በስንታየሁ ወልደኃዋርያት
የትኞቹም ፖለቲከኞች ከውሸት በስተቀር እውነትን ፊት ለፊት አይናገሩም፡፡ አቦይ ስብሐት ግን ውሸትም ይሁን እውነት የሚያምኑበትን ጉዳይ ፊት ለፊት ከሚነግሩን ፖለቲከኞች መካከል ግንባር ቀደም መሆናቸውን አውቃለሁ፡፡ ያመኑበትን ጉዳይ የፖለቲካ ሊፕስቲክ ሲቀቡት አይውሉም፡፡ ሆኖም ብዙውን ጊዜ ሊሉት የፈለጉትን በደንብ ስለማይተነትኑ፣ የተናገሩትን ለማብራራት ሌላ ተንታኝ ይፈልጋል፡፡
ባለማወቅ፣ በግዴለሽነትና በመዘንጋት ካልሆነ በስተቀር ኢሕአዴግ ወደ ሥልጣን ከመጣበት ከ1983 ዓ.ም. ጀምሮ አቦይ ለሚዲያ የሰጧቸውን ቃለ መጠይቆች በሙሉ እንደገና ብታዳምጡ፣ ለፖለቲካ ብለው ወዲያ ወዲህ ሲቀለማምዱ አታገኟቸውም፡፡ እንደ ፖለቲከኞች ብዙ ቀለማማና (Colorful) ቆልማማ ጉዳዮችን ተናጋሪ አይደሉም፡፡ በእርግጥ ዕድሜ ተጭኗቸው ነገሮች ሳይደራረቡባቸው በፊትም ቢሆን አልፎ አልፎ በመጠኑ የሚያምምቱ (Vague) አገላለጦችን ያዘወትራሉ፡፡ ለመዋሸት ብለው የሚቀላምዱት እንቶ ፈንቶ ግን የለም፡፡ ማንን ፈርተው? ሕወሓቶች እንደ አባት የሚመለከቷቸውና ወደ 90 ዓመታቸው እየተቃረቡ ያሉና ገና ብዙ ያልሳቱ ሽማግሌ ናቸው፡፡ ሕወሓት ያደረገውንና ያላደረገውን አምታትተው ያለፈን ‹‹መልካም›› ነገር ቢመኙ በእሳቸው አልተጀመረም፡፡ አዛዥ ናዛዥ የሆኑበት ያለፈ ነገር ይናፈቃል፡፡ ሰው የወለደውን ልጅና አድራጊ ፈጣሪ የነበረበትን የራሱን ‹‹መልካም›› ጊዜ አይናፍቅም? የሚገርመኝ ግን በደም የተገነባ አገርን መናፈቃቸው ነው፡፡ ‹‹በደም የተገነባ አገር›› ሲባል፣ ውድ የሆነ መስዋዕትነት ተከፍሎ የተገነባ አገር ለማለት የሚውል አባባል ነው፡፡ ዕውን ሕወሓት ለኢትዮጵያ ሲል ደም ከፍሏል? ሕወሓቶች በዚህ የሚስቁ ይመስለኛል፡፡ በግሌ ሁሌም በምፀት እንደ ሳቅሁኝ ነው፡፡
ያለችው ኢትዮጵያ፣ ሕወሓት በደም አበላ ያጠመቃት አገር ናት እንጂ በደም የገነባት የጋራ አገር አይደለችም፡፡ በደም አጥምቆ፣ በደም መስመር የምትገነባ አገር ዘርግቶ፣ ደም አሁንም በአገሪቱ ውስጥ እንደ ጎርፍ እየፈሰሰ ነው፡፡ ሕወሓት የዛሬ ስድስት ዓመት አካባቢ ደምን ለሌሎች ብሔረሰቦች አውርሶ፣ እሱ ግን የጠራ ውኃ ሊጠጣ ወደ ፈለቀበት የምንጭ ውኃ ተሰብስቧል፡፡ ችግሩ፣ ከዚያም ከዚያም ተጠራርቶ በአንድነት ከተሰባሰበ በኋላ ምንጩን አደፈረሰው፡፡ ሕዝብ ንፁህ ውኃ እንዳይጠጣ በደም በከለው፡፡ ሕዝቡን በደም አጠመቃቸው፡፡ ሕወሓት ልጃቸው ነውና፣ አቦይ ለወለዱት ልጃቸው ቢሳሱለት ማን ይፈርድባቸዋል? በከንቱ ያፈሰሰውና ሊያፈስ የተዘጋጀው ደም አልታያቸውም፡፡ እንኳን ለሽማግሌው አቦይ ስብሐት፣ ለወጣት ሕወሓታውያንም አልታያቸውም፡፡ በአቦይ አልፈርድባቸውም፡፡
ዛሬ ላይ ቆመው፣ ከሃምሳ ዓመታት በፊት ጀምሮ ድርጅታቸው ሲያቀነቅነው የነበረውንና በማንነት/ቋንቋ ልዩነቶች/ክልሎች መሠረት ላይ በጻፉት ሕገ መንግሥት ላይ ያቆሙት ‹‹ብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች›› የማንነት ፌዴሬሽን መሆኑን ረስተው፣ ‹‹አማራ፣ ኦሮሞ፣ … እያላችሁ አትከፋፍሉ›› አሉን (የተናገሩት ሕወሓትን ለተካው የብልፅግና መንግሥት መሆኑ ነው መሰለኝ፡፡ ሌላ ለማን ሊሆን ይችላል?)፡፡ የጻፉት ሕገ መንግሥት በማንነት/በቋንቋ መሠረት ላይ መሆኑና በዚያ ሕገ መንግሥት 30 ዓመታት ያስተዳደሩ መሆናቸውን ዘንግተውታል፡፡ ስለዘነጉት እንጂ ውሸት ለመናገር አስበው እንዳይደለ ግልጽ ነው፡፡ ለምሳሌ፣ ከተናገሯቸው መከፋፈያዎች መካከል አንዱን ብቻ በመጥቀስ ላሳይ፡፡
‹‹አማራ ራሱን ኢትዮጵያዊ እንጂ አማራ አይልም፡፡ በአማራ ስም የተደራጀ ድርጅት ባለመኖሩ፣ ኢሕዴንን ወደ ብአዴን ለውጠን የአማራ ድርጅት ፈጠርን›› በማለት የተናገሩት አቦይ ዛሬ ‹‹አማራ፣ ኦሮሞ፣ በማለት አትከፋፍሉ›› ይሉናል፡፡ ሕወሓት በሕገ መንግሥቱ ያልጻፈውን ነገር ብልፅግና ዛሬ አዲስ አልፈጠረም፡፡ ብልፅግና ሕወሓት ያበለሻሸውን ተረክ ጭምር በምክክር ሒደት ለማረም፣ ኮሚሽን አቋቁሞ ‹‹ኑ በአንድ ላይ እንምከር›› እያለ ነው፡፡ አቦይ ማንን ነው አትከፋፍሉ የሚሉት? ስለ አማራ ያነሳሁት አቦይ ያሉትን ለማስታወስ እንጂ ለሌላ የፖለቲካ ዓላማ አይደለም፡፡ አቦይ ለማዋሸት ሳይፈልጉ፣ ንግግራቸው እንደምን ቀላማጅ እንደሚያስመስልባቸው ለማሳየት ስል ያቀረብኩት አንድ ምሳሌ ብቻ መሆኑ ይታወቅልኝ፡፡
በኢትዮጵያ ውስጥ የተመሠረቱ ‹‹ነፃ አውጪ ንቅናቄዎች›› በሙሉ፣ ከሻዕቢያ ጀምሮ እስከ ሕወሓት፣ ከኦነግ እስከ ኦብነግ፣ ሌሎችም በሕወሓት የተፈለፈሉ ድርጅቶች የተመሠረቱት በተሳሳተ ተረክ ላይ አይደለም? ከሕወሓት/ኢሕአዴግ በፊት የነበሩ መንግሥታት በመሉ የአማራ ገዥዎች እንደነበሩ በመቁጠር ማታገያ የሚሆናቸውን ግንባር ቀደም የጋራ ጠላት ከፊታቸው አስቀምጠው አልነበረም እንዴ ኢትዮጵያን በነፃ አውጪነት ስም በደም አበላ ሲያጠምቋት የነበረው? ‹‹ሌሎች ብሔሮች በአንድ ብሔር ሲጨቆኑ ነበር›› በማለት የየብሔረሰባቸውን ደጋፊዎች ለማሰባሰብ እንዲችሉ አንድ ጠላት አስፈልጓቸው ነበር፡፡ እያደር ‹‹እኛ የአማራን ገዢ መደብ እንጂ ሕዝቡን አልፈረጅንም›› በማለት ለማለስለስ ቢሞክሩም፣ የትግል መስመራቸውንና ጠላታቸውን ግን እስከ ዛሬም ድረስ አልለወጡም፡፡ ዛሬም ድረስ የሁሉም ጠላት ተደርጎ የሚቆጠረው ሕወሓት ጠላቴ ነው በማለት የፈረጀው ተፈራጅ ነው፡፡ ብዙውን ጊዜ እንደ ጌታቸው ረዳ ዓይነት ፖለቲከኛ ‹‹የአማራ ኤሊት›› በማለት የጠላታቸውን ስም ማሞካሸት ቢሻውም፣ ያ ጠላት ቀድሞ ሲፈረጅ ከግንባር ቀደም ፈራጆች መካከል ደግሞ አቦይ ስብሐት አሉበት፡፡ ሕወሓት ለኢትዮጵያ ከሠራላት የሠራባት ይበልጣል፡፡ ሕወሓት በአገሪቱ የፈጸመባት ወንጀል በርካታ ነው፡፡ ታሪክን በወፍ በረር መቃኘት ሀቁን ሊያሳይ ይችላል በማለት አምናለሁ፡፡ ዛሬ ላይ ሆኖ ሕወሓት በብልፅግና ላይ ሊያላክክ አይችልም፡፡
ከ1983 እስከ 1998 ዓ.ም. (1991 እስከ 2005 እ.ኤ.አ.) የነበሩት 15 ዓመታት ለኢትዮጵያውያን ሁሉ በጣም ከባድ የነበሩ ወቅቶች ነበሩ፡፡ ከዝርፊያና ማንነት/ቋንቋ ፖለቲካ መደላድል ሥራዎቹ ውጪ ሕወሓት/ኢሕአዴግ ለሕዝብ ምንም ለውጥ ያላመጣባቸው ጊዜያት ነበሩ፡፡ ደርግን ተቃውመው የአገሪቱን ፖለቲካና ኤኮኖሚ ለመለወጥ ወደ ስልጣን መጥተዋል ብሎ ከገመታቸው ቡድኖች ምንም ለውጥ ያለማየቱ በራሱ ሕዝቡን ተስፋ ያስቆረጠበት ወቅትም ነበር፡፡ የተጠቀሱት 15 ዓመታት ቅራኔዎች የተስፋፉባቸውና ግራ መጋባት የነገሰባቸው በመሆናቸው በመላ አገሪቱ በፖለቲካ፣ በኢኮኖሚ ዕድገትና በማኅበረሰብ ልማት ረገድ ዝቅጠት የደረሰበትና ዕድገት ባለበት የረገጠበት ወቅት እንደነበር እንዴት ይረሳል?
በአንፃራዊነት፣ ሕወሓት፣ አባላቱና ከእሱ ጋር በማበራቸው በአንድ ሌሊት ኢንቨስተር የሆኑ አጃቢዎቹ ደስተኞችና በእብሪት የተወጠሩም ነበሩ፡፡ ሁሉም ነገር ባለበት እንዲረግጥ በርካታ የሚታዩና የማይታዩ ምክንያቶች ቢኖሩበትም፣ የሕወሓት/ኢሕአዴግ በማንነት/ቋንቋ/ዘር የተደቆሰ ፖለቲካና አድሏዊ የኤኮኖሚ ፖሊሲ ዋና ምክንያቶች የነበሩ ይመስለኛል፡፡ ሕወሓት የአገርን ሀብት ዘራፊና ቂመኛ ድርጅት በመሆኑ፣ ጠላት ብሎ የተነሳበትን ክፍል (ለምሳሌ፣ አማራንና ኦሮሞን) በማሳደድ ጊዜውን አጥፍቷል፡፡ ሕወሓት ለወጣበት ክፍል የሚያዳላ ፍርደ-ገምድል በመሆኑ የራሱን ወገን ሥፍራ እስኪያሲዝ ድረስ ሌሎች የአገሪቱ ብሔረሰቦች ተራ መጠበቅ ነበረባቸው፡፡
በትንሹ እንኳን ‹‹በጦርነት ጉዳት የደረሰባቸውን ማቋቋም›› በሚል ለትግራይ ቅድሚያ በሚሰጥ ስትራጂው ካለተቀናቃኝ የአገሪቱን ሀብት ለራሱ የደለደለበትን አካሄድ ብቻ ማጤኑ ይበቃል፡፡ በሕወሓት/ኢሕአዴግ አስተዳደር ውስጥ ዘረኝነትና ጭፍን አድልኦ በአገሪቱ ሰፍኖ አልነበረም? በመሆኑም፣ የመጀመሪያዎቹ ከአሥር እስከ አስራ አምስት ዓመታት ለሕዝቡም ሆነ ለሕወሓት/ኢሕአዴግ ከባድ ወቅቶች ነበሩ፡፡ በወቅቱ ሕወሓት ራሱ የፈጠራቸው ሦስት ዓይነት ጫናዎች/መባከኖች ነበሩበት፡-
አንደኛው፣ ሕወሓት ስግብግብ ስለሆነ የቱን ዘርፎ የቱን እንደሚተው አጥቶት በሁሉም ውስጥ (በሥልጣኑም፣ በገንዘቡም፣ በመሬቱም፣ በቁሳቁሱም፣…) በአንድ ጊዜ መባከን ከበደው፡፡ ሊመሰርታት ለሚያስባት ታላቋ ትግራይ ሁሉንም ነገር መዝረፍና ማከማቸት የነበረበት መስሎ ታይቷል፡፡ በብዙ የጣረውም ለዚያ ነበረ፡፡ በዚህ ረገድ ጠንካራ አንድነት ያለው ድርጅት ይምሰል እንጂ፣ ድርጊቱ ባካኝ አድርጎት ታይቷል፡፡ አገሪቱን ለማስተዳደር ጨንቆት (በዕውቀት ማነስ) ስለነበር፣ በሚፈጥራቸው ውዥንብሮች ሽፋን ሰጪነት ቀላል መስሎ በታየው የዝርፊያ፣ የእስርና የግድያ መረቦቹ ላይ ተጠምዶ ነበር፡፡ እንደ ኢትዮጵያ ያለ ትልቅ አገር ማስተዳደር ቀላል አይደለም፡፡ አገርን ማስተዳድር ጠመንጃ እንደመተኮስ የቀለለው አልመሰለኝም፡፡
ሁለተኛው፣ ዜጎችን ካለ አድልኦ በሕግ መሠረት የማስተዳደር ልምድ ስላልነበረው ሕጋዊነት ከበደው፡፡ በመሆኑም የመጀመሪያዎቹ ዓመታት ሕግ አልባ ነበሩ፡፡ ራሱ ሕግ በመሆን የሕግን ደብዛ ረምርሞት ሲራመድ ታይቷል፡፡ በወቅቱ የበረው ስንቱ ኢ-ሕጋዊነት ይነሳል? በዝምታ ልለፈው፡፡
ሦስተኛው፣ ለታላቋ ትግራይ ብቻ የሰፋው ጠባብ የነፃነትና የልማት ጥቡቆ ለሰፊዋና ታላቋ ኢትዮጵያ ሊሆናት አልቻለምና ሐሳቡን ማስፋት ከበደው፡፡ እንደ ጠበበ ሲውተረተር ጊዜ አልበቃ አለው፡፡ ባከነ፡፡
በአጠቃላይ ሰፊ አገርና ሕዝብ ማስተዳደር ከብዶት፣ አገሪቱን እየከፋፈለ ለራሱና ለደጋፊዎቹ ጥቅምን ለመሰብሰብ በዘረፋ ብቻ ተሰማርቶ ነበር የሚለውን ሐሳብ፣ ከደጋፊዎቹ በስተቀር ብዙዎች ይስማሙበታል፡፡ ቀለል አድርጎ ሲታይ ይህንን ቢመስልም፣ የመንግሥትነት ባህሪ ተላብሶ መረጋጋት የጀመረው ከኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት በኋላ እንደነበር አቦይ አይስቱትም፡፡ በአቶ በረከት ‹‹የሁለት ምርጫዎች ወግ›› መጽሐፍ ውስጥ ከምርጫ 1997 ዓ.ም. በኋላ ሕወሓት ዴሞክራሲን ለማስፈንም ሆነ ልማትን ከገጠር ወደ ከተማ ለማምጣት እንደተነሳ ይገልጣል፡፡ ሕወሓት/ኢሕአዴግ በ1997 ዓ.ም. ምርጫ ወቅት ጥቂት የማይባሉ የምክር ቤት መቀመጫዎችን በተቃዋሚዎች በማጣቱና አዲስ አባበን ሙሉ በሙሉ በመሸነፉ፣ ራሱን ገምግሞ ወደ ልማት አቅጣጫ ትኩረቱን ለማድረግ ውሳኔ ላይ መድረሱ ተነስቷል፡፡ ይህ እንግዲህ ከ1983 እስከ 1997 ዓ.ም. ባሉት 14 ዓመታት ሕወሓት ምን ሲፈጥር እንደነበር በወቅቱ የነበረ ያውቀዋል በማለት ልዝለለው፡፡ ዕይታ ከቆሙበት ቦታ አንፃር መሆኑ እርግጥ ቢሆንም፣ ያዩትን አለመመስከር ንፉግነት ነውና በወቅቱ የነበረ ይመስክር፡፡
በወቅቱ የኢትዮጵያ ሕዝብ በሰላም ዕጦት ተወጥሮ፣ ሠርቶ እንዳይበላ በመድልኦ ታጥሮና ተጨንቆ እጅግ ከባድ በሆነ ሁኔታ ውስጥ ይገኝ ነበር፡፡ የዚያን ዓይነቱ ስሜት ሕወሓት ለነበሩና ለደጋፊዎቻቸው ሊሰማቸው አይችልምና አቦይ እንዴት ሊሰማቸው ይችላል? አቦይ ደግሞ በተፈጥሯቸው ፖለቲካዊ ውሸትና ነገር ማሳመር አይችሉበትም፡፡
በደም ተገነባ የተባለለትን የሕወሓት/ኢሕአዴግን የአስተዳደር/አገዛዝ ወቅቶችና ስትራተጂዎች በአምስት ዓበይት ክፍሎች/ክንዋኔዎች በመክፈል የሽግግር ወቅትንና የኢፌዲሪ መንግሥቱን ጠባዮች አጭር ትንተና ማቅረብ ይቻላል (በዚህ ጉዳይ ላይ “Azmach and Zemecha” በሚል ርዕስ በ2010 ዓ.ም. (2018 እ.ኤ.አ.) በእንግሊዝኛ በጻፍኩት መጽሐፍና፣ በኋላም የተወሰኑ ምዕራፎችን ብቻ በመውሰድ ‹‹ሦስቱ የኢትዮጵያ መንግሥታትና ተቃዋሚዎቻቸው›› በሚል ርዕስ የራሴኑ ጽሑፍ በ2015 ዓ.ም. ወደ አማርኛ በመለስኩት መጽሐፍ ውስጥ ተተንትኗል) ፡፡
የመጀመሪያ ክንዋኔዎች የተካሄዱት ከግንቦት 1983 እስከ 1987 ዓ.ም. (1991-1994 እ.ኤ.አ.) በነበሩት አራትና አምስት ዓመታት ወቅት ነው፡፡ ወቅቱ ከፋፍለህ ግዛው፣ በማንነት/በዘር/ጎሳ መካከልና በውስጣቸው ሚናን መለያና ጥላቻን ማፋፊያ (ግድያን ጨምሮ) በግልጽ የተደረጉባቸው ዓመታት ነበሩ ማለት ይቻላል (በአርባጉጉ፣ በበደኖ፣ በጨለንቆና በተለያዩ የከተማና የገጠር ሥፍራዎች ሲካሄዱ የነበሩ ግድያዎች በነማንና መቼ ተፈጸሙ?)፡፡ ወቅቱ፣ በግንባሩ ከሙከራ ስህተት የመማር ሒደትና (Trial and Error period)፣ ሕወሓት/ወያኔ ለዘላቂ ጥቅሙ የሚፈልጋቸውን የወደፊት ድብቅ ዕቅዶቹን ለመዘርጋት የሠራበት ጊዜ ነበር፡፡ ሕወሓት/ወያኔ የአገሪቱን ገንዘብ፣ የተለያዩ ቋሚና ተንቀሳቃሽ ንብረቶችን የጦርነት ካሳ አድርጎ በመቁጠር እየዘረፈ የንግድ ካምፓኒዎቹን ያስፋፋበት ወቅት ነበር፡፡ ማንም ተናጋሪ አልነበረውም፡፡ ከፈለገው ከተማ የፈለገውን ዘርፎ መውስድ ይችል ነበር፡፡ ማን አይገባህም (ገ ይጠብቃል) ሊለው ይችላል? መንግሥትን ማን ደፍሮ? ሕግ አልነበረም፡፡
የሕወሓት ዓላማ፣ ‹‹ማንም የኢኮኖሚውን የበላይነት የጨበጠ ክፍል የፖለቲካውንም የበላይነት ለረዥም ጊዜ ለመቆጣጠር ይችላል›› በሚል መርህ ላይ የተመሠረተ ነበር፡፡ ሕወሓት/ወያኔ በወቅቱ በግልጥ እንዳለው፣ የወሰዳቸው ንብረቶች ደርግን ለመጣል ለተሰውት የትግራይ ታጋዮች ‹‹የደም ዋጋ›› ነው፡፡ በዚህ የሽግግር ወቅት በሰላምና የዕርቅ ኮንፍረንስ በመሳተፍ የመንግሥት አካል ለመሆን ተስፋን ሰንቀው የነበሩት የተለያዩ ድርጅቶች (ኦነግ፣ የደቡብ ሕዝቦች ዴሞክራሲ ኅብረት፣ የሲዳማ አርነት ንቅናቄ) የሽግግሩን መንግሥት ጥለው ወጡ፡፡ ኤርትራም ነፃነቷን አወጀች፡፡ አቦይ ስብሐት፣ ‹‹የኤርትራ ጥያቄ የቅኝ ግዛት ጥያቄ ነው›› በማለት፣ ኤርትራ እንድትገነጠል ከሁሉም በላይ አቋም በመያዝ የሚታወቁ እንደነበሩ አውቃለሁ፡፡ ሕወሓት/ኢሕአዴግ ለራሱ እንጂ፣ ኢትዮጵያ እንድታሸንፍ ፍፁም ጥሮ አያውቅም፡፡ ‹‹በደም የገነቧት›› ኢትዮጵያ ወደ እሳቸው (ሕወሓት) እንድትመለስላቸው የጠየቁት አቦይ፣ ‹‹ኢትዮጵያ ቅኝ ገዢ ናትና ኤርትራ አትገባትም›› በማለት ከአገሪቱ ዘላቂ ጥቅም በተፃራሪ ቆመው የሞገቱ አልነበሩም? ዛሬ ኢትዮጵያ ወደብ-አልባ የሆነችው በሳቸውና በሕወሓት ፀረ-ኢትዮጵያ አቋም ነው በማለት የሚሞግት ሰው ተሳስቷል? አገሪቱ በወደብ-አልባነት ከጎረቤቶቿ ጋር ደም ወደ መቃባት እንድታመራ ማን አስቀድሞ ጠነሰሰው?
ከግንቦት 1983 እስከ 1987 ዓ.ም. (1991 እስከ 1994 እ.ኤ.አ.) በነበሩት አራትና አምስት ዓመታት ሕወሓት/ወያኔ ለድብቅ ዓላማው የሚያግዙትን ታማኝ የማንነት/የቋንቋ/የጎሳ ድርጅቶች (Ethnic Parties/Groups) ማደራጀትና የግንባሩ ደጋፊዎችና አጫፋሪዎች እንዲሆኑ በሰፊው መሥራት ጀመረ፡፡ ቀደም ሲል ወደ ትግራይ ጠቅልሎ የወሰዳቸው የአማራ አፅመ ርስቶች (ወልቃይት፣ ጠለምት፣ ራያ፣ …) ላይ ጥያቄ እንዳይነሳና የጎሳ ፖለቲካውን እንዲያጠናክርለት የሚያስችሉትን የማንነት/የቋንቋ ክልሎችን መዘርጋትና ሕጋዊ መልክ እንዲኖራቸው በጥንቃቄ ሠራ፡፡ ሁሉም ክልል በቋንቋው/ማንነት ተስታክኮ የተከለለለትን አካባቢ የራሱ (የማንነቱ) መሆኑን ብቻ እንዲመለከት፣ ሌሎችን የማኖርም ሆነ ያለማኖር መብቱ የራሱ መሆኑን በውስጡ እንዲያሰርጽና ለወደፊት የእርስ በእርስ ማዋጊያ ሊሆን የሚችለውን አደገኛ የልዩነት መሠረት በሕገ-መንግሥቱ ጭምር እንዲተከል አደረገ፡፡ “ራስን በራስ ማስተዳደር›› በሚለው መርህ ላይ በመንተራስ፣ የተለያየ የቋንቋ ብዝኃነት ያላቸው ሌሎች የአገሪቱ ብሔረሰቦች በሕወሓት ተከልሎ ከተሰጣቸው የማንነት/የቋንቋ ክልል ውጪ መኖር ጭንቅ እንዲሆንባቸው መሠረትን ጣለ፡፡
እንግዲህ ይህን ሁሉ ዘንግተው ወይም ቸል በማለት ነው አቦይ ‹‹አማራ፣ ኦሮሞ፣ … እያላችሁ አትከፋፍሉ›› የሚሉን፡፡ በእርግጥ በዕድሜያቸው መጨረሻ ላይ በእሳቸውና በድርጅታቸው ሕወሓት አማካይነት የተሠራውን ስህተት በይፋ ተናግረው የውስጣቸውን እውነት ማወጃቸው ያስመሰግናቸዋል፡፡ በእኔ እምነት፣ ኢትዮጵያውያንን በማንነት አትከፋፍሉ ማለታቸው፣ እሳቸውና ድርጅታቸው የሠሩትን ስሕተት በይፋ ማመናቸው ነው፡፡ በድርጅታቸው ሕወሓት የረቀቀውንና አገሪቱን በማንነት/ቋንቋ የከፋፈለውን ሕገ መንግሥት በይፋ መኮነናቸው ነው፡፡ በማንነት መከበር ስም አሁንም በየአቅጣጫው የብዝኃነትን አስተሳሰብ በሚጫንና የማንነት/ቋንቋ የበላይነትን በየሥፍራው በሚያነግሥ መልኩ የሚደረገው ሩጫ እንዲገታ መምከራቸው ነው፡፡ አማራ፣ ኦሮሞ፣ … በመባባል ልዩነትን ለመፍጠርና አንዱ የበላይ የሚሆንበትን ሥርዓት ለመፍጠር አትታገሉ፣ የሚበጀው ለሁሉም ብሔረሰቦቿ እኩል የሆነች ኢትዮጵያን ማቆየት ነው እያሉን ነው፡፡ አገሪቱን ከከፋፈሉና በደም የምትገዛበትን መንገድ ከወጠኑላት በኋላ፣ ከ30 ዓመታት በላይ ቆይተው ‹‹በማንነት አትከፋፍሉ›› በማለት መናገራቸው የንስሀ ጉዞ መሆኑ እሙን ነው፡፡ ድርጅታቸው ሕወሓትስ እንደሳቸው ያስብ ይሆን? ወይስ ንግግራቸው የአቦይ የመጃጀት ውጤት ነው ይላቸው ይሆን? ሕወሓት ድርጅት በመሆኑ፣ የመሥራቹን የአቦይ ስብሐትን ሐሳብ ተቀብሎ አብረው ንስሀ በመግባት የኢትዮጵያን ሕዝብ ይቅርታ ቢጠይቁ እንዴት መልካም ነበር!
ብዝኃነት በማንነት ፖለቲካ ብቻ ነው የሚስተናገደው ያለው ማነው? ሕወሓት ካዋቀረው ሌላ ለኢትዮጵያ ብዝኃነት የሚስማማ ሕብረ-ብሔራዊ ፌዴራላዊ ሥርዓት የለም? በአንድ ላይ መክራችሁ በብዝኃነቷ ያጌጠች ዴሞክራሲያዊትና ፌዴራላዊት ኢትዮጵያን ገንቡ ነው የአቦይ መልዕክት፡፡ አቦይ አሰላስለው የሚናገሩ ጥሩ ፖለቲከኛ ባለመሆናቸው እንጂ (Politically Correct ያልሆኑ ለማለት) ለማስተላለፍ የፈለጉት እውነት ያ ይመስለኛል፡፡ የመጨረሻ እውነተኛ ኑዛዜያቸውን ሳይሆን ይቀራል የቸሩን?
አቦይ ዘንግተውት እንደሆነ ነው እንጂ፣ በመጀመሪያ የኢትዮጵያ ብሔረሰቦችን በማንነት በመከፋፈል ‹‹ብሔር፣ ብሔረሰብ ሕዝቦች›› በማለት በዲስኩሩ ያበሰረና በሕገ መንግሥቱ በመቅረጽ እንደ ሃይማኖት እንዲመለክ ያደረገው ሕወሓት ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ ባንዲራ የመፈረጂያ መሣሪያ እንዲሆን ያደረገው ሕወሓት አይደለም? አቦይ ደግሞ የሕወሓት መሥራች ናቸው፡፡
ቀድሞም ቢሆን አገሪቱ ከ80 በላይ ቋንቋዎች የሚነገርባትና በርካታ ብሔረሰቦች ያሉባት አንድ አገር ናት በመባል የቆየች እንጂ፣ ብዝኃነት የሌላት አንድ አገር ናት ተብላ አታውቅም፡፡ በሕወሓት አፈራረጅና አገሪቱ በቋንቋ ክልሎች እንድትከለል እንደማድረጋቸው፣ ከ80 በላይ ቋንቋዎች ያሉባት ኢትዮጵያ ብሔሮቿም (ክልሎቿ) ከ80 በላይ ሊሆኑ በተገባ ነበር እንጂ 12 እና 13 የብሔር ክልሎች ብቻ ሊሆኑ ባልተገባ ነበር በማለት የሚሞግቱ ሰዎች አሉ፡፡ አገሪቱ የተከፋፈለችው በቋንቋ ማንነት አይደለም እንዴ? ብሔር በተባሉት ክልሎች ውስጥ ያሉ የብሔረሰብ ማንነቶችስ ወዴት ይቅሩ? እነሱስ ቋንቋና ባህል ያላቸው አይደሉም? ለምን ‹‹ይደፍጠጡ››? በማለት ለዴሞክራሲ በእጅጉ የሚቆረቆሩ ‹‹ክልላውያን›› አሉ፡፡ ሕወሓት፣ በትግራይ ክልል ያሉ ‹‹ሕዳጣን ብሔረሰቦች›› መብታቸውን ይጠይቃሉ በማለት አስቀድሞ ደፍቆ ይዞት እንጂ፣ ከራሱ ክልል ውጪ የሚያራምደው ሐሳብ ከላይ የተጠቀሰውን 80 የክልል መንግሥታትን ሊሆን ይችል ይሆን እንዴ?
ኢትዮጵያን፣ ብዝኃነትን አቅፋ የያዘች አንድ ትልቅ አገር (ብሔር) አድርጎ ማየት አንድ ነገር ነው፡፡ በአገሪቱ ውስጥ የተለያዩ ብዝኃነትን ለማስተናገድ የሚበጅ የፌዴራል አስተዳደር መከተልና፣ የአገሪቱ ብሔረ-ሰቦች በብዝኃነት ውስጥ (በኢትዮጵያ አገራቸው ውስጥ) ራሳቸውን እንዲያስተዳድሩ ማድረግ ደግሞ ሌላ ነገር ነው፡፡ እያንዳንዱ በየፓርቲው የተደራጀው ብሔረ-ሰብ ሁሉ ብሔር (አገር) ነኝ እያለ የየራሱን አገር በመመሥረት ላይ አትኩሮ መሥራት ደግሞ ፍፁም የተለየ ጉዳይ ነው፡፡ እንደዚያ ከሆነ ኢትዮጵያ 80 ቦታ ልትሸነሸን ነው? ማሰብ በራሱ ይከብዳል፡፡ በአገራዊ ምክክር ወቅት ይጠራ ይሆን?
ከዛሬ ሃምሳ ዓመታት በፊት የተጠየቁትን ጥያቄዎችና የየብሔረሰቦችን (በተለይ የአማራን፣ የኦሮሞን፣ የትግሬን) ኤሊት ኮሚኒስቶችን አመለካከት ይዘው ነው አሁንም ‹‹በብሔር፣ ብሔረ-ሰቦችና ሕዝቦች›› ስም እንቅልፍ ሳይተኙ የሚያቀነቅኑት፡፡ ዛሬም በኢትዮጵያ ውስጥ ኮሚኒዝም ሕይወት ዘርቶ አለ፡፡ በሶሻል ዴሞክራሲ፣ በሊበራል ዴሞክራሲ ቢሸፍኑት ዋጋ የለውም፡፡ የመሬትንና የግል ሀብት መብትን ዜሮነት በማየት ብቻ ኮሚኒዝምን በዓይን ማየት ይቻላል፡፡ ዛሬ የእነ ሌሊንና የስታሊን የኮሚኒዝም ዓለም የለም፡፡ ያለው ከዚያ ፍፁም የተለየ ዓለም ነው፡፡ የኢትዮጵያ ኮሚኒስቶች ግን ገና በሌኒንና ስታሊን ዘመን ውስጥ ሆነው እንደተኙ ናቸው፡፡ አቦይ ‹‹ላብ አደሩን፣ አርሶ አደሩንና አብዮታዊ ምሁሩን ይዘን ብቻ ነው አሁንም ለውጥ የምናመጣው›› ያሉን ጊዜ እኮ ሩቅ አይደለም፡፡ ሕወሓት ሁለት እግር አለኝ ብሎ ሁለት ዛፎች ላይ ለመውጣት የሚጥር እንደነበር ብዙዎች የሚመሰክሩት ጉዳይ ነው፡፡ ሰው በራሱ የግል ሀብት ላይ እንኳን መብት የለኝም በማለት እንደማሰብ ያለ ምን ዓይነት ኮሚኒዝም ይኖራል?
በኢትዮጵያ ያለው ሁሉም ጉዳይ በኮሚኒዝም አመለካከት በናወዙ ፖለቲከኞች የተሳከረ መሰለኝ፡፡
በወቅቱ በአብዛኛው ብሔረ-ሰቦች ሕወሓት ካደረሰባቸው መከራ ለመላቀቅ ባላቸው ዓላማ ስለኢትዮጵያ እንደ አገር መኖር (ስለ ኢትዮጵያ አንድነት) አስፈላጊነት እያነሱ መሆናቸው ይደመጣል፡፡ ድንቅ ሐሳብ ነው፡፡
ይህ ‹‹የኢትዮጵያ አንድነት›› የሚለው ሐሳብ በራሱ ግን፣ በግልጽ ተተንትኖ መታወቅ ያለበት ይመስለኛል፡፡ ‹‹አንድነት›› ሲባል፣ ምን ዓይነት አንድነት አስበው ይሆን ፖለቲከኞች የሚናገሩት? ዜጎችስ ምን ዓይነት የኢትዮጵያ አንድነትን ይሆን የሚጠብቁት? ይህ ሁኔታ ‹‹የኋላን ናፋቂነት›› እንዳይመስል ዘመኑን የዋጀ አስተሳሰብ ሊቸረው የሚገባ እንደሆነ ይታየኛል፡፡ አለበለዚያ ሁሎችም እንደፈለጋቸው ወይም እንደተመቻቸው ይተረጉሙታል ብዬ እሠጋለሁ፡፡
ልዩ ልዩ ብዝኃነት (Diversity) እንዴት በአንድነት ውስጥ ሊገለጥ ይችላል? የሚለው በራሱ ‹‹የፖለቲካ አይዲዮሎጂ›› ሊሆን የሚችል፣ ለሁሉም የቀረበ የቤት ሥራ መስሎ ይታየኛል፡፡ ይህንን የቤት ሥራ ሳይሠሩ ‹‹አንድነት›› ማለት፣ ምን ዓይነት አንድነት ብለው ለሚጠይቁ ክፍሎች መልስ ለመስጠት ያስቸግራል ብዬ እገምታለሁ፡፡
የቀደመው ዓይነት አሃዳዊ አንድነት ወይስ ልዩ ልዩ ብዝኃነትን (Diversity) ያቀፈ ራስን በራስ የማስተዳደር ፌዴራላዊ አንድነት? ፌዴራላዊ አንድነቱ ዜጋዊ ወይስ ማንነታዊ/ጎሳዊ (Ethnic ወይም በቋንቋ/ማንነት ላይ የተመሠረተ)? ‹‹አንድነቱ ከዜጋ ፖለቲካ›› አኳያ ሲታይ ‹‹ከአሃዳዊ አንድነት›› የሚለየው በምንድነው? እንዴት ቢሆን ነው ልዩ ልዩ ብዝኃነትን (Diversity) የያዘ፣ ኢትዮጵያዊ ዜግነትን ማዕከል ያደረገና ሁሉን በእኩልነት የሚጠቅም ራስን በራስ የማስተዳደር የብዝኃነት ፌዴሬሽን ሊገነባ የሚችለው? ‹‹ኮንፌዴሬሽናዊ አንድነት›› ነው ስለ ኢትዮጵያ አንድነት የሚቀነቀነው? … ወዘተ፣ የሚሉት ቀድመው መመለስ (መ ይጠብቃል) ያለባቸው ይመስለኛል፡፡ ሁሉም ጊዜ እንደሚጠይቅ ባልጠራጠርም፣ ቅድሚያ ማግኘት ያለበት ነገር ታውቆ ዕርምጃን መጀመር ብልኅነት መሆኑን አምናለሁ፡፡ መንገዱን አስቀድሞ በግልጥ ማየትና መተለም ወሳኝ ነው፡፡ የአገራዊ ምክክሩ ለእንደዚህ ዓይነቱ ግልጽነት ይበጅ ይሆን? ያልተሞከረን ነገር መሞከር መልካም ነው፡፡
በወቅቱ በብዛት የሚወሳው ስለ መደመር ነው፡፡ መደመር ማለት ግን ‹‹አንድነት›› ማለት ብቻ አይመስለኝም፡፡ አንድነት ማለት ከሆነም፣ ምን ዓይነት አንድነት የሚለውን ገና በግልጥ አልመለሰም፡፡ በእርግጥ በሒሳብ ቀመር U (ዩኒየን) ሁሉንም በአንድ ላይ የመደመር (የማከማቸት) ሒደትን ይሰጣል፡፡ ልክ የ ሀ ግልባጭ የሆነው በ(ኢንተርሴክሽን) ተመሳሳይ የሆኑ ነገሮችን ከትልቁ ስብስቦች ቀንሶ (ነጥሎ) በአንድ ላይ በመሰብሰብ የማስቀመጥ ምልክት እንደሆነ ሁሉ፡፡
ቀድሞም እኮ ኢትዮጵያ የተመሠረተችው በመደመር ነው፡፡ ልዩነቱ በዛሬው የንቃተ ህሊና ደረጃ የሚፈረጅ የመደመር ሒደት አለመሆኑ ነው፡፡ ወድዶ በመደመርና፤ በጦርነት፣ በፍልሰት ወይም በሌላ ስልት የሕዝብን ፍላጎት ሳይጠይቁ (መደመርን ሳያውጁ) መደመር መቻል (በጦርነትም ይሁን በሰላማዊ ፍልሰት) የመሆኑ ጉዳይ ነው፡፡ ምናልባት መደመር የሚለው ዕሳቤ፣ የኢትዮጵያን ያለፉና የዛሬ ታሪኮችን ያመዛዘነና የወደፊቱን ያቀደ፣ የፖለቲካዊ፣ ኤኮኖሚያዊና ማኅበረ-ሰባዊ ትርጉሞችን ሊያቅፍ የሚችል የአስተዳደር አቅጣጫ ከሆነ ወደፊት የበለጠ የምንረዳው ይሆናል፡፡ ለጊዜው ግን፣ መደመርን፣ ልዩነቶችን እንደያዙ በአንድ ላይ መሰብሰብና ለጋራ ዕድገት በአንድ ላይ እየሠሩ መልማት/ማደግ/መበልፀግ በሚለው ተርጓሜው ልቀጥልና፣ አቦይ ከማለፋቸው በፊት በዚህ ላይ ያላቸውን ሐሳብ ለጋዜጠኞች ቢያጋሩልን አደራ ማለት እፈልጋለሁ፡፡ አቦይ ሐሳብ ይኖራቸዋል፡፡ አይዋሹም፡፡
ሕወሓት በቆመበት ተቸንክሮ የቀረ በመሆኑ እንዲህ ዓይነት ጉዳይ ላይገባው ይችላል፡፡ ዝንተ ዓለም ‹‹ነፃ አውጪ›› በመባል ራሱን እንኳን በአዲስ ሐሳብ ነፃ የማያወጣ ድርጅት አይደንቅም? ምን ዓይነት አባዜ ነው? ራሱን ነፃ ያላወጣ ሌላውን እንዴት አድርጎ ነፃ ሊያጣ ይችላል? ስሙን እንኳን ቢቀይረው በማለት የሚገረሙ ብዙዎች ናቸው፡፡
ዛሬም በደም ማጥመቅና መጠመቅ ያልበቃው ሕወሓት አቦይ ስብሐትን ዛሬ ቢሰማቸውና ላፈሰሰውና እየፈሰሰ ላለው ደም ‹‹ይቅርታ››፣ “ይብቃን!” በማለት በይፋ ንስሐ ቢገባ የሁሉንም ኢትዮጵያዊ ምርቃት ባገኘ ነበር፡፡ ግን አያደርገውም፡፡ ገና ‹‹በደም የገነባት ኢትዮጵያ ትመለስልን›› በማለት ጠይቆ ተጨማሪ ደም እንዲፈስ በነበረበት ተቸንክሮ እንደሚቀጥል ይጠበቃል፡፡
ይልቅስ ሕወሓት መስራችህን የአቦይ ስብሐትን ምክር ስማ፡፡ ‹‹ኢትዮጵያውያንን አማራ፣ ኦሮሞ፣ እያላችሁ አትከፋፍሉዋቸው›› ብለዋል፡፡ ቀድም ስሕተት ተሠርቷልና ‹‹ይቅርታ›› በማለት አውጁና በንስሐ ከኃጢአታችሁ ስርየትን አግኙ፡፡ አገርም ከደም አበላ ትንሽ ዕረፍት ታግኝ፡፡ እስቲ ደም አድርቅ ዕርምጃዎችን ሞክሩ? የኢትዮጵያ ሕዝብ ደም ሰልችቶታል፡፡
ሰላም ለኢትዮጵያ፡፡ ሰላም ለሁላችን፡፡
ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እየገለጽን፣ በኢሜይል አድራሻቸው [email protected] ማግኘት ይቻላል፡፡