የዲጂታል ግብይትን ለመቆጣጠር መንግሥት ያወጣቸው ሕጎች ቢኖሩም፣ አሁንም ግብይቱን ለማስፋፋት ቀሪ ሥራዎች እንደሚጠበቁ በጥናት ተመላከተ፡፡
የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የንግድ ሥራ ትምህርት ቤት የማርኬቲንግና ማኔጅመንት ትምህርት ክፍል፣ በዲጂታል ዘመን የሚደረጉ ግብይቶችንና የዲጂታል የመገበያያ ዘዴዎችን በሚመለከት፣ ሚያዚያ 29 ቀን 2018 ዓ.ም. ባዘጋጀው የውይይት መድረክ የኢትዮጵያ የዲጂታል ግብይት ጥናቶች ቀርበዋል፡፡
በኢትዮጵያ ያለውን የዲጂታል ግብይት የሚመለከት ጥናት ያቀረቡት የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የንግድ ሥራ ትምህርት ቤት መምህር ምናለ አሻግሬ (ዶ/ር)፣ በመንግሥት ተነሳሽነት የወጡ ሕጎችና መመርያዎች መኖራቸውንና ነገር ግን የዲጂታል ግብይ በሚፈለገው መጠን መስፋፋት እንዲችል አሁንም ቀሪ ሥራዎች እንደሚጠበቁ ተናግረዋል፡፡
አስፈላጊ የሕግ ማዕቀፎችን በሚመለከት ሲያብራሩ በዲጂታል ንግድ ወቅት የሚፈጠርን አለመግባባት ለመፍታት የሚያስችል ግልጽ የሆነ የታክስ ሥርዓት፣ በዲጂታል የታዘዘ ዕቃ ካልተፈለገ የሚመለስበት አሠራር አለመኖር ክፍተት መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የዲጂታል ግብይት እየጨመረ መምጣቱንና በተለይም የተለያዩ የማኅበራዊ ሚዲያዎችን ተጠቅመው ንግድ የሚያካሂዱ ግለሰቦች እየጨመሩ መሆናቸውን ምናለ (ዶ/ር) ተናግረዋል፡፡ ሆኖም ግብይቱን ለማስፋፋት እንቅፋት የሆኑ ምክንያቶችን በዕድሜ፣ በፆታ፣ በገቢ ደረጃ፣ በገጠርና በከተማ ነዋሪዎች በመከፋፈል ባቀረቡት ጥናት አስረድተዋል፡፡
ዝቅተኛ የስማርት ቀፎና የዲጂታል ፋይናንስ አገልግሎት ተደራሽነት አነስተኛ መሆን፣ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሕዝብ በዲጂታል ንግድ እንዳይሳተፍ አድርጎታል ብለዋል፡፡
ዲጂታል ግብይት ሲታሰብ በቅድሚያ ሻጩ በቂ አቅርቦት ስለመኖሩ፣ የደንበኛ ዕውቀትና እምነት ስለማደጉ፣ ግብይቱ የሚካሄድበት የንግድ መድረክ ምን ያህል ጠንካራ ነው የሚለውን ማወቅ እንደሚገባና ንግዱን ለማካሄድ የተዘጋጁ የሕግ ማዕቀፎች ምን ያህል ምቹ ናቸው የሚለውን መመልከት እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
From The Reporter Magazine
የማርኬቲንግ ማኔጅመንት ትምህርት ክፍል ኃላፊ መስፍን ወርቅነህ (ዶ/ር)፣ በኢትዮጵያ የዲጂታል ግብይት ጅማሬ መኖሩንና አንዳንድ ተቋማት ሥራቸውን ወደ ዲጂታል እየቀየሩ መሆናቸውን፣ ሥራዎቹ እንዲጠናከሩና በአገር አቀፍ ደረጃ ውጤት ማምጣት እንዲቻል ተጨማሪ ሥራዎች እንደሚጠበቁ ጠቁመዋል፡፡
ሌሎች ችግሮች እንዳሉ ሆነው በቂ የሆነ የሕግ ማዕቀፍ አለመኖር የዲጂታል ግብይት አፈጻጸም ዝቅተኛ እንዲሆን አድርጎታል ያሉት መስፍን (ዶ/ር)፣ ጥናቶች የሚያሳዩትም ይህን ነው ብለዋል፡፡
መድረኩን ያዘጋጀው የማርኬቲንግና ማኔጅመንት ትምህርት ክፍል ላለፉት 40 ዓመታት በመማር ማስተማር፣ በምርምርና በማኅበረሰብ አገልግሎት ተሳትፎ ሲያደርግ መቆየቱንና ካሪኩለሙን አሁን ካለው የዲጂታል ቴክኖሎጂ ለውጦች ጋር ለማጣጣም ክለሳ ለማካሄድ በዝግጅት ላይ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
From The Reporter Magazine
በዲፕሎማ፣ በዲግሪና በማስተርስ ፕሮግራሞች በርካታ ምሩቃንን በየዓመቱ እንደሚያስመርቅና በሚቀጥለው የትምህርት ዘመን የዶክትሬት ዲግሪ ተማሪዎችን ተቀብሎ ለማስተማር በሴኔት መፅደቁን የትምህርት ክፍሉ ኃላፊ ተናግረዋል፡፡
