ከሰማንያ አምስት በመቶ በላይ ኢትዮጵያውያን የሚተዳደሩት በግብርናው ዘርፍ ቢሆንም፣ በዘርፉ ያለው የሴቶች ተሳትፎ በጣም ዝቅተኛ መሆኑ ይነገራል፡፡ ‹‹ወንዶች ወደ ሜዳ ሴቶች ወደ ጓዳ›› በሚልና መሰል የሴቶችን ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ተሳትፎ በእጅጉ የሚቀንሱ አመለካከቶችና ልማዶች በማኅበረሰቡ ዘንድ መስረፃቸውና ይህንን ለመቀየር የሚሠሩ ሥራዎች በቂ ለውጥ ባለማምጣታቸው ዛሬም ሴቶች ከበርካታ ችግሮች አልተላቀቁም፡፡ በማኅበራዊ፣ በኢኮኖሚያዊና በፖለቲካዊ ተሳትፎም እንዲገደቡ አድርጓል፡፡
ምንም እንኳን ችግሩ ዓለም አቀፋዊ ቢሆንም፣ በአፍሪካ ባሉ አገሮች በተለይም ከሰሃራ በታች በሚገኙት ችግሩ ተንሰራፍቶ ይገኛል፡፡ ዛሬም ድረስ በርካታ አፍሪካውያን ሴቶች በኢኮኖሚ ራሳቸውን ሳይችሉ፣ በወንዶች አልያም የመንግሥትና የረጂ ድርጅቶች ጥገኛ በመሆን በረሃብና በችግር ሲገረፉ ማየት አልቀረም፡፡
በአፍሪካ ማኅበረሰቡ በተለይም ይበልጥ የምግብ ዋስትና ችግር ያለባቸው ሴቶች ራሳቸውን በምግብ እንዲችሉ የሚበቃ ሰፊ የግብርና ዘርፍ ቢኖርም፣ በተለያዩ ምክንያቶች ሴቶችን የሚያሳትፍ ፖሊሲዎችና ስተራቴጂዎች በአግባቡ አለመተግበራቸው ችግሩን ካባባሱት ይጠቀሳል፡፡
ችግሩን ለመፍታትና ሴቶች በግብርናው ዘርፍ ያላቸውን ተሳትፎ ከፍ ለማድረግ በአኅጉር ደረጃ በጋራ ለመሥራት የሚያስችሉ ፖሊሲዎችና መመርያዎች ቀርበዋል፡፡ የጋራ ስምምነቶችም ተደርሰዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል ለአፍሪካ የምግብ ዋስትናና የምጣኔ ሀብት ዕድል በር ከፋች ነው የተባለለት ‹‹የአፍሪካ አረንጓዴ ጥምረት (አግራ) አንዱ ነው፡፡
አግራ ኢትዮጵያውያን ሴቶች በተለይ በግብርናው ዘርፍ የነቃ ተሳትፎ እንዲያደርጉ የተለያዩ ሥራዎችን በመሥራት ላይ መሆኑን በተቋሙ የኢትዮጵያ የፕሮግራም መሪ ኒኮላስ ኦባሪ ይናገራሉ፡፡
ሴቶችን በግብርናው ዘርፍ ለማብቃትና ለውጥ ለማምጣትም በኢትዮጵያ በአግሪ ቢዝነስ ዘርፍ ያሉ ሴቶችን ለማጠናከር ሰሞኑን መድረክ ተዘጋጅቶም ነበር፡፡
በዚሁ መድረክ ላይ ተገኝተው በተለይ ለሪፖርተር ሐሳባቸውን ያካፈሉት ሚስተር ኒኮላስ ኦባሪ፣ በግብርናው ዘርፍ ተሰማርተው የሚገኙ ሴቶች ላይ በርካታ ፈተናዎች እንደሚገጥማቸው አስረድተዋል፡፡
ለሥራ መጀመሪያ የሚሆን ገንዘብ እጥረትና በጠንካራ ፖሊሲ አለመደገፍ፣ የትብብርና የድጋፍ ማነስ ሴቶች በግብርናው ዘርፍ የላቀ ተሳትፎ እንዳያደርጉ ማነቆ ከሆኑት ጉዳዮች ጥቂቶቹ ናቸውም ብለዋል፡፡
ችግሩን ለመፍታትና የሴቶችን ተሳትፎ ለማሳደግ የሁሉም ርብርብ ያስፈልጋል ያሉት ኒኮላስ፣ ሥራ ፈጣሪ ሴቶች በገንዘብም ሆነ በቴክኖሎጂ ታግዘው ሥራዎችን እንዲሠሩ መደገፍ ሊሰመርበት የሚገባ ጉዳይ ስለመሆኑ ያስረዳሉ፡፡
ሴቶች በዕውቀት ላይ ተመሥርተው ምርት እንዲያመርቱ ከማድረግ ባሻገር ያመረቱት ምርት በቂ የገበያ ትስስር እንዲኖረውና በቀላሉ ወደ ገበያ እንዲደርስላቸው ሊሠራ እንደሚገባም ይጠቁማሉ፡፡
እንደ ኒኮላስ አባባል፣ ሴቶች ካሉበት ችግር ለመውጣትና ያለባቸውን ጫና ለማቃለል በግል ከመሥራት ይልቅ በጋራ ተረዳድተውና ተወያይተው ቢሠሩ የበለጠ ውጤታማ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡
ኢትዮጵያውያን ሴቶችና እናቶች ብዙውን ጊዜያቸውን የሚያሳልፉት ልጆችን በማሳደግና በመንከባከብ በመሆኑ፣ በተለይ በኢኮኖሚው ዘርፍ በንቃት ለመሳተፍ ትልቅ ፈተና ይሆንባቸዋል ያሉት ደግሞ በአግራ የወጣቶችና የሥርዓተ ፆታ አካታችነት ዳይሬክተር ሚስስ ናና አሞዓ ናቸው፡፡
አፍሪካ ፍትሐዊ የንግድ ሥርዓት የላትም በተለይ ደግሞ ሁኔታው ለሴቶች ያልተመቸ ነው ያሉት ናና፣ አግራ በሴቶች የሚመሩ የግብርና ንግዶችን ለማበረታታትና ፍትሐዊ ዕድገትን ለማምጣት በኢትዮጵያና በሌሎች የአፍሪካ አገሮች እየሠራ ስለመሆኑ ተናግረዋል፡፡
ሴቶች በተለይ በአግሪ ቢዝነስ የነቃ ተሳትፎ እንዲኖራቸው በገንዘብና በቴክኖሎጂ መደገፍ አስፈላጊ ነው የሚሉት ዳይሬክተሯ፣ በኢትዮጵያ በተለይ በገጠሩ አካባቢ ያሉ ሴቶች ከግብርናው ጋር የተቆራኘ ሕይወት የሚያሳልፉ በመሆናቸው በተለያዩ የግብርና ውጤቶች ላይ ተሳታፊና ተጠቃሚ ሊሆኑ እንደሚገባም ይገልጻሉ፡፡
የሴቶችን ኢኮኖሚያዊ ተሳትፎ ለማሳደግ ደግሞ ከማስተማር ጀምሮ ሥር ነቀል መሻሻል እስኪመጣና ከወንዶች ጋር እኩል ተሳታፊ እስኪሆኑ ድረስ፣ የፖሊሲ ማሻሻያዎን ከማድረግ ጀምሮ ሌሎች አስፈላጊ ክትትልና ድጋፎችን ማድረግ የሁሉም ድርሻ ነው ሲሉ ያክላሉ፡፡
የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ከተሰጠው አንዱና ዋነኛው ኃላፊነት የሴቶችን መብት በማስከበር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማስቻል ነው የሚሉት ደግሞ፣ የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር አማካሪ ደበበ ባሩድ (ዶ/ር) ናቸው፡፡
ቀደም ሲል የነበረው ፖሊሲ የሴቶችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ እንዳልነበረ የሚጠቅሱት ደበበ (ዶ/ር)፣ በተለይ በገጠር የሚኖሩ ሴቶች የመሬት ባለቤት እንዳልነበሩ አስታውሰዋል፡፡
ነገር ግን ዛሬ ላይ በፖሊሲ ተደግፎ ገጠር ውስጥ የምትኖር ሴት እንደ ወንድ እኩል የመሬት ባለቤት የመሆን መብት ተከብሮላት፣ መንግሥት ትኩረት ሰጥቶ የገንዘብ ብድርና ሌሎች አቅርቦት እንዲኖራት እንዲሁም ምርት እንድታመርትና የገበያ ዕድሉን እንድታገኝ በርካታ ሥራዎች እየተሠሩ ስለመሆኑ ተናግረዋል፡፡
በሴቶች ተጠቃሚነትና አምራችነት በኩል የመንግሥት ትልቁ ሥራ ፖሊሲ ማውጣት ነው ያሉት ደበበ (ዶ/ር)፣ በዚህም በፌደራልና በክልሎች ደረጃ ፖሊሲ እንዲወጣ ተደርጓል፣ ሴቶችም የሚወከሉበት አደረጃጀት ተቋቁሟል ብለዋል፡፡
በአገሪቱ ቀደም ሲል የነበሩ አመለካከቶች ሙሉ ለሙሉ ተቀይረዋል ብሎ መውሰድ ባይቻልም፣ ቀደም ሲል በሴቶች ላይ የነበረውን የተሳሳተ እይታ ከሌሎች ዓለማት ተሞክሮን በመውሰድ ሴቶችን በማስተማር፣ መብታቸውን ከሰው እጅ ሳይሆን ተደራጅተው በራሳቸው ታግለው እንዲያገኙ መንግሥት እየሠራ ነው ብለዋል፡፡
አማካሪው በፌደራልና በክልሎች ደረጃ ሴቶችን ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሠራ ነው ይበሉ እንጂ፣ በኢትዮጵያ የሴቶች መብት በተባለው ልክ እየተከበረ አይደለም የሚሉ ድምፆች ይሰማሉ፡፡ በኢኮኖሚውም ቢሆን የሴቶች ተጠቃሚነት በእጅጉ ዝቅተኛና ተደራሽነት የሚጎለው ስለመሆኑ ይነገራል፡፡
ለሴቶች መብት መከበር እንደማሳያም ሴቶች ወደ ትምህርት ቤት መሄድና የተማሩ ሴቶችን ማፍራት መሆኑን የተማረች ሴት እንዳልተማረችው ሴት መብቷ ሲገፋ ዝም እንደማትል ለመብቷም በእጅጉ እንደምትታገል፣ መብትና ጥቅሟንም እንደምታስከብርና በዚህም በአሁኑ ወቅት በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሴቶች ወደ ትምህርት ቤት መሆናቸውን አንስተዋል፡፡
በሚኒስቴሩና ከዚያ በታች ባሉ አስተዳደሮች ውስጥ የሴቶች ተሳትፎ ቀደም ሲል ከነበረው በእጅጉ የተሻሻለ ነው የሚሉት ደበበ (ዶ/ር)፣ የተማሩ ሴቶች ወደ ሥልጣን ከመጡና ከተሳተፉ ለሴቶች ማነቆ የሚሆኑ ፖሊሲዎችን የማሻሻል ዕድል እንደሚኖርና የሴቶች ጥቃት እንዲቆም የሚታገሉበት ምቹ ለመፍጠር እንደሚያግዝ አክለዋል፡፡
እኩል ተጠቃሚነትና መብትን ለማሻሻል በተለይ በገጠር የሚኖሩ ሴቶች የግንዛቤ ለውጥ እንዲያመጡ ማስተማር፣ ሴቶች ከወንዶች እኩል መብት እንዳላቸው ማስረዳት፣ የሴቶችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማሳደግ እንዲሁም የማኅበረሰቡን ተጠቃሚነት ማሳደግ ስለመሆኑ ለሁሉም ማሳየትና አጠናክሮ መቀጠል አስፈላጊ ስለመሆኑም ተናግረዋል፡፡
ሴቶች በኢኮኖሚ ራሳቸውን እንዲችሉና ኑሮአቸውን እንዲያሻሽሉ በተለይ በግብርናው ዘርፍ ተሳታፊ ሊሆኑ ይገባል ያሉት ደበበ (ዶ/ር)፣ ለዚህ አሳሪ የሆኑ ፖሊሲዎችና መመሪያዎች ካሉ ሊሻሽሉ እንደሚገባ ጠቁመዋል፡፡
አግራ በአፍሪካ የምግብ ዋስትና ችግርን ለመዋጋት በሚል በ550 ሚሊዮን ዶላር በጀት የተቋቋመው በ2015 ዓ.ም. ነበር፡፡ ድርጅቱ አኅጉሪቱ የራሷን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ ለምታደርገው ጥረት የበኩሉን አስተዋጽኦ ያደርጋል በሚል በቀድሞው የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ የቦርድ ሊቀመንበርነት የተጀመረ ሲሆን፣ በ15 የአፍሪካ አገሮች ውስጥ 28 ሚሊዮን አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ ለማድረግ በማቀድ እየሠራ ይገኛል።
የአየር ንብረት ለውጥ እና እንደ ማዳበሪያ ያሉ የግብርና ግብዓቶች ዋጋ መናርን ጨምሮ በቀጠናው በአነስተኛ የኑሮ ደረጃ የሚገኙ አርሶ አደሮች ወቅታዊውን የውጭ ጫና ተሸክመው ለሚያልፉ ሴቶች በተለይም በአየር ንብረት ለውጥ ተፅእኖ ምክንያት ሥጋት ውስጥ ለሚሆኑ አካባቢዎች ትኩረት ሰጥቶ የሚንቀሳቀስ በጎ አድራጎት ድርጅት ነው።