ የብልፅግና ፓርቲና የበጎ አድራጎት ድርጅት ተወካይ ታዛቢዎችን ተመልክተናል፡፡ የየትኛውም ሌላ ፓርቲ ተወካይ ጣቢያውን በጎበኘንበት ወቅት አልነበረም፡፡
ሪፖርተር በተገኘበት በለንደን ፓርክ ምርጫ ጣቢያ ድምፅ አሰጣጡ ለ1፡15 ሰዓት የዘገየበት ምክንያት ለምርጫ ጣቢያው የመጣው የክልል ምክር ቤት ዕጩዎች ድምፅ መስጫ የምርጫ ክልል 28 ሳይሆን፣ የምርጫ ክልል 17 ነው በሚል ግርታ ነው፡፡ ሆኖም ታዛቢዎች የብልፅግና፣ የሲቪክ ማኅበራት 1፡32 ሰዓት ላይ ቃለ ጉባዔ ፈርመው 1፡36 ሰዓት ሲሆን ምርጫው ተጀምሯል፡፡ በተጨማሪም የብልፅግና ተወካይ የክልል ምክር ቤት የመጣው ወረቀት ላይ ያላቸውን ልዩነት አሥፍረው ምርጫው ተጀምሯል፡፡
ምንም እንኳን ማልዶ የመጣው መራጭ ተራውን ይዞ የጠበቀ ቢሆንም፣ የምርጫ አስፈጻሚዎች ስለድምፅ አሰጣጡ ሒደት ማብራሪያ ትምህርት እየሰጡ አልነበረም፡፡
በብሩህ ተስፋ ሰሚት ሶስተኛ በር በብሎክ 61 የጋራ መኖሪያ ቤቶች ግቢ ውስጥ የሚገኝ የምርጫ ክልል የምርጫ ጣቢያ ሲሆን፣ ከዋና ጣቢያው ተጨማሪ ንዑስ ጣቢያን ያካተተ ነው፡፡
የምርጫ ጣቢያው ኃላፊ አቶ ሶፊሳ ብርሃኑ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ በዋና ጣቢያው 1,505 መራጮች ተመዝግበዋል፡፡ በድምፅ መስጫው ዕለት 12፡00 ሰዓት መጀመር የነበረበት ድምፅ አሰጣጥ፣ ‹‹የክልል ምክር ቤት ድምፅ መስጫ ወረቀት ተሳስቶ የተሠራጨ ነው›› በሚል በተፈጠረው ግርታ በሰዓቱ ሳይጀመር ዘግይቶ፣ 1፡20 ሰዓት ላይ ቃለ ጉባዔ በመያዝ ድምፅ መሰጠት መጀመሩን ገልጸዋል፡፡
የምርጫ አሰጣጥ ሒደቱን የብልፅግና ፓርቲ ታዛቢ አቶ ሸምሱ አብደላ፣ ሕይወት ሞገስ የሰኔ 16 ሰላምና ለውጥ ተምሳሌት በጎ አድራጎት ማኅበር፣ የአካል ጉዳተኞች ማኅበር ታዛቢ፣ ስንታየሁ ቸርነት ሲከታተሉ ነበር፡፡
ሪፖርተር የምርጫ ጣቢያውን በጎበኘበት ወቅት አንድ የተፎካካሪ ፓርቲ ታዛቢ አልነበረም፡፡ 11፡00 ሰዓት ላይ ባደረገው ድጋሚ ምልከታ በወቅቱ በርካታ መራጮ ድምፅ ለመስጠት ተራቸውን ሲጠባቁ አስተውሏል፡፡
የድምፅ አሰጣጥ ሒደቱ እስከ ሌሊቱ 6፡00 መራጮች በአዲስ አበባ ምርጫ ክልል 28 ወረዳ 10 ውስጥ ሰሚት ለንደን ፓርክ፣ ጤና ጣቢያ፣ ብሩህ ተስፋ ምርጫ ጣቢያ ድምፃቸውን ሰጥተዋል፡፡
በዕለቱ ሪፖርተር ያነጋገራቸው አቶ ዓብይ ገብረ መድኅን ከምሽቱ 2፡25 ሰዓት ወደ ምርጫ ጣቢያው ሄደው 4፡15 ሰዓት ላይ ድምፅ ሰጥተው እንደተመለሱ ገልጸዋል፡፡ በዚህም ወቅት ተራቸውን የሚጠብቁ ከ150 በላይ መረጮች ተራቸውን እየጠበቁ እንደነበር ምልከታቸውን አጋርተዋል፡፡
በምርጫ ክልል 28 ውስጥ ልዩ ስሙ ማሪያም መሄጃ አካባቢ በነበረው የወረዳ 10 ምርጫ ጣቢያ ቁጥራቸው ከ300 በላይ የሚሆኑ መራጮች ድምፅ ለመስጠት ከምሽቱ 2፡30 ሰዓት ላይ ረዥም ሠልፍ ይዘው ሲጠባበቁ ተመልክቷል፡፡ በዚህ ምርጫ ጣቢያ ውስጥ የነበረው ንዑስ ጣቢያ የተመዘገቡ መራጮች ምሽት ላይ በተቀላጠፈ ሁኔታ ድምፃቸውን ሰጥተው ተመልሰዋል፡፡
በድምፅ መስጫው ማግሥት ማክሰኞ ግንቦት 25 ቀን 2018 ዓ.ም. በምርጫ ጣቢያ ለንደን ፓርክ፣ ሰሚት ጤና ጣቢያ ብሎክ 291 ቅጥር ግቢ እስከ ቀኑ 6፡00 (ቅኝት ባደረግንበት ወቅት) የድምፅ ቆጠራ እየተካሄደ መሆኑን አይተናል፡፡
የሰሚት ጤና ጣቢያ ምርጫ ጣቢያ ኃላፊ ወ/ሮ በሀርልኝ አወል ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ የድምፅ አሰጣጡ ሒደት እስከ ሌሊቱ 6፡00 ሰዓት እንደተካሄደና በመቀጠልም ቆጠራ መጀመራቸውን፣ እንዲህም ሆኖ ቆጠራው እስከ እኩለ ቀን እየተካሄደ ነበር፡፡
እንዲሁም በለንደን ፓርክ ምርጫ ጣቢያ ድምፅ ቆጠራው ማክሰኞ ግንቦት 25 ቀን 2018 ዓ.ም. ሪፖርተር በተገኘበት 5፡00 ሰዓት ላይ እንደተካሄደ ተመልክተናል፡፡ ኃላፊዋ ወ/ሪት ትዕግሥት አለኸኝ ቆጠራው እንዳለቀ ውጤት እንደሚለጠፍ ገልጸዋል፡፡
በተጨማሪም በብሩህ ተስፋ፣ ሰሚት ጤና ጣቢያ ቆጠራውን በተመለከተ ከሰዓት በኋላ የምርጫ ጣቢያዎችን ኃላፊ ሪፖርተር በስልክ አነጋግሮ ቆጠራውን እያካሄዱ መሆኑን፣ ነገር ግን ሙሉ ለሙሉ እንዳልጨረሱና ሲያልቅ ውጤቱን እንደሚለጥፉ አሳውቀዋል፡፡
