
በጌታነህ አማረ
ለአንድ አገር ዕድገትም ሆነ ውድቀት ዋናውና ትልቁን ሚና የሚጫወተው የሚያራምደው ርዕዮተ ዓለም ወይም ዕሳቤ ነው፡፡ አሁን አሁን ዓለማችን ላይ ያሉ የርዕዮተ ዓለም ዕሳቤዎች ነባሮቹንና በየጊዜው የሚወለዱ ችግሮችን ተጋፍጠው መፍትሔ ለመስጠት አቅም ሲያንሳቸው በስፋት ይታያል፡፡ በመሆኑም እነዚህ ዕሳቤዎች ያለባቸውን ችግር መርምሮ ዕልባት መስጠት ፈጽሞ ለነገ የማይባል ትልቅ የቤት ሥራ ሊሆንና በተለየ መንገድ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡ ይህንንም ተከትሎ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የመጣው የመደመር ዕሳቤ ነባር ከሚባሉት ሊበራሊዝም፣ ሶሻሊዝም፣ ኮሙዩኒዝምና ኒዮ ሊበራሊዝም ለየት ባለ አተያይ የመጣ የዕሳቤ ዓይነት ነው፡፡ የእነዚህ ዕሳቤዎች አንዱ ከአንዱ ያላቸው ድክመትና ጥንካሬ የሚለካው ካላቸው የነፃነትና የእኩልነትን ችግር የመፍታት አቅም አንፃር ነው፡፡
እንግዲህ እዚህ ዓለም ውስጥ የችግሮች መነሻም ሆነ የመፍትሔዎች ምንጭ መሠረት ነፃነት ነው፡፡ ነፃነት ችግር ስላለበት ኢእኩልነትን የበኩር ልጁ አድርጎ ወልዶታል፡፡ በመካከላቸው ፀብ፣ አለመግባባትና ትልቅ ተቃርኖ አለ፡፡ የዚህ ውጤት ደግሞ በዓለም ላይ ትልቁ መስፈርት የሌለው መከራና ችግር እንዲኖር አድርጓል፡፡ እናም የዕሳቤዎች መወለድ ሁሉ ዋና ዓላማ በእኩልነትና በነፃነት መሀል ያለውን ተቃርኖ ወይም ልዩነት ከቻሉ ማጥፋት ወይም ደግሞ ማጥበብና ሚዛን መሥራት ነው፡፡ ከዚህ አንፃር የትኛው ዕሳቤ ልዩነቶችን የማጥፋት ወይም ደግሞ የማጥበብና ሚዛን የመሥራት ኃይል ወይም አቅም አለው የሚለውን መርጦ ለችግሮች መፍቻ ጥቅም ላይ ማዋል የአገሮች ምርጫ ቢሆንም፣ አሁን ግን የትኛውንም ዕሳቤ መርጦ ጥቅም ላይ ማዋል ለችግሮች መፍትሔ መስጠት አልተቻለም፡፡
ስለዚህ እዚህ ጋ ቆሞ ለምን የሚለውን ጥያቄ ማንሳትና ለጥያቄው አግባብነት ያለው መልስ መስጠት ተገቢ ነው፡፡ በመሆኑም ይህንን ጥያቄ ለማንሳትም ሆነ መልስ ለመስጠት የዚህ ጽሑፍ መነሻ ርዕሰ ጉዳይ የመደመር ዕሳቤ ስለሆነ ጥያቄውና መልሱ የት ጋ እንደሆነ ለማየት እንሞክር፡፡ ከዚህ በፊት በዚሁ ጋዜጣ ‹‹የማክሮ ኢኮኖሚ ፖሊሲ አውጪዎች ችግር የት ጋ ነው ያለው?›› በሚል ርዕስ እ.ኤ.አ. የካቲት 12 ቀን 2025 (February 12, 2025) ልናገር በሚለው በዚህ ጋዜጣ ዓምድ ላይ በጻፍኩት ጽሑፍ፣ የአንድን አገር ኢኮኖሚ ለመግለጽ በእግር የሚነዳን ብስክሌት ምሳሌ በማድረግ ያስረዳሁበት መንገድ መኖሩ የሚታወስ ነው፡፡ በተመሳሳይ ‹‹የመደመር መንግሥት መጽሐፍ›› እና ዕሳቤውን ለማስተዋወቅ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በእግር የሚነዳ ብስክሌትን ምሳሌ በማድረግ ለማስተዋወቅ ተሠርቶ የቀረበው ማስታወቂያ በእጅጉ የመሰጠኝና ቀልቤን የሳበው ሆኗል።
ይህ ማስታወቂያ በጣም የሚገርምና የመደመር ዕሳቤን ቀለል ባለ መንገድና በጥቂት ደቂቃዎች ውስጥ ጠቅለል አድርጎ ማንም ሰው በቀላሉ እንዲረዳው ሆኖ የቀረበ ነው፡፡ በመሆኑም በመደመር ዕሳቤ ውስጥ ያለውን ድክመትና ጥንካሬ ለማስረዳት ይህን ማስታወቂያ መጠቀምን ቀላል መንገድ አድርጌ መርጬዋለሁ፡፡
በመጀመሪያ የተሠራውንና የተላለፈውን ማስታወቂያ ልክ ማየት ስጀምር ለምንና ምን ለማስተዋወቅ እንደሆነ ባላውቅም ትኩረቴን ግን በተለየ መልኩ የሳበው ሆኗል፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት ደግሞ ከላይ እንደጠቀስኩት አቀራረቡ ከዚህ ቀደም በዚህ ጋዜጣ ላይ ከጻፍኩት ጽሑፍ ጋር መመሳሰል ስላለው ነው።
ታዲያ ይህ ማስታወቂያ የውስጤን ሐሳብ ስለገለጸልኝ እኔ ለጻፍኩት ጽሑፍ የተሠራ እስኪመስለኝ ድረስ ከፍተኛ ደስታና ዕርካታ ተሰምቶኛል። በዚህም የማስታወቂያው ይዘትና አቀራረብም ሆነ መልዕክቱን ያስተላለፈበት መንገድ እኔን በገባኝ ልክ በጣም የሚገርምና የሚደነቅ ሆኖ አግኝቸዋለሁ። በስተመጨረሻም ማስታወቂያው የመደመር መጽሐፍን እያስተዋወቀ እንደሆነ የመጽሐፉን ስም እየጠራ ሲያስተዋውቅ ይሰማል፡፡ ጉዳዩ ይህ ከሆነ ዘንዳ በዚያ ሁሉ የማስታወቂያ ሒደት ውስጥ የመደመር ዕሳቤ ጥንካሬና ድክመት የቱ ጋር እንዳለ ለመረዳት ቀላል ነው፡፡ ይህ ማስታወቂያ የተሠራበት መንገድ በጣም ድንቅ ከመሆኑ የተነሳ የሌሎች የፋልስፍና ዕሳቤ የምንላቸውን ሊበራሊዝም፣ ኮሙዩኒዝም፣ ሶሻሊዝምና ኒዮ ሊበራሊዝም ድክመቶችና ጥንካሬዎችን በዚያች በአጭር ደቂቃ ቪዲዮ ውስጥ በቀላሉ መረዳትና ማወቅ ይቻላል።
From The Reporter Magazine
ቪዲዮው ልክ ሲጀምር አንድ ግለሰብ ከእነ ሙሉ የጉዞ ትጥቅ በመሆንና በእጁ የካርታ ፕላን በመያዝ በደሳሳና አባጣ ጎርባጣ በበዛበት ሠፈር (መንደር) ውስጥ ሳይክል ሲያሽከረክር ይታያል፡፡ ከዚም ትንሽ እንደተጓዘ የሳይክሉ የቴክኒክ ሁኔታ ያጠራጠረው በሚመስል ሁኔታ ካሰበ በኋላ ጉዞውን በመግታት የሳይክሉን የቴክኒክ ሁኔታ ሲፈትሽ ይታያል። ይህን ፍተሻም ሲያደርግ ትኩረት ያደረገው የሳይክሉን ፔዳል በእጁ ይዞ በማዞር ሰንሰለቱ ወይም ችንጋው ከጥርሱ (ጊር) ጋር በመናከስ በትክክል መዞር አለመሩን ፈትሾ ለጉዞ ብቁ መሆኑንና አለመሆኑን ያረጋግጣል። ካረጋገጠም በኋላ በዚያ ተደስቶ በረዥሙ በመተንፈስ ጉዞው አስተማማኝና ቀላል እንደሚሆንለት ተስፋ በማድረግ በደስታ ከተነፈሰ በኋላ ጉዞውን ሲጀምር ይታያል። ትንሽ ከተጓዘም በኋላ መስቀለኛ (መንታ) መስቀለኛ መንገድ ላይ ሲደርስ የሚሄድበት አቅጣጫ ወዴት እንደሆነ ለማወቅ ቆም ብሉ በእጁ የያዘውን ፕላን ሲያነብና ሲያስብ ይታያል፡፡
ያ በካርታው ላይ ያየውና ያሰበው መንገድ የመደመር ዕሳቤና ከተለመደው አስተሳሰብ ለየትና ወጣ ያለ እንደሆነ ለማስገንዘብ ይመስላል፡፡ ከዚያም ‹‹ትክክለኛውን መልስ ከመፈለግ በፊት ትክክለኛውን ጥያቄ ማንሳት ይቀድማል፤›› የሚል ንግግር በድምፅ ይመጣል፡፡ ከዚያም በመቀጠል ‹‹ምን ትፈልጋለህ?›› የሚል ንግግር ከመጣ በኋላ ጥያቄና መልሱን ያገኘ በሚመስል ሁኔታ በማለምና በማቀድ እንደገና ጉዞውን ሲቀጥል ይታያል፡፡ ከዚያም ሌሎች ተጓዦች ጉዞውን በመቀላቀል አብረውት ሲጓዙ ይታያል፡፡
በመቀጠልም ንግግሮች ይቀጥላሉ፣ ‹‹ካለንበት ችግርና ካለንበት የብልፅግና ደረጃ አንፃር በተለመደው መንገድ በመጓዝ የተለየ ውጤት ልናመጣ አንችልም ይልቁንስ ሚዛን ጠብቀን በግልጽና በተለየ መንገድ መሄድ ይኖርብናል፤›› ይላል በዚያ ጊዜ ውስጥ ግን ሳይክሎቹ ምቾት ባለው መንገድ ላይ በተሳካ ሁኔታ ሲጓዙ ይታያል፡፡ አሁንም ንግግሩን ቀጠል በማድረግ እንዲህ በማለት ይጀምራል፡፡ ‹‹ኋላ ከቀረንበት ወደፊት በመሻገር ከችግር አዙሪት ለመላቀቅና ተወዳዳሪ ሆነን መውጣት የምንችለው በመደመር መንግሥት የዕድገት ምህዋር ውስጥ ሚዛን ጠብቀን ስንገባ ነው፤›› እያለም ሳይክሎቹ አሁንም ምቾታቸው በጨመረ መልኩ በኮሪደር መንገድ ላይ ሲጓዙ ይታያል፡፡ ንግግሩን አሁንም እንዲህ ሲል ይቀጥላል፣ ‹‹ሕዝብን ያማከለ ወቅትን የዋጀ ሞዴል ተግባራዊ ለማድረግ መጓዝ ኢትዮጵያን የወደፊት ሕይወታችን በመልካም ጎኑ እንዲቀርፁ ያስችላል፡፡ ሲል ሳይክሉን በተለየ ሁኔታ ከፊት ቀድሞ የሚነዳው መሪውን ለቆ በደስታ ሲጓዝ ይታያል፤››፡፡ በመሠረቱ እንደ እኔ ዕይታ ያ ቦታ እንደ ሰላም፣ ዕድገትና ብልፅግና ቦታ የሚቆጠር ሲሆን አጠቃለን ስናየው ደግሞ የኢትዮጵያ ትንሳዔ ማለት ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ ከዚያም ተናጋሪው ንግግሩን ይቀጥላል፣ ‹‹ለትክክለኛው ጥያቄ ትክክለኛው መልስ የመደመር መንግሥት ነው፤›› ይላል፡፡ በመቀጠልም፣ ‹‹የበለፀገችና ገናና ኢትዮጵያን በጥቂት ዓመታት ውስጥ ዕውን የሚያደርግ መንገድ የኢትዮጵያ ፍኖተ ካርታ›› እያለ መጽሐፉን በማሳየት ማስታወቂያው ያበቃል፡፡
From The Reporter Magazine
ይህ ማስታወቂያ የመጽሑፉን መሠረታዊ ጽንሰ ሐሳብ ፍንትው አድርጎ የሚያሳይ ሲሆን፣ ችግሩና ጥንካሬውም የት ጋ እንዳለ ለመጠቆም ያቀልልናል፡፡ እንደተመለከትነው ሳይክል አሽከርካሪው የመደመር ዕሳቤ ለጉዞው ትክክለኛ መሠረት ሆኖት ከደሳሳ ሠፈር ወጥቶ በበለፀገው ከተማ በተለየ ደስታና ዕርካታ በሰመረው መንገድ ላይ በተለየ መተማመን መሪውን ለቆ ሳይክሉን ሲያሽከረክር ይታያል፡፡
ነገር ግን በገሃዱ ዓለም የመደመርም ሆነ የሌሎች ዕሳቤዎች እንደ ሳይክሉ ውጤት አምጥተዋል ብሎ መናገር አይቻልም፡፡ ምክንያቱም ሳይክሎቹ ሁሉንም ዜጋ ከዚያ ጎስቋላና ደሰሳ ሠፈር አሳፍረው በበለፀገው ከተማ መንገድ ላይ ሲሄዱ አልታዩም። ይልቁንም በጎስቋላው ሠፈርም ሆነ ባማረው መንገድ ላይ የተጎሳቆሉ ዜጎች በሳይክሎቹ መልካም ጉዞ ሲቋምጡ ይታያሉ እንጂ በደስታ ሲዋጡ አይታዩም፡፡ ይህ ለምን ሆነ ብሎ መጠየቅ እጅግ በጣም ጠቀሚ ነው፡፡ ጉዞው ሁሉንም የኅብረተሰብ ክፍል አቅፎ የማይሄድና የተወሰነ አካባቢንና ዜጎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ ነው፡፡ ለምን ይኼ ሆነ? ምክንያቱም ሳይክሉ አሳፍሮ የሚሄደው የተወሰኑ የኅብረተሰብ ክፍሎችን ብቻ ነው፡፡ ሁሉንም የኅብረተሰብ ክፍሎች ለምን ይዞ አይሄድም? ምክንያቱም የአቅም ውስንነት አለ፡፡ ያ የአቅም ውስንነት ከየት መጣ? ለብዙኃኑ ሕዝብ መጓዣ የሚሆነው ሳይክል ችንጋው (ሰንሰለቱ) ላልቷል አጥሯል ወይም ሰፍቷል፡፡ ሁሉንም ዜጋ አሳፍሮ መሄድ አይችልም፡፡ ታዲያ መፍትሔው ምንድነው? ብለን ስንጠይቅ መልሱ የላላውን ችንጋ ለክቶ በመግጠም ወይም በረጂስትሮ እንደሚስተካከለው ሁሉ በችንጋ የሚመሰለውን የኢኮኖሚ ፖሊሲ በተርኒንግ ፖይንት አስተካክሎ ወደ ሰላም፣ ዕድገትና ብልፅግና ጉዞ መጀመር ለኢትዮጵያ የመጨረሻ አማራጭ ነው፡፡ ይህ ማለት ደግሞ ትንሳዔዋ ነው፡፡
እንግዲህ በአጠቃላይ ዓለም ላይ ሊፈቱ የሚችሉ በርካታ ችግሮች አሉ፡፡ ከነዚህ ውስጥም ዋና ዋና የሚባሉት አራት ናቸው እነሱም የነፃነትና እኩልነት ችግር፣ የድህነትና ኋላቀርነት ችግር፣ የኑሮ ውድነትና የሥራ አጥነት ችግርና ዘርፈ ብዙ ተንከባላይና በየጊዜው የሚወለዱ ችግሮች ናቸው፡፡
ከእነዚህ ሁሉ ችግሮች ውስጥ ከላይ በሦስተኛ ደረጃ ላይ የተጠቀሰው የኑሮ ውድነትና የሥራ አጥነት ችግር ሌሎቹን ችግሮች ለመፍታት በጣም መሠረታዊና ወሳኝ ነው፡፡ በመሆኑም የኢኮኖሚ ፖሊሲው ችግር በተርኒንግ ፖይንት ስተራቴጂካዊ ሲስተም ተቀረፈ ማለት በነፃነትና እኩልነት መሀል ያለው ክፍተት ይጠባል፡፡ የኑሮ ውድነትና የሥራ አጥነት ይጠፋል፡፡ ድህነትና ኋላቀርነት ይጠፋል፡፡ በመቀጠልም ዘርፈ ብዙ ተንከባላይና በየጊዜው የሚወለዱ ችግሮች በራሳቸው ጊዜ ይጠፋሉ ማለት ነው፡፡ ይህ የኢትዮጵያ ትንሳዔ ማለት ነው፡፡
ከላይ በምሳሌነት የተጠቀምነው ሳይክል የተለያዩ ክፍሎች አሉት፡፡ እነዚህ ክፍሎችም በኢኮኖሚው ውስጥ ላሉት የመዋቅር ክፍሎች በምሳሌነት ያስረዱናል፡፡ ከእነዚህ መዋቅሮች ውስጥም ዋና ዋና የሚባሉት የሳይክሉ መቀመጫና ዘንጎች፣ እነዚህ ማለት ተቋም ሲሆኑ በመንግሥትና የግል ድርጅቶች ይመሰላሉ፡፡
ፔዳል፣ የኃይል ማሳረፊያ (ማስተላለፊያ) ይህ ማለት ኃይል ለመፍጠር የሚያገለግል ክፍል ነው፡፡ ይህም በሰው፣ በነዳጅ ወይም በኤሌክትሪክ ኃይል ይመሰላል፡፡ ችንጋ ወይም ሰንሰለት በኢኮኖሚ ፖሊሲ ይመሰላል፡፡ ጥርስ ወይም ጊር፣ በኢኮኖሚ ሴክተር (ግብርና፣ ማዕድን፣ ማኑፋክቸሪንግ፣ አይሲቲ፣ ቱሪዝም፣ ኮንስትራሽን (ግንባታ)፣ አገልግሎትና ሌሎች ዘርፎች ይመሰላል፡፡ ሳይክል ጋላቢ (Bicycle Rider) ይህ በሠለጠነና በሥነ ምግባር በበለፀገ ዜጋ ይመሰላል፡፡ ሪጂስትሮ የኢኮኖሚ ፖሊሲውን ልኬት በምንመጥንበት ተርኒንግ ፖይንት ይመሰላል፡፡
ይህን ሳይክል ለማንቀሳቀስ ዕሳቤ ወይም ጽንሰ ሐሳብ ያስፈልጋል፡፡ ጽንሰ ሐሳቦቹ ደግሞ በተለያዩ ሐሳባውያን ፈልቀዋል፡፡ እነሱም ሊበራሊዝም፣ ሶሻሊዝም፣ ኮሙዩኒዝም፣ ኒዮ ሊበራሊዝምና መደመር ናቸው፡፡ የነዚህ ሁሉ ዓላማ አንድ ነው፡፡ ይህም ሳይክሉን አንቀሳቅሶ በመንዳት የሚፈለገው ሰላም፣ ዕድገትና ብልፅግና ቦታ ላይ መድረስ ነው፡፡ ዓላማቸው አንድ ሆኖ የሚሄዱበት (የሚያስቡበት) መንገድ ግን የተለያየ ነው፡፡ ለምን? ምን ለያያቸው? የቱ ጋር ተለያዩ? የተለያዩበት ቦታ ከተገኘስ የትኛው ዕሳቤ ሁሉንም ሊያስማማ ይችላል? ይህ ወሳኝ ጥያቄና መልሱም የዓለም ችግር ሁሉ መፍትሔ መሆን የሚችል ነው፡፡ ይህ በጣም ወሳኝ ጥያቄና መልስ ነው፡፡ እነዚህን ጥያቄዎች ከመመለሳችን በፊት መታወቅ ስላለበት ነገር እንበል፡፡ የሁሉም ጽንሰ ሐሳቦች መሠረት ነፃነትና እኩልነት ነው፡፡ የነፃነትና እኩልነትን ልዩነት ለመፍታት ደግሞ ሁለት አማራጮች አሉ፡፡ እነሱም መንግሥትና ገበያ ናቸው፡፡ መንግሥት ማለት ነፃነትንና እኩልነትን ቁጥጥር በማድግ አስጠብቃለሁ ሲል፣ ገበያ ማለት ደግሞ ተፈጥሮን መሠረት በማድረግ ሥውርና በማይታየው እጅ ለዜጎች ነፃነትንና እኩልነትን የሚያስጠብቅ ነው፡፡
እነዚህ ገበያ (ሥውር እጅ)፣ ነፃነትና ተፈጥሮ የሚባሉት ነገሮች ለጽንሰ ሐሳብ አመንጪዎች ራስ ምታት ሆነውባቸዋል፡፡ በመካከላቸው ጣልቃ እየገባን እናስተካክል፣ ጉድለታቸውን እንሞላለንና መስመር እናስይዛለን እያሉ በስፋት ሲታገሉ ይታያል፡፡ እነዚህ ጽንሰ ሐሳቦች (ሊበራሊዝም፣ ሶሻሊዝም፣ ኮሙዩኒዝምና ኒዮ ሊበራሊዝም) ችግሩን ለመፍታት የሚሞክሩበት መንገድ ገበያ (ተፈጥሮ) በራሱ የሚፈታበትና በገበያ ውስጥ የመንግሥት ጣልቃ ገብነት ሲኖር ነው ብለው ሲያምኑ፣ የመደመር ዕሳቤ ደግሞ በመንግሥት ጣልቃ ገብነትና በገበያ መሀከል የሚደረግ ትብብር ነው ብሎ ያምናል፡፡ እናም በአሁኑ ጊዜ ዕሳቤዎች ሁሉ ከተፈፈጥሮ ይልቅ በነፃነትና በእኩልነት መካከል ያለውን ልዩነት ከተፈጥሩ ይልቅ በራሳቸው ለመፍታት ሌት ከቀን መከራ ሲያዩ ይታያል፡፡ ይህ ማለት በአሁኑ ጊዜ ከተፈጥሮ ጋር ግብግብ መፍጠር ፈጽሞ የማይቻል መሆኑ መታወቅ ያለበት ጉዳይ ነው፡፡
ስለዚህ ከላይ ያነሳሁትን ጥያቄ ለመመለስ ሳይክል አሽከርካሪው ጉዞ ከመጀመሩ በፊት መጀመሪያ የፈተሸው ችንጋው በትክክል መዞሩንና አለመዞሩን ነው፡፡ ችንጋው ከጥርሱ ጋር በደንብ ተናክሶና ሚዛኑን ጠብቆ የሚዞር ከሆነ ጉዞው የተሳካ ይሆናል፡፡ ነገር ግን አጥሮ ወይም ረዝሞ ከጥርሱ ጋር በመናከስ ለመዞር ችግር ከገጠመው ችንጋው በደንብ ተለክቶ መታሰር አለበለዚያም ደግሞ በሪጂስትሮ መስተካከል ይኖርበታል፡፡ ይህ ሳይደረግ ግን ከእነ ችግሩ መጓዘ ጉዞው በብዙ ችግሮች የተሞላ ስለሚሆን፣ የሚደረገው ጉዞ አስቸጋሪና ውጤታማ ሳይሆን ቀርቶ ወደ ሚፈለገው ሰላም ዕድገትና ብልፅግና የማያደርስ ይሆናል፡፡ በመሆኑም አሁን ያሉት ዕሳቤዎች የገጠማቸው ችግር ይሄው ነው፡፡ ወደ ሰላም ዕድገትና ብልፅግና ለመድረስ ሲነሱ ችንጋውን ወይም የኢኮኖሚ ፖሊሲውን ለክተው አላሰሩትም ወይም ደግሞ በረጂስትሮ አላስተካከሉትም፡፡ ይህን ባለማድረጋቸው ወደ ሰላም፣ ዕድገትና ብልፅግና የሚያደርጉት ጉዞ ሁሉ በጣም አስቸጋሪ፣ መስዋትነትን የሚጠይቅ፣ ፈታኝና እልህ አስጨራሽ ሲሆንባቸው ይታያል፡፡
ነገር ግን በአሁኑ ጊዜ አገሮች የገጠማቸውን ችግር በአስተውሎት ቆም ብለው በማሰብ ያልተስተካከለውን ችንጋ በልኬት ገጠማ ወይም በሪጂስትሮ እንደሚስተካከል ሁሉ፣ የኢኮኖሚ ፖሊሲውም ተርኒንግ ፖይን ስትራቴጂ በሚባለው ሲስተም በማስተካከል አሁን ከገቡበት የኢኮኖሚ፣ የፖለቲካና የማኅበራዊ ቀውስ በመውጣት ወደ ሰላም፣ ዕድገትና ብልፅግና የሰመረ ጉዞ በማድረግ ቦታው ላይ መድረስ ይገባቸዋል ያ ቦታ ትንሳዔ ነው፡፡ እንግዲህ በዚህ ጉዳይ ላይ ኢትዮጵያ ቀዳሚ ሆና ከተገበረችው ትንሳዔዋ ተረጋገጠ ማለት ነው፡፡
ይህን ትንሳዔ በመያዝ ለአፍሪካ ብሎም ለአለም ብርሃን በመሆን ወደ ቀድሞ ታላቅነቷ ትመለሳለች የሚባለውም በዚህ መንገድ ነው፡፡ ይህን ለማድረግ ደግሞ ጠንካራና ይህን ወደ ተግባር መለወጥ የሚችሉ ጀግኖች ያስፈልጓታል፡፡ እንግዲህ ይህ ኩነት በኢትዮጵያ ታሪክ ከተከወኑ መካከል በጥንት ዘመን የተከወኑት የኪነ ጥበብ ግንባታ (አክሱም፣ ላሊበላ፣ ፋሲልና ጀጎል)፣ የዓድዋ ድልና የህዳሴ ግድብ ድሎች በላይ ድል ሆኖ የሚተገበረው የኢትዮጵያ ትንሳዔ መረጋገጥ ድል ከፍተኛውን ሥፍራ እንደሚይዝ የሚጠበቅ ኩነት ነው፡፡
ሁሉም ዕሳቤዎች (ሊበራሊዝም፣ ሶሻሊዝም፣ ኮሙዩኒዝም፣ ኒዮ ሊበራሊዝምና መደመር) ችንጋው ጋር ያለውን ችግር ካስተካከሉ ሁሉም ውጤታማ መሆናቸውን በመገንዘብ በአንድነት ሊበራሊዝም የሚባለው ዕሳቤ ሁሉኑም የሚያስማማ ይሆናል፡፡ በመሆኑም የመደመር ዕሳቤ ውጤታማ ሆኖ ለመቀጠልና ኢትዮጵያን ወደ የሚፈለገው ሰላም፣ ዕድገትና ብልፅግና አድርሶ ትንሳዔዋን በማረጋገጥ ታላቅ፣ በዓለም ላይ ስሟ የገነነ አገር ለማድረግና በዓለም ላይ ቀድሞ ምሳሌ መሆን ካሰበ በፍጥነት ኢኮኖሚው የገጠመውን ችግር በተርኒንግ ፖይንት ስትራቴጂካዊ ሲስተም ማስተካከል ይኖርበታል በሚለው ምክረ ሐሳብ ጽሑፌን እያጠቃለልኩ፣ ልጠቁም የምፈልገው ነገር ቢኖር የውኃው ልክ (ወርቃማው አማካይ) ቦታ መገኛ በተርኒንግ ፖይንት ላይ መሆኑን ነው፡፡
ከአዘጋጁ፡- ጸሐፊው የባንክና የኢኮኖሚ ባለሙያ ሲሆኑ፣ ጽሑፉ የእሳቸውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እየገለጽን በኢሜይል አድራሻቸው [email protected] ማግኘት ይቻላል፡፡