- የ50 ሺሕ ብር ቅጣትና ለሁለት ወራት ከሥምሪት ይታገዳሉ ተብሏል

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በወላይታ ዞን፣ ሶዶ ከተማ ነዳጅ ቀድተውና ሥምሪት ወስደው ለሕዝብ የትራንስፖርት አገልግሎት በማይሰጡ ተሽከርካሪዎች ላይ ዕርምጃ እየወሰደ መሆኑን፣ የሶዶ ከተማ ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ መምርያ አስታወቀ፡፡
የሶዶ ከተማ ትራንስፖርትና ሎጂቲክስ መምርያ ኃላፊ ወ/ሪት መቅደስ በዛብህ ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ ለሕዝብ ትራንስፖርት የሚሰጡና ሥምሪት የወሰዱ አንዳንድ ተሽከርካሪዎች ነዳጅ ከቀዱ በኋላ ወደ መናኸሪያ ገብተው አገልግሎት በመስጠት ላይ አይደሉም፡፡ ጥቂት የማይባሉ አሽከርካሪዎችም መናኸሪያ ውስጥ ተሽከርካሪዎቻቸውን በማቆም ከእነ ረዳቶቻቸው እየተደበቁ ይገኛሉ ብለዋል፡፡
በመሆኑም የከተማው ትራንስፖርት መምርያ መናኸሪያ ግቢ ውስጥ ተሽከርካሪዎቻቸውን አቁመው የተሰወሩትን በመለየት ሰሌዳቸውን ፈቶ ዕርምጃ እየወሰደ የሚገኝና በቀጣይም በእንዲህ ዓይነት ተግባር በተሰማሩ ተሽከርካሪዎች ላይ የ50 ሺሕ ብር ቅጣት፣ እንዲሁም ለሁለት ወራት ከሥምሪት መርሐ ግብር የሚያግዳቸው መሆኑን አስታውቀዋል፡፡
‹‹የከተማው ትራንስፖርት መምርያ ያለውን የነዳጅ እጥረት ችግር ለመቅረፍ ተሽከርካሪዎች ነዳጅን በቁጠባ እንዲጠቀሙ የማድረግ ሥራዎች እየሠራ ይገኛል፤›› ያሉት ኃላፊዋ፣ የሕዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ ተሽከርካሪዎች በማደያዎች ቅድሚያ አግኝተው እንዲስተናገዱ ግብረ ኃይል ተቋቁሞ የሚሠራው ሥራ አንዱ ተጠቃሽ ነው ብለዋል፡፡
ወ/ሪት መቅደስ እንደተናገሩት፣ በሶዶ ከተማ መናኸሪያ ወደ 62 መስመሮች በየቀኑ የትራንስፖርት ሥምሪት ይሰጥባቸዋል፡፡ በእነዚህ መስመሮችም ከ1,500 በላይ ተሽከርካሪዎች እንቅስቃሴ የሚያደርጉ ሲሆን፣ በቀን ከ25 ሺሕ በላይ የሰው ምልልስ የሚደረግበት ነው፡፡ በመሆኑም ካለው የነዳጅ ችግርና ያለውንም ነዳጅ በቁጠባ ለመጠቀም እንዲቻል ለሕዝብ አገልግሎት የሚሰጡ ተሽከርካሪዎች በተራ እንዲቀዱ እየተደረገ እንደሚገኝና በዚህም በቀን ከ60 እስከ 100 ተሽከርካሪዎች ነዳጅ ከማደያዎች እንዲያገኙ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል፡፡
ሆኖም ከሚያዝያ 8 ቀን 2018 ዓ.ም. ጀምሮ ወደ 118 የሚደርሱ ተሽከርካሪዎች ነዳጅ ከማደያ ከቀዱ በኋላ ወደ መናኸሪያ ሳይገቡ ቀርተዋል ያሉት ኃላፊዋ፣ በዚህም ምክንያት ትራንስፖርት ተጠቃሚው ሕዝብ ከሌሊቱ 10፡00 ሰዓት ጀምሮ መናኸሪያ ቢደርስም አገልግሎት ለማግኘት ተጉላልተዋል ሲሉ ገልጸዋል፡፡
በመሆኑም ተሽከርካሪዎቻቸውን መነኸሪያ አቁመው የተሰወሩ 50 ተሽከርከሪዎች፣ በማኅበሮቻቸው አማካይነት እንዲጠሩ በማድረግ ሰሌዳቸው ተፈቶ፣ 1 ሺሕ ብር እንዲቀጡና ወደ አገልግሎት እንዲመለሱ ሲደረግ፣ ነዳጅ ቀድተው አገልግሎት ለመስጠት ፈቃደኛ ያልሆኑ አሽከርካሪዎችም ተይዘው 50 ሺሕ ብር እንዲቀጡና ለሁለት ወራት ከሥምሪት መርሐ ግብር እንዲታገዱ በመደረግ ላይ መሆኑንም አስታውቀዋል፡፡
From The Reporter Magazine
ለሕዝብ አገልግሎት የሚሰጡና ነዳጅ ቅድሚያ እንዲያገኙ የተደረጉ አንዳንድ ተሽከርካሪዎች ነዳጅ ከቀዱ በኋላ የሚደበቁበትና አገልግሎት የማይሰጡበት ዋናው ምክንያት በጥቁር ገበያ ነዳጁን ስለሚሸጡት ነው ያሉት ኃላፊዋ፣ ከጥቂት ቀናት በፊት በዚሁ ተግባር ሲሳተፉና ነዳጅ ከመኪና ወደ ጀሪካን ሲገለብጡ የተገኙ አሽከርካሪዎች በቁጥጥር ሥር ውለው ጉዳያቸው በሕግ እየታየ እንደሚገኝም ጠቁመዋል፡፡
የዲቻ ደረጃ 1 የሕዝብ ማመላለሻ ማኅበር ሥራ አስኪያጅ አቶ ዮናስ ሻንካ በበኩላቸው እንደተናገሩት፣ ‹‹አንዳንድ ተሽከርካሪዎች ከማደያ ነዳጅ ከቀዱ በኋላ በአግባቡ የትራንስፖርት አገልግሎት እየሰጡ አይደለም፣ ከተቀመጠው ታሪፍ በላይም ሕዝብን እያስከፈሉ የሚገኙበት ሁኔታ በመታየት ላይ ነው ብለዋል፡፡
በመሆኑም ነዳጅ ከማደያ ቀድተው አገልግሎት በማይሰጡና ከታሪፍ በላይ በሚያስከፍሉ ተሽከርካሪዎች ላይ የሚወሰደውን ዕርምጃ ማኅበራችን ይደግፋል ያሉት አቶ ዮናስ፣ አንዳንድ አሽከርካሪዎች የነዳጅ እጥረቱን እንደ ጥሩ አጋጣሚ በመቁጠር የቀዱትን ነዳጅ በሕገወጥ መንገድ በጥቁር ገበያ ላይ በሊትር እስከ አንድ ሺሕ ብር እየሸጡ ይገኛሉ፡፡ ማኅበሩም እንዲህ ዓይነት ወንጀል የሚፈጽሙ አሽከርካሪዎችን በመለየት ቅጣት እንዲጣልባቸው እያስደረገ እንደሚገኝም አስታውቀዋል፡፡