የኢትዮጵያ የግል ዘርፍ በተደጋጋሚ ከሚያነሳቸው ጥያቄዎች መካከል የፋይናንስና የውጭ ምንዛሪ እጥረት በዋናነት ይጠቀሳል፡፡ በተለይ በማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ዘርፍ ውስጥ ይህ ችግር ጎልቶ የሚታይ መሆኑ በየመድረኩ የሚነሳ ጉዳይ ነው፡፡ የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ፣ የፀጥታ ችግር፣ የጥሬ ዕቃ አቅርቦት እጥረት፣ ኢንዱስትሪዎቻቸውን ለማስፋፋት ገጠመን የሚሉት የቦታ ችግሮችና የመሳሰሉ ጥያቄዎች ቢኖራቸውም፣ ከፋይናንስ ጋር የተያያዘው ችግር ግን ከሁሉም ተግዳሮቶቻቸው በላይ እንደሆነ ሲገልጹ መስማት የተለመደ ነው፡፡
በማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ላይ ከ20 ዓመታት በላይ የሠሩትና የአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፉን የሚወክለው የኢትዮጵያ ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት ሆነው ሲያገለግሉ የቆዩት አቶ አበባየሁ ግርማ እንደሚገልጹትም፣ አምራች ኢንዱስትሪዎች ያለባቸው የፋይናንስ እጥረት ካሰቡት ለመድረስ ወደኋላ እየጎተታቸው ነው። ዘርፉን ወደፊት ለማራመድ ዋና ዋና ተብለው ከሚጠቀሱ ተግዳሮቶች ውስጥ አንዱ የፋይናንስ አቅርቦት ችግርና የውጭ ምንዛሪ ለማግኘት ያለው አበሳና ቢሮክራሲ እንደሆነም ይጠቅሳሉ፡፡
ለአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ ከባንኮች እየቀረበ ያለውም ብድር አሁን አሁን መጠነኛ መሻሻል ታየበት እንጂ፣ የኢትዮጵያ ባንኮች በየዓመቱ ከሚያበድሩት ጠቅላላ ብድር ውስጥ አሥር በመቶ ያልሞላ መሆኑንም አስታውሰዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት ባንኮች ከ90 በመቶ በላይ ብድራቸው ወደ ግሉ ዘርፍ የሚፈስ ነው በሚባልበት ወቅት እንኳን፣ ለአምራች ኢንዱስትሪ የደረሰው ተነጥሎ ሲታይ ከ15 በመቶ የበለጠ እንዳልሆነ አቶ አበባየሁ ይገልጻሉ። ይህ የሚያሳው ዘርፉ ለአገራዊ ኢኮኖሚው ሊሰጥ የሚችለውን ጠቀሜታ ያገናዘበ የፋይናንስ አቅርቦት እያገኘ ያለመሆኑን ነው፡፡ ኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅም እንዲገደብ እንደ ምክንያት ሊቀርብ የሚል ችግር ካለም ይኼው የፋይናንስ እጥረት ስለመሆኑ አብራርተው፣ የውጭ ምንዛሪ እጥረቱም በተመሳሳይ የሚገለጽ ነው ይላሉ፡፡ ለጥሬ ዕቃ ግዥ የሚሆን የውጭ ምንዛሪ በማጣት ፋብሪካዎች ሲቆሙ መታየታቸውን፣ አሁን በአንፃራዊነት የውጭ ምንዛሪ አቅርቦት ቢኖርም ችግሩ ዘላቂ መፍትሔ እንደሚሻው ሳያመለክቱ አላለፉም፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የተከታታይ ዓመታት መረጃዎች እንደሚያሳዩት ባንኮች ለኢንዱስትሪው ዘርፍ የሚሰጡት ብድር ከጠቅላላ ብድራቸው አንፃር ሲታይ ከ15 በመቶ ያልበለጠ ነው፡፡
ባንኮች ለተለያዩ ዘርፎች የሚሰጡት ብድር ከባንክ ባንክ የተለያየ ቢሆንም፣ ሁሉም ባንች ቅድሚያ የሚሰጡት ትርፍ የሚያስገኝላቸውን ዘርፍ ነው፡፡ ለአብዛኛዎቹ ባንኮች ከብድር አቅርቦት አንፃር የማኑፋክቸሪንግ በአራተኛና አምስተኛ ደረጃ ላይ የሚቀመጥ ነው፡፡
በመንግሥት ባለቤትነት ሥር የሚገኙት የኢትዮጵያ ልማት ባንክና የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ለኢንዱስትሪ ዘርፍ የሚሰጡት ብር ከፍ ብሎ መታየቱ በድምር ሲታይ ለኢንዱስትሪ የሚቀርብ ብድር እስከ 15 በመቶ ድረስ እንዲደርስ አድርጎታል እንጂ፣ የግል ባንኮች ለአምራቹ ኢንዱስትሪው ዘርፍ የሚሰጡት ብድር ከሌሎች ዘርፎች ጋር ሲነፃፀር አነስተኛ ስለመሆኑ የአቶ አበባየሁ ማብራሪያ ያመለክታል፡፡
From The Reporter Magazine
እስካሁን በነበረው አሠራር የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ የሚገጥማቸው የፋይናንስ አቅርቦት እጥረት የተለየ ምክንያት አለው የሚሉት የኢኮኖሚ ባለሙያው አወት ተክኤ በበኩላቸው፣ አንዱ ብድር ለማግኘት የሚጠየቀው የብድር ማስያዣ (ኮላተራል) ከፍተኛ ሆኖ መገኘት ነው፡፡ በተለይ ለአነስተኛ፣ መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች ብድር ለመስጠት የሚጠየቀው የማስያዣ መጠን ከሚጠየቀው ብድር ሁለትና ሦስት እጥፍ መሆኑ ለዘርፉ የሚሰጠውን ብድር መጠን ዕድገት እንዳቀጨጨው ገልጸዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት በባንኮች ላይ የተጣለው ዓመታዊ የብድር ዕድገት ገደብም ሌላው ችግር መሆኑን የጠቀሱት አቶ አወት፣ የባንኮች የብድር ወለድ መጠናቸው ከፍተኛ ሆኖ መገኘትም ሌላው ተጠቃሽ ጉዳይ መሆኑን ያመለክታል፡፡ የኢንዱስትሪዎቹ አንፃርም በጋራና በትብበር ወይም ተቀናጅቶ አለመሥራት ለፋይናንስ እጥረት ያጋልጣቸዋል፡፡ እንዲህ ያሉ ሁኔታዎች ተደጋግሞ መታየት ዕድገታቸውን ገትቷቸዋል፡፡
ለችግሩ ማሳያ አድርገው የጠቀሱት ባለፉት ሦስት ዓመታት በኢትዮጵያ ትልልቅ የሚባሉ ኢንዱስትሪዎች ውስጥ 29 በመቶ የሚሆኑት ብቻ የፋይናስ አቅርቦት ማግኘታቸውን ነው። ባለፉት ሦስት ዓመታት የፋይናንስ አቅርቦት ያገኙት አነስተኛ መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች ደግሞ ከአራት በመቶ በታች መሆናቸውን በመጥቀስ ያለውን የፋይናንስ ክፍተት አመላክተዋል፡፡
From The Reporter Magazine
ሰሞኑን በተዘጋጀው ኢትዮጵያ ታምርት ኤግዚቢሽን ላይ የተገኙት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ አንዱስትሪ ዘርፉ ያለበትን የፋይናንስ እጥረት ለማቃለል መንግሥት አንድ ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ አንድ ሕግ እንደሚወጣ ይፋ አድርገዋል፡፡ ይህ ሕግ ባንኮች ለኢንዱስሪዎች የሚያቀርቡትን የብድር መጠን ከፍ የሚያደርግና ከጠቅላላ ብድራቸው ለኢንዱስትሪው ዘርፍ የሚወጣው ብድር እንዲለይ የሚያደርግ ነው፡፡
ለዘርፉ እየቀረበ ያለው ብድር በቂ ባለመሆኑ ታሳቢ ተደርጎ ይወጣል የተባለው ይህ አዲስ ሕግ ምን ዓይነት ይዘትና አስገዳጅ ድንጋጌዎች ይኖሩታል? የሚለው ጉዳይ ባይታወቅም፣ ለዘርፉ የተደረገው የፋይናንስ አቅርቦት ግን ከፍ የሚል መሆኑን የሚያረጋግጥ ነው፡፡
መንግሥት የኢንዱስትሪውን ወይም የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉን አንገብጋቢ የተባለ ችግር ከግምት በማስገባት እንዲህ ወዳለው ውሳኔ ላይ መግባቱ ተገቢ ነው የሚሉት አቶ አበባየሁ፣ ለዕርምጃው አድናቆትና ምሥጋና አለኝ ብለዋል፡፡
‹‹አሁን ባለው ሁኔታ መንግሥት ኢንዱስትሪውን ባልተንሸዋረረ ሁኔታ እያየ ነው ማለት ነው፡፡ ወይም እኛ የምንሰጣቸውን ጉድለቶችና ክፍተቶች ተቀብሎ እየሄደ መሆኑን የሚያመላክት ስለመሆኑም ማሳያ መሆኑን አክለዋል፡፡
ይወጣል የተባለው ሕግ የፋይናንስ አቅርቦትን ከማሻሻልና መጠኑን ከፍ ከማድረግ ባሻገር፣ አጠቃላይ የብድር አሰጣጡና ትግበራው ላይም ትኩረት ያስፈልገዋል፡፡ አሁን በሥራ ላይ ባለው መመርያ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ በተወሰነ ደረጃ ለማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ ቅድሚያ የሚሰጥበት አሠራር ቢኖረውም፣ ወደ ባንኮች ሲሄድ ብዙ ችግሮች ያሉበት ስለመሆኑ ያስታውሳሉ፡፡ ኢንዱስትሪውን እንዲደግፍ ቢፈለግም በቀጥታ መደረግ አለበት ተብሎ አስገዳጅ ነገር የለም፡፡ አንዳንዴ ባንኮች ለኢንዱስትሪው ብድር ቢፈቅዱልም በተግባር ግን ብድሩን ለመመለስ አስቻይ ያልሆኑ ሁኔታዎች ያስቀምጣሉ፡፡
ለምሳሌ ብድሩ የመመለሻ ጊዜውን ያሳጥሩታል፡፡ ስለዚህ ብድሩን ፈቅደዋል፣ ነገር ግን በዚያ ጊዜ ውስጥ መመለስ አዳጋች ስለሚሆን ብድሩ ይንጠለጠላል፡፡ ስለዚህ አዲሱ ድንጋጌ ውስጥ መካተት ካለባቸው ድንጋጌዎች ውስጥ ለማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ የሚሰጥ ብድር የረዥም ጊዜ መሆን እንዳለበት በግልጽ መቀመጥ እንደሚኖርበትም ገልጸዋል፡፡ የብድር ማስያዣ ንብረት መጠን ከፍተኛ ሆኖ መገኘትም ቸግር መሆኑን ገልጸው፣ ይህ ጉዳይም የአዲሱ ሕግ አካል መሆን አለበት የሚል እምነት አላቸው፡፡
አዲሱ ይወጣል ተብሎ የተገለጸ ሕግ የፋይናንስ አቅርቦትን ከማፀደቅ ሌላ፣ ከወለድ ምጣኔ ጋር የተያያዙ ችግሮችንም ሊፈታ እንደሚገባ አቶ አበባየሁ ተናግረዋል፡፡ በኢትዮጵያ ያሉ ባንኮች አሁን የሚያስከፍሉት የብድር ወለድ ምጣኔ ከፍተኛ እየሆነ ከመምጣቱ አንፃር፣ ይህንን ታሳቢ ያደረገ ድንጋጌ ሊካተት ይገባል የሚል እምነት አላቸው፡፡ አምራች ኢንዱስትሪትውን ለመደገፍ የሚወጣ ሕግ ከሆነ ለማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ የሚሰጠው ብድር ከፍ ሊያደርግ የሚያስችል ይሆናል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን፣ የወለድ ምጣኔም ከሌሎች ዘርፎች ሊለይ መቻል እንደሚኖርበት አቶ አበባየሁ ይገልጻሉ፡፡ ወለድ ምጣኔም ከሌሎች ዘርፎች ሊለይ መቻል እንደሚኖርበት አመልክተዋል፡፡
የባንኮች የብድር ወለድ የከተማውን አሠራር በየጊዜውና በየወቅቱ ከሚከሰት የዋጋ ንረት ጋር የተሳሰረ ስለሆነ፣ የወለድ ምጣኔው እየጨመረ ይሄዳል፡፡ ስለዚህ ይወጣል የተባለው ሕግ ለኢንዱስትሪው ዘርፍ የሚሰጥ ብድር የጊዜ ገደብ ተሰጥቶት ወለዱም ቋሚ ምጣኔ እንዲኖረው ያስፈልጋል፡፡
የማፋክቸሪንግ ዘርፍ የሚያጋጥመውን የፋይናንስ እጥረት በተመለከተ፣ አሁን መንግሥት አወጣዋለሁ የሚለው ሕግ ቢሻር የበለጠ ጠቀሜታ ሊሰጥ የሚችለው ግን ራሱን የቻለ የኢንዱስትሪ ባንክ ማቋቋም መሆኑን አቶ አበባየሁ ይምናሉ፡፡
ይህንን ጥያቄ ከዚህ ቀደም ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመሩት አንድ የውይይት መድረክ ላይ ማንሳታቸውን በማስታወስ መንግሥት የኢንዱስትሪውን ዘርፍ የፋይናንስ ችግር ለመፍታት ከታሰበው አዲስ አሠራር ጎን ለጎን፣ የኢንዱስትሪ ባንክ ማቋቋም በብርቱ መታሰብ ያለበት ጉዳይ ስለመሆኑና እስካሁንም እንዲህ ያለ ባንክ ማቋቋም አለመቻሉ ሊያስቆጭ እንደሚገባ ጠቅሰዋል፡፡
‹‹በተቻለ መጠን በዘርፉ ያለን ተዋንያኖችና የመንግሥትም ድጋፍ ተጨምሮ አንድ ኢንዱስትሪ ባንክ ማቋቋም አስፈላጊ ነው፤›› ያሉት አቶ አበባየሁ፣ ሌላው ቢቀር ባንኮች ይዋሃዱ እየተባለ ስለሆነ፣ ከሚዋሃዱ ባንኮች መካከል አንዱ የኢንዱስትሪ ባንክ ሆኖ እንዲወጣ ማድረግ የሚቻልበት ዕድል መኖሩንም ጠቅሰዋል፡፡
ባንኮች አሁን ተገደው ለኢንዱስትሪ ዘርፍ ይህንን ያህል አበድሩ ከሚለው አሠራር በተሻለ ጠቃሚ የሚሆነው፣ ዘርፉን የሚመለከት ባንክ መኖር የተሻለ ሊሆን የሚችልበት ሁኔታ ይኖረዋል፡፡
የግል ባንኮች አሠራር ትርፍን መሠረት ያደረገ እስከሆነ ድረስ፣ በአስገዳጅነት የሚተገበር የብድር አሰጣጥ ዘላቂ መፍትሔ ሊያመጣ ስለማይቻልና ፍላጎቱም እያደገ ስለሚመጣ የብድር ጥቄያው ራሱን በቻለ ባንከ መደገፍ ጠቃሚ እንደሚሆንም አብራርተዋል፡፡ ይህ ማለት ባንኮች ለኢንዱትሪው አያበድሩ ማለት ሳይሆን ራሱን በቻለ ኢንዱስትሪውን ቢደግፉ የብድር ጥያቄ ፍላጎትን ስለሚደግፍ ነው፡፡
የኢኮኖሚው ባለሙያው አቶ አወት፣ መንግሥት የቅድሚያ ሊሰጠው ይገባል ብሎ ከለያቸው ዘርፎች ውስጥ ኢንዱስትሪው አንዱ በመሆኑ፣ ይወጣል የተባለው ሕግ ባንኮች ከጠቅላላ ብድራቸው የተወሰነ ያህሉን ለኢንዱስትሪው እንዲሰጡ የሚያስገድድ ሊሆን ይችላል፡፡
ለምሳሌ ከጠቅላላ ብድራቸው 20 እና 30 በመቶ ለኢንዱስትሪው አበድሩ የሚል ከሆነ ይህ ውሳኔ ዘርፉን ሊያግዝ ይችላል ዘላቂ መፍትሔ ግን ይሆናል ባለው አያምኑም፡፡ ተፅዕኖም ቢኖረው እንደሚችል ጠቁመዋል፡፡ ዘላቂ ላይሆን የማይችለው ባንኮች ይህንን ብድር የሚሰጡት ካላቸው ገንዘብ ላይ ነው፡፡ ተጨማሪ ካፒታል አሰባስበው አይለደም፡፡ ዘርፉ ደግሞ ካፒታል የሚፈልግ ነው፡፡ ስለዚህ የሚሰጡት ብድር ዘርፉን ለያዩት እንጂ መጠኑ ያው ነው፡፡ ይህ ሲሆን ደግም ለተወሰነ ጊዜም ቢሆን ለኢንዱስትሪው ብልጫ ያለው ብድር ማቅረብ ያስችላል፡፡ ሌላው ዘርፍ ግን ስለሚያስርብ ከዚህ ሌላ ሌሎች አማራጮች መታየት ይኖባቸዋል የሚል ትንተና ሰጥተዋል፡፡
አሁን እየታሰበ ያለው ሕግ ጊዜያዊ መፍትሔ ሆኖ ለዘላቄታው ግን ኢንዱስትሪዎች በካፒታል ገበያ በኩል ፋይናንስ እንዲቀርብላቸው የሚያስችል አሠራር በተለየ ትኩረት መተግበር አንዱ ሊሆን ይችላል፡፡ አሁን እየተስፋፋ ያለውን የዲጂታል የብድር አቅርቦት በማስፋት በአማራጭነትን ኢንዱትሪውን ወደሚደግፍበት ሁኔታ ማመቻቸትም ጠቃሚ እንደሚሆን ገልጸዋል፡፡
መንግሥት ያወጣል ተብሎ የሚጠበቀው አዲስ ሕግ ታሳቢ ሊያደርገው ይገባል ተብሎ ከጠቀሷቸው ውስጥ ለኢንዱስትሪው ዘርፍ ሊፈቀድ የሚችለው የብድር መጠን የትናንቱን ኢንዱስትሪዎች ሊመልስ የሚገባ መሆኑን ነው፡፡ በእሳቸው እምነት የበለጠ ድጋፍ የሚገባው ተተኪ የሆኑ ምርቶችን የሚያመርቱ ኢንዱስትሪዎች መሆን ይገባቸዋል፡፡ ይህ ብቻ አይደለም፣ ኢንዱስትሪ ወይም አምራች ዘርፍ በሚል የሚጠቀሱ በአሥር ሺዎች የሚቆጠሩ በመሆኑ፣ በሁሉም ደረጃዎች ላይ ያሉ አምራቾች ሊወጣ በሚችለው መሥፈርት መሠረት ብድሩን ማሰባጠር ያስፈልጋል፡፡
አነስተኛ፣ መካከለኛና ከፍተኛ ኢንዱስትሪዎች እንደ ጠቀሜታቸውና አስፈላጊነታቸው ሊሰጣቸው የሚችለው የብድር መጠንና የወለድ ምጣኔ በማያሻማ መልኩ ሊቀመጥ ይገባል፡፡ አንዳንዴ በመቶኛ የሚቀመጥ አሠራር ችግር እንዳይፈጥር ማድረግ ይገባል፡፡
ይህም አንድ ባንክ ከዓመት አንድ ቢሊዮን ብር ለኢንዱስትሪ ማበደር አለበት ከተባለ፣ አንድ ቢሊዮን ብሩን ለአንድ ወይም ለሁለት ድርጅቶች ባንኮች ማኑፋክቸሪንግ ዘርፉን እየደገፉ ከሄዱ በተዘዋዋሪ እነሱም እየተጠቀሙ ይሄዳሉ የሚል እምነት ነው ያላቸው፡፡ በተለይ አምርተው ለውጭ ገበያ የሚያቀርቡ ካሉ ግብይቱን በእነሱ በኩል የሚካሄድ ከሆነ ተጨማሪ የውጭ ምንዛሪ ገቢ ሊያገኙ ይችላሉ፡፡ ሰጥቶ እኔ ከጠቅላላ ብድሬ ይህንን ያህል ብድር ሰጥቻለሁ ሊል ይችላል፡፡ ስለዚህ ዘርፉን ለመደገፍ ሊሰጥ የሚገባው ብድር ለጥቂቶች ብቻ የሚያደላ ሊሆን ስለሚችል ሕጉ ወደ ሥራ ሲገባ እንዲህ ያሉ አሻሚ የሆኑ ነገሮችን ሁሉ አጥርቶ ሊወጣ ይገባል የሚል እምነት አላቸው፡፡
ዛሬ ከመካከለኛ ኢንዱስትሪው ወደ ከፍተኛ ኢንዱስትሪ እየተሸጋገሩ ያሉት ስለዚህ በተመረጡ ዘርፎች ብቻ ተብሎ ምርጫ የሚደረግ ከሆነ፣ ሀብቱን ወደ አንድ አካባቢ ብቻ ማከማቸት ብቻ የሚለውን አቶ አበባየሁ እኔ በግሌ አልደግፈውም ብለዋል፡፡ ባይሆን ለተወሰኑ የሚለው ነገር ቀርቶ ለአገራዊ ኢኮኖሚው በሚሰጠው ጠቀሜታ ያላቸው ተብሎ ለምሳሌ ተኪ ምርት አምራቾች፣ አምርቶ ላኪዎች ፕራዮሪቲ ይሰጣሉ ተብሎ፣ ሌሎቹ ግን በሚወጣው መሥፈርት ድጋፍ ማግኘት ይኖርባቸዋል፡፡
ስለዚህ እንደመደበኛው የገንዘብ መጠን ትንሹም ትልቁም ተጠቃሚ መሆን አለባቸው፡፡ ለእኔ ፋብሪካ ግብዓት የሚያቀርቡ በማክሮ ፋይናስ ደረጃ ያሉ አምራቾች ታሳቢ ተደርገው ነው፡፡ የብድር ተጠቃሚ ካልሆኑ የእኔ ብድር ማግኘት ብቻ ሊገኝ የሚችለው ዓመት ላይ ተፅዕኖ ስለሚያሳርፍ ብድሩ ትልቁንም ትንሹንም መመመልከት ይኖርበታል ያሉት አቶ አበባየሁ፣ ሕጉም በሚስማማ መልኩ ቢወጣ ይገባል፡፡
በማኑፋክቸሪንግ ዘርፉን እንዲደግፍ ሲባል በፋይናንስ አቅርቦት ብቻ ሊወሰን አይገባም የሚል ሐሳብ ይነሳል፡፡ አቶ አበባየሁም፣ በዚህ ይስማማሉ፡፡ ማኑፋክቸሪንግ ዘርፉን እንደግፋለን የሚለው ነጋ ጠባ ይነገራል፡፡ ለምሳሌ ከታክስ አንፃር በቅርቡ በተደረገው የግብር አዋጅ ማሻሻያ ኢንዱስትሪው እንደ የትኛውም ንግድ ነው፡፡ እንዲህ ያሉ ኢንዱስትሪውን ዘርፍ ለመደገፍ መንግሥት አወጣዋለሁ ባለው ሕግ ዙሪያ አስተያየት ለመስጠት፣ አሁን ላይ ከባድ ቢሆንም፣ ዓላማው ዘርፉን መደገፍ እንደሆነ የገለጸ አንድ የኢኮኖሚ ባለሙያ፣ እንዲህ ያሉ ሕጎች ግን አዲስ አለመሆናቸውን ሳይገልጹ አላለፉም፡፡
ከዚህ ቀደም የብድርና የውጭ ምንዛሪ አቅርቦቶችን በተመለከተ ቅድሚያ ለእነዚህ ምርቶችና ዘርፎች ይሰጥ የሚል አሠራር ሲተገበር ቆይቷል፡፡ እነዚህ አሠራሮች ቅድሚያ ሊሰጣቸው ይገባል ከተባለ የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ አንዱ ነበር፡፡
በተለይ ከውጭ ምንዛሪ አቅርቦት ጋር በተያያዘ ቅድሚያ ይሰጣቸው ተብለው ከተጠቀሱት ውስጥ ነዳጅ፣ ማዳበሪያና መድኃኒቶችና የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ ነው፡፡ ነገር ግን በነበረው የውጭ ምንዛሪ እጥረት ማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ከቀዳሚዎቹ ሦስት ምርቶች የሚያስፈለጋቸው የውጭ ምንዛሪ ከተሟላ በኋላ በመሆኑ፣ የሚያስተናገዱበት ማኑፋክቸሪንጉ ወረፋ ጥበቃ ረዥም ጊዜ ይቆዩ እንደነበር መጥቀስ፣ አሁንም በብድር አቅርቦት ተመሳሳይ ችግር እንዳይፈጠር የቀድሞ አሠራሮች ምን አስገኙ? የሚለው መታየት እንዳለበት ይገልጻሉ፡፡
እንደ ባንክ ባለሙያው ማብራሪያ ኢንዱስትሪ ተብሎ ለየትኛው የኢንዱስትሪ ዓይነት የሚለው ጥያቄ መልስ ሊያገኝ ይገባል ብለዋል፡፡ ማኑፋክቸሪንግ ተብሎ ብዙኃኑን የማይጠቅም ቅጣት አዘል ሊባል የሚችለውን መለየት ያስፈልጋል፡፡ በተለይ አብዛኛዎቹ ሸማቾች ጋር ግንኙነት ያላቸው ምርቶችን የሚያመርቱ ኢንዱስትሪዎች ከሆኑ ለእነሱ ቅድሚያ መስጠት ተገቢ መሆኑን ሳያመለክቱ አላለፉም፡፡
አዲስ ይወጣል የተባለው ሕግ ዙሪያ ያነጋገርናቸው ሌላው የባንክ ባለሙያ በበኩላቸው፣ አንድን ዘርፍ ለማገዝ ከተፈለገ ባንኮች ከጠቅላለ ብድራቸው ይህንን ያህል በመቶ የሚሆነውን ቅድሚያ ሊሰጠው ለተፈለገው ዘርፍ ይሰጥ የሚለው አሠራር፣ በሌሎች አገሮችም የተለመደ ነው ብለዋል፡፡ ልክ አሁን ኢትዮጵያ ለኢንዱስትሪው ዘርፍ የሚሰጠው የብድር መጠን ይህንን ያህል ይሁን ተብሎ እንደታሰበው እንደ አገር ከታሰበ ሊበረታ የሚችል መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግር መረዳት የቻሉት አዲስ የሚወጣው ሕገ ባንኮሰች ከጠቅላላ ብድራቸው ይህንን ያህል በመቶ የሚሆነውን ለማኑፋቸሪንግ ዘርፍ እንዲሰጡ ሊያስገድድ የሚችል ነው፡፡
አንዱስትሪውን ለማሳግ እስከሆነ ድረስ ባንኮች ይደግፉታል የሚል እምነት ያላቸው እኚህ ባለሙያ፣ ችግሩ ግን አሁን ያለው የባንኮች 24 በመቶ የብድር ገደብ እያለ በዚሁ ላይ ይተግበር የሚባል ከሆነ ለባንኮች አስቸጋሪ ሊሆን እንደሚችል ገልጸዋል፡፡
አሁን ባንኮች የምንሰጠው ብድር ለዚህ ዘርፍ ይህንን ያህል ስጡ የሚል አሠራር የለም ያሉት የባንክ ባለሙያው፣ አሁን ያለው መመርያ የብድር መጠናቸው ከ24 በመቶ በላይ መሆን የለበትም የሚል ነው፡፡ ለፈለጉት ዘርፍ የፈለጉትን ያህል እንዲያበድሩ የሚፈቅድ ነው፡፡ ይወጣል ተብሎ የሚጠበቀው ሕግ ግን ከጠቅላላ ብድራችሁ ይህንን ያህል ለማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ መሆን አለበት የሚል ሆኗል ማለት ነው፡፡
ይህ ሕግ በእርግጥም ለማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ አጋዥ ሊሆን ይችላል ያሉት ባለሙያው፣ ማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ውስጥ ያሉ አካላት ካለባቸው በሚቀመጠው መሥፈርት መሠረት ተጠቃሚ ሊያደርጋቸው እንደሚችል አስታውቀዋል፡፡ ሆኖም ‹‹የሚወጣው ሕግ እንዴት ይተገበራል?›› የሚለው ላይ ሕጉ በሚገባ ሊያስቀምጣቸው የሚገቡ ጉዳዮች እንዳሉ ግን ሳይገልጹ አላለፉም፡፡
አቶ አወት ለማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ እየቀረበ ያለው የብድር አቅርቦት እጥረት ቢታይበትም፣ መሻሻሎች ያሳየ ስለመሆኑ ግን ይገልጻሉ፡፡ ከለውጡ በፊት የነበረውና አሁን ባለው መካከል ሰፊ ልዩነት ያለው መሆኑንም አመልክተዋል፡፡ ይህንን ወደ በለጠ ደረጃ ለማሳደግ ግን ባንኮችም ሆኑ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ሪስክ ለመቀነስ ብለው እየሠሩባቸው ያሉ ድንጋጌዎችን ማላላት እጅግ ጠቃሚ ስለመሆኑ ገልጸዋል፡፡
ዘርፉን ለመደገፍ መታየትና መስተካከል አለበት ብለው ከገለጹት ውስጥ መንግሥት በማስያዣ ላይ እየተገበረ ያለውን ሕግ ማሻሻል አንዱ ነው፡፡ አሁን ይወጣል የተባለው ሕግም ቢሆን አሁን ባለው የብድር ማስያዣ ድንጋጌ ምን ያህሉን ሊስተናገድ ይችላል የሚለውን ማየት እንዳለባቸው ገልጸዋል፡፡
ለብድር እንቅፋት እየሆነ ያለው የማስያዣ ጉዳይ ከሆነ በተለይ ለመካከለኛና ለአነስተኛ ኢንተርፕራይዞች የማስያዣ ጫናቸውን ለመቀነስ መንግሥት ራሱ ዋስ ሊሆን የሚችልበት አሠራር መዘርጋትን ሁሉ የሚጠይቅ በመሆኑ፣ ከብድር አቅርቦት ጋር የተያያዙ መፍትሔዎች እንዲህ ያሉ ነገሮችን ሁሉ ታሳቢ ያደረጉ ሊሆን ይገባል፡፡ አዳዲስ የብድር ፕሮጀክቶችም ገበያ ውስጥ መፍጠር አስፈላጊ መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡
