በዓለም ዙሪያ የሚካሄዱ ጦርነቶች በአብዛኛው እየቆሙ ወይም ወደ መጠናቀቂያቸው እየተቃረቡ ነው፡፡ እንደ ምሳሌ የሚጠቀሱትም በሩሲያና በዩክሬን፣ እንዲሁም እስራኤል ከሐማስና ከሂዝቦላህ ጋር ስታደርጋቸው የነበሩ ደም አፋሳሽ ጦርነቶች ወደ መጠናቀቂያቸው ተቃርበዋል፡፡ በተለይ በእስራኤልና በሐማስ መካከል የተኩስ አቁም ተደርጎ የእስረኞች ልውውጥ እየተደረገ ሲሆን፣ ከመኖሪያቸው ተፈናቅለው ተንከራታች የነበሩ ፍልስጤማውያን ስደተኞች ወደ ፍርስራሽነት የተለወጠችው ጋዛ በገፍ እየተመለሱ ነው፡፡ በእስራኤልና በሂዝቦላህ መካከል በተደረሰው የተኩስ አቁም ስምምነት ሊባኖሳውያን ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ሰላማቸው እየተመለሰ ነው፡፡ ዶናልድ ትራምፕ የአሜሪካን ሥልጣነ መንበር ከተረከቡ ወዲህ ለዩክሬን የሚደረገው ድጋፍ በመቆሙ፣ ከሩሲያ ጋር የሚደረገው ጦርነት በእጅጉ እየተቀዛቀዘ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚካሄዱ ደም አፋሳሽ ግጭቶች በአስቸኳይ እንዲቆሙ ለሰላማዊ ንግግርና ድርድር ዕድል ይሰጥ፡፡ በኢትዮጵያ ልማት በስፋት ማከናወን የሚቻለው ሰላም ሲሰፍን ብቻ ነው፡፡
ሁለተኛ ጉባዔውን ለሦስት ቀናት በአዲስ አበባ ከተማ እያካሄደ ያለው ገዥው ፓርቲ ብልፅግና በዛሬው ዕለት እንደሚያጠናቅቅ ይጠበቃል፡፡ በዚህ ጉባዔው ትልልቅ ውሳኔዎች እንደሚተላለፉ በፓርቲው ምክትል ፕሬዚዳንት ከቀናት በፊት በይፋ መነገሩ ይታወሳል፡፡ ከሚጠበቁት ትልልቅ ውሳኔዎች መካከል የሰላም ጉዳይ ግንባር ቀደም መሆን ይኖርበታል፡፡ አገሪቱን የመምራት ኃላፊነት የወሰደው ገዥው ብልፅግና ፓርቲ ከውስጣዊ ጉዳዮቹ በተጨማሪ፣ በአገራዊ ዙሪያ መለስ ጉዳዮች ላይ ሲነጋገር ለሰላም መስፈን የሚያስፈልጉ አማራጮችን በሚገባ በማየት ውሳኔ ላይ መድረስ አለበት፡፡ በዓለም ዙሪያ የሚካሄዱ ትልልቅ ግጭቶች ቆመው የሰላም አየር እንዲነፍስ እየተጠበቀ ሳለ፣ በኢትዮጵያም የጦር መሣሪያዎች ድምፅ እንዳይሰማ የሚያስችሉ ተስፋ ሰጪ ውሳኔዎች መተላለፍ ይኖርባቸዋል፡፡ ለዓመታት በግጭቶች ምክንያት የደረሱ ዕልቂቶች፣ ውድመቶችና መፈናቀሎች እንዲቆሙ ለሰላማዊ ንግግርና ድርድር በሩ ይከፈት፡፡
በግጭት ውስጥ ያሉ ሁሉም አካላትና የአገር ጉዳይ የሚያገባቸው ወገኖች በሙሉ በእኩልነት፣ በመከባበር፣ በመተሳሰብና በኃላፊነት ስሜት ኢትዮጵያ ከውድመት ውስጥ የምትወጣበትን መንገድ በጋራ ያመቻቹ፡፡ ማንም አሸናፊ የማይሆንበት ግጭት ያተረፈው የሕዝብ ዕልቂት፣ መፈናቀል፣ መራብ፣ መጠማት፣ መታረዝ፣ መጠለያ አልባ መሆን፣ አካላዊና ሥነ ልቦናዊ ጉዳት፣ የመሠረተ ልማቶች ውድመትና ተስፋ ማጣት ብቻ ነው፡፡ ስለዚህ በቀና መንፈስ መቀራረብ የሚፈጠርባቸውን የተለያዩ ዘዴዎች፣ እንዲሁም አገራዊ ነባር የግጭት አፈታት ሥልቶችና የሽምግልና ሥርዓቶችን ጭምር በመጠቀም ዓለም ማጣጣም የጀመረውን ሰላም መቌደስ ተገቢ ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ በመከባበርና በእኩልነት መርህ ለመመራት ራስን ማዘጋጀት ያስፈልጋል፡፡ ለኢትዮጵያ ሰላም ሲባል ማንኛውም ዋጋ ተከፍሎ ሕዝባችን ከገባበት ድባቴ ውስጥ ይውጣ፡፡ በአሁኑ ጊዜ ጦርነት ያለው ኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ ነው ተብሎም በዓለም መዘባበቻ አንሁን፡፡
አገር በማስተዳደር ላይ ያለው ብልፅግና ፓርቲ የሚመራው መንግሥት ከማንም በላይ ትልቅ ኃላፊነት አለበት፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ በመካሄድ ላይ ያሉ ግጭቶች በሙሉ እንዲቆሙ ከግማሽ በላይ መንገድ ለመጓዝ ተነሳሽነቱን ይውሰድ፡፡ ከመንግሥት መሠረታዊ ባህርያት ውስጥ ሁሉን ቻይነት፣ ለሚቀርቡለት ጥያቄዎች በአግባቡ ምላሽ የሚሰጥ፣ አገርንና ሕዝብን ማዕከል ለሚያደርጉ ጉዳዮች ትኩረት የሚቸር፣ በማንኛውም ሁኔታ ውስጥ የዜጎችን ፍላጎት ለማሟላት ጥረት የሚያደርግ፣ ለሕግ የበላይነት መከበር ማንኛውንም ዓይነት መስዋዕትነት የሚከፍልና ሌሎች መሰል ቁምነገሮች ይጠቀሳሉ፡፡ ይህ ሲባል ግን በየሥርቻው በሚፈበረኩ አጀንዳዎችና ትርክቶች በመሳብ፣ ግርታ የሚፈጥሩ ግለሰቦች ወይም ስብስቦች ንትርክ ውስጥ መዘፈቅ አለበት ማለት አይደለም፡፡ ነገር ግን ለአገር ሰላም የሚጠቅሙ መፍትሔዎች ከተለያዩ አቅጣጫዎች ሲጠቆሙ ትኩረት መስጠት ይኖርበታል፡፡ ኢትዮጵያን የሚጠቅማት ሰላም ስለሆነ ሰላማዊ መፍትሔዎች ይታሰብባቸው፡፡
ሌላው ትኩረት ሊሰጣቸው የሚገባው ለቅራኔም ሆነ ለግጭት መቀስቀስ ምክንያት የሆኑ ድርጊቶች ነው፡፡ ከዚህ ቀደም ለብልፅግና ፓርቲ በምርጫ ድምፅ ሰጥተው የመረጡት፣ ድጋፍ ሲሰጡት የነበሩ፣ እንዲሁም አባላቱ ጭምር የሚያሳስቡት ከሕግና ከሥርዓት ውጪ በመንግሥት መዋቅሮች ውስጥ የሚፈጸም ሙስና፣ በኔትወርክ ተደራጅቶ መዝረፍ፣ ለእኩልነትና ለጋራ ተጠቃሚነት ጠንቅ የሆኑ ብልሹ አሠራሮች እንዲወገዱ ነው፡፡ አገር በሕግና በሥርዓት ስትተዳደር ሕገወጦች አይፈነጩም፣ ለቅራኔና ለግጭት አባባሽ ድርጊቶችም መጋለጥ አይኖርም፡፡ ስለሆነም ገዥው ፓርቲም ሆነ መንግሥት የአገር ሰላምን ሊያደፈርሱ የሚችሉ ሁሉም ዓይነት ብልሹ አሠራሮች እንዲወገዱ ጥረት ያድርጉ፡፡ ችግሮች ከውስጥ መፅዳት ሲጀምሩ ለቅራኔም ሆነ ለግጭት መንስዔ የሚሆኑ ክስተቶች ይቀንሳሉ፡፡ በፖለቲካ ተዋንያን መካከል ለዓመታት የሚያስቸግረው ሻካራ ግንኙነት መልኩን እየቀየረ መቀራረብና መግባባት ይጀመራል፡፡ መግባባት ለንግግርና ለድርድር አመቺ ሁኔታ ሲፈጥር ለሰላም መስፈን ዕድል ይገኛል፡፡
ኢትዮጵያ በዓለም ዙሪያ በልማትም ሆነ በሌሎች መመዘኛዎች በዝቅተኛ ደረጃ ላይ ከሚገኙ አገሮች አንደኛዋ ናት፡፡ ሥር የሰደደ ድህነትና ዘርፈ ብዙ ችግሮች ያሉባት ኢትዮጵያ በግጭት ውስጥ ለመቀጠል የሚያስችል አቅም የላትም፡፡ በከፍተኛ የዕዳ ጫና ውስጥ ያለች አገር ለጦርነት የሚውል ኢኮኖሚያዊ አቅም እንደሌላት ማንም የሚገነዘበው እውነታ ነው፡፡ መሠረታዊ የሚባሉ ፍላጎቶችን ለዜጎቿ ለማሟላት በእጅጉ የምትቸገር አገር ግጭት ውስጥ ትቀጥል ማለት፣ በበርካታ ሚሊዮኖች ሕይወት ላይ እንደ መቀለድ ነው የሚቆጠረው፡፡ ለዘመናት ሲንከባለሉ በመጡ ትርክቶች ምክንያት በፖለቲካ ልሂቃኑ ውስጥ የከረሙ፣ እንዲሁም በዚህ ዘመን እንደገና ታድሰው ለግጭትና ለዕልቂት የዳረጉ ቅራኔዎች መላ ሊፈለግላቸው ይገባል፡፡ ወደ ጥፋት የሚወስደውን ጎዳና ሙጥኝ ከማለት ይልቅ ካለፉት ስህተቶች በመማር ለሰላም ግንባታ መተባበር ይሻላል፡፡ ለልዩነቶች ሁሉ ዕውቅና በመስጠት የጋራ ራዕይ ይዞ በብሔራዊ ጉዳዮች ላይ ስምምነት መፍጠር የሥልጣኔ ምልክት ስለሆነ፣ ለዘለቄታዊ ሰላም ሲባል ድርድር መተኪያ የሌለው አማራጭ ይሁን!