
የዘንድሮውን የእግዚእ ኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል አስመልክተው፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ የካቶሊክና የመካነ ኢየሱስ አብያተ ክርስቲያን አባቶች በዋዜማው ባስተላለፉት መልዕክቶቻቸው አሳሳቢውን አገራዊ ጉዳይ ቃኝተው ነበር፡፡ ከእንኳን አደረሳችሁ ባሻገር ያንፀባረቁትን የሰላም ጥሪ እንደሚከተለው ቀርቧል፡፡
– ቅንብር በሔኖክ ያሬድ


‹‹እርስ በእርስ ለመጠፋፋት መሽቀዳደም ምን ይሉታል? ይህስ ለማን ይበጃል?›› ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ
እግዚአብሔር ሰብአዊነታችንን በምልአተ ተዋሕዶ በዓለማችን እንዲገለጥ የሆነበት ዋና ምክንያት እሱ እንዳስረዳን እኛ በሕይወት እንድንኖር ነው፡፡ ይህንንም ያደረገው ከሁሉ በላይ የሆነ ሌላ ገፊ ኃይል ገፋፍቶት ሳይሆን ድንበር የለሽና ፍጹም ፍቅሩ አነሳስቶት እንደሆነ ከቅዱሳት መጻሕፍት እንረዳለን፡፡ ፍቅሩ እኛ ከምናውቀው ፍቅር ሁሉ በላይ መሆኑንም በዚህ እናስተውላለን፡፡ ለጠላቶቹ ሕይወት ፍቅርና ሰላም ሲል እነሱን ከመሆን አልፎ እስከ ቤዛዊ መሥዋዕት የሚዘልቅ ፍቅር እጅግ በጣም ታላቅ ነው፡፡
እግዚአብሔር ለእኛ ያለው ፈቃድ እኛ በሕይወት በሰላምና በፍቅር እንድንኖርለት ከሆነ የእኛ ግብረ መልስም ከዚህ የተለየ ሊሆን አይገባም፡፡ ታዲያ በቃሉ ለመኖርና ለእሱ ለመታዘዝ ቃል የገባን እኛ ክርስቲያኖች ይህን ሁሉ እርግፍ አድርገን በመተው እርስ በእርስ ለመጠፋፋት መሽቀዳደም ምን ይሉታል? ይህስ ለማን ይበጃል? የአንድ ሀገር ሕዝቦች ይመካከራሉ፣ ይቻቻላሉ፣ ይታገሣሉ፣ ጊዜ ሰጥተው ያስቡና መፍትሔ ያበጃሉ እንጂ ማን በማን ላይ ይነሣል? ይህ ለማንኛችንም አይበጀንምና ወደ አእምሮአችን እንመለስ የሚል ጥሪ የወቅቱ የቤተ ክርስቲያናችን መልእክት ነው፡፡
*****
From The Reporter Magazine


‹‹መገዳደል አብቅቶ ስለ ሰላም ሁሉም ተባብሮ እንዲሠራ ስንል በእግዚአብሔር ስም እንጠይቃለን››
ብፁዕ ካርዲናል አቡነ ብርሃነኢየሱስ
From The Reporter Magazine
የልደት በዓል መሪያችን፣ መጋቢያችን፣ ጠባቂያችን እራሱን የሰጠበት በዓል ስለሆነ ስለ ወገኖችና ስለ ሰው ልጆች ክብር የምንሠራበት፣ ሕዝቦች የሚከባበሩበት፣ የሚዋደዱበትና የሚተሳሰቡበት፤ የጦርነትና የግጭት መንፈስ ከአገራችን የሚወገድበት፤ ሰላም በአገራችንና በሕዝቦቻችን መካከል የሚወርድበትን፣ ከጥፋት ይልቅ ወደ አንድነትና ኅብረት የሚመጡበት፣ የተሰደዱትና የተፈናቀሉ ወገኖቻችን ወደ ስፍራቸውና ቄያቸው የሚመለሱበት፣ ተማሪው በትምህርቱ፣ አርሶ አደሩ በግብርና ሥራው፣ ሠራተኛው በየሥራ መስኩ ተሰማርቶ፣ መገዳደል አብቅቶ ልጆቻችንም ጭንቀትንና ችግርን ሳይወርሱ በንጹህ ሐሳብና ህሊና መልካም ዜጎች ሆነው እንዲኖሩ ስለ ሰላም ሁሉም ተባብሮ እንዲሠራ ስንል በእግዚአብሔር ስም እንጠይቃለን፡፡
*****


‹‹ግጭቶችና አለመረጋጋቶች ተወግደው ፍጹም መግባባት እንዲኖር ሁሉም ሊተጋ ይገባል››
ቄስ ዮናስ ይገዙ (ዶ/ር)፣ የመካነ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን ፕሬዚዳንት
በዓለማችን የሰላም ጉዳይ እጅግ አሳሳቢ በሆነበት በአሁኑ ጊዜ የጌታችን የኢየሱሰ ክርስቶስን የልደት በዓል ስናከብር እግዚአብሔር በራሱና በሰው ልጆች መካከል፣ እንዲሁም በሰው ልጆች መካከል የነበረውን ጥል አስወግዶ ሰላምን ለማውረድ ያደረገውን ማሰብ ብቻ ሳይሆን የክርስቶስን ምሳሌነት ለመከተል መወሰንን ይጨምራል፡፡ በተለይም በአሁን ጊዜ በአገራችን በአንዳንድ አካባቢዎች የሚታዩ ግጭቶችና አለመረጋጋቶች ተወግደው በሕዝቦች ሁሉ መካከል ፍጹም መግባባት እንዲኖር፣ የአገር ልማትና ሁለንተናዊ ዕድገት እውን ይሆን ዘንድ ሰው ሁሉ በየፊናው መልሙን ሁሉ በማድረግ ሊተጋ ይገባል፡፡