አራት ዓመታትን ጠብቆ የሚመጣው የአሜሪካ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ዘንድሮ ሊከናወን የሁለት ወራት ዕድሜ ቀርቶታል፡፡ ፕሬዚዳንታዊ ክርክር በሪፐብሊካንና በዴሞክራት ዕጩዎች በቀድሞው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕና በአሁኗ ምክትል ፕሬዚዳንት ካማላ ሃሪስ መካከል የሠላ ትችትን በመለዋወጥ እንደቀጠለ ነው፡፡
ይሁን እንጂ ፕሬዚዳንታዊ ክርክር እየቀጠለ ባለበት ወቅት በትራምፕ ላይ ለሁለተኛ ጊዜ የግድያ ሙከራ ተቃጥቶባቸዋል፡፡
የአሜሪካ መንግሥት ሹማምንት እንዳስታወቁት፣ በዶናልድ ትራምፕ ላይ በሰንበቱ የግድያ ሙከራ የተቃጣባቸው ፍሎሪዳ በሚገኘው የጎልፍ ክለባቸው ነው፡፡
ትራምፕ ከሁለት ወራት በፊት በፔንሲልቫኒያ ግዛት የምርጫ ቅስቀሳ ላይ ዲስኩር በሚያሰሙበት ጊዜ በተተኮሰባቸው ጥይት ጆሯቸውን መጭረፉ ይታወሳል፡፡
በቀድሞ ፕሬዚዳንት ርስት በሆነው የጎልፍ መጫወቻ ሜዳ ላይ ጥቃቱን ለመፈጸም የተንቀሳቀሰውና በቁጥጥር ሥር የዋለው ተጠርጣሪ የ58 ዓመት ዕድሜ ያለው ሪያን ዌስሊ የሐዋይ ግዛት ነዋሪ መሆኑን የአሜሪካ ሚዲያዎች ዘግበውታል፡፡
ዶናልድ ትራምፕ ፍሎሪዳ በውቅያኖስ ዳርቻ ላይ በሚገኘው የትራምፕ ኢንተርናሽናል ጎልፍ ክለባቸው ከመጫወታቸው በፊት አንድ ታጣቂ ለ12 ሰዓታት ያህል ቁጥቋጦ ውስጥ ተደብቆ እንደነበር ተዘግቧል፡፡ በዕለተ እሑድ ከሰዓት በኋላ ትራምፕና ጓደኛቸው የሪል ስቴት ገንቢው ስቲቭ ዊትኮፍ በዌስት ፓልም ቢች ሲደርሱ ሞቃታማ ደመናማ ነበር፡፡
‹‹በጎልፍ ሜዳ ከትራምፕ ከ300 እስከ 500 ሜትር ርቀት ላይ የሚገኘው ተጠርጣሪ በሰንሰለታማው አጥር ሥር ሆኖ ጠበንጃውን አነጣጥሮ ያየው የልዩ ጥበቃ ጓድ ባልደረባው ተኩስ ከፍቶበታል፤›› ይላል የቢቢሲ ዘገባ፡፡
ትራምፕ ምንም ዓይነት ጉዳት ሳይደርስባቸው በልዩ ጥበቃ አባላት አካባቢውን ለቀው እንዲሄዱ ተደርገዋል፡፡ የቀድሞ ፕሬዚዳንት ሰኞ ምሽት ላይ ‹‹አራት ወይም አምስት ሊሆኑ ይችላሉ›› የተኩስ ድምፅ እንደሰሙ ተናግረዋል፡፡
የልዩ ጥበቃ ምሥጢራዊ አገልግሎት ባለሟሉ በተጠርጣሪው አቅጣጫ ከ300 እስከ 500 ሜትሮች ርቀት ላይ ተኩስ ከፍቶ እንደነበር፣ ሆኖም ታጣቂው ትራምፕን በግልጽ ለማየት ዕድል አለማግኘቱን የፌዴራል መርማሪዎች ተናግረዋል፡፡
ትራምፕ በኤክስ (የቀድሞ ትዊተር) ገጻቸው በቀጥታ ሥርጭት ባደረጉት ንግግር፣ ‹‹ምሥጢራዊ አገልግሎት ጥቃት መሆኑን አውቆ ወዲያው ያዙኝ፤›› ብለዋል፡፡ ‹‹ወደ ተሽከርካሪ ውስጥ ገብተን በጥሩ ሁኔታ ተንቀሳቀስን፡፡ እኔ ከአንድ የጥበቃ ባልደረባ ጋር ነበርኩ ጥሩ ሥራም ሠርቷል፡፡››
‹‹ታጣቂው ምንም ዓይነት ጥይት አልተኮሰም፤›› ያሉት መርማሪዎች የተደበቀው በቁጥቋጦዎችና በረዣዥም የዘንባባ ዛፎች ውስጥ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
ተጠርጣሪው እሑድ ማለዳ በአካባቢው አቆጣጠር ከ1፡59 ሰዓት ጀምሮ አድፍጦ ይጠባበቅ ነበር፡፡ የተያዘውም ሁለት ዲጂታል ካሜራዎች፣ በጥቁር ፌስታል ውስጥ ምግብ፣ ኤስኬኤስ ዓይነት ከፊል አውቶማቲክ ጠመንጃ ጋር ነው፡፡
የሪፐብሊካኑ ፕሬዚዳንታዊ ዕጩ በቅስቀሳ ዘመቻቸው በማይሰማሩበት ጊዜ በየእሑዱ በዌስት ፓልም ቢች ጎልፍ ክለብ እንደሚያሳልፉ ነዋሪዎች ይናገራሉ፡፡
ይሁን እንጂ የልዩ ጥበቃ ቡድን (ሴክሬት ሰርቪስ) ዳይሬክተር ሮናልድ ሮው ሰኞ ላይ እንደተናገሩት፣ ‹‹የቀድሞው ፕሬዚዳንት ወደ እዚያ መሄድ እንኳን አልነበረባቸውም፡፡ ሆኖም ልዩ ጥበቃዎቹ በመጨረሻ ደቂቃ ላይ የደኅንነት ዕቅድ ማዘጋጀት ነበረባቸው፤››
እንደ ቢቢሲ ዘገባ፣ የከሸፈው ሴራ በፓልም ቢች የሚገኙን የትራምፕ ጎረቤቶች አንገብጋቢ ጥያቄዎችን እንዲያነሱ አድርጓቸዋል፡፡
ተጠርጣሪው የቀድሞው ፕሬዚዳንት ጎልፍ ለመጫወት እንደሚወጡ ያውቅ ነበር ወይስ ግምት ነበር? በቁጥቋጦ ውስጥ ተደብቆ ይህን ያህል ጊዜ ለምን ሳይታወቅ ቀረ?
ታጣቂው ከተደረሰበት በኋላ በጥቁር ኒሳን መኪና መሣሪያውንና ቦርሳውን ጥሎ ቢያመልጥም፣ አንዲት ሴት የመኪናውን ታርጋ ፎቶ አንስታ ለመርማሪዎች በመስጠቷ በፀጥታ ኃይሎች በተደረገው ክትትል ሊያዝ ችሏል፡፡
የ58 ዓመቱ ተጠርጣሪ ሪያን ፍርድ ቤት ቀርቦ በጦር መሣሪያ መያዝ ወንጀል ተከሷል፡፡
ሪያን በኖርዝ ካሮላይና ግዛት ወንጀሎችን ይፈጸም እንደነበር፣ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጹ ላይ በተካሄደው ምርመራም የውጭ ዜጎች ወደ ዩክሬን በመጓዝ ከሩሲያ ጎን እንዲሠለፉ የሚጠይቅ ጽሑፎች ማስፈሩም ተነግሯል፡፡
የፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ተፎካካሪ የሆኑት ካማላ ሃሪስ በኤክስ ገጻቸው ትራምፕ ደህና በመሆናቸው ደስተኛነታቸውን የገለጹት ሁከት በአሜሪካ ቦታ የለውም በማለት ጭምር ነው፡፡
ባለፈው ሐምሌ የተፈጸመውን የግድያ ሙከራ በመመርመር ላይ ያለውና ከዴሞክራቲክና ከሪፐብሊካን ፓርቲዎች የተውጣጣው የጋራ ግብረ ኃይል በቀድሞው ፕሬዚዳንት ላይ ጉዳት ባለማድረሱ ዕፎይታ እንደተሰማው መግለጹን ቪኦኤ ዘግቧል፡፡