የቴክኖሎጂውን ፈጣን ዕድገት ተከትሎ ተማሪዎች በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ሆነው እንዲወጡ የሰው ሠራሽ አስተውሎትን (AI) በሥርዓተ ትምህርት ለማካተት፣ የካሪኩለም ክለሳና ማሻሻያ እየተደረገ መሆኑን የትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ።
ሰው ሠራሽ አስተውሎት በምርምር፣ በሳይንሳዊ ሥራዎች፣ እንዲሁም በመማር ማስተማር ሒደት ውስጥ ዕገዛ እንዲያደርግ ፍላጎት በመኖሩ በሥርዓተ ትምህርት አካቶ ለመተግበር ማሻሻያ እየተደረገ መሆኑን፣ በትምህርት ሚኒስቴር የምርምርና የማኅበረሰብ ጉድኝት ሥራ አስፈጻሚ ሠራዊት ሃንዲሶ (ዶ/ር) ተናግረዋል።
ሥራ አስፈጻሚው ይህንን ያሉት ቅድስት ማርያም ዩኒቨርሲቲ ከመዳ ወላቡና ከወለጋ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር «ዘርፈ ብዙ ምርምር ለዘላቂ ልማት» በሚል መሪ ቃል ሰኔ 23 ቀን 2018 ዓ.ም. ባዘጋጀው ሴሚናር ላይ ነው።
ቴክኖሎጂው በዓለም አቀፍ ደረጃ አከራካሪ የሆኑ አጀንዳዎችን ይዞ የመጣ ቢሆንም፣ ትምህርት ሚኒስቴር «ቴክኖሎጂውን እንዴት በአግባቡ እንጠቀም?» በሚለው መርህ ላይ ትኩረት አድርጎ እየሠራ መሆኑን ሥራ አስፈጻሚው አስረድተዋል።
ይሁን እንጂ አሠራሩን ወደ ሕግና የፖሊሲ ማዕቀፍ ከማሳደግ በፊት በቂ ዕውቀትና ግንዛቤ መያዝ ስላለበት፣ በርካታ አካላትን በሒደቱ ላይ ማሳተፍ እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል።
ለዚህም ተስማሚ የአሠራር ሥርዓት ለመዘርጋትና ጉዳዩን በስፋት ለማጥናት እንዲቻል ልምዱና ዕውቀቱ ያላቸው ከተለያዩ የሙያ መስኮች የተውጣጡ ባለሙያዎችን ያካተተ፣ «መልቲ-ዲሲፕሊነሪ» ቡድን ተቋቁሞ ጥናት እየተካሄደ መሆኑን ሠራዊት (ዶ/ር) አስታውቀዋል።
የቴክኖሎጂው የአጠቃቀም ደረጃ ምን መምሰል እንዳለበትና እስከ ምን ድረስ ጥቅም ላይ ሲውል ነው ትክክል የሚባለው የሚለውን መስፈርት በሒደት ለመለየት እየተሠራ መሆኑን ገልጸው፣ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚሠሩ የምርምር ሥራዎችን ውጤታማነት በተመለከተም በአሁኑ ወቅት በአገር ውስጥ በአማካይ በዓመት ከ14 ሺሕ በላይ ምርምሮች እንደሚካሄዱ ጠቁመዋል።
From The Reporter Magazine
ይህም ከፍተኛ ሀብትና የተመራማሪዎች ጉልበት የሚፈስበት በመሆኑ ሚኒስቴሩ ከኅትመት ባለፈ ወደ ተግባር ለማሻገር ኢኒሼቲቭ እየቀረፀ መሆኑን ያስረዱት ሠራዊት (ዶ/ር)፣ ምርምሮች በቀላሉ በኢንዱስትሪው ውስጥ መተግበር እንዲችሉ ‹‹ከምርምር ወደ ንግድ›› የሚል አሠራር መዘርጋቱን አብራርተዋል።
የሰው ሠራሽ አስተውሎት የሚያመነጫቸውን ሥራዎች ለመቆጣጠርና የቅጂ መብት (Copyright) ሕግን አሁን ካለው የቴክኖሎጂ ደረጃ ጋር ለማስማማት የአገር ውስጥና የውጭ አገሮች ተሞክሮዎችን መቃኘት እንደሚያስፈልግ፣ የመዳወላቡ ዩኒቨርሲቲ መምህር ዓለሙ ባልቻ በጉባዔው ላይ ባቀረቡት ጥናት ገልጸዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት በአገር ውስጥ ያለው የቅጂና ተዛማጅ መብቶች ጥበቃ አዋጅ ቁጥር 410/1996 እና የማሻሻያ አዋጁ የኤአይ ቴክኖሎጂዎችንና ተያያዥ ክፍተቶችን ያላካተቱ በመሆናቸው፣ አፋጣኝ ማሻሻያ ማድረግ እንደሚገባ አሳስበዋል።
From The Reporter Magazine
እንደ ዩናይትድ ኪንግደም፣ ቻይና እና ደቡብ አፍሪካ ያሉ አገሮች የኤአይ ሥራዎችንና በኮምፒዩተር የሚመነጩ ፈጠራዎችን ወደ ሕግ ሥርዓታቸው በማስገባት ረገድ ተለዋዋጭና ተግባራዊ አቀራረብ መከተላቸውን የገለጹት ዓለሙ፣ በተለይም ቴክኖሎጂውን ለማሳደግ የሌሎችን በቅጂ መብት የተጠበቁ ሥራዎችን የመጠቀም መብት ይጥሳል ወይስ እንደ ልዩ ሁኔታ ይፈቀዳል የሚለው ምላሽ ሊያገኝ እንደሚገባ ጠቅሰዋል።
በአሁኑ ወቅት ተማሪዎች ሙሉ በሙሉ በኤአይ ቴክኖሎጂ ላይ ጥገኞች እየሆኑ መምጣታቸው በመማር ማስተማሩና በምርምር ሥራዎች ላይ ትልቅ ተግዳሮት እየደቀነ በመሆኑ፣ በትምህርት ተቋማት ደረጃ የተወሰኑ የውስጥ መመርያዎች መዘጋጀታቸውንና እንደ ተርኒቲን (Turnitin) ያሉ ሶፍትዌሮችን በመጠቀም የኤአይ ድርሻን እስከ 30 በመቶ ብቻ ለመቀበል ጥረት እየተደረገ መሆኑን ያስረዱት ዓለሙ፣ ይህንን ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት ትምህርት ሚኒስቴር ማዕከላዊ የሕግ ማዕቀፍና ወጥ መመሪያ ሊያዘጋጅ እንደሚገባ ሐሳብ አቅርበዋል።
በቅድስት ማርያም ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ማኅበረሰብ ግንኙነት ምክትል ፕሬዚዳንት ምሥጋናው ሰለሞን (ዶ/ር) ዘርፈ ብዙ የምርምር ጉባዔዎችን ማዘጋጀት በአንድ ሙያ ላይ ብቻ ያተኮሩ ግኝቶችን ከተለያዩ የሙያ መስኮች፣ ከመምህራን፣ ከተማሪዎችና ከሥራ ላይ ካሉ ባለሙያዎች ጋር በአንድ ጠረጴዛ ዙሪያ በመወያየት የተሻለ አገር በቀል መፍትሔ ለማፈላለግ እንደሚያግዝ ተናግረዋል።
በአሁኑ ወቅት የሰው ሠራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂና የኢትዮጵያ የ2030 ዲጂታላይዜሽን ጉዞ ትልቅ ትኩረት የተሰጠው ጉዳይ በመሆኑ፣ ተቋማት የምርምር ውጤቶቻቸውን ወደ ተግባር በመለወጥ ረገድ ለፖሊሲ አውጪዎችና ለባለድርሻ አካላት የፖሊሲ አቅጣጫዎችን እያመላከቱ መሆኑን ምሥጋናው (ዶ/ር) አብራርተዋል። በተለይም ተማሪዎች በቴክኖሎጂው ብቻ ጥገኞች እንዳይሆኑና አጠቃቀማቸው ላይ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ዩኒቨርሲቲው ተርኒቲን የተባለውን የኮፒራይትና የኤአይ ጽሑፎችን መለያ ሶፍትዌር ተግባራዊ ማድረጉን አስረድተዋል፡፡
በምርምር ሴሚናሩ ላይ የቀረቡት ጥናቶች በአገር ደረጃ ያሉትን የፖሊሲና የአሠራር ክፍተቶች በግልጽ ያሳዩ በመሆናቸው፣ በቀጣይ የሚወጡ ሕጎችንና ስትራቴጂዎችን ለማበልፀግ ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳላቸው ተገልጿል።
በተለይም በባንኪንግና በኢንሹራንስ ኢንዱስትሪው ማነቆዎች፣ እንዲሁም አከራካሪ በሆኑት በኤአይና በኮፒራይት አጠቃቀም ዙሪያ የቀረቡት የምርምር ውጤቶች የባለድርሻ አካላትን ግንዛቤ ከማሳደግ ባለፈ፣ ችግሮችን በማስረጃ ላይ ተመሥርቶ ለመፍታትና ተስማሚ የአጠቃቀም ሥርዓትን ለመቅረጽ እንደ አንድ ትልቅ መነሻ የሚያገለግሉ መሆናቸው ተመላክቷል።