የፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የ2017 ዓ.ም. የቤተሰብ፣ የፍትሐ ብሔር፣ የወንጀልና የአፈጻጸም መዛግብት በተለያዩ የመመዘኛ መሥፈርቶች ኦዲት ተደርገው ለመጀመሪያ ጊዜ ይፋ ሆነ፡፡
የፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ሰኔ 6 ቀን 2018 ዓ.ም. ለሦስተኛ ጊዜ ባዘጋጀው የባለድርሻ አካላት የውይይት መድረክ፣ የፌዴራል ፍርድ ቤቶች የዳኝነት ኢንስፔክሽንና የመዝገብ ኦዲት መመርያ ቁጥር 19/2016፣ የድኅረ ውሳኔ መዝገብ ምርመራ መደረግ እንዳለበት በሚደነግገው መሠረት ያከናወነውን ኦዲት ይፋ አድርጓል፡፡
ኦዲት የተደረጉት መዛግብት በአራት መከፈላቸውንና እያንዳንዱ የመዝገብ ዓይነት በተለያዩ መመዘኛዎች መታየቱን፣ በፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የንፋስ ስልክ ላፍቶ ተጠሪ ዳኛ አቶ ዳንኤል ዱጋሳ ገልጸዋል፡፡
ከሐምሌ 1 ቀን 2016 ዓ.ም. እስከ ሰኔ 30 ቀን 2017 ዓ.ም. ባሉት ጊዜያት፣ በፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በ13 ምድብ ችሎቶች ታይተው እልባት በማግኘት የተዘጉ 594 መዛግብት የተካተቱበት መሆኑን አስረድተዋል፡፡
የኦዲት ግኝቶችን በዝርዝር ያቀረቡት በፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የዳኝነት አገልግሎት ኢንስፔክሽን ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ዳንኤል አበበ፣ የመጥሪያ አደራረስ ውጤታማነት 94.8 በመቶ መሆኑንና ለ442 መዛግብት መጥሪያ በአግባቡ ስለመድረሱ መረጋገጡን ተናግረዋል፡፡ ነገር ግን የተከሳሽ አድራሻ በክሱ ላይ የተገለጸ ሆኖ ሳለ በቀጥታ ለተገልጋይ ተደራሽ ያልሆነውን የጋዜጣ ጥሪ የማድረግ ድርጊት መታየቱን ገልጸዋል፡፡
በፍትሐ ብሔር ሥነ ሥርዓት ሕግ አንቀጽ 137 እና 145 መሠረት የተጠየቁ ማስረጃዎች የተስተናገዱበትን አግባብ የተመለከተው ኦዲቱ፣ መረጃ ካላቸው መዛግብት መካከል ከፍተኛና በጣም ከፍተኛ ውጤት ያላቸው 128 መሆናቸውንና 56 መዛግብት ደግሞ ዝቅተኛና በጣም ዝቅተኛ ውጤት እንዳላቸው ጠቁመዋል፡፡
ሆኖም የተጠየቁ መዛገብት ሳይቀርቡ ክስ መስማት በብዛት እየተሠራበት ያለ በመሆኑ ሊታረም እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
From The Reporter Magazine
የመጀመሪያ ደረጃ መቃወሚያ ሲቀርብ አከራክሮ በሕግ አግባብ ብይን ስለመሰጠቱ የተመለከተው ኦዲቱ፣ 56.1 በመቶ የሚሆኑት መዛግብት ላይ መቃወሚያ እንዳልቀረበ መረጋገጡን፣ በቀረበ መቃወሚያ ላይ የተቃራኒ ወገንን ክርክር ሳይሰሙ ብይን የመስጠት ግድፈት መስተዋሉን አብራርተዋል፡፡
በ369 መዛግብት ላይ ዳኞች የሰጧቸው ትዕዛዞች የሕግ ሥነ ሥርዓቱን በሚገባ የተከተሉ፣ ለባለጉዳዩም ሆነ ለአስፈጻሚ አካላት ግራ መጋባትን የማይፈጥሩ ሆነው መገኘታቸውን ተናግረዋል፡፡
የፍርድ አሰጣጥ ሒደቱ የፍትሐ ብሔር ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር 180 እስከ 183 ያሉትን የተከተለ ስለመሆኑ ኦዲት የተደረገ ሲሆን፣ 89.3 በመቶ የሚሆኑ ውጤቶች በሕጉ የተደነገገውን መሥፈርት አሟልተው የተጻፉ መሆናቸው እንደሚያሳይ አቶ ዳንኤል ገልጸዋል፡፡
From The Reporter Magazine
ሆኖም ውሳኔ ሲሰጥ ተገቢውን ሕግ አለመጥቀስ፣ የሚቀርቡ ማስረጃዎችን የፍርዱ አካል አለማድረግና ሁለት ዓይነት ፍርድና ውሳኔ መስጠት መስተዋሉን አክለዋል፡፡
የአፈጻጸም መዝገብ ከመዘጋቱ በፊት እንደ ፍርዱ መፈጸሙን ማረጋገጥና ያልተፈጸመ ከሆነ ምክንያት መግለጽን በሚመለከት 68 በመቶ መዛግብት ከፍተኛና በጣም ከፍተኛ ውጤት እንዳላቸው፣ 25.9 በመቶ የሚሆኑ መዛግብት ግን መካከለኛ፣ ዝቅተኛና በጣም ዝቅተኛ ውጤት እንዳላቸው መረጋገጡን አስታውቀዋል፡፡
በወንጀል መዛግብት የተከሳሽን ማንነት ማረጋገጥ፣ መብቶቹን ማሳወቅና የእምነት ክህደት ቃል በግልጽና በዝርዝን መጻፍን በሚመለከት 88 መዛግብት የተሻለ አፈጻጸም እንዳላቸውና 40 መዛግብት ላይ ክፍተት መታየቱን አብራርተዋል፡፡
ክፍተቶቹም በዋናነት የተከሳሽ ማንነት ሳይረጋገጥ ክርክር ተደርጎ ውሳኔ መስጠት፣ የተከሳሽን ማንነት በአግባቡ አለማረጋገጥና የእምነት ክህደት ቃልን በአግባቡ አለመቀበል መሆናቸውን ሳይጠቅሱ አላለፉም፡፡
በ48 መዛግብት የተከሰሱ ተከሳሾች አቅም ካላቸው የፈለጉትን ጠበቃ የማቆም፣ አቅም ከሌላቸው ተከላካይ ጠበቃ የማግኘት መብታቸውን በማስከበር ረገድ ክፍተቶች እንደታዩባቸውና 58 መዛግብት ይህ መብታቸው እንደተከበራለቸው በኦዲት ተረጋግጧል ብለዋል፡፡
የዋስትና መብትን በሚመለከት 81.3 በመቶ መዛግብት የዋስትና መብት አያያዝ ሕገ መንግሥታዊ ድንጋጌዎችን የተከተለ መሆኑን፣ ነገር ግን ያለ በቂ ምክንያት ዋስትና የመከልከል፣ በዋስትና ላይ የግራ ቀኝ አስተያየት አለመስማት፣ ለተከሳሽ ተመጣጣኝ ያልሆነ ዋስትና ማዘዝ፣ ፍርድ ሲሰጥ ዋስትና አለማንሳትና በዋስትና ላይ ውሳኔ ለመስጠት ተደጋጋሚ ቀጠሮ የመስጠት ድክመቶች መታየታቸውን አስረድተዋል፡፡
በአጠቃላይ ኦዲት ከተደረጉ 238 የፍትሐ ብሔር መዛግብት ውስጥ 196 ያህሉ እጅግ ከፍተኛና ከፍተኛ፣ 40 መዛግብት መካከለኛና ዝቅተኛ ጥራት እንዳላቸው ገልጸዋል፡፡
በኦዲቱ ከተካተቱ 128 የወንጀል መዛግብት ውስጥ 105 መዛግብት እጅግ ከፍተኛና ከፍተኛ፣ 23 መዛግብት መካከለኛና ዝቅተኛ ጥራት ማስመዝገባቸው፣ ከ81 የቤተሰብ መዛግብት ውስጥ 71 እጅግ ከፍተኛና ከፍተኛ፣ 10 መዛግብት መካከለኛ፣ ዝቅተኛና በጣም ዝቅተኛ የጥራት ደረጃ ላይ እንደሚገኙ አብራርተዋል፡፡ ከ147 የአፈጻጸም መዛግብት ውስጥ ደግሞ 131 መዛግብት እጅግ ከፍተኛና ከፍተኛ፣ 16 መዛግብት ደግሞ መካከለኛና ዝቅተኛ ጥራት እንዳላቸው በኦዲት መረጋገጡን አቶ ዳንኤል ጠቅሰዋል፡፡
ባለፉት ጊዜያት በርካታ ስኬቶች መመዝገባቸውን የገለጹት የፌዴራል መጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት አቶ ፉአድ ኪያር፣ ያም ሆኖ ግን አሁንም ሊቀረፉ የሚገባቸው ውስንነቶች መኖራቸውን ተናግረዋል፡፡ ከእነዚህ መካከልም የዳኝነት አገልግሎት አሰጣጥ ጥራት ጉዳይ አንዱ ነው ብለዋል፡፡
ፍርድ ቤቱ በ2017 ዓ.ም. ባስጠናው የተገልጋይ እርካታ ጥናት ከ24 መለኪያዎች ውስጥ በ17 መለኪያዎች ከ75 በመቶ በላይ በማምጣት በዓለም አቀፍ መመዘኛ ከፍተኛ አፈጻጸም ቢያገኝም፣ ዝቅተኛ አፈጻጸም ካገኘባቸው ጉዳዮች ውስጥ የዳኝነት አገልግሎት ጥራት አንዱ መሆኑ ለኦዲቱ መደረግ መነሻ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ከጥናቱ በተጨማሪ በየዕለቱ ከሚመጡ አቤቱታዎችና ከባለድርሻ አካላት የሚነሳ ውስንነት ጭምር መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
