- ፍላጎቱን ለማሳካት አምስት ቢሊዮን ዶለር ያስፈልጋል ብሏል

በኢትዮጵያ የሚታየውን የዲጂታል ኢኮኖሚ ፍላጎት ለማሟላት በመጪዎቹ ሁለትና ሦስት ዓመታት፣ አሁን በሥራ ላይ ያለውን የቴሌኮም መሠረተ ልማት በእጥፍ ማሳደግ እንደሚገባ፣ የሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አሳሰቡ፡፡
የሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዊም ቫንሄለፑት ይህን የተናገሩት፣ ከሚያዝያ 12 ቀን እስከ ሚያዝያ 13 ቀን 2018 ዓ.ም. በአዲስ አበባ በተካሄደው የአውሮፓ ኅብረትና የኢትዮጵያ ቢዝነስ ፎረም ነው፡፡
‹‹የቴሌኮም ኢንዱስትሪው በመሠረተ ልማት ግንባታ ትልቅ ሚና ይፈልጋል›› ያሉት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፣ ሳፋሪኮም ወደ ኢትዮጵያ ከገባ ገና አምስት ዓመታት ቢሆነውም ዘርፉ በርካታ ዕድሎች አሉት ብለዋል፡፡ ይሁን እንጂ ኢትዮጵያ ያሏትን 15 ሺሕ የቴሌኮም ማማዎች አሁን ካለው አገራዊ ፍላጎትና ምኞት ጋር ለማጣጣም ከተፈለገ፣ መሠረተ ልማቱ በመጪዎቹ ሁለትና ሦስት ዓመታት በእጥፍ መጨመር አለበት ሲሉ አስረድተዋል፡፡ መሠረተ ልማቱን ለማሟላት እስከ አምስት ቢሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልግ አስረድተዋል፡፡
ሳፋሪኮም ኢትዮጵያ በግማሽ ቢሊዮን ዶላር ያህል የቴሌኮም መሠረተ ልማት ግንባታ ውስጥ ገብቷል ያሉት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፣ ነገር ግን አጠቃላይ የቴሌኮም ኢንዱስትሪው አምስት ቢሊዮን ዶላር ተጨማሪ ኢንቨስትመንት ይፈልጋል ብለዋል፡፡
ስኬታማና አትራፊ ኢንዱስትሪ ተጨማሪ ኢንቨስትመንት ይዞ ይመጣል ያሉት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፣ ሦስተኛ የቴሌኮም ኦፕሬተር ወደ ዘርፉ ሲገባ የሚደረገው ሪፎርም ስኬት ይሆናል ብለዋል፡፡ ‹‹ሦስተኛ የቴሌኮም ኩባንያ ቢገባ ደስተኛ ነኝ፣ ያ ደግሞ የጤነኛ ቴሌኮም ኢንዱስትሪ ማሳያ ነው፤›› ሲሉም አክለዋል፡፡
በኢትዮጵያ የቴሌኮም ኢንዱስትሪ ውስጥ ሰፊ የገበያ ዕድል ስለመኖሩ ሲያብራሩም፣ በኢትዮጵያ በየቀኑ 10,000 ሕፃናት ሲወለዱ በአውሮፓ ኅብረት በየቀኑ 9,500 ሕፃናት ይወለዳሉ ብለው፣ ይህ የሕዝብ ቁጥር በኢትዮጵያ ያለውን መልካም ዕድል ማሳያ ነው ብለውታል፡፡
ሳፋሪኮም የዲጂታል ኢኮኖሚ ሕይወት ፍላጎት እያደገ ከመምጣቱ ጋር ተያይዞ፣ የዲጂታል መሠረተ ልማቶች የበለጠ እንዲስፋፋ ይሠራል ብለዋል፡፡
From The Reporter Magazine
ወደ ኢትዮጵያ ለሚገባ ኩባንያ ዕድሉ ሰፊ ነው የሚሉት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፣ ያን ለመረዳት ጊዜ ወስዶ ኢኮኖሚው እንዴት እንደሚንቀሳቀስ፣ ባህሉ ምን እንደሚመስል መረዳት ትልቁ ቀዳሚ ሥራ መሆኑንና ይህንን ለመረዳት በቂ ትዕግሥት ያስፈልጋል በማለት ተናግረዋል፡፡
የምሥራቅ አፍሪካና የመካከለኛው ምሥራቅ የኖኪያ ፕሬዚዳንት ሚኮክ ላቫንቲ በበኩላቸው፣ ሦስተኛ የቴሌኮም ኦፕሬተር በኢትዮጵያ መግባቱ በዘርፉ የበለጠ ኢንቨስት ለማድረግ ተጨማሪ ሀብት ማምጣት ያስችላል ብለዋል፡፡
የሳፋሪኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ በኢትዮጵያ የኢንተርኔት ኔትወርክ እያለም በአጠቃላይ ካሉት የስልክ ቀፎዎች ስማርት ስልኮች ያላቸው ከግማሽ በታች በመሆናቸው፣ ለሚፈለገው ተደራሽነት ትልቅ መሰናክል መሆኑን ተናግረዋል፡፡
From The Reporter Magazine
የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር አማካሪ አቶ አብዮት በቶ፣ ባለፉት አምስት ዓመታት የሞባይል ተጠቃሚዎች ቁጥር በመሠረታዊነት መቀየሩን ገልጸዋል፡፡ በዚህም የሞባይል ስልክ ተጠቃሚዎች ቁጥር ወደ 90 ሚሊዮን መድረሱን፣ የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች ቁጥር ደግሞ 55 ሚሊዮን፣ እንዲሁም የዲጂታል ክፍያ ተጠቃሚዎች ቁጥር 60 ሚሊዮን ደርሷል ብለዋል፡፡
ይሁን እንጂ አሁንም ከፍተኛው ቁጥር ላይ ለመድረስ ገና መሆኑን ገልጸው፣ ዕድገቱን የበለጠ ለማሳካት የቴሌኮም መሠረተ ልማቶችን ማሟላት የመጀመሪያ ቅድሚያ እንደሚሆን አስረድተዋል፡፡
በአውሮፓ ኅብረትና በኢትዮጵያ ቢዝነስ ፎረም ጉባዔ ላይ የአውሮፓ ኅብረት ዓለም አቀፍ ትብብር ኮሚሽነር ጄዜፍ ሰከላ፣ የገንዘብ ሚኒስትር ደኤታዋ ወ/ሮ ሰመሪታ ሰዋሰው፣ የአውሮፓ ኅብረት አገሮች አምባሳደሮች፣ በኢትዮጵያ መዋዕለ ንዋያቸውን ያፈሰሱ የኩባንያ ኃላፊዎችና ተወካዮችን ጨምሮ በርካታ ተሳታፊዎች ተገኝተዋል፡፡