- ከ4,400 በላይ ድርጅቶች የንብረት ምዝገባ አለመደረጉ በሪፖርት ተጠቅሷል
የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ሲመዘገቡ ወይም የፈቃድ የምስክር ወረቀት ሲወስዱ ለሥራ በመረጧቸው ክልሎችና የከተማ አስተዳደሮች፣ ምንም ዓይነት እንቅስቃሴ ያላደረጉ መኖራቸውን ማረጋገጡን፣ የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት አስታወቀ፡፡
ዋና ኦዲተር በተለያዩ የባለበጀት የመንግሥት ተቋማት ላይ ያከናወነውን የክዋኔ ኦዲት አፈጻጸምና ዋና ዋና ግኝቶች፣ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሰኔ 11 ቀን 208 ዓ.ም. ሲያቀርብ ነው ይህንን ያስታወቀው፡፡
ኦዲቱ ከተከናወነባቸው ተቋማት መካከክል የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ተቆጣጣሪ ባለሥልጣን ድርጅቶችን ሲመዘግብ ትክክለኛ አድራሻቸውን አጣርቶ ባለመያዙ፣ በድርጅቶቹ ላይ ክትትልና ቁጥጥር ለማድረግ ሲፈለግ በምዝገባ ወቅት በሚሰጡት አድራሻና ስልክ እንደማይገኙና የት እንዳሉ ለማወቅ አለመቻሉን ሪፖርቱ ያስረዳል፡፡
የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶችን ንብረት ምዝገባ በማድረግ መረጃዎችን በማደራጀት ለማረጋገጥ ኦዲት ሲደረግ፣ ባለሥልጣኑ ከ5,000 በላይ ድርጅቶች ውስጥ 631 (12 በመቶ) ብቻ የንብረት ምዝገባ ማድረጉን መረጋገጡ ተገልጿል፡፡ የድርጅቶቹ ንብረቶች የተመዘገቡት ባልተደራጀ ሁኔታና በወቀት መሆኑን፣ ወደ አንድ የመረጃ ቋት (Database) ሥርዓት አለመግባታቸው በኦዲት መረጋገጡ ተመላክቷል፡፡
በሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅትነት ተመዘግበው ነገር ግን የበጎ አድራጎት ሥራ የማይሠሩና ለገቢ ማመንጫ ብቻ እየሠሩ ያሉ ድርጅቶች መኖራቸው የገለጸው የኦዲት ሪፖርቱ ሳንፎርድ፣ ተርኪሽ ማሪፍ፣ ጀርመንና ግሪክ ትምህርት ቤቶች በሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅትነት ቢመዘገቡም፣ የበጎ አድራጎት ሥራ እያከናወኑ እንዳልሆነ በኦዲት መረጋገጡ ተገልጿል፡፡
ባለሥልጣኑ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ተጠቃሚ ያደረጓቸውን ቦታዎች መረጃ በማደራጀት ተጠቃሚዎችን ለመለየት የሚያስችል ጥናት አለማድረጉን፣ መነሻ የሚሆኑ ልየታዎችን በማዘጋጀት ፕሮጀክቶች በሁሉም አካባቢዎች እንዲዳረሱና ፍትሐዊ ሥርጭት እንዲኖር ከሚመለከታቸው አካላት ጋር አለመሠራቱ በሪፖርቱ ተካቷል፡፡ በኦዲት ሪፖርቱ የሲቪል ማኅብረሰብ ድርጅቶች የሥራ ኃላፊዎችን አስተያየት ለማካተት ከተቋሙ ሥራ ኃላፊዎች በተደጋጋሚ ጥረት ቢደረግም ለማካተት አለመቻሉ ተብራርቷል፡፡
ዋና ኦዲተር በጤና ሚኒስቴር የእናቶችና ሕፃናት ሞት ቅነሳ ፕሮግራም አፈጻጸም ውጤታማነትን በተመለከተ ባከናወነው የክዋኔ ኦዲት፣ በአገር አቀፍ ደረጃ በጤና ተቋማት በሠለጠነ የሕክምና ባለሙያ የሚሰጡ የወሊድ አገልግሎቶች ሽፋን አፈጻጸም ግኝቱን በሪፖርቱ አሳይቷል፡፡ በ2015 በጀት ዓመት የአገልግሎት ሽፋኑን ከ68 በመቶ ወደ 73 በመቶ ለማሳደግ ታቅዶ 75 በመቶ ማድረስ እንደተቻለ ሪፖርት የተደረገ ቢሆንም፣ በክልሎች ማለትም አማራ 64 በመቶ፣ አፋር 30 በመቶ፣ ጋምቤላ 41 በመቶ፣ ቤንሻንጉል ጉሙዝ 42 በመቶ፣ ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ 59 በመቶ፣ ሶማሌ 51 በመቶ፣ ድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር 72 በመቶ ከአገሪቱ አማካይ አፈጻጸም በታች ያስመዘገቡ ናቸው ብሏል፡፡
From The Reporter Magazine
በ2016 በጀት ዓመት ሽፋኑን ከ75 በመቶ ወደ 78 በመቶ ለማድረስ ታቅዶ የነበረ መሆኑን፣ ሽፋኑ 74 በመቶ ቢደርስም ይህም ከተቀመጠው ዓመታዊ መነሻ በታች መሆኑን፣ ሰባት ክልሎች (አፋር ክልል 37 በመቶ፣ አማራ 57 በመቶ፣ ሶማሌ 51 በመቶ፣ ቤንሻንጉል ጉሙዝ 45 በመቶ፣ ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ 54 በመቶ፣ ጋምቤላ 44 በመቶ፣ ድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር 71 በመቶ) ከአገራዊ አማካይ አፈጻጸም በታች መሆናቸው ተጠቅሷል፡፡
በአዲስ አበባ ኤርፖርት ጉምሩክ በተለያዩ መንገዶች የተወረሱ ንብረቶች ለሽያጭ የወጣው ጨረታ ቢሰረዝም ግምታዊ ዋጋቸው የ24 ሚሊዮን ብር የሚሆኑት መሸጣቸውን፣ በአዳማ ጉምሩክ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት በጨረታው ሳይወዳደሩ አሸናፊ ለተደረጉ አካላት 23.7 ሚሊዮን ብር የሚያወጡ ዕቃዎች የተሸጡ መሆናቸውን በሪፖርቱ ተመላክቷል፡፡
በሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ሥር በሚገኙ የፌዴራል ግብርና ቴክኒክና ሙያ ማሠልጠኛ ኮሌጆች፣ በኢፌዴሪ የቴክኒና ሙያ ሥልጠና ኢንስቲትዩትና በቱሪዝም ማሠልጠኛ ኢንስቲትዩት ላይ አፈጸጸማቸውን በተመለከተ በተደረገው ኦዲት ተቋማቱ በመቋቋሚያ ደንባቸው መሠረት የሚመሯቸውን ቦርዶች መሰየም የሚገባቸው ቢሆንም፣ ከ2014 ዓ.ም. ጀምሮ ቦርድ እንዳልተሰየመላቸው መገንዘቡን ገልጸዋል፡፡
From The Reporter Magazine
በኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ የኤርፖርት መሠረተ ልማት ሥራዎችና ኤሮኖቲካል ያልሆኑ ገቢዎች አፈጻጸም ውጤታማነትን በተመለከተ አከናወንኩት ባለው ኦዲት፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ የሚያስተዳድራቸው ኤርፖርቶች መሪ ዕቅድ (Master Plan)፣ የመሬት አጠቃቀም ካርታና የይዞታ ካርታ ሊኖራቸው የሚገባ ቢሆንም ከአዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት መሪ ዕቅድ በስተቀር፣ የተቀሩት 22 ኤርፖርቶች እንደሌላቸው አረጋግጫለሁ ብሏል፡፡
