
በትንሳዔ በዓል ማግሥት ከቦሌ ድልድይ ወደ ሳሪስ አቦ ልንጓዝ ነው፡፡ መንገዱ ጭር ብሎ የታክሲ መጫኛው ደሴት ውስጥ በርካታ ሚኒባሶች ቆመዋል፡፡ ወያላው ለበርካታ ቀናት የረሳው ጥሪ ሳይወድ በግድ፣ ‹‹ቦሌ ሚካኤል፣ አዲሱ ሠፈር፣ ሳሪስ…›› እያለ ከቅርብ እስከ ሩቅ ሲጣራ፣ ‹‹አሄሄ… ታክሲ ጥበቃ ፀሐይ ላይ ከመንቃቃት ተርፈን ዛሬ ተፈላጊዎች ሆነን ጥሪ ሲደረግልን መስማት ተመስገን ያስብላል…›› እያለች አንዲት አጠርና ደልደል ያለች ጠይም ወይዘሮ ተሳፈረች፡፡ ‹‹‹ለሁሉም ጊዜ አለው› አይደል እንዴ የሚባለው?›› ብሎ ፊቱ የማይፈታ የሚመስል ጎልማሳ ሲናገር፣ ‹‹‹ካልተሳፈሩበት ቶሎ ተሸቀዳድሞ ጊዜ ታክሲ አይደለም አይጠብቅም ቆሞ› የሚለውን ጥቅስ ምነው በዚህ ዘመን አይቼው አላውቅም?›› የሚል ድምፅ ጋቢና ከተሰየሙት አንዱ ከማለቱ፣ ‹‹የአነጋገር ዘዬና ምሳሌማ ድሮ ቀረ፡፡ አሁንም በድሮ ተረት፣ ምሳሌ፣ አባባል፣ ብቻ ምን አለፋችሁ ሙዚቃስ ብትሉ የድሮው አይደል እንዴ እንደገና እየታደሰ ያለው…›› የሚለው አብሮት የተቀመጠው ጎልማሳ ነው፡፡ ነገርን ነገር ያነሳዋል በሉ!
‹‹አሁንማ ሁሉም እየተነሳ ‹ኦልድ ኢዝ ጎልድ› እያለ ሙዚቃውን በየዓይነቱ እያጣጣመ ነው፡፡ ለመሆኑ የአሁኑ ትውልድ የራሱ ዓርማ፣ ቀለም፣ ዓላማ፣ መርህ፣ አቅጣጫ፣ ፍላጎት ሳይኖረው ቀርቶ ነው ወይስ ዕርባና ቢስነት በዝቶ ነው…›› ብላ ያቺ ወይዘሮ ቀጠለች፡፡ ‹‹የአሁኑ ትውልድ ዕድሜ ለአርተፊሻል ኢንተለጀንስ የራሱን ማንነት የሚያሳይበት ጊዜ ሩቅ አይደለም…›› ብሎ ከኌላ መቀመጫ አንዱ ሎጋ ወጣት ምላሽ መስጠት ሲጀምር፣ ‹‹አርተፊሻል ኢንተለጀንስ አልክ? ከምሥልና ከድምፅ ማጭበርበር፣ የሰው ሥራ የራስ አስመስሎ ከማቅረብ፣ በጥናት ተለፍቶ መገኘት ያለበትን ዕውቀት በአቌራጭ እየመነተፉ ከማምጣትና ተገቢ ካልሆኑ ድርጊቶች መታቀብ ከተቻለ ብዙ ነገሮች መሥራት ይቻላል፡፡ ትልቁ ችግር ግን እኛ ዘንድ ሲደርስ ሁሉም ነገር ከጠቀሜታዊ እሴትነቱ ይልቅ አጥፊነቱ እየበዛ ፋይዳ ቢስነት ይበራከታል…›› የሚለው ኮስታራው ጎልማሳ ነው፡፡ ያሰኛል!
የተሳፈርንባት ሚኒ ባስ ሞልታ በወያላው የተለመደው ‹‹ሳበው!›› ማሳሰቢያ ጉዞ ተጀመረ፡፡ ወጣቱ ወያላ የዕድሜ እኩያው ከሆነው ሾፌር ጋር በኌላ ማጮለቂያ መስተዋት እየተያዩ ወሬ ጀመሩ፡፡ ‹‹ለበዓል የፈሰክበት የዶሮ ወጥ እንዴት ነበር?›› ብሎ ወያላው ጥያቄ ሲያቀርብ፣ ‹‹ዘንድሮ ዶሮ የበላነው ቲክቶክ ላይ ነው…›› እያለ ሾፌሩ ሲመልስ፣ ‹‹እናንተ በበይነ መረብ ከፈሰካችሁ ምቾት ላይ ናችሁ ማለት ነው…›› ብላ ከሾፌሩ ጀርባ የተቀመጠች ከሲታ ሴት ስትስቅ፣ ‹‹እኔማ በበዓል ቀን ከጓደኞቼ ጋር ዙም ሚቲንግ ላይ ሆነን የባጡን የቆጡን እየቀባጠርኩ ባልሸውደው ኖሮ ሰቀቀኑ ይገድለኝ ነበር…›› እያለ አንዱ አጠገቡ ለተቀመጠው ሲያወራ ሰማነው፡፡ በዚህ መሀል ስልክ የተደወለለት ደግሞ፣ ‹‹በሕይወቴ እንዲህ ዓይነት በዓል አላየሁም፡፡ የቅርጫ ሥጋው፣ ፍየሉ፣ ዶሮው፣ ጠጁ፣ ቢራውና ውስኪው እንደ ጉድ ተበላ፣ እንደ ጉድ ተጠጣ…›› እያለ ለደዋዩ በኩራት ሲነግረው፣ ‹‹አወይ አንቺ ዓለም ነገርሽ ዝብርቅርቅ…›› የሚለው ኮስታራው ጎልማሳ ነው፡፡ ያስብላል!
ወያላው ሒሳብ እየሰበሰበ፣ ‹‹እኔን ግርም የሚለኝ ኑሮ ተወደደ ተብሎም የእኛ ሰው እንደ አቅሚቲም ቢሆን መቀማመሱ አይቀርም…›› ሲል፣ ‹‹የፈጣሪ ሥራ ነው እንጂ እንደ ሰው ቢሆን ኖሮ ረሃብ ፍግም የሚያደርገው ብዙ ነበር…›› እያለ ወያላው መደገፊያ ላይ የተቀመጠ ምስኪን መሳይ እጆቹን ወደ ፈጣሪ ዘርግቶ ምስክርነቱን በመስጠት ሲቀጥል፣ ‹‹…ለምሳሌ እኔ ዶሮም፣ ጥሬ ሥጋም፣ ጥብስም፣ ቅቅልም፣ ዱለትም በልቻለሁ፡፡ ጠላ፣ አረቂና ጠጅም አላጣሁም፡፡ ይህንን ሁሉ ያንበሸበሸኝ ፈጣሪ አምላኬ ነው፡፡ አንዲት ደግ እናት ልጃቸው ቤት ልከውኝ እስኪበቃኝ ከሁሉም ዓይነት ጠግቤ እንድበላ አድርገውኛል፡፡ ማን ፈቅዶ…›› ሲል፣ ‹‹ፈጣሪ አምላክ ነዋ…›› የምትለው ወይዘሮዋ ነበረች፡፡ ‹‹በዚህ ፈጣሪ በተረሳበት ዘመን አመስጋኝ ሲኖር መልካም ነው፡፡ ለተደረገልን ሁሉ ማመስገን መቻል አለብን፡፡ ምስጋና ፈጣሪን ደስ የሚያሰኝ ታላቅ በረከት ነው…›› የሚሉት ድምፃቸው ያልተሰማ አዛውንት ናቸው፡፡ እውነት ነው!
ቦሌ ሚካኤልን አልፈን ስንገሰግስ ከወደ ሬዲዮኑ የመካከለኛው ምሥራቅ ጉዳይ ተነስቶ ሐተታ ሲሰማ፣ ‹‹ሾፌር በሕግ አምላክ በበዓል ሰሞን ቢያንስ አረፍ እንበልበት እንጂ፡፡ በእነሱ ጦስ ምክንያት አይደል እንዴ ነዳጅ ጠፍቶ አሳራችንን የምናየው? ባለችን ገንዘብ እንኳ ሸማምተን በዓልን በአንፃራዊም ቢሆን ተደስተን ማሳለፍ ሲገባን አንገታችንን በሐዘን የደፋነው፡፡ ምድረ ጥጋበኛ አዲስ የዓለም ሥርዓት ለማዋለድ እኛን መከራ ያበሉናል፡፡ በእነሱ ጥጋብ ምክንያት ሁሌም የሚጎዱት እኛን መሰል ድሆች ናቸው…›› እያለ ጎልማሳው ምሬቱን ሲናገር ሾፌሩ ሬዲዮኑን ዘግቶ ዘፈን ከፈተ፡፡ ኤፍሬም ታምሩ በዚያ ዘመን አይሽሬ ድምፁ፣ ‹‹ወይ ዘንድሮ… ወይ ዘንድሮ…›› ሲል፣ ከበርካታ ዓመታት በፊት ሳይሆን ዛሬ በሰበር የለቀቀው ይመስል ነበር፡፡ ‹‹እንዲያው ልፉ ብሏችሁ እንጂ እዚህ አገር መቼም ቢሆን ደህና ጊዜ ኖሮ አያውቅም…›› የምትለዋ ከሲታዋ ሴት ናት፡፡ ‹‹ጊዜ የምንለው አስማተኛ ነገር አንዱን ላይ ሲያወጣ ሌላውን እየፈጠፈጠ መቀጠሉ እውነት ስለሆነ በራሳችን እንጂ በእሱ መማረር አይኖርብንም…›› የሚሉት አዛውንቱ ናቸው፡፡ ይገርማል፣ ይደንቃል!
‹‹አባታችን ጊዜማ በራሱ ምኅዋር እንደሚንቀሳቀስ መቼ አጣነው? አስቸጋሪ የሆነው ግን የሰው ነገር ነው፡፡ ዛሬ ደህና ነው ያልነው ድንገት ሌላ ይሆናል፡፡ ለቅዱስነት የቀረበ ነው ያልነው ከመቼው ሰይጣን እንደሚሆን እንጃ፡፡ ታምነው አደራ የተሰጣቸው አደራ በል ሆነው ያሳቅቁናል፡፡ ትልቅና የተከበሩ ናቸው ያልናቸው ከመርካቶ ኪስ አውላቂ የላቀ ሌብነትና አጭበርባሪነት ያሳዩናል፡፡ ዓለማዊውን ነገር ሁሉ ንቀው ሕይወታቸውን ለመንፈሳዊ ሰጡ ያልናቸው በፍቅረ ንዋይ ታውረው ግራ ያጋቡናል፡፡ አባቴ ምን አለፋዎት ይህ ጊዜ አስፈሪ እየሆነ ነው…›› ብሎ ኮስታራው ጎልማሳ በብስጭት ሲናገር ውስጡ በበደልና በግፍ ብዛት ተስፋ የቆረጠ ይመስል ነበር፡፡ ወያላው ትክ ብሎ እያየው፣ ‹‹ጋሼ በዚህ ጊዜ እኮ እኔ ምን አገባኝ ብሎ ዳር መያዝን የመሰለ መልካም ነገር የለም…›› ብሎ ሲነግረው ጎልማሳው ሳቀ፡፡ ንዴት ይሁን መገረም ግን እንጃ!
ታክሲያችን አዲሱን ሠፈር አልፋ እየከነፈች ነው፣ የታክሲ ውስጥ ወግም ቀጥሏል፡፡ ሴት ወይዘሮዋ ድንገት ስልኳ ሲጠራ ቦርሳዋን በቄንጥ ከፍታ አወጣችው፣ አይፎን 16 ነው፡፡ በጌጠኛ ከቨር ያማረውን ስልክ አውጥታ፣ ‹‹እንኳን አብሮ አደረሰን…›› ብላ በደማቅ ፈገግታ የመልካም ምኞት ልውውጥ ካደረገች በኌላ፣ ‹‹ቤንዚን ፍለጋ አልሠለፍም ብዬ በሚኒ ባስ ታክሲ ተሳፍሬ እነ ማዘር ጋ እየሄድኩ ነው፡፡ በእናትሽ ከሰፊው ሕዝብ ጋር በታክሲ መጓዝ ለካ ትልቅ ዩኒቨርሲቲ ነው? እኔም ራሴ ሐሳብ እያዋጣሁ ታክሲዋን የእንግሊዝ ፓርላማ አስመስለናታል…›› እያለች ስትስቅ፣ ‹‹እያመመው መጣ… ሴትዮዋ በበዓል ምድር ታክሲ ውስጥ የፈረንጅ ፓርላማ ዓይነት ያደራጃሉ አስብላ ልታሳፍሰን ነው እንዴ?›› እያለ ጋቢና ከተቀመጡት አንደኛው ሲስቅ፣ ‹‹አይዞህ ቢያንስ ለጊዜውም የእንግሊዝ ፓርላማ አባላት ተብለን መጠራታችን ሊያኮራህ ይገባል እንጂ ሊያስፈራህ አይገባም…›› ብሎ ጓደኛው ቀለደ፡፡ ይሻላል!
From The Reporter Magazine
ሳሪስ አቦን ከፊት ለፊታችን እያየን ስንንደረደር፣ ‹‹ከመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት አትራፊው ማን የሚሆን ይመስላችኌል?›› ብሎ ወጣቱ ከመጨረሻ ወንበር ጥያቄ ሲያቀርብ፣ ‹‹ማንም ያትርፍ ወይም ይክሰር እኛ የምንፈልገው ሰላምና የደሃ ምግባችንን ነው…›› የሚለው ኮስታራው ጎልማሳ ነው፡፡ ‹‹ሰላም አስፈላጊና አንገብጋቢ ጉዳይ ነው፡፡ ሰላም ከሌለ እንኳን ምግብ በሕይወት መኖርም አይታሰብም፡፡ ወጣቱ ላቀረብከው ጥያቄ አጭሩ መልሴ አትራፊዎቹ ሩሲያና ቻይና ሲሆኑ አሜሪካኖች፣ እስራኤሎች፣ ኢራናውያን፣ እንዲሁም ሀብታሞቹ ዓረቦች ግን ይከስራሉ…›› የሚለው በዚህ ሁሉ ጉዞ ምንም ያልተናገረ ከወጣትነት አለፍ ያለ ቁመተ ሎጋ ነው፡፡ ‹‹ወንድሜ ትርፍና ኪሳራ የሚለካው በሚጨበጥና በሚለካ ውጤት እንጂ በመላምት ስላልሆነ፣ መጨረሻውን ሳናይ ድምዳሜ ላይ መድረስ አይቻልም፡፡ መጀመሪያ ጦርነቱ ተጠናቆ የመጨረሻው ውጤት ይታይ…›› እያለች ወይዘሮዋ ታክሲዋ ስትቆም ወያላው ሳሪስ አቦ መድረሳችንን ‹‹መጨረሻ…›› እያለ በሩን ከፍቶ ተራ በተራ ወርደን ተሰነባብተን ተለያየን፡፡ መልካም ጉዞ!