በኢትዮጵያ የቤት ሠራተኛና አሠሪዎችን የተመለከቱ ጉዳዮችን በግልጽ የሚመራ የሕግ ማዕቀፍ ባለመኖሩ፣ ዕድሜያቸው ለሥራ ያልደረሱ ሕፃናት ለቤት ውስጥ ሠራተኝነትና ቤት ውስጥ ለሚፈጸም የመብት ጥሰት እየተዳረጉ መሆናቸው ተገለጸ፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ ከ5.6 ሚሊዮን በላይ የቤት ሠራተኞች አሉ ተብሎ እንደሚገመት፣ የቤት ሠራተኞችን የቅጥር ሁኔታ፣ ጥቅማ ጥቅም፣ የሥራ ስምምነትና የሥራ ከባቢን ጨምሮ በሚገባ የሚያስተዳድርና የሚመራ ራሱን የቻለ ሕግ አለመኖሩ ተጠቅሷል፡፡
ፎረም ፎር ሶሻል ስተዲስ የተሰኘው አገር በቀል ድርጅት ለረዥም ጊዜ ሲጠበቅ እንደ ነበር የተገለጸው የቤት ውስጥ ሠራተኞችን የተመለከተ ሕግ እንዲወጣ ሲካሄድ በቆየው ውትወታ፣ በሥራና ክህሎት ሚኒስቴር እየተዘጋጀ ነው የተባለ አዲስ ረቂቅ ሕግ ላይ የፖሊሲ ውይይት መድረክ ትናንት ማክሰኞ ሰኔ 16 ቀን 2018 ዓ.ም. አዘጋጅቶ ነበር፡፡
በውይይቱ የተሳተፉ አንድነት የሴት ሠራተኞች ማኅበር ፕሬዚዳንት ወ/ሮ ሒሩት አበራ ስለጉዳዩ ሲያብራሩ፣ በኢትዮጵያ አሥር ክልሎች ማኅበራቸው እየተንቀሳቀሰ ቢሆንም በየቤቱ ያለው የሠራተኞች አያያዝ ለመደራጀት ቀርቶ መብት ለመጠየቅ አስቸጋሪ ነው ብለዋል፡፡ ሁሉንም ሠራተኞች አባል ለማድረግ አዳጋች መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ፕሬዚዳንቷ በመላ አገሪቱ አሉ ከሚባሉ የቤት ሠራተኞች ውስጥ 94,000 ያህሉ አባላት መሆናቸውንና በአገሪቱ ሕግ ምንም እንኳ መደራጀት መብት ቢሆንም የቤት ሠራተኞች የቅጥር ሁኔታ፣ የአሠሪና ሠራተኛ ግንኙነት፣ የደላላና የኤጀንሲ ሚና፣ የደመወዝና የጥቅማ ጥቅም ጉዳይ፣ በአጠቃላይ የኑሮ ሁኔታ እንዴት መመራት እንዳለበት በሕግ መደንገግ ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
በመላ አገሪቱ ለሥራ በሚያደርጉት እንቅስቃሴ አሥር ዓመት ያልሞላቸው ሕፃናት ጭምር በር ተዘግቶባቸው የቤት ሠራተኛ ሆነው የሚያገለግሉ መኖራቸውን፣ ነገር ግን ማንም የሚጮህላቸው አለመኖሩን አስረድተዋል፡፡
በሕግ ከተፈቀደው ዕድሜ በታች ከመሥራታቸው ባለፈ የሚደርስባቸው ድብደባ፣ የደመወዝ ነጠቃ፣ ምግብና መሠረታዊ አገልግሎቶች መከልከልና የመሳሰሉት የሚፈጽሙት ሠራተኞች ከጅምሩ ስምምነት ፈጽመውባቸውና አሠሪውም ተስማምቶ ወደ ሥራ እንዲገቡ የሚያደርግ ሕግ ባለመኖሩ ነው ብለዋል፡፡ ይሁን እንጂ እየተዘጋጀ ያለው ሕግ ይህን ችግር የሚቀርፍ በመሆኑ ሒደት አሳታፊ ሆኖ እንዲሆን፣ የቤት ሠራተኞች መብታቸውን እንዲያውቁ ጠንካራ የማስተማር ሥራ ይጠይቃል ብለዋል፡፡
From The Reporter Magazine
በፎረም ፎር ሶሻል ስተዲስ የፖሊሲ ጥናት ባለሙያው አዲሱ መሠረት (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ የውትወታው ጊዜ ተጠናቆ አሁን የሕግ ዝግጅት እየተካሄደ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ነገር ግን በዝግጅት ላይ ያለው ሕግ የቤት ውስጥ ሠራተኞች ሊረዱት በሚችሉ ቋንቋ ቀላል ተደርጎ ቁልፉን ጉዳይ እንዲይዝ ማድረግ ያስፈልጋል ብለዋል፡፡ አክለውም ሕጉ ቀለል ተደርጎ ከመውጣት ባሻገር በአሠሪውና በሠራተኛው መካከል የሚኖረውን ግንኙነት በሥርዓቱ በመምራት ለአገር ኢኮኖሚ የሚያበረክት፣ የሠራተኞችን ሕይወት የሚለውጥና የአሠሪውንም ጥቅም የሚጠብቅ መሆን እንደሚኖርበት አሳስበዋል፡፡
የፎረም ፎር ሶሻል ስተዲስ ዋና ሥራ አስፈጻሚ የራስ ወርቅ አድማሴ፣ ‹‹በድህነት ውስጥ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን የሚመለከት ጉዳይ ምንጊዜም የሚያንገበግበን፤›› ጉዳይ ነው ብለው፣ በዋነኝነት ሴት የቤት ሠራተኞች የፆታና የመደብ ጭቆና ይደርስባቸዋል ብለዋል፡፡ የቤት ሠራተኞችን አባዎራዎች፣ እማወራዎችና ጥበቃዎች ጭምር ጭቆናው ውስጥ ስላሉበት ችግሩ በሕግ መፍትሔ እንዲያገኝ አሳስበዋል፡፡
