
አዋሽ ኢንሹራንስ አክሲዮን ማኅበር በተጠናቀቀው የሒሳብ ዓመት ከታክስ በኋላ 956.7 ሚሊዮን ብር ማትረፉን አስታወቀ። ከታክስ በፊት የነበረው የኩባንያው ትርፍ 1.1 ቢሊዮን ብር መሆኑ ታውቋል።
አዋሽ ኢንሹራንስ ጥቅምት 22 ቀን 2018 ዓ.ም. ባካሄደው የባለአክሲዮኖች ጉባዔ ላይ የ2017 ሒሳብ ዓመት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርቱን ያቀረበ ሲሆን፣ በሒሳብ ዓመቱ ከታክስ በፊት 1.1 ቢሊዮን ብር በማግኘት የመጀመሪያው የግል የኢንሹራንስ ኩባንያ መሆኑ ተመላክቷል።
በኢንሹራንስ ኢንዱስትሪው ከአንድ ቢሊዮን ብር የተሻገረ ትርፍ መመዝገቡ ሪፖርት የተደረገው ከሦስት ዓመታት በፊት ነበር፡፡ ይህም በመንግሥት የኢትዮጵያ መድን ድርጅት የተመዘገበ ነው፡፡ በወቅቱ ከታክስ በፊት አስመዝግቦት የነበረው ትርፍ 1.3 ቢሊዮን ብር ሲሆን በ2017 መጠናቀቂያ ላይ 1.98 ቢሊዮን ብር በማትረፍ በኢንዱስትሪው ከፍተኛ የሚባለውን የትርፍ መጠን በማጻፍ የሚጠቀስ ነው፡፡ የአዋሽ ኢንሹራንስ የሒሳብ ዓመቱ ትርፍ በኢንዱስትሪው ሁለተኛው ከፍተኛ በመሆን የሚጠቀስ ሲሆን፣ ከግል የኢንሹራንስ ኩባንያዎች ደግሞ በቀዳሚነት የሚቀመጥ ስለመሆኑም የኩባንያው መግለጫ ያመለክታል፡፡


የአዋሽ ኢንሹራንስ የዳይሬክተሮች ቦርድ ሊቀመንበር አቶ ታደሰ ገመዳ ለጠቅላላ ጉባዔው ባቀረቡት ሪፖርትም ኩባንያቸው በሒሳብ ዓመቱ ያስመዘገበው ትርፍ በኢንዱስትሪው በግል የኢንሹራንስ ኩባንያዎች በከፍተኛነቱ የሚጠቀስ ነው፡፡ በሒሳብ ዓመቱ ከታክስ በኋላ ያስመዘገበው ትርፍ ከቀዳሚ ዓመት በ27 በመቶ ብልጫ ያለው መሆኑንም አመልክተው የአንድ አክሲዮን የትርፍ ድርሻ ምጣኔ 36 በመቶ መሆኑን አመልክተዋል፡፡
አዋሽ ኢንሹራንስ የሒሳብ ዓመቱ አፈጻጸም በትርፍ ብቻ ሳይሆን በሌሎች የኢንሹራንስ አገልግሎት በኢንዱስትሪው ገበያ ብልጫ የወሰደባቸው ዘርፎች መኖራቸውን ጭምር የሚያመለክት ነው፡፡ በዕለቱ በቀረበው ሪፖርት አዋሽ ኢንሹራንስ በ2017 የሒሳብ ዓመት አጠቃላይ ያሰባሰበው ዓረቦን በ43 በመቶ በማደግ 4.53 ቢሊዮን ብር ማድረስ ችሏል፡፡ በሒሳብ ዓመቱ ካሰባሰበው ዓረቦን ውስጥ ከፍተኛውን ድርሻ የሚይዘው
ጄኔራል ኢንሹራንስ (Non-Life) ሲሆን ከዚህ ዘርፍ የተሰበሰበው ዓረቦን ከ3.7 ቢሊዮን ብር በላይ ነው፡፡ የሕይወት ዘርፍ ኢንሹራንስ የዓረቦን ገቢውም የ48 በመቶ ዕድገት የታየበትና ከ565.2 ሚሊዮን ብር የተሰበሰበበት ነው፡፡ እንደዚሁም በተካፉል የኢንሹራንስ ዘርፍ 156 ሚሊዮን ብር የተሰበሰበበት ሲሆን፣ ከዚህ ዘርፍ የተሰበሰበው ዓረቦን ከቀዳሚው ዓመት የ124 በመቶ ዕድገት ያሳየ ነው ተብሏል፡፡ እነዚህ አፈጻጸሞች ኩባንያው ባለፉት 13 ዓመታት ከግል ኢንሹራንስ ኩባንያዎች መሪነቱን ይዞ እንዲቀጥል ማስቻሉን የኩባንያው መግለጫ አመላክቷል፡፡ በኢንዱስትሪው ውስጥ የያዘውን የገበያ ድርሻ በተመለከተ በተሰጠ ተጨማሪ መረጃ ከጄኔራል ኢንሹራንስ በዘርፉ ማሰባሰብ የተቻለው የዓረቦን መጠን ከአሁንም ከ17ቱ የግል ኢንሹራንስ ኩባንያዎች የገበያ መሪነቱን ይዞ እንዲቀጥል ማስቻሉን ነው፡፡ በሕይወትና ጤና መድን (Life Assurance) ዘርፍ ደግሞ ከሁሉም የአገሪቱ ኢንሹራንስ ኩባንያዎች ብልጫ ያለው የገበያ ድርሻ መያዙን ይጠቅሳል፡፡ በዚህ ዘርፍ በዓመቱ ውስጥ ብልጫ ያለውን ዓረቦን የሰበሰበው አዋሽ ኢንሹራንስ መሆኑንም ያመለክታል፡፡ በዚህ ዘርፍ በ2017 ከአዋሽ ኢንሹራንስ ቀጥሎ ከሕይወት መድን ዘርፍ ከፍተኛውን ዓረቦን የሰበሰበው የኢትዮጵያ መድን ድርጅት ነው፡፡ እንደ ሕይወትና ጤና መድን ዘርፍ ሁሉ በሸሪዓ መርህዎች በሚገዛው የተካፉል ዘርፍም አዋሽ ኢንሹራንስ ትልቁን የገበያ ድርሻ መውሰዱን ይኸው የኩባንያው አዋሽ ኢንሹራንስ በ2017 የሒሳብ ዓመት የተከፈለ ካፒታሉን በ38 በመቶ በማሳደግ 2.65 ቢሊዮን ብር ማድረስ ችሏል፡፡ ኢንሹራንስ ኩባንያው የተፈረመ ካፒታሉም አራት ቢሊዮን ብር ነው፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ አዋሽ ኢንሹራንስ የራሱን አዲስ የዋና መሥሪያ ቤት ለመገንባት ቀደም ብሎ መርጦ የነበረውን ዲዛይን በማሻሻል ወደ ግንባታ ሥራው መግባቱን የአዋሽ ኢንሹራንስ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ጅባት ዓለምነህ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
From The Reporter Magazine
ይህ ባለ 4B+G+35 ወለል ያለው የዋና መሥሪያ ቤት ሕንፃ ግንባታ ልደታ ክፍለ ከተማ ውስጥ የሚካሄድ ሲሆን፣ የሕንፃ ግንባታ የዲዛይን ማሻሻያ ሥራ (Design Revision)፣ ከተደረገ በኋላ የሾሪንግና የመሠረት ቁፋሮ ሥራዎችን ሙሉ በሙሉ በማጠናቀቅ፣ የዋናው ሕንፃ ግንባታ እየተከናወነ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል፡፡
ይህን የዋና መሥሪያ ቤት ሕንፃ ግንባታ ለማከናወን የተመረጠውና ውለታ በመፈጸም የግንባታ ሥራውን የጀመረው ቻይና ሬልዌይ ሰቨን ግሩፕ የተባለው የቻይና ኩባንያ ነው፡፡ ኩባንያው የስትራክቸራል ግንባታውን ለማካሄድ የኮንትራት ውል የተፈራረመበት የገንዘብ መጠንም 3.64 ቢሊዮን ብር እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡
አዋሽ ኢንሹራንስ መስከረም 20 ቀን 1987 ዓ.ም. ፈቃድ አግኝቶ ታኅሳስ 1987 ዓ.ም. በይፋ ሥራውን የጀመረ ኩባንያ ነው፡፡ በምሥረታ ወቅት ባለአክሲዮኖቹ 456 የነበሩ ሲሆኑ አሁን ላይ የባለአክሲዮኖች ብዛት 2,168 ደርሷል፡፡
From The Reporter Magazine
የኩባንያው የቅርንጫፍና የአገናኝ ቢሮዎቻች ብዛት በዓመቱ መጨረሻ 71 የደረሰ ደርሷል፡፡ የሽያጭ ወኪሎችን ብዛት ከ300 በላይ በማድረስ ከ100 ሺሕ በላይ ለሚሆኑ ደንበኞች ቀልጣፋና አስተማማኝ የመድን አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛል።