
በዓለም አቀፍ ደረጃ በየዓመቱ 10.7 ሚሊዮን ሰዎች በቲቢ በሽታ የሚጠቁ ሲሆን፣ ከ1.2 እስከ 1.3 ሚሊዮን የሚደርሱት ደግሞ ሕይወታቸውን በበሽታው ያጣሉ። ኢትዮጵያ በሽታው ከፍተኛ ጫና ካሳደረባቸው 30 አገሮች ተርታ ስትሆን፣ በየዓመቱም 19,000 ዜጎች በቲቢ በሽታ ታጣለች፡፡
ጤና ሚኒስቴር የዓለም ቲቢ ቀንን አስመልክቶ በጤናው ዘርፍና በሚዲያ ባለሙያዎች መካከል ያለውን ትብብር ለማጠናከር ባካሄደው የሚዲያ ፎረም ላይ ንግግር ያደረጉት በሚኒስቴሩ የበሽታዎች መከላከልና መቆጣጠር መሪ ሥራ አስፈጻሚ ሕይወት ሰለሞን (ዶ/ር)፣ መንግሥት ለአንድ የቲቢ ታካሚ በዓመት ከስድስት ሺሕ እስከ ስምንት ሺሕ ዶላር የሚደርስ ከፍተኛ ወጪ እንደሚያወጣ ገልጸዋል።
የቲቢ መድኃኒት ለታማሚዎች በነፃ እንደሚሰጥ፣ መድኃኒቱን ገዝቶ የሚጠቀም ካለ እየገዛ ያለው የተሰረቀ መድኃኒት መሆኑን ሊገነዘብ እንደሚገባም አሳስበዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት ከ2,000 በላይ ጤና ተቋማት ምርመራና ሕክምና እየሰጡ መሆኑንና ለ1,000 ተቋማት መመርመርያ መሣሪያዎች መሠራጨታቸውን፣ በገጠሩ አካባቢ ለሚገኙ 690 ላቦራቶሪዎች የሶላር ፓነል ዝርጋታ መከናወኑንም አመልክተዋል።
በኢትዮጵያ ከሚከሰቱ የቲቢ ዓይነቶች 70 በመቶው ሳምባን፣ 30 በመቶው ደግሞ ሁሉንም የሰውነት ክፍሎች የሚያጠቁ መሆናቸውን አስረድተዋል።
ለሁለት ሳምንትና ከዚያ በላይ የሚቆይ ሳል፣ ትኩሳት፣ ማታ ማታ ማላብ፣ የሰውነት ክብደት መቀነስና አልፎ አልፎ ደም የቀላቀለ አክታ የበሽታው ዋነኛ ምልክቶች መሆናቸውን ያስረዱት ሕይወት (ዶ/ር)፣ አንድ የታመመ ሰው ሲያስል ወይም ሲያስነጥስ እስከ 40,000 የሚደርሱ ጥቃቅን ጠብታዎችን ወደ አየር እንደሚለቅ፣ ለአምስት ደቂቃ ብቻ ሲያወራ ደግሞ 3,000 ጠብታዎችን በመልቀቅ በሽታውን በቀላሉ ከሰው ወደ ሰው ሊያሰራጭ እንደሚችል፣ ለቲቢ በሽታ ይበልጥ ተጋላጭ የሆኑትም ከታካሚ ጋር አብረው የሚኖሩ፣ የስኳር ሕመምና የኤችአይቪ ቫይረስ ያለባቸው እንዲሁም የአየር ዝውውር በሌለው ቤት የሚኖሩ ሰዎች መሆናቸውን አክለዋል።
በሌላ በኩል ባለፉት ስድስት ወራት 1,460 አዳዲስ የሥጋ ደዌ ታማሚዎች መለየታቸውንና በአጠቃላይም 1,800 ሰዎች በሕክምና ላይ እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡
From The Reporter Magazine
በጤና ሚኒስቴር የበሽታዎች መከላከልና መቆጣጠር ዴስክ ኃላፊ አቶ ታዬ ለታ በበኩላቸው፣ የሳንባ ነቀርሳ በሽታ ማይኮባክቴሪየም ቲዩበርክሎሲስ በሚባለው ተህዋሲያን የሚከሰትና አልፎ አልፎም በማይኮባክቴሪየም ቦቪስና አፍሪካነስ ዝርያዎች አማካይነት ወደ ሰው ልጅ ሊተላለፍ እንደሚችል ተናግረዋል።
እንደ ኃላፊው ገለጻ፣ በሽታው ዛሬም ድረስ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛውን የሞት መጠን የሚያስመዘግብ ቀዳሚው ተላላፊ በሽታ ሆኖ ቀጥሏል፡፡ እ.ኤ.አ. በ2024 በዓለም 10.7 ሚሊዮን ሰዎች በበሽታው ሲያዙ፣ 1.23 ሚሊዮን የሚሆኑት ደግሞ ሕይወታቸውን አጥተዋል፡፡
ምንም እንኳን በዓለም አቀፍ ደረጃ 8.3 ሚሊዮን አዳዲስ ታካሚዎች ወደ ሕክምና ቢገቡም፣ መድኃኒት የተላመደ ቲቢ ካለባቸው 390,000 ሰዎች መካከል ሕክምና ማግኘት የቻሉት 164,545 ወይም 42 በመቶው ብቻ መሆናቸው፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያለውን ከፍተኛ የሕክምና ክፍተት እንደሚያሳይም ጠቁመዋል፡፡
From The Reporter Magazine
ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ. ከ2021 ጀምሮ ከፍተኛ የቲቢ ጫና ካለባቸው 30 የዓለም አገሮች ተርታ ውስጥ ስትሆን፣ የበሽታው ጉዳትም አሳሳቢ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ፣ እ.ኤ.አ. በ2024 የኢትዮጵያ የቲቢ ሥርጭት መጠን በየ 100,000 ሕዝብ ውስጥ 141 ሰዎችን እንደሚያጠቃና በዓመት 186,000 አዳዲስ ተጠቂዎች እንደሚመዘገቡ አስታውሰዋል፡፡
በኢትዮጵያ በየዓመቱ 19,000 ሰዎች ወይም በየወሩ 1,583 ሰዎች ወይም በቀን 53 ሰዎች በየሰዓቱ ደግሞ ሁለት ሰዎች በዚሁ በሽታ ምክንያት ሕይወታቸውን ያጣሉ፡፡
እንደ አቶ ታዬ ገለጻ፣ አዲስ የሚያዙ ታካሚዎች የመድኃኒት መላመድ መጠን 1.1 በመቶ ሲሆን፣ ቀደም ሲል ሕክምና በጀመሩት ላይ ደግሞ 11.9 በመቶ ሆኖ ተመዝግቧል። በአሁኑ ወቅት በአገር አቀፍ ደረጃ 2,500 ያህል መድኃኒት የተላመደ ቲቢ ተጠቂዎች ይኖራሉ ተብሎ ይገመታል፡፡
የኢትዮጵያ የቲቢ መቆጣጠሪያ መርሐ ግብር ባለፉት ዓመታት ተስፋ ሰጪ ውጤቶችን አስመዝግቧል፡፡ ከ2015 ዓ.ም. አንፃር ሲታይ የቲቢ ሥርጭት በ30 በመቶ ቀንሷል እንዲሁም የሞት መጠን በ46 በመቶ ዝቅ እንዲል ተደርጓል።
በተለይም ከኮቪድ-19 ወረርሽኝ በኋላ ታካሚዎችን የመለየት ሥራ በ42.5 በመቶ ማደጉን የገለጹት አቶ ታዬ፣ የላቦራቶሪ አቅም መጎልበትና በኅብረተሰቡ የሚደረግ ንቁ ተሳትፎ ለውጤቱ መገኘት እንደ አንድ ምክንያት ይጠቀሳል፡፡ በተለይም የቲቢ ሞለኪውላር ምርመራ ማዕከላት ቁጥር ባለፉት ሦስት ዓመታት ውስጥ ከ372 ወደ 1,058 ማደጉ የምርመራ ተደራሽነትን በእጅጉ አሳድጎታል ብለዋል፡፡
በሰው ሠራሽ አስተውሎት (ኤአይ) የታገዘ የዲጂታል ኤክስሬይ ምርመራ ማሽን በ225 ጤና ተቋማት ውስጥ ሥራ ላይ መዋሉን ኃላፊው አስረድተዋል፡፡
ባለፉት ስድስት ወራት ብቻ በቴክኖሎጂ በመታገዝ የሶማሌ ክልልን ሳይጨምር ለ138,157 ሰዎች ምርመራ የተደረገ ሲሆን፣ ከእነዚህም ውስጥ 22,752 ሰዎች የበሽታው ምልክት ታይቶባቸው በላቦራቶሪ በተደረገ ምርመራ 3,550 በበሽታው መያዛቸው ተረጋግጦ ወደ ሕክምና መግባታቸውንም ጠቁመዋል፡፡
በክልል ደረጃም በደቡብ ኢትዮጵያ፣ ሲዳማ፣ ኦሮሚያና አማራ ክልሎች የተለያዩ ሥራዎች የተከናወኑ ሲሆን፣ በትግራይ ክልል ጭምር የዲጂታል ኤክስሬይ ምርመራ አገልግሎት በመሰጠት ላይ እንደሚገኝ አቶ ታዬ አክለዋል፡፡
እንደ አቶ ታዬ፣ የኩፍኝ በሽታም አሁንም ትኩረት የሚሻ ጉዳይ ነው፡፡ ዘንድሮ 1,710 የኩፍኝ ተጠቂዎች ተለይተዋል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ 83.6 በመቶው አዲስ ታካሚዎች ናቸው፡፡ ምንም እንኳን ውጤቶች ቢመዘገቡም፣ በአገሪቱ አንዳንድ አካባቢዎች ያለው ጦርነትና ግጭት፣ ድርቅ እንዲሁም የተፈናቃዮች በብዛት በአንድ ላይ መኖር ለበሽታው መስፋፋት ምክንያት ናቸው፡፡
የቲቢ በሽታን ለማጥፋት የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ማስፋፋት፣ የሕክምና ግብዓቶችን ማሟላትና በግጭትና በተፈጥሮ አደጋ የሚጎዱ ዜጎችን ተደራሽ በማድረግ የሞት መጠንን መቀነስ እንደሚቻልም ጠቁመዋል፡፡