የሚጥል በሽታ ከኅብረተሰብ የጤና አደጋዎችና ተላላፊ ካልሆኑ በሽታዎች መካከል አንዱና ዋነኛው ነው፡፡ ባልታሰበ ሰዓት፣ ቦታና ጊዜ የሚጥል ሲሆን፣ በጤና ላይ ከሚያስከትለው እክል ባሻገር በትምህርት፣ በሥራና በኢኮኖሚ ዕድገት ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ያሳድራል፡፡ አብዛኛው የኅብረተሰብ ክፍልም በሽታውን ከባዕድ አምልኮና ከእርኩስ መንፈስ ጋር ሲያያይዙት ወይም ሲያገናኙት ይስተዋላል፡፡
በሚጥል በሽታ ታማሚ ላይ የሚደርሰው አድሎና መገለል፣ ወደ ጤና ተቋም ሄዶ ተገቢውን ሕክምናና ምርመራ አለመውሰድ፣ የመድኃኒት ዕጦትና የዋጋ ውድነት፣ ኅብረተሰቡ በበሽታው ዙሪያ ያለው ግንዛቤ አናሳ መሆን ችግሩን ይበልጥ አወሳስቦታል፡፡
የሚጥል በሽታ ከሰው ወደ ሰው የማይተላለፍና ታክሞ መዳን የሚችል ነው፡፡ ታካሚው ሕክምናውን በሚገባ ከተከታተለ ከበሽታው 75 ከመቶ ያህል እንደሚላቀቅ፣ ሥራውንና ትምህርቱን በአግባቡ የማከናወን ብቃት እንደሚኖረው በዘርፉ የተሰማሩ ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡
በሽታው በተለያዩ ምክንያቶች ሊከሰት እንደሚችል፣ ከምክንያቶቹም መካከል አንዱ በጭንቅላት ላይ የሚደርስ ጉዳት እንደሆነ ባለሙያዎች ይገልጻሉ፡፡
እንደ ዓለም ጤና ድርጅት፣ በዓለም ላይ 50 ሚሊዮን የሚደርሱ ሰዎች በሚጥል በሽታ የተያዙ ናቸው፡፡ በአፍሪካም ከ25 ሚሊዮን በላይ ይገኛሉ፡፡
የጤና ሚኒስትር ደኤታ ደረጄ ድጉማ (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ በኢትዮጵያ ይህ ነው የሚባል የተሠራ ጥናት ባይኖርም፣ የሚጥል በሽታ ሕመምተኞች ቁጥር ሁለት ሚሊዮን እንደሚደርስ ይገመታል፡፡ ታማሚዎችም አማራጭ ባህላዊ ሕክምናን ለማፈላለግ ሲባል በሚወስዱት ጊዜ በርካታ ውስብስብ ችግሮች ያጋጥማቸዋል፡፡
የሚጥል ሕመም ካለባቸው ሰዎች መካከል 85 ከመቶ የሚሆኑት ምንም ዓይነት ሕክምና አልጀመሩም፡፡ ተገቢውን ሕክምና ያላገኘ የሚጥል በሽታ ደግሞ ለሞት ይዳርጋል፡፡ እንዲሁም ትምህርትና ሥራን ለመቋረጥና ከማኅበራዊ ኩነቶች ለመገለል ምክንያት ይሆናል፡፡
‹‹የእኔ የሚጥል ሕመም ጉዞ›› በሚል መሪ ቃል አሥረኛው ብሔራዊ የሚጥል ሕመም ወር የካቲት 3 ቀን 2017 ዓ.ም. ታስቦ በዋለበት ሥነ ሥርዓት ላይ ሚኒስትር ደኤታው እንዳብራሩት፣ የሚጥል ሕመም፣ የአዕምሮና ሌሎች ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን ለማከምና ለመከላከል የሚያስችል የአምስት ዓመት እስትራቴጂክ ዕቅድ ተዘጋጅቶ ወደ ሥራ ተገብቷል፡፡
ኢትዮጵያ ለረዥም ዓመታት ተላላፊ በሆኑ በሽታዎች ላይ ስትሠራ መቆየቷን፣ አሁን ግን ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች ዜጎችን ለሞት እየዳረጉ መምጣታቸውን፣ ከዚህም ውስጥ አንዱ የሚጥል በሽታ መሆኑን ገልጸው፣ ይህንኑ ችግር ለመቅረፍ ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶት እየተሰራና ሁሉም ሆስፒታሎች የሚጥል ሕመምን ከመለየት ጀምሮ ሕክምናው ላይ ትኩረት ሰጥተው እንዲሠሩ እየተደረገ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
በጤና ሚኒስቴር የበሽታዎች መከላከልና መቆጣጠር ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሕይወት ሰለሞን (ዶ/ር)፣ በሚጥል በሽታ ታማሚዎች ላይ በየዕለቱ የሚታየው ዘርፈ ብዙና የማግለል ሁኔታን ለመቀነስና የሕክምና፣ የመድኃኒት አቅርቦትና የሕክምና ግብዓትን ለማሟላት ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት ልዩ ትኩረት ሊሰጡባቸው እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡
የጤና ሚኒስቴርም ባለሙያዎችን ከማብቃት፣ የጤና ተቋማትን ከማዘጋጀትና የመድኃኒት አቅርቦትን ከማሻሻል ባለፈ በጤና ኤክስቴንሽን ፓኬጅ ውስጥ በማካተት ማኅበረሰቡን በልዩ ሁኔታ ለመድረስ በቁርጠኝነት እየሠራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የኬር ኢፕሊፕሲ ኢትዮጵያ መሥራችና ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ እናት በእውነቱ፣ ለታካሚዎች ፈተና ከሆነባቸው ጉዳዮች አንዱና ዋነኛው የመድኃኒትና የሕክምና ግብዓት እጥረት መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በጥቅምት ወር 2008 ዓ.ም. የተቋቋመው ኬር ኤፕሊፕሲ ኢትዮጵያ እስካሁን ድረስ ለ1185 የጤና ባለሙያዎች በኢፕሊፕሲ ምርምርና ሕክምና ዙሪያ ያተኮረ ሥልጠና፣ 12,400 ቤቶችን በመጎብኘት ለ1,400 የምክር አገልግሎት፣ ለ2,800 በሽተኞች የሕይወት አድን መድኃኒት በነፃና ለ3,700 መምህራን በኢፕሊፕሲ ዙሪያ ሥልጠና መስጠቱን የሕመሙ ተጠቂ ወ/ሮ እናት ተናግረዋል፡፡