
የሱዳን ፈጥኖ ደራሽ ሠራዊት (አርኤስኤፍ) ኤል ፋሽርን መቆጣጠሩ የሱዳን መንግሥት መከላከያ የመጨረሻ ጠንካራ ይዞታን ከማሳጣት ባለፈም፣ አገሪቱን ወደ ሌላ የጨለማ ምዕራፍ መሸጋገሩን የሰብአዊ መብት ተቆርቋሪ ድርጅቶች እየገለጹ ነው፡፡ ካለፈው ሳምንት ወዲህ በሱዳን የሰብአዊ መብት ጥሰትና ጥቃት እየተባባሰ መሆኑንም ያክላሉ፡፡


ባለፈው ሳምንት የዳርፉር ዋና ከተማ የሆነችውን ኤል ፋሽር የተቆጣጠረውና በመሐመድ ሃምዳን ደጋሎ (ሄሚቲ) የሚመራው የሱዳን ፈጥኖ ደራሽ ሠራዊት፣ በሺዎች የሚቆጠሩ የአካባቢው ነዋሪችን ከቀያቸው በማፈናቀል ለአዲስ ጥቃት እየተዘጋጀ መሆኑ ደግሞ የሰብዓዊ ቀውሱን የከፋ ያደርገዋል ሲል የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) አሳስቧል፡፡
ቀድሞም ለዓመታት በዘለቀ ግጭት ሳቢያ ለቸነፈር (ጠኔ) የተጋለጠው የዳርፉር ነዋሪ፣ አርኤስኤፍ በአል ፋሽር ያደረገውን ጭፍጨፋ በመፍራት መሰደድ የጀመረው ባለፈው ሳምንት ነበር፡፡
በተያዘው ሳምንት ደግሞ ሠራዊቱ ኤል ኦቢያድ ከተማን ለማጥቃት ማቀዱን ተከትሎ ነዋሪዎች ከኤል ኦቤያድ መውጣት ጀምረዋል፡፡
ሠራዊቱ አል ፈሽርን በተቆጣጠረ በሳምንት ጊዜ ውስጥ ከ70 ሺሕ በላይ ነዋሪዎች ከቀያቸው የተፈናቀሉ ሲሆን፣ የተፈናቃዮች ቁጥር እያየለ የመጣውም የሠራዊቱ ግድያና ሰብዓዊ መብት ጥሰት እየቀጠለ በመምጣቱ መሆኑን ተመድ ገልጿል፡፡


አርኤስኤፍ አል ፋሽርን ከመንግሥት መከላከያ ቁጥጥር ነፃ ካደረገ በኋላ፣ በከተማው አለመረጋጋት መፍጠሩ፣ እ.ኤ.አ. በ2023 በምዕራብ ዳርፉር አልጌኒና ከተማ እንዳደረገው ጎሳን መሠረት ያደረገ ጥቃት ሊፈጽም ይችላል በሚል ተፈጥሮ የነበረው ሥጋት ዕውን መሆኑ፣ ጅምላ ግድያ፣ የቤት ለቤት ፍተሻና ግድያ እየፈጸመ ስለመሆኑም ሆርን ኢንስቲትዩት በድረገጹ አስፍሯል፡፡
የአርኤስኤፍ አባላት የገደሏቸውንና የሚያሰቃዩዋቸውን በቪዲዮና በምሥል እየለቀቁ መሆኑ፣ ቀድሞውንም በረሃብና በከፋ ሰብዓዊ ቀውስ ለተጎዳው የዳርፉር ሕዝብ አዲስ የግድያና የሰቆቃ ማዕበል ይዞ መምጣቱንም ጠቁሟል፡፡
From The Reporter Magazine
በሺዎች የሚጠሩ እየተሰደዱ ባሉበትና የንፁኃን ግድያ ባየለበት በአሁኑ ወቅት፣ የሱዳን መከላከያ ሠራዊትና አርኤስኤፍ ኤል ኦቢድን ለመቆጣጠር ከፍተኛ ፍልሚያ ለማድረግ ዝግጅት እያደረጉ ይገኛል፡፡ ሁለቱ ተቀናቃኞች ራሳቸውን ለኤል ኦቢድ ጦርነት ሲያዘጋጁ፣ ከዚሁ መሳ ለመሳ የሱዳን ሕዝብ አስከፊ በተባለ ሰብዓዊ ቀውስ ውስጥ ወድቋል፡፡ በተለይ በኤል ፋሽርና በአካባቢው ያለው ሰቆቃ የከፋ መሆኑን አልጄዚራ ዘግቧል፡፡
በከተማው የሰብዓዊ ዕርዳታ ሠራተኞች ሳይቀሩ እየተገደሉ ነው፡፡ በአሥር ሺዎች የሚቆጠሩ በቸነፈር ተመትተዋል፡፡ መውጫ ያጡ የኤልፋሽር ከተማ ነዋሪዎችም እዚያው በሰቆቃ ውስጥ ወድቀዋል፡፡
ተመድና ሌሎች ዓለም አቀፍ ተቋማትም የአርኤስኤፍ ሠራዊት በጅምላ ግድያ፣ በአሰቃቂ ድብደባ፣ በመድፈርና በፆታዊ ጥቃት መሰማራታቸውን፣ ሰዎችን በማገት ገንዘብ እየጠየቁ ስለመሆናቸውም ማረጋገጣቸውን አሳውቀዋል፡፡
From The Reporter Magazine
ንፁኃን እያስተናገዱት ካለው ድብደባና ግድያ ባለፈ በምዕራብ ኮርዶፋን በኤል ማሽርና በካዱጊሊ በዓለም አቀፍ መሥፈርት መሰረት በከፍተኛ ደረጃ የተቀመጠው ቸነፈር/ጠኔ መግባቱንም ተመድ አስታውቋል፡፡
በዳርፉርና በኮርዶፋን ተጨማሪ 20 አካባቢዎችም ወደ ረሃብ አደጋ እየገቡ መሆኑን አሳውቋል፡፡ በአካባቢዎቹ በመስከረም 2018 ዓ.ም. በነበረ መረጃ 375 ሺሕ ሰዎች ቸነፈር/ጠኔ እንደመታቸው ተነግሮ ነበር፡፡
በመላ ሱዳን ደግሞ 6.3 ሚሊዮን ሰዎች ለከፋ ረሃብ መጋለጣቸውና ረሃቡ ወደ ቸነፈር እየተቀየረ ስለመሆኑም ተነግሯል፡፡
እንደ ሰብዓዊ ድግፍ አድራጊዎች፣ በርካታ ሱዳናውያንም በረሃብና በተመጣጠነ ምግብ እጥረት ሊሞቱ ይችላሉ፡፡
በሱዳን እየደረሰ ላለው ጭፍጨፋና ሰብዓዊ መብት ጥሰት አርኤስኤፍ ላይ ምርመራ እያደረገ ስለመሆኑም ዓለም አቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት ጥቅምት 24 ቀን 2018 ዓ.ም. አስታውቋል፡፡
ጎሳን መሠረት ያደረገ ጥቃት፣ መድፈርና መጥለፍን ጨምሮ ፆታዊ ጥቃት፣ ንፁኃን፣ የሕክምና ተቋማትና ባለሙያዎች ላይ የሚደረግ ጥቃትንም በምርመራው ማካተቱንም አክሏል፡፡
በሱዳን ለ18 ወራት የዘለቀውን ጦርነት ለማስቆም እዚህ ግባ የሚባል ዲፕሎማሲያዊ ጥረት አልታየም፡፡ በአገሪቱ ያለው የፖለቲካ ሁኔታም ከዕለት ዕለት እየተመሰቃቀለ እንጂ መሻሻልን አላሳየም፡፡
አሜሪካ፣ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች፣ ግብፅና ሱዳን የሱዳንን ጦርነት ለመገላገልና ጦርነት የሚያበቃበትን ፍኖተ ካርታ ለመተግበር በአሜሪካ ቢሰባሰቡም ውጤት አላመጡም፡፡ ጦርነቱን ለማስቆም ሆነ የተኩስ አቁም ስምምነት ለማስፈጸም የተደረገው ዲፕሎማሲያዊ ጥረትም ውጤት አልባ ሆኗል፡፡