በተሾመ ብርሃኑ ከማል
ልዩ ልዩ ስታቲስቲካዊ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት አብዛኛው የዓለም ሕዝብ ወጣት ነው፡፡ በዓለም ላይ እጅግ አስገራሚና አስደናቂ ሥራዎች የተከናወኑትም በአብዛኛው በወጣትነት ዕድሜ ነው፡፡ ስለሆነም አገራችንን ጨምሮ በሌሎች አገሮች ያሉና የነበሩ ወጣቶች ሕዝብ አስተባብረው አገራቸውንና ዓለማቸውን መርተዋል፡፡ በርካታ አሳሾች በመላው ዓለም የተንቀሳቀሱት በወጣትነት ዕድሜያቸው ነው፡፡ ብዙ ነገሮች የተፈጠሩት በወጣትነት ዕድሜ ነው፡፡ የዓለማችን የሃይማኖት መሪዎች እምነታቸውን፣ አመለካከታቸውንና ፍልስፍናቸውን ይዘው ብቅ ያሉት በወጣትነት ዕድሜያቸው ነው፡፡ ጥንትም ሆነ ዛሬ ዓለም የወጣቶች ናት፡፡
በዓለማችን፣ በክፍለ አኅጉራችን፣ በአገራችን ብሎም በክልላችን የሚገኙ ወጣቶች በአፍላ የጉርምስና ጊዜያቸው አንዳች ተግባር አከናውነው ለመታወቅ ይመኛሉ፡፡ ለምሳሌ በአንድ አነስተኛ የገጠር ቀበሌ የሚገኝ ወጣት አንድም በአካባቢው እንዳለ ሀብታም ገበሬ፣ ጀግና ነጭ ለባሽ፣ ወታደር፣ አስተማሪ፣ የሃይማኖት መሪ ወይም ሌላ ለመሆን ይመኛል፡፡ በዞንና በክልል ከተሞች የሚገኝ ወጣት ደግሞ በአካባቢው ከሚያየው፣ በሬዲዮ ከሚሰማው፣ በቴሌቪዥን ከሚመለከተውና በትምህርት ቤት አስተማሪው ከሚነግሩት ትልቅ ሰው መካከል ከእሱ ዝንባሌ ጋር የሚሄደውን አንዱን ወይም ሁለት፣ ሦስቱን በመምረጥና እንደ አርዓያ በመውሰድ ‹‹እኔም እንደ እሱ/እንደ እሷ እሆናለሁ፤›› ብለው ይመኛሉ፡፡ በመሠረቱ በየትኛውም አኅጉርና አገሮች ያሉ ታልልቅ ሰዎችም ታልልቅ የሆኑት በተመሳሳይ ሁኔታ መሆኑን ማስተዋል ያስፈልጋል፡፡
ወጣቶች ትልቅ ሰው ለመሆን አርዓያ የሚያደርጓቸው ወይም እንደ ሞዴል የሚወስዷቸው በልጅነት ዕድሜያቸው በቅድሚያ ያስባሉ፡፡ አባትና እናታቸው፣ ጎረቤቶቻቸውና ጓደኞቻቸው ከሚናገሯቸው ይነሳሉና፡፡ ወጣቶቹ አፍላ የጉርምስና ጊዜቸውን ጨርሰው የሁለተኛና የሦስተኛ ደረጃ ተማሪዎች ሲሆኑ ደግሞ ከክልል ወጣ በማለት በዓለም ታዋቂ ወደ ሆኑት ሰዎች ያተኩራሉ፡፡ አፍሪካን ከቀጥታና ከእጅ አዙር ቅኝ አገዛዝ ነፃ አውጥተው በራሷ አቅጣጫ እንድትጓዝ እንዳደረጓት እንደ ፍሬድሪክ ዳግላስ (1817 እስከ 1895 ዓ.ም.)፣ እንደ ሐሪት ተብማን (1820 እስከ 1913 ዓ.ም.)፣ እንደ ካሪቢያኑ የታሪክ ምሁር፣ ደራሲው፣ ኃያሲውና ፖለቲከኛው ሮበርት ጀምስ (1901 እስከ1989 ዓ.ም.) በአፍሪካና በመላው ዓለም የሚገኙ ጥቁር ሕዝቦች በእኩልነት፣ በወንድማማችነትና በልማት እንዲኖሩ በመታገል ግንባር ቀደም ሰው ሆኖ ለመገኘት፣ እንደ ክዋሜ ኒክሩማህ (1909 እስከ 1972 ዓ.ም.)፣ እንደ ጁሌስ ኔሬሬ (1922 እስከ 1999 ዓ.ም.)፣ በምድረ አሜሪካ ለጥቁሮች ነፃነት እንደታገለው ማርቲን ሉተር ኪነግ (1929 እስከ 1968 ዓ.ም.)፣ እንደ ኒልሰን ማንዴላ ከልጅነታቸው ጀምሮ በአጠቃላይ ለሕዝብ፣ በተለይም ለወገን ዕድገት ያልተቋረጠ ጥረት አድርጎና ስምን ለዘለዓለም በማይረሳ የታሪክ ማኅደር አስፍሮ ማለፍ? ወይስ እንደ ቢልጌት በልፅጎ ለዓለም መለወጥ አስተዋጽኦ ማድረግ? ወይስ እንደ አልበርት አይነሽታይን በሳይንስ ምርምር የዘለዓለም ቁንጮ ሆኖ መኖር?
በአጭሩ በየትኛውም የዕውቀት ዘርፍ ታዋቂ ለመሆን የፈጠራ ችሎታን ማሳደግ ያስፈልጋል፡፡ ፈጠራ ማለት ደግሞ ከዚህ ቀደም ያልነበረውን ነገር ህልውና እንዲኖረው ማድረግ ብዙ ሰዎች ሊያደርጉት የሞከሩት፣ ነገር ግን የሚስጥሩን ቁልፍ አጥተው በጅምር የተውቱን ከፍፃሜ ማድረስ… ሲሆን፣ የሚፈጠረውም ጉዳይ በሳይንስ በኢንዱስትሪ በምሕንድስና፣ በፖለቲካ፣ በኪነ ጥበብ፣ ወዘተ ሊሆን ይችላል፡፡
‹‹ሥነ ባህርይ መግቢያ›› በሚል ርዕስ ኧርነስት አር ሂጋርድና ሪቻርድ አርኪንሰን (Ernest R. Higrad & Richard Arkinson) ስለፈጠራ በተነተኑበት ንዑስ ርዕስ ውስጥ ‹‹ፈጠራ ሥነ ባህሪያዊና ፍልስፍናዊ ገጽታ ሲኖረው በሥነ ባህርይ መልኩ ከግለሰቦች ህሊናዊ አመለካከት ማለት ካካበቱት የሕይወት ገጠመኝ (ልምድ) የሚመነጭ ነው፤›› ሲሉ ጄ.ዋላንስ ደግሞ ‹‹ፈጠራ መዘጋጀትን ለመፍጠር የሚያስችል ሁኔታ ማመቻቸትን መረጃዎችን መሰብሰብንና የተሰበሰበውን መረጃ አቀነባብሮ ለመግለጽ መቻልን ያጠቃልላል›› ይላሉ፡፡
ዶ/ር ጆን ደብሊው ጋርድነር (Dr. John W. Gardner) ግን እያንዳንዱ ትውልድ ለዓለማችን አንድ አዲስ ነገር ፈጥሮ ማለፍ እንዳለበት አበክረው ባሳሰቡበት ጽሐፋቸው፣ ‹‹ወጣቱ ትውልድ (የአባቶቹን አደራ መጠበቅ ብቻ ሳይሆን) የራሱን ታሪክ እንዲሠራ የሚገጥመውን ውስብስብ አዋኪና አስቸጋሪ ሁኔታ ማለፍ እንዳለበት መንገር አለብን›› በማለት ይጀምሩና ‹‹ይህንን ዕውነት የሚቀበል ሁሉን ለማወቅና ለማሰስ የሚፈልግ በራሱ አነሳሽነት ያንንም ያንንም የሚዳስስና የሚነካካ አዲስ ነገር ይፈጥራል፡፡ ከሳይንቲስቶች ጋር ተገናኝቶ ለመሆኑ ይህንን ነገር እንዴት አገኘኸው?›› ብሎ ቢጠየቅ ስከታተል ወይም ጉጉት ነው የሚል ይሆናል›› ይላሉ፡፡
From The Reporter Magazine
ዶ/ር ጋርድነር ስለፈጠራ ሲገልጹ፣ ‹‹ፈጠራ አንዳንድ ጊዜ ሥርዓትን የሚያናጋ ኃይል ነው እየተባለ ሲነገር ይሰማል፡፡ ነገር ግን ሥርዓት የሚናጋው በተለያየ ምክንያት፣ በተለይ ከሥርዓቱ መበስበስ (ከውስጣዊ ቅራኔ) ነው›› ሆኖም በዚህ ጊዜ የፈጠራ ሥራዎች በአዲሱ ሥርዓት እንደሚያብቡና የተሻለ ሁኔታ እንደሚያጋጥማቸው የታወቀ ነው፡፡ ስለዚህ ፈጠራን የሚፈሩ ሕመሙን ሳይሆን ዶክተሩን ከሚፈሩ ሕፃናት ተነጥለው አይታዩም በማለት ያስተምራሉ፡፡
የፈጠራ ሥራ ወጤቶች በተጠቃለለ መልካቸው ካልተስተዋሉ በስተቀር በተለያዩ ሰዎችና ጊዜያት የተገኙትን ከተመለከትን እንደ ሁኔታው የተለያዩ ሆነው እናገኛቸዋለን፡፡ አልበትር እንስታይን ገና የ16 ዓመት ወጣቱ ከነበረበት ጊዜ አንስቶ ጥያቄውን ለመመለስ ለሰባት ዓመታት ያህል ጥረት ሲያደርግ (ሲዘጋጅና መረጃ ሲሰበስብ) ቆይቷል፣ እያለ ምርምሮችንና ጥናቶችን አካሂዷል፡፡ ማስረጃዎችን ካጠናከረና የአንፃራዊነትን (ሬላቲቪቲን) ጽንሰ ሐሳበ ካገኘ በኋላ ይህንን አብራርቶ ለመጻፍ አምስት ሳምንታት ብቻ ወስዶበታል፡፡
ኤ.ኤች በክረል (A.H Becquerel) የዩራኒየም ውሁድ የፎቶግራፍ ማድረቂያ ቆርቆሮውን (Photographic Plate) እንደ ጎዳው ሲመለከት ምንም ጥረት ሳያደርግ የሬዲዮ አክቲቭ ሚስጥር እንደ ተከሰተለት ሁሉ፣ አሌክሳንደር ፍሌሚንግም ቢሆን የፔኒሲሊንን ጠቃሚነት የተረዳው ባክቴሪያዎችን ሲያሳድግ (በአጋጣሚ) ነው፡፡
From The Reporter Magazine
የፈጣሪ ሰዎችን የፈጠራ ጥረታቸው የሥራ ጊዜያቸውን ብቻ ሳይሆን፣ የዕረፍትና የመኝታ ጊዜያቸውን ብቻ ሳይሆን፣ የዕረፍትና የመኝታ ጊዜያቸውንም ይሻማቸዋል፡፡ ዴካርቴስ (Descartes) ስለጂኦሜትሪ የቀመረው በሁለት ሕልሞቹ እንደሆነ ጠቁሟል፡፡ ፍሬዴረክ በኩል (Friedrich Kekule) በቤንዛኒ ውስጥ ያሉትን ካርቦኖችና ኃይድሮጂኖች አቀማመጥ ያገኘው እሳት ሲሞቅ እንቅልፍ ወሰዶት (በሕልም ዓለም ውስጥ) በነበረበት ጊዜ ነው፡፡ ኸርማን ሂልፕረሽት (Herman Hilprecht) የተባለው ዕውቅ አርኪዮሎጂስትም የባቢሎናውያን ጽሑፍ መቼ እንደተጻፈ ያወቀው ከእንቅልፉ ሲነቃ ነው፡፡ ሄንሪ ፓይንኬር (Henre Poincare) የተባለው ዕውቅ ሊቅ አስቸጋሪ የነበረውን ሥሌት ለማግኘት የቻለው ደግሞ አውቶቡስ ለመሳፈር አንድ እግሩን እበሩ ላይ እንዳሳረፈ ነው፡፡ ሞዛርትም ሚስቱ ልትወልድ ምጥ በያዛትና እሱም በሚስቱ መጨነቅ መንፈሱ ዕረፍት ባጣበት ጊዜ ያስብበት የነበረውን ሙዚቃ ደርሷል፡፡
የፈጠራ ሰዎች በአጋጣሚ ይሁን በህልም ከእንቅልፍ እንደነቁም ሆነ በራዕይ ስለጉዳዩ ብዙ ሲያስቡ፣ ሲጨነቁ፣ ሲያወጡና ሲያወርዱ እንደሆነ ከጥናቶች ለመረዳት ይቻላል፡፡ ሆኖም ሰው ተረግዞ ለመውለድ 270 ቀናት፣ ላም 280 ቀናት፣ ውሻ 61 ቀናት፣ ዝሆን 630 ቀናት፣ ጥንቸል 30 ቀናት፣ ዓይጥ ከ19 እስከ 21 ቀናት እንደሚያስፈልጋቸው ሲታወቅ ለፈጠራ ግን የሚያስፈልገው ጊዜ ሥነ ሕይወታዊ ዕድገት ባለመሆኑ፣ እንደ አጋጣሚውና እንደ ተጨባጭ ሁኔታው በመሆኑ እንዲህ ሲወሰን ያልቻለ ነው፡፡
ፈጠራ ከአንዳንድ ብልህ ሰዎች (Genius) ጋር ተያይዞ የሚቀርብ ቢሆንም፣ ‹‹ስጦታ፣ ተሰጥዖስ ከየት መጣ?›› የሚለውን ጥያቄ የጥንት ግሪካውያንና ሮማውያን በዘር ሐረግ የሚተላለፍ በየጊዜውም ራሱን የማይለዋውጥ መሆኑን ያምኑ ነበር፡፡
የመካከለኛው ምዕተ ዓመት ፈላስፎች ደግሞ የፈጠራ ችሎታ በአማልክት እንደሚሰጥና እነዚህም አማልክት በሰዎች እየተመሰሉ ወይም በሰዎች ልቦና በማደር አንድ ነገር ከምንም ተነስቶ ህልውና እንዲያገኝ ማድረግ ይችሉ እንደነበር ያምኑ ነበር፡፡ ይህንንም ቅዱስ ኦጉስቲን ሲገልጹ መለኮት ያደለው አንድ ሰው ለዓለም የሚጠቅም ሥራ ሊያከናውን ይችላል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ «ሰው የፈጠራ ሥራዎችን ሊያከናውን የሚችለው በመለኮት ላይ ባለው እምነት ብቻ ሳይሆን፣ በመለኮት ሥራ ላይ በሚያደርገው ተሳትፎም ጭምር ነው›› ይላሉ፡፡
ፈጠራ ሌላ ሳይሆን ‹‹ዛሬ ያለውን ነገር መለወጥ፣ ማሻሻል፣ ማሳደግ፣ የበለጠ ጠቃሚ እንዲሆን ማድረግ›› ማለት ሲሆን፣ በሌላ መልኩም ዛሬ ትክክል የሚመስለው ነገ ስህተት ሊሆን ስለሚችል ሁኔታዎችን በየጊዜው እየተከታተለ ሚዛናቸውን እንዲጠብቁ የሚያበቃ ነው፡፡
የሒሳብ ሥሌት ጠቢቡና ሳይንቲስቱ ጃኮብ ብሮኖቭስኪ (Jacob Bronowski) የዕውቀትና የምናብ ምንጭ (The Origin of Knowledge and Imagination) በተሰኘው መጽሐፋቸው ‹‹ፈጠራ የተገኘው ይህ ልክ አይደለም እስኪ በሌላ መንገድ እንሞክር አይደለም፣ እስኪ በሌላ መንገድ እንሞክረው በማለት ነው፡፡ ማንም ቢሆን ዕውነትን ፈጠራን (እንዳስቀመጠው ዕቃ) ብድግ ሊያደርገው አይችልም›› እንደዚህ ከሆነ ዓለምን የተሻለች ማድረግ አይቻልም፣ በማለት ሰው ዓለምን ለመለወጥ ካለው ፍላጎት፣ የፈጠራ ውጤት ሊያገኝ እንደሚችል እንደ ዶ/ር ጋርድነር አጥበቀው ያሳስባሉ፡፡ በ18ኛው ምዕተ ዓመት በነበረው ኢማኑኤል ካንት (I. Kant) ‹‹የፈጠራ ሥራ ከሰው ልጅ ግንዛቤ ለአንድ ነገር ከሚያድርበት ስሜትና ያንን ጉዳይ ለማወቅ ከሚያደርገው ጥረት ጋር ተዋህዶ በአዲስ መልክ እንዲፈጥር ያስችለዋል›› የሚል ትንታኔ ከመስጠቱ በፊት፣ ፈጠራ ከመለኮታዊ ኃይል በረከት እየወጣ ቢሄድም፣ ከዕድል ወይም ከአጋጣሚ ቢሄድም ከዕድል ወይም ከአጋጣሚ ጋር ለማቀናጀት በፍራንሲስ ቤከን (Francis Bacon)፣ በተለይም በቲ ሆቤስ (T. Hobber) በጆን ሉክ (John Locke) እና በዴቪድ ሂዩም (David Hume) ጥረት ተደርጎ ነበር፡፡
በአሥራ ዘጠነኛውና በሃያኛው ምዕተ ዓመት የነበሩት ሐሳባውያን ፈላስፎች ደግሞ የፈጠራ ሜካኒካልና ቴክኒካል በማለት ለይተው አስቀምጠውታል፡፡ ስለሕይወት ከሚፈላሰፉት (Life Philosophy) ውስጥ ኤች ቢርገሰን (H. Bergason) የተባሉት ሊቅ፣ ‹‹ፈጠራ በሰው ንቃተ ህሊና ውስጥ ያለ ማቋረጥ የሚወለድ፣ የሚያድግና በዚህም የዕድገት ሒደት የሚበስል (Matoration) ነው›› በማለት ያስረዳሉ፡፡
ኤ.ጄ. ስፒርኪን (A.G. Spirkin) ደግሞ ‹‹በፈጠራ ሥራ ሒደት ህሊናዊና ነባራዊ ሁኔታዎች የሚያበረክቱት አስተዋፅኦ እጅግ የላቀ ነው፡፡ ይህም ከግል ወይም ከልብ የመነጨ ለፈጠራ የመነሳት ፍላጎት በዚህ የሚያበቃ በተግባር የዳበረ ዕውቀትና ፈጠራውን ዳር ሊያደርስ የሚችል ግምት (Imagination) አስፈላጊ ነው›› ይላሉ፡፡
ፈጠራን በአጭሩ «አዲስ ነገር መፍጠር ወይም የተጀመረውን ዳር ማድረስ ተብሎ በሁለት መክፈል ይቻላል፡፡››
ለሁለቱም ክፍሎች ግን እንደ ኤች ቪ ፔትሮቭስኪ (H.V.Petrovsky) አገላለጽ ‹‹ለመፍጠር የሚያነሳሳ መንፈስ አንድ ነገር ለማወቅ ከውስጥ የሚመነጭ ብርቱ ፍላጎትና ጠንካራ ስሜት ለመፍጠር የሚያስችል ያላሳለሰ ጥረት ወይም የድርጊት እንቅስቃሴ መንፈሳዊንና አካላዊ ኃይልን ለዚህ ተግባር ማዋል ስለሚፈጠረው ጉዳይ ያካበቱትን ዕውቀት ሁሉ በአንድ ላይ ማቀነባበር የሚያውኩትን ችግሮች ደረጀ በደረጃ ማስወገድ አስፈላጊ ነው፡፡›› ቁስ አካላዊ የሥነ ባህርይ ምሁራን ደግሞ ‹‹አዲስ ነገርን ለማፍለቅ (ለመፍጠር) የሚችል ሰው ሁሉ እንደ ፕላቶና የኘላቶ ተከታዮች ከሰዎች የተለየ ስጦታ አለው›› ማለት ባይቻልም፡፡ እንደ ሊዮናርዶ ዳቪንቺ ያሉት ልዩ (ከፍተኛ) ተሰጥዖ እንዳላቸው ያምናሉ፡፡
ዛሬ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ከመቼውም ጊዜ በፈጠነ ሁኔታ በመሮጥ ላይ ባለበት ዘመን ከመቶና ከሺሕ ዓመታት በፊት ከነበረው ያልተሻለ አድርገው እየሠሩ ‹ፈጠራ› ቢባልላቸው ማምረቻ መሣሪያዎች መሥራትና እነዚህን ከገበያ ውጪ የሆኑ ፋብሪካዎችን እየተጠቀሙ በኋላ ቀር ኢኮኖሚ ለመላቀቅ ጥረት ቢደረግ ‹ፈጠራ› የሚባለው ጥገና ‹‹ቢወቅጡት እምቦጭ›› ከመሆን ሊዘል አይችልም፡፡ አዲሱ ትውልድም ከዘመኑ የሳይንስ ውጤት ጋር ለማስተዋወቅ ጥረት ማድረጉ እንጂ፣ ብዙ መቶ ዓመት ወደ ኋላ ሄዶ እንዲሠራ መንገድ መክፈቱ የጠራውን ሥልጣኔ ጭጋግ እንደሚያለብሰው መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡
የፈጠራ ሰዎች በኪነትና በሳይንስ ዘርፍ የፈጠራ ሥራ ለዓለማችን የሚያበረክቱ ናቸው፡፡ ሆኖም ሁሉም የፈጠራ ሰዎች እኩል የፈጠራ ውጤቶችን እያበረክቱም፡፡ አንድ ሺሕ ያህል ነገሮችን ፈጥሯል እየተባለ እንደሚነገርለትና ግራማፎንን የኤሌክትሪክ መብረቅ አደጋ መከላከያን የኤሌክትሪክ አምፓልን ሠራ እየተባለ እንደሚተረክለት ቶማስ ኤዲሶን (1847 እስለ 1931 ዓ.ም.)፣ ሙዚቃን በመድረስ፣ በማቀነባበርና በማጎልመስ እንደታወቀው ለድዊንግ ቫን ቢቶቭን (1770 እስከ 1827 ዓ.ም.)፣ የተለያዩ የመከላከያ መድኃኒቶችን እንደ ሠራው ሊዊ ፓስተር (1822 እስለ 1895 ዓ.ም.)፣ ልዩ ስጦታው ማንኛውንም ነገር ሊሠራ ያስቻለው ብልህ እያለ ታሪክ የሚመሰክርለት ሠዓሊው፣ መሐንዲሱና አናፂው ሊዮናርዶ ዳቪንቺ (1452 እስከ 1519 ዓ.ም.)፣ የኤሌክትሪክ ፈላስፋ ተብሎ የሚታወቀውና ዕድሜ ልኩንም ስለኤሌክትሪክ አጥንቶ ስፋትና ጥልቀት ያለውን ተግባር እንዳከናወነው ማይክል ፋራዳይ (1991 እስከ 1867 ዓ.ም.)፣ የሰው ልጅ አመጣጥ ታሪክን ወይም ስለአዝጋሚ ለውጥ በአጠቃላይ ሰፊ ጥናት እንዳካሄደው ቻርልስ ዳርዊን (1809 እስከ 1882 ዓ.ም.)፣ ያሉት ግን ከፍተኛ የፈጠራ ሥራ ያበረከቱ ታላላቅ ሰዎች እንዲያውም ልዩ ስጦታ ያላቸው ናቸው፡፡
ጃኮቭ ብሮኖቭስኪ ስለፈጠራ ሰዎች ሲገልጹ፣ ‹‹… ምንጊዜም ዓለም መለወጥ አለባት ብለው የሚያምኑ፣ ለመለወጧም ለሚተኳቸው መረማመጃ መድረክ ወይም መሣሪያ የሚሆኑ… ናቸው፤›› ብለዋል፡፡
ዶ/ር ጋርድነርም የፈጠራ ሰዎች ግልጽ ሲሆኑ፣ ግልጽነታቸው ለሰው ብቻ ሳይሆን ለድምፅ፣ ለተፈጥሮ ውበትና ለብርሃን ለቅርፅ ነው፡፡ ሆኖም የፈጠራ ሰዎች በምርመር ተውጠው ሲጓዙ ለሚያያቸውም እንድም እንደ ቀውስ፣ አለበለዚያም ለዕብደት አንድ ሐሙስ የቀራቸው መስለው ሊታዩ ይችላሉ፡፡ ታላቁ አሌክሳንደር ዲዮጋን ወደ ተባለው ፈላስፋ ሄዶ ምን ቢደረግለት እንደሚሻ ቢጠይቀው፣ ‹‹ከፊቴ ዘወር እንድትል›› ብሎ መመለሱ፣ እንድ ማስረጃ ይሆናል፡፡ አንዳንድ የፈጠራ ሰዎችን ስሜት የማይረዱ ሰዎች እየወጉዋቸው ካላዳመጡ የሚያስለቅስ ነገር ሲነግሯቸው ሲስቁ ወይም ‹ጉድ› የሚያሰኝ ነገር ሲፈጽሙ ከሰውነት ባህርይ አውጥተው ያዩዋቸው ይሆናል፡፡ ነገር ግን እውነተኛው ነገር ጆን ዳብሊዩ ጋርድነር እንዳሉ ‹‹ውስጣዊ ስሜቱን አፈኖ ለመያዝ ወይም ለመቆጣጠር ወይም ከምናቡ ለመውጣት ባለመፈለጉ›› ሲሆን፣ ዶናል ዳብሊው ማክኪኖን (Donald W. Mackinon) እንዳሉት ደግሞ ‹‹ንቃት ህሊናን በቁጥጥር ሥር ከማድረግ ነፃ ለቆ እንዲህ ባደርግ እንዲህ ሊሆን ይችላል ከሚል ሥጋት፣ ፍርኃትና ጭንቀት በመላቀቅ ብቻ ሳይሆን ችግሮችን ፊት ለፊት በመጋፈጥ ነው፡፡››
«ብዙ ወጣቶች ፈጠራው ሁሉ ያለቀ እየመሰላቸው ምን ሊፈጠር ይችላል?» ብለው ራሳቸውን ይጠይቃሉ፡፡ ስለዚህም ጉዳይ ከጓደኞቻቸው ጋር ይወያያሉ፡፡ የዘመናችን ፈጠራም ከመሬት አልፎ ወደ ጠፈር አካላት ያተኮረ ይመስላል፡፡ በዚህ ረገድ ከፍተኛ ደረጃ ላይ ደርሰዋል የሚባሉት ሩሲያና ዩናይትድ ስቴትስ እንኳን ገና ብዙ ይቀራቸዋል፡፡ ነገሩ ኒል አርምስትሮንግ ጨረቃ ላይ ባረፈበት ጊዜ አንዱ ሴኔተር «እኛ የጠፈር ጌቶች ነን፡፡ ወደ ፈለግንበት መሄድ እንችላለን›› ብሎ አፉን ሞልቶ እንደተናገረውና በመገናኛ ብዙኃን እንደተናገረው አይደለም፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነም እነዚህ ዛሬ ‹ልቀዋልና መጥቀዋል› እየተባለ የሚነገርላቸው አገሮች ያላቸው የጠፈር አካላት የመመርመሪያ መሣሪያም ሆነ ቅርብ ወደሆኑ ሥፍራዎች የሚመጥቁባቸው መሣሪያዎች ገና ብዙ የሚቀራቸው ናቸው፡፡
የጠፈሩ ምርምር በውጥን ላይ ቢሆንም በመሬት ላይ መሠራት ያለባቸው ነገሮች ራሳቸው ብዙ መሆናቸውን ነገሮች ራሳቸው ብዙ መሆናቸውን ማጤን ያሻል፡፡ ‹‹ፈልሳሚ ሰው» (Inventive Man) በሚል ርዕስ ሮበርት ኢ. ሙለር (Robert E.Miiler) ባሳተሙት መጽሐፋቸው እንደገለጹትም ‹‹የለውጡ ነፋስ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ተጠናክሮ ወደ ታላቅ የፈጠራ ማዕበልነት እየተለወጠ ነው፡፡ ሳይንስ አዳዲስ ነገሮችን በማስገኘት ላይ ነው፡፡›› በእርግጥም ከጥቂት ዓመታት በፊት የዓለምን ሕዝብ ያስጨንቅ የነበረው ፈንጣጣ ደብዛው እንደጠፋ ሁሉ፣ ጤና ተውሳኮች ላይ ያደረገው መመራመርና ያስመዘገበው መልካም ውጤት ረሃብንና ድንቁርናን ለማስወገድ ያደረገው ጥረት መልካም ዕርምጃውን አሳይቶለታል፡፡
በአንፃሩም አልበርት አንስታይን የቴርሞ ኑክሌርን ቦምብ ንድፍ (Sketch) ሲሠራ በፈገግታ ነበር፡፡ ነገር ግን የእሱ ግኝት ዓለማችንን ሥጋት ላይ ጥሏታል፡፡ ሆኖም ዛሬ ወደ ጠፈር መንኮራኩሮች ሊመጥቁ የቻሉት እሱ በደረሰበት የአቆም ሚስጥር መታወቅ ነው፡፡ ወደፊትም ያለ አቶሚክ ኃይል የትራንስፖርት እንቅስቃሴ የማይታሰብ ይሆናል ተብሎ ይገመታል፡፡ እርግጥ የሰው ልጅ አቶምን ያሳወቀው አንጎሉ ሌላም ሊያሳውቀው ይችላል፡፡ ዋናው ቁም ነገር የዓለም ሕዝብ በግኝቱ ዓለምን ሊያለማ እንጂ ለጥፋት ሊዳርጋት መሆን እንደሌለበት ማጤኑ ላይ ነው፡፡
እንደ እውነቱ ከሆነ ሰው ተፈጥሮን ለመቆጣጠር ገና መጀመሩ ነው፡፡ ብዙ ያልተዳሰሱ የምርምር ዘርፎች አሉ፡፡ ሰው ወደ ፈጠራ አቅጣጫ ባተኮረ መጠን አዳዲስ ነገሮች ብልጭ ይሉለታል፡፡ እነዚህም ብልጭታዎች ያድጋሉ፡፡ የሚፈጥሩ ሰዎች በብዙ ቁጥር የፈጠራው መስክም የዚያኑ ያህል ይሰፋል፡፡ ብዙ ሊፈጠሩ የሚችሉ ነገሮች አሉ፡፡ ፈጠራ የሁኔታዎችን መመቻቸት፣ ትዕግሥትን፣ መስዋዕትነትን… ይጠይቃል፡፡ ያለ ጥረትና ያለ ውጣ ውረድ የሚሆን ነገር የለም፡፡ ምኞትም ብቻ አይበቃም፡፡ ‹‹የዕድገት መሠረቱ ሥራ ነው›› እንዲሉ ፈጣሪ ሰዎችን ማስገኘት ብቅ ብቅ የሚሉትንም ሐሳባቸውን እንዲያዳብሩ አመቺ ሁኔታን መፍጠር ይጠይቃል፡፡ የሺሕ ዓመታት በፊት የነበሩትን ሥራዎች ማድነቅ ወይም ‹‹ሠራሁ፣ አሠራሁ፣ አሠራራሁ›› ማለት ብቻ ፈጠራን የትም አያደርስም፡፡ ይልቁንም አባት ልጅን የመምራት ጊዜና ልጅና አባት እኩል የሚራመዱበት ጊዜ አልፎ ልጅ አባቱን የሚመራበት ጊዜ ላይ የደረስን ስለሆነ፣ ከዚህ አኳያ ወጣቶች ጊዜያቸውን በትክክል ተጠቅመው ዓለም ከደረሰችበት ለመድረስ ታጥቀው መነሳት ይኖርባቸዋል፡፡
ወጣቶች የፈለጉበት ደረጃ ለመድረስ ዓላማና ዓላማውን ከግብ ለማድረስ የሚያስችል መርሐ ግብር አውጥቶ መንቀሳቀስ በጣም ጥሩና ተፈላጊ ነገሮች ናቸው፡፡ ችግር የሚሆነው ዓላማን በትክክል ያልተገነዘቡና ተገንዝበው ደግሞ እንደምን ከግብ እንደሚያደርሱ ያላወቁ እንደሆነ ነው፡፡ ዳሩ ግን እንደ እዚህ ያለው ችግር የሚያደርሰው በወጣቶች ላይ ብቻ ሳይሆን በብዙ መቶ ሚሊዮን በሚቆጠሩ ሰዎች ላይም ነው፡፡ አር. ጀ. ሂይሶርን ‹‹በአንድ ሥራ ለመታወቅ መፈለግ ጥሩ ቢሆንም፣ ዓላማን ከግብ ለማድረስ የሚቻለው ሐሳብን ያለ መወላወል ወይም ከወዲያ ወዲህ ባለመርገጥ በቀጥታ ለመጓዝ የተቻለ እንደሆነ ሲሆን፣ ወደፊት ለመሥራት የምናቅደውንም ካለፈው ትምህርት ተመርኩዘን መሆን እንዳለበት መዘንጋት የለበትም፡፡ በአዕምሯችን መያዝ የሚኖርብን ታላቅ መርህም ጉዟችን በክብ ቀለበት ዙሪያ መሸከርከር ሳይሆን በቀጥታ መደመር መጓዙን ማረጋገጥ ነው፡፡ ዓላማችን ግቡን እንዲመታ በእርግጥ የምንፈልግ ከሆነም ፍላጎታችን የእኛ ተገዥ እንጂ እኛ የፍላጎታችን ተገዥ እንዳንሆን ማስተዋል እጅግ ጠቃሚ ይሆናል፡፡ ከዚህም ጋር ለዓላማችን ግብ መምታት በወግ፣ በብልኃት፣ በሥርዓትና ሁኔታዎችን በቅደም ተከተል ለማከናወን በተፈጥሮ ችሎታችን መጠቀም ይኖርብናል፡፡
በመሠረቱ የዓላማችን ግቡን መምታት በሕይወታችን ውጤታማነታችንና ድል አድራጊነታችንን፣ እንዲሁም ደስተኛነትን የሚያስከትል ሲሆን፣ በሥራችን ክብርን፣ ዕድገትን፣ ታማኝነትን፣ አዲስ ነገር የማወቅ ጉጉትን ለሚቀርብልን ጥያቄ መልስ መስጠትን፣ ካለንበት ማኅበራዊ ሕይወት ወደ አዲሰ ማኅበራዊ ሕይወት የመግባት ዕድልን ያጎናፅፈናል፡፡ ይሁንና ዓላማችን ግቡን ሊመታ የሚችለው ከተፈጥሮ ችሎታችን ከዕውቀታችን ከየዕለቱ ማኅበራዊ ኑሯችንና ግንኙነታችን ጋር በጥብቅ የተሳሰረና ለዚህ ዓላማና ግብ መምታት ደከመኝ ሰለችኝ ሳይሉ መሥራትን ይጠይቃል፡፡ በሌላ ትከሻ ተውጣጥቶ ለማለፍም ሆነ ሊሆን የማይችል ዓላማ ግን ደንቆሮነት ይሆናል፡፡ ሰዎች ብዙውን ጊዜ በሥራቸው ከማይረኩበት የብስጭት፣ የመራራ ኑሮን ገደብ የሌለው የሐሳብ መርከብ ሆነው ከሚቀሩበት በርካታ ምክንያቶች አንዱ ይኼው ተጨባጭ የማይሆን ህልማቸው ዕረፍት ስለሚነሳቸው ነው፡፡ ግብ ወዳለው ዓላማችን ስንጓዝ ከአንድ ዕርከን ወደ ሌላው ዕርከን ብንሸጋገር ውጤታችን ራሱ መንፈሳችንን ከፍ እያደረገው ይሄዳል፡፡ እያንዳንዷን አዲስ ቀን በአክብሮት እንድንቀበላትና እንድናስተናግዳት፣ ነገን ደግሞ በታላቅ ጉጉት እንድንጠብቃትና ለእሷ የሚበጅ ሥራ እንድናዘጋጅላት ያስችለናል፡፡
ብዙ ሰዎች ውድቀት የሚያጋጥማቸው ምናልባት አሁን ካሉበት ተነስተው ባለመጀመራቸው፣ አሁን ለመጀመር ቢፈልጉ ደግሞ ምናልባት ለዓላማው ግብ መምታት ዕሙን ያልሆነ ጊዜ ነው ብለው ይገምቱ ይሆናል፡፡ በእርግጥም በጣም አስፈሪና አስጨናቂ በሆነ ጊዜ አንድ የሚያስደስት ነገር ለመሥራት የሚከብድ ይመስላል፡፡ ነገር ግን አስፈሪና አስጨናቂ ሁኔታዎች ድል ሊያደረጉ የሚችሉት የሚያስደስት ነገር ለመሥራት በሚፈልጉና በሚሠሩ ሰዎች ያልተቋረጠ ትግል መሆኑን መዘንጋት አይኖርበትም፡፡ ስለሆነም ወጣቶች እንደሚያደንቋቸው ታላላቅ ሰዎች ትልቅ ለመሆን ‹‹ዓላማዬ ግቡን ቢመታ ተጠቃሚ የምሆነው እኔ ነኝ፡፡ ስለዚህ እኔ ለእኔ አለሁ፤›› ብለው ዘወትር ለራሳቸው መንገር ይጠበቅባቸዋል፡፡
እዚህ ላይ አንዳንድ ወጣቶች ፈጠራን ከሀብት ጋር በማያያዝ «ገንዘብ ቢኖረኝ ይህን አደርግ ነበር፡፡ ገንዘብ ስለሌለኝ ግን ላደርገው አልቻልኩም›› ብለው ሲናገሩ ይሰማል፡፡ ነገር ግን ይህ ስህተት መሆኑን ብዙ ምሳሌዎችን ጠቅሶ ማስረዳት ይቻላል፡፡ ለምሳሌ ታላቁ የኮትላንድ የታሪክ ሊቅና ብዙ ትምህርታዊ ጽሑፎችን ያበረከተው ቶማስ ካርላይል ቤተሰቡ የካልቪን (የፕሮቴስታንት) ሃይማኖት ጥብቅ አማኞችና በዝቅተኛ ደረጃ የሚገኙ ሠርቶ አዳሪዎች ነበሩ፡፡ ነገር ግን ከመጀመሪያው አንስቶ ማንበቡን፣ ማጥናቱንና መመራመሩን በመቀጠል አዕምሮውን በትምህርት አበለፀገ፡፡ የ23 ዓመት ወጣት ሲሆንም ከአንድ ምሁር የሚጠበቀውን አስተዋጽኦ ማበርከት ጀመረ፡፡ በሚጽፍቸው የታሪክና የምርምር፣ እንዲሁም በጋዜጠኝነት ሙያው የሚያቀርባቸው ሕግ ነክ ትንታኔዎች አድናቆትን አተረፉለት፡፡
የመንግሥት ባለሥልጣን፣ ጋዜጠኛና ሳይንቲስትም የነበረው ቤንጃሚን ፍራንክሊን አባቱና ለእናቱ አምስተኛ ልጅ ነበር፡፡ አባቱን ደሃ ስለነበረም በ17 ዓመቱ ፊላደልፊያ በሚገኝ አንድ ማተሚያ ቤት ተቀጠረ፡፡ ወዲያውኑም የራሱን የሆነ ማተሚያ ቤት ለማቋቋም ፈለገ፡፡ ከጊዜ በኋላም የሚፈልገውን የማተሚያ መሣሪያ ገዛና ወደ አሜሪካ በመመለስ ‹ፔንሲልቫኒያ ጋዜት› የሚል ጋዜጣ ማሳተም ጀመረ፡፡ የጋዜጣው ዋና አዘጋጅም ራሱ ስለነበረ ተቀባይነትና የሥራው ተነባቢነት ከፍተኛ ሆነ፡፡ ቀጥሎም ዛሬ ዩኒቨርሲቲ የሆነውን የፔንሲልቫኒያ ኮሌጅ አቋቋመ፡፡ በ40 ዓመቱ ላይም ስለኤሌክትሪክ ማጥናት ጀመረ፡፡ በ48 ዓመቱም የእንግሊዝ ሮያል ሶሳይቲ አባል የመሆን ዕድል አጋጠመው፡፡
የፕሮቴስታንት ሃይማኖት መሥራች የሆነው ጀርመናዊው ማርቲን ሉተር ከ1483 -1546 ዓ.ም. ድረስ የነበረ ሊቅ ሲሆን የአንድ ተራ ገበሬ ልጅ ነው፡፡ ይሁንና ተራው ገበሬ አባቱ የሚወደው ልጅ ከፍተኛ ሥልጣን እንዲኖረው ይመኝ ስለነበረ ያለ የሌለ ንብረቱን መስዋዕት አድርጎ ሕግ እንዲማርለት ይፈልግ ነበር፡፡ ማርቲን ሉተር ግን የሚወደው ጓደኛው ከጎኑ በመብረቅ ተመትቶ ሲሞት በማየቱ ሁሉንም ነገር እርግፍ አድርጎ በመተው ወደ ሃይማኖት ትምህርት አዘነበለ፡፡ በዚህም ጎዳና ያደረገው ጉዞ ቀናውና በቪተንበርግ ዩንቨርሲቲ የሃይማኖት ፍልስፍና ትምህርት መስጠት ጀመረ፡፡
ደ ሞንተንዬ ከ1553 – 1592 ዓ.ም. የኖረ ፈረንሣዊ ደራሲ ሲሆን፣ በፈረንሣይ ውስጥም ከፍተኛ የመንግሥት ሥልጣን ነበረው፡፡ ይሁንና በ37 ዓመት ዕድሜው ራሱን በጡረታ በማግለል ገጠር ሄዶ መኖር ጀመረ፡፡ በዚህም የገጠር ቤቱ ፎቅ ላይ የራሱን መኝታ ቤትና መድኃኒት ቤት በማድረግ፣ ምድር ቤት ደግሞ ሕዝብ ተሰብስቦ ፀሎት የሚያደርስበት መጠነኛ አዳራሽ አድርጎት ነበር፡፡ ፎቅ ተኝቶም ሆነ ተቀምጦ በሺሕ የሚቆጠሩ መጻሕፍቱን ለማንበብ ሲችል ምድር ቤት ያሉት ምዕመናን ሲዘምሩና ሲፀልዩ ደግሞ ከፍተኛ ደስታ ይሰጠው እንደነበር ከሕይወት ታሪኩ መረዳት ይቻላል፡፡
ከ1632 – 1662 የኖረው ብሌዝ ፖስካል የተወለደው ከሌረሞ ፌራ በተባለው በፈረንሣይ ማዕከላዊ ግዛት ቢሆንም እንኳን፣ አብዛኛው የሕይወት ዘመኑን ያሳለፈው በፈረንሣይ ውስጥ ነው፡፡ ፖስካል በሒሳብ ሥሌት የአንድ ሳይንቲስት ያህል ዝንባሌ ያሳየው የ16 ዓመት ወጣት በሆነበት ጊዜ ሲሆን፣ አባቱ እጅግ አድካሚ በሆነ መንገድ ሒሳቡን ሲየሠላ በመመልከቱም የመጀመሪያውን የሒሳብ ሥሌት መሣሪያ አዘጋጀ፡፡
ቮልቴር የ30 ዓመት ወጣት እስኪሆነው ድረስ በሥነ ጽሑፍ ሰዎች ዘንድ ባለቅኔነቱ እምብዛም ተቀባይነት አላገኘም፡፡ ከዚያ በኋላ ግን ከብዙ የፊውዳሉ ሥርዓት አራማጆች ጋር በማጣላቱ ለሕይወቱ አሥጊ ከሆነ ደረጃ ላይ ደረሰ፡፡ በዚህም ምክንያት ወደ ኢንግላንድ ሄደ፡፡ በዚያም ለሦስት ዓመታት ያህል እንደኖረ በወቅቱ በጣም ዝነኛ የነበረውን፣ ነገር ግን ፈረንሣይ ውስጥ የማይታወቀውን የሼክስፒርን ተውኔቶችና የብሪታኒያን አስተዳደር ሥርዓት ለማወቅ ቻለ፡፡ ወደ አገሩ ሲመለስም በፈረንሣይ የነበረው ፈላጭ ቆራጭ ዘውዳዊ አገዛዝ ምን እንደሚመስልና ከእንግሊዛውያን ሕይወት አንፃር በማስተያየት አንድ መጽሐፍ ለማሳተም ቻለ፡፡
ፈረንሣዊ የፍልስፍና ጸሐፊ ዣንዣክ ሩሶ የተወለደው እ.ኤ.አ. 1718 ጄኔቫ ውስጥ ነው፡፡ የአንድ ሰዓት አዳሽ ልጅ ነው፡፡ ይሁንና እናቱ በሕፃንነቱ ስለሞቱ በዘመድ አደገ፡፡ ሩሶ ባበረከተው ከፍተኛ የፖለቲካና የፍልስፍና ሥራዎች የሚታወቅ ቢሆንም፣ በልጅነትና በወጣትነት ዕድሜው ደልቶት የኖረ ሰው አልነበረም፡፡ በዚህም የተነሳ ይመስላል ያደረበት ስሜታዊነትና የብስጩነት ባህርይ ከሰዎች ጋር አላስማማውም፡፡ አንድ ቦታ ላይ ተቀምጦ የመሥራት ዕድል ሳይገጥመው ከአንዱ ሥፍራ ወደ ሌላው በመዞር አብዛኛውን የሕይወት ዘመኑን አሳልፏል፡፡ የእነ ጆን ሉክ ፍልስፍና ተከታይ የነበረው ሩሶ የራሱን አስተሳሰብ በመጨመር መንግሥት በምክር ሕዝቡን መምራት እንደሚገባው፣ የመንግሥት አመራር አባላትም የሕዝብ አገልጋዮች እንደሆኑ ለሕዝብ ደኅንነት መቆም እንዳለባቸውና ሕዝቡም ከአደጋ ሊጠብቅቸው እንደሚገባ አጥብቆ ተከራክሯል፡፡
ማጠቃለያ
እስካሁን በተመለከትነው በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ አገር ያሉ ኢትዮጵያውያን ወጣቶች በዚህ ረገድ ለቀበሌያቸው፣ ለክልላቸው ብሎም ለአገራቸው ምን ሠርተው ታላቅ ሰዎች መሆን ይችላሉ? ብለን ስንጠይቅ እጅግ በርካታ ያልተዳሰሱ ነገሮች በዓይነ ህሊናችን መጥተው ይደነቀራሉ፡፡ ዳሩ ግን ፍለጋውን ለፈጠራ ለተነሳሱት ወጣቶች ለራሳቸው እንተወው፡፡ ይህ ሲሆን ያለ አንዳች ጥርጥር ኢትዮጵያ በወጣት የፈጠራ ልጆቿ ወደ ጥንታዊ ክብርና ዝናዋ ትመለሳለች፡፡
ይህ ጽሑፍ በከፊል የተወሰደው ‹‹ታላላቅ ሰዎችና ጥቅሶቻቸው›› በሚል ርዕስ በ2007 ዓ.ም. ካሳተመው መጽሐፍ የወሰደው መሆኑን በአክብሮት ይገልጻል፡፡
ከአዘጋጁ፡- ጸሐፊው አንጋፋ ጋዜጠኛ፣ ደራሲ፣ የእስልምና ጉዳዮች ተመራማሪ፣ እንዲሁም የታሪክ አጥኚ ሲሆኑ፣ ጽሑፉ የእሳቸውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እየገለጽን፣ በኢሜይል አድራሻቸው [email protected] ማግኘት ይቻላል፡፡
