- የዋጋ ንረትንና የብር አቅም መዳከምን ለመከላከል ጠንካራ የፖሊሲ ምላሽ ያስፈልጋል ብሏል
በያሬድ ንጉሤ
የዓለም የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) የኢትዮጵያ የዋጋ ንረት አኃዝ በተያዘው እ.ኤ.አ. 2025 አጋማሽ ድረስ 25 በመቶ እንደሚደርስ ተነበየ፡፡
አይኤምኤፍ ይህንን ያስታወቀው ኢትዮጵያን አስመልክቶ ረቡዕ ጥር 21 ቀን 2017 ዓ.ም. ይፋ ባደረገው ሪፖርቱ ሲሆን፣ የዋጋ ንረቱ ወደ ነጠላ አኃዝ የሚወርደው ደግሞ እ.ኤ.አ. በ2028 እንደሆነ ገልጿል፡፡
ተቋሙ አክሎ እንደገለጸው የዋጋ ንረቱ ትንበያ የሚያሳየው ጭማሪ መንግሥት ተግባራዊ እያደረገ ያለው የነዳጅ ዋጋ ማሻቀብ የሚያስከትለው ነፀብራቅ ነው፡፡
እ.ኤ.አ. በ2025 የመጀመሪያዎቹ ሦስት ወራት ውስጥ የኢትዮጵያ መገበያያ ገንዘብ ወይም ብር ከውጭ አገሮች መገበያያዎች ጋር ሲነፃፀር ያለው አቅም እንደሚቀንስም ነው አይኤምኤፍ በትንበያው የገለጸው፡፡ ለዚህ ምክንያቱ ደግሞ በተለይ አገሮች የውጭ ምንዛሪ ገበያውን በፍላጎትና አቅርቦት ላይ የሚመሠረት (Floating Exchange Rate) ሲያደርጉ፣ በተደጋጋሚ የሚከሰትና የተለመደ እንደሆነ የምጣኔ ሀብት ባለሙያዎች ያስረዳሉ፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ በሐምሌ 2016 ዓ.ም. የውጭ ምንዛሪ ፖሊሲ ማሻሻያ ከተደረገ በኋላ የአገሪቱ የዋጋ ንረት 19 በመቶ ከነበረበት ከመስከረም እስከ ጥቅምት 2017 ዓ.ም. ድረስ ወደ 17 በመቶ መውረዱን፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ መግለጹ ይታወሳል፡፡ ለዚህም የምግብና ምግብ ነክ ያልሆኑ ሸቀጦች ዋጋ መቀነሱ አንድ ምክንያት እንደሆነ አይኤምኤፍ በዚሁ ሪፖርቱ ጠቁሟል፡፡
ከውጭ ምንዛሪ ፖሊሲ ለውጡ በኋላ የተከሰተው የዋጋ ንረት አነስተኛ ነው ያለው አይኤምኤፍ፣ ይሁንና የሸቀጦችና የአገልግሎቶች ዋጋ በተለይም የነዳጅ ዋጋ ጭማሪ በቀጣይ ጊዜያት እንደሚኖር ለሚጠበቀው የዋጋ ንረት ማሻቀብ የራሱ የሆነ አስተዋጽኦ እንደሚኖረውም በሪፖርቱ አትቷል፡፡
የገንዘብ ተቋሙ ሪፖርት ከዚሁ ጋር በተያያዘ የብር ከውጭ ምንዛሪ ጋር ያለው የመግዛት አቅም መዳከም (Devaluation) ለዋጋ ንረቱ ያበረከተው አስተዋጽኦ በአንፃራዊነት የተወሰነ ነው ብሏል፡፡
ከአገልግሎቶች የዋጋ ጭማሪ ጋር በተያያዘም ከመስከረም 2017 ዓ.ም. ወዲህ በኤሌክትሪክ ፍጆታ ላይ የ20 በመቶ የታሪፍ ጭማሪ መደረጉን፣ በሚቀጥሉት አራት ዓመታትም በየሦስት ወራት የአገልግሎት ዋጋ ጭማሪ እንደሚኖር በሪፖርቱ ተካቷል፡፡
አይኤምኤፍ ከኢኮኖሚ ዕድገት ጋር በተያያዘ ትንበያው የአገሪቱ ኢኮኖሚ ዕድገት መቀዛቀዝ በማሳየቱ 6.6 በመቶ እንደሚሆን፣ ለኢኮኖሚ ዕድገቱ መቀዛቀዝ በምክንያትነት የሚጠቀሱት ደግሞ ወደፊት ሊከሰቱ ይችላሉ የሚባሉ የዜጎች ቅሬታ፣ የፀጥታ ዕጦትና ቀጣናዊ ግጭቶች ናቸው ብሏል፡፡
በሌላ በኩል መንግሥት ከግብር አሰባሰብ አኳያ ጥሩ መሻሻል አሳይቷል ያለው ሪፖርቱ፣ ካለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀር በዚህ ዓመት 70 በመቶ ብልጫ ያለው የገቢ ግብር መሰብሰቡንም አስታውቋል፡፡ ለዚህ የግብር አሰባሰብ መሻሻል በተጨማሪ እሴት ታክስ (ቫት) ላይ የተደረገውን ጨምሮ የኤክሳይስ ታክስ ማሻሻያዎች፣ እንዲሁም የግብር መሠረቱን ለማስፋት የተከናወኑ ሥራዎች ድርሻ የጎላ ነው ብሏል፡፡ የውጭ ምንዛሪ ማሻሻያው በሐምሌ 2016 ዓ.ም. ተግባራዊ ከተደረገ በኋላም ከገቢ ምርቶች የተገኘው ገቢ በአንድ ወር ውስጥ የ92 በመቶ ጭማሪ አሳይቷል ነው ያለው፡፡
አይኤምኤፍ ከውጭ ምንዛሪ ገበያው ጋር በተያያዘም አለመረጋጋት ሊከሰት ይችላል ያለ ሲሆን፣ ይህም ምርትንና የገበያ ልማትን ሊጎዳ ይችላል ሲል ጠቁሟል፡፡
ቀጣይነት ሊኖረው የሚችል የዋጋ ንረትንና የብር አቅም መዳከምን መከላከል ጠንካራ የፖሊሲ ምላሽ የሚሻ ጉዳይ ነው በማለት፣ ከዚህ አኳያ የሚስተዋል መዘግየት ግን ኅብረተሰቡ በምላሹ ጫና መፍጠር እንዲጀምር ከማድረግ በተጨማሪ ሌሎች አደጋዎች ይኖሩታል ሲል አይኤምኤፍ በሪፖርቱ አስጠንቅቋል፡፡