- የሕወሓት አመራሮች ጦርነት የሚፈልጉት ሥልጣናቸውን ለማራዘም ነው ብለዋል
- ከትግራይ ውትድርና ፈርቶ የወጣ ተፈናቃይ ነው
የጠቅላይ ሚኒስትሩ የምሥራቅ አፍሪካ ጉዳዮች አማካሪ አቶ ጌታቸው ረዳ በፕሪቶሪያ ስምምነት መቀሌን በፌዴራል የፀጥታ መዋቅር ሥር ማድረግና በትግራይ ክልል ሁለት ከተሞች ላይ የመከላከያ ካምፖችን ማቋቋም የሚሉና የስምምነቱ አካሎች እንዲቀሩ መደረጋቸውን በማስታወስ፣ ‹‹በሙሉ እምነት ሕዝባችንን የተሟላ ከሚባል ጥፋት ያዳነ በሚል የተንቀሳቀሰበት ስምምነት ነው ያደረግነው፣ ስለዚህ እኔ በዚህ ጉዳይ ይፀፅተኛል የምለው ነገር የለኝም፤›› አሉ።
አቶ ጌታቸው ይህንን ያሉት ትናንት ማክሰኞ ሰኔ 30 ቀን 2018 ዓ.ም. በሃርመኒ ሆቴል በሴንተር ፎር ሪስፖንሲብል ኤንድ ፒስፉል ፖለቲክስና በትግራይ ብሮድካስት ሰርቪስ በጋራ በተዘጋጀ፣ ትግራይን የተመለከተ የውይይት መድረክ የመክፈቻ ንግግር ሲያደርጉ ነው።
አቶ ጌታቸው በንግግራቸው ሰፋ ያለ ጊዜ ወስደው የትግራይ ክልል ነባራዊ ሁነቶችን የተመለከተ፣ እንዲሁም በኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ከፓርቲነት ተሰርዞ በአሁኑ ወቅት ክልሉን እያስተዳደርኩ ነው ስለሚለው የሕወሓት አመራር ክፍል፣ የቀደመና አሁናዊ እንቅስቃሴዎችም ማብራሪያ ሰጥተዋል።
በዚህም የፕሪቶሪያ ስምምነትን በተመለከተ አስቀድሞ በጦርነቱ ወቅት ስለነበሩ ጉዳዮች፣ እንዲሁም እስካሁን ድረስ ለሕዝብ ይፋ ሳይደረጉ የቆዩ ጉዳዮችን ዳሰዋል።
ስምምነቱን በተመለከተ በሰጡት ማብራሪያ፣ ‹‹ፕሪቶሪያ የተፈራረምነው እኮ ከፌዴራል መንግሥት ጋር ለመሥራት ነው፣ እንደዚያ ነው የሚለው። ያደረግኩት ምርጫ ትክክል አልነበረም፡፡ ስለዚህ አንድ ሕገ መንግሥት የሚለውን ተቀብያለሁ፣ አዲስ አበባን ተቀብያለሁ፣ ብለን ነው የተስማማነው፤›› ብለው፣ ‹‹ፕሪቶሪያን የሚያውቅ ሰው አለ? አንብቦ የሚያውቅ ሰው አለ?›› ሲሉ ጠይቀዋል።
‹‹የመቀሌ ከተማ ፀጥታ በፌዴራል መንግሥት ሥር ይሁን ይል ነበር የፕሪቶሪያ ስምምነት። በሒደት ነው እሱ አያስፈልግም ተባብለን ተስማምተን በራሳችን ሥር ያስገባነው። ቀድሞ ቀርቦ በነበረው በውሉ ክፍል መሠረት የመቀሌ ከተማ ፀጥታ በፌዴራል መንግሥት ሥር ነው መሆን የነበረበት። ተስማምተን የመጣነው ናይሮቢም ድረስ የተወያየነው፣ አዲጉደምና አጉላዕ የመከላከያ ካምፖች እንደሚኖሩ ተስማምተን ነው፡፡ የሚመለከተው ሥራ አስፈጻሚም ነበረ፡፡ ከመቀሌ ከተማ ሆነንማ አንንቀሳቀስም ተብሎ ቦታ እየተመረጠም ነው የነበረው፣ ይህንን የተቀበለ አመራር ነው፤›› ብለዋል።
ጦርነቱ ሲጀመር በአመራሩ በኩል የነበረውን የተሳሳተ ሥሌትና የግንኙነት ክፍተት ያስረዱት አቶ ጌታቸው፣ «እኔ እንዳልኳችሁ ጦርነቱ ሲጀመር ሁላችንም አመራር ውስጥ የነበርን ሰዎች በተሳሳተ ሥሌት የጠበቅነው ነገር ነበር። አንዳንዱ በሦስት ሳምንት መንግሥትን እንገለብጣለን ብሎ ያስብ ነበር፤» ብለዋል። በወቅቱ የነበረውን የቋንቋና የጽንሰ ሐሳብ አለመግባባት ሲያብራሩም፣ «እኔ ቃል አቀባይ ሆኜ ገለጻ ሲደረግ በትግርኛ አንድ በተደጋጋሚ ይነገረን የነበረ ቃል “መሓይሺና” ማለት ቀጥተኛ እንደወረደ የአማርኛ ትርጉሙ አሻሽለናል ማለት ነው። እናም እኔ ገለጻ ሲደረግልኝና ይህ ቃል ሲነገረኝ የሚገባኝ የነበረው ወደ ፊት ገፍተናል፣ አሸንፈናል ነው የነበረው። በኋላ ከመቀሌ መውጣት እንዳለብን ሲነገረን ትንሽ ልንግባባ አልቻልንም። አሸንፈናል ስትሉን አልነበረም ወይ ስል ለካ ማፈግፈግ ለማለት ነው ቃሉ ጥቅም ላይ ሲውል የነበረው፤» በማለት በወቅቱ የነበረውን ሁኔታ ገልጸዋል።
From The Reporter Magazine
አመራሩ የነበረበትን አቅም በተመለከተም አቶ ጌታቸው ሲናገሩ፣ «በዚያን ሰዓት አመራሩ በምንም መልኩ ይህን ያህል አስተዋጽኦ አድርጓል የሚያስብል ትልቅ ሥራ አልሠራም፣ አንድም። ምናልባት እጅ አለመስጠት ቁምነገር ከሆነ እጅ አልሰጠንም አዎ። ይህ እንደ ትልቅ ውጤት (ክሬዲት) ሊቆጠር ይገባል የሚል እምነት የለኝም፤» ብለው፣ የተፈጠረውን ቀውስ በማስቆም ረገድ ዋናውን ሥራ የሠራው ወጣቱ መሆኑን ገልጸዋል።
«ከዚያ ውጪ በእኛ አመራር ምክንያት የተፈጠረን ቀውስ ለመቀልበስ በተደረገው ጥረት ውስጥ በራሱ ምክንያት፣ በራሱ መንገድ፣ በራሱ የተንቀሳቀስ ወጣት ነው ቁምነገር የሠራው፤» ብለዋል።
ይህ የጦርነት ቀውስ በፕሪቶሪያው ስምምነት መቋጨት እንደነበረበት የተናገሩት አቶ ጌታቸው፣ በስምምነቱ መሠረት በአገሪቱ አንድ ወጥ የጦር ሠራዊት መኖር እንዳለበት በይፋ ተስማምተው መንቀሳቀሳቸውን አስታውሰዋል።
From The Reporter Magazine
«እንደዚያም ሆኖ መጨረሻ ላይ በሰላም ስምምነት ይህ ነገር መቀልበስ መቻል አለበት፣ ኢትዮጵያውያን ነን ካልን፣ የሕገ መንግሥቱ ተገዥ ነን፡፡ በፕሪቶሪያ ስምምነት መሠረት አንድ ሠራዊት ብቻ ነው ያላት ኢትዮጵያ፡፡ ስለዚህ የትግራይ ሠራዊት፣ የአማራ ሠራዊት፣ የግል ሠራዊት የሚባል ነገር ሊኖር አይችልም፡፡ በሚዲያም እንደተነገረው በይፋ ሠራዊቱ ወደ ሰላማዊ ኑሮ የሚመለስበት ሁኔታ ይፈጠራል፤» መባሉን አስረድተዋል።
አክለውም በትግራይ የተከሰቱ ችግሮችን ለመቀልበስ በመልሶ ግንባታ ሥራዎች ላይ መስማማታቸውንና ይህም ሕዝብን ከጥፋት ያዳነ ምርጫ መሆኑን አውስተዋል።
«ትግራይ ውስጥ የተከሰቱት ሁሉም ችግሮች መቀልበስ የሚያስችል የመልሶ ግንባታ ሥራዎች መከናወን መቻል አለባቸው፣ የተፈጠሩ ሕገ መንግሥታዊ ቀውሶች መቀልበስ አለባቸው ብለን ተስማምተን፣ በሙሉ እምነት ሕዝባችንን የተሟላ ከሚባል ጥፋት ያዳነ በሚል የተንቀሳቀሰበት ስምምነት ነው ያደረግነው፤» በማለት አብራርተዋል።
በሰላም ስምምነት ሒደቱ ላይ ምንም ዓይነት ፀፀት እንደሌላቸው የጠቀሱት አቶ ጌታቸው፣ ይልቁንም ከዚያ ቀደም ስለሰላም ለማሰብ ጊዜ መውሰድ እንደነበረባቸው ጠቅሰዋል።
«እኔ የምፀፀትበት የምለው ነገር የለኝም፣ በዚህ ጉዳይ ላይ። የምፀፀትበት ነገር ካለ ከእኛ ምናልባት ጊዜ ወስደን ስለሰላም ብናስብ ኖሮ ብዬ ነው፤» ካሉ በኋላ፣ ከፕሪቶሪያ ስምምነት በፊት ከትግራይ መንግሥት ባለሥልጣናት ጋር ለመወያየት የተፈጠሩ ዕድሎችን በተለያዩ ምክንያቶች ወደኋላ በማለት መጠቀም አለመቻሉ፣ አሁንም የሚያሳምም ጉዳይ መሆኑን ተናግረዋል።
አቶ ጌታቸው አሁንም ቢሆን የሰላም ስምምነቱን በሙሉ ድምፅ ደግፎ መንቀሳቀስ እንደሚገባ በማሳሰብ፣ ሥልጣንን ብቻ የሙጥኝ በማለት ሕዝብን ወደ ጥፋት የሚወስዱ አካላትን ተችተዋል።
«የትግራይ ወጣት የሚገባውን ሰላም፣ የትግራይ ሕዝብ የሚገባውን ሰላም ከማግኘት አንፃር የፕሪቶሪያውን ስምምነት ነክሰን ይዘን ብንንቀሳቀስ ኖሮ፣ ሁሉም ባለድምፅ በዚህ ጉዳይ ላይ ቢሠራ ኖሮ ሊፈጠር የሚችለውን ነገር ማሰብ ጥሩ ነው። ከዚህ ባለፈ እንዳልኩት ከሥልጣንና ከሥልጣን ውጪ አለማስተዋል፣ አሁንም ስህተትን ለመደጋገምም ሥልጣኑ የእኔ ነው፣ ሕዝብን ለጥፋት መጠቀምና ሥልጣኑ የእኔ ነው የሚል አመራር አሁንም ሥልጣኑን ነክሶ ይዞ ወደ ሌላ የጥፋት መንገድ ሊያስገባን የሚፎክርበት ሁኔታ አለ፤›› ብለዋል።
ከፕሪቶሪያ ስምምነት ባሻገር ስለተፈናቃዮች፣ የግዳጅ አፈሳዎችና የክልሉ ትምህርት ቢሮ የ12ኛ ክፍል አገር አቀፍ ፈተናን በክልሉ አዘጋጅቼ እፈትናለሁ ማለቱን አስመልክቶም ሐሳባቸውን ገልጸዋል።
ተፈናቃዮችን አስመልክቶ በሰጡት ማብራሪያ የሕዝቡን የሰላም ድምፅ ማሰማት የሚያስችል ሥራ መከናወን አለበት ብለው እንደሚያምኑ ገልጸው፣ ‹‹ተፈናቃዮች ስላልተመለሱ ነው አሁን ለጦርነት የማቅራራው የሚለው አካል፣ ተፈናቃዮች እንዲመለሱ ፍላጎት እንዳልነበረው ይታወቃል። ከፌዴራሉ መንግሥት ጋር ተፈናቃዮችን መመለስ በተመለከተ ለመድረክ መገለጽ የሌለባቸው የተስማማንባቸው ብዙ ነገሮች ነበሩ፡፡ አሁን የምንሰማቸው ወታደሮች ታደሰን ጨምሮ፣ አሁን አመራር ነን የሚሉ ሰዎች ሳይቀሩ ዝርዝር ጉዳዩን ያውቃሉ። ግን የተፈናቃዮች መመለስ የእንጀራቸው መድረቅ ነው ብለው ስላመኑ ተፈናቃዮችን መመለስ አይፈልጉም፤›› ብለዋል።
አቶ ጌታቸው አያይዘውም በሚዲያ ማንም ያስተዳድራቸው ይመለሱ ተብለዋል ያለ ሰው እንደሌለ ‹‹ይህ ሐሰት ነው›› ሲሉ በማስታወቅ፣ አሁንም በትግራይ ከአሥር ሺዎች የበለጡና እስከ መቶ ሺሕዎች የሚደርሱ አዳዲስ ተፈናቃዮች መፈጠራቸውን ጠቁመዋል። ‹‹ለእኔ ከትግራይ የውትድርና ግዳጅ አፈሳ ፈርቶ የሚመጣ ሰው ተፈናቃይ ነው። ሥራ ፍለጋ አይደለም የመጣው እዚህ፤›› ብለዋል።
በርካታ የትግራይ ተወላጆች እየታሰሩ ነው የሚል ሪፖርት በተደጋጋሚ የቀረበላቸው በመሆኑ በቅርቡ ከፌዴራልና ከአዲስ አበባ ፖሊስ ጋር ውይይት ማድረጋቸውን ጠቅሰው ስለሁኔታው አስረድተዋል።
‹‹አንዳንዱም የነበረው ሁኔታ ያስደነግጣል። በእርግጥ ከፀጥታ አካላቱ ጋር ስለምንነጋገር በአጭር ጊዜ ውስጥ ያላግባብ የታሰሩ ሰዎችን ማስፈታት ላይ ጥሩ ነው፣ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር እንገናኛለን። ነገር ግን አንድ ቦታ ለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ፣ በአንድ ምሽት ብቻ 300 አካባቢ የትግራይ ተወላጆች ታስረው ነበር። ከዚያ ውስጥ በትክክል ይህ ነው ሊባል በሚችል ወንጀል ተጠርጥረው እንዲቆዩ የተደረጉት ዘጠኙ ብቻ ናቸው፤›› በማለት ገልጸዋል።
አቶ ጌታቸው በቁጥጥር ሥር ውለው ከነበሩ ሰዎች ብዙኃኑ ተፈናቃይ መሆናቸውንና መኖሪያ ስለሌላቸው፣ በአንድ ቤት ውስጥ በርካታ ሰዎች እየኖሩ እንደሚገኙም ጠቅሰዋል።
በአዲስ አበባ በፀጥታ ኃይል ቁጥጥር ሥር ማስተካከል እንዳለ ሆኖ፣ ‹‹አሁን ትግራይ ውስጥ ያለውን ቀውስ ተደራጅተን ማስቆም ካልቻልን ከትግራይ በመኮብለል ብቻ የሚፈታ ችግር የለም፤›› ብለዋል።
‹‹በአሁን ወቅት የትግራይ ወጣት እየተሰደደ በየቀኑ 50 ሰው ደረሰ፣ አሁን 200 ምናምን ሰው ደርሷል፣ ሞት የተፈረደበት በብዛት እስር ቤቶች እንደሚገኝ መረጃ ይደርሰናል፤›› ብለው፣ አልፎም የሕክምና ባለሙያ ዶክተሮችን ጨምሮ ወጣቶች ወደ ጎረቤት አገሮች ተሠልፈው የሚሄዱበት ሁኔታ የፈጠረ ትግራይ አመራር መቀየር መቻል አለበት ሲሉም አክለዋል፡፡
አሁን በትግራይ ሥልጣን ይዣለሁ የሚለው አመራር፣ ‹‹ወጣትን በማስፈጀት ላይ የተመሠረተ ውትድርና ተይዞ ሲንቀሳቀስ እንዲሁ ከጎን ሆኖ መመልከት አይገባም፤›› ያሉት አማካሪ ሚኒስትሩ፣ ‹‹የፌዴራል መንግሥት ያጠፋው ጥፋት ካለ እንታገለዋለን፣ የምንታገለው ሀቅን ይዘን ነው፣ የሌለ ነገር እየፈጠርን አይደለም። እኔ በሚገባኝ ልክ የተፈናቃዮችን መመለስ በተመለከተ የፌዴራል መንግሥት ሙሉ በሙሉ ቁርጠኛ አቋም ወስዶ ነበር። ይህንን ፍሰሐ ያውቃል፣ ታደሰ ያውቃል፣ ዮሐንስ ወልደ ጊዮርጊስ ያውቃል፣ ምግበይ ያውቃል፣ ሁሉም ያውቃሉ። ተስማምተው ጨርሰው ሄደው ነበር። ግን አያዋጣቸውም፣ ለወርቅ ንግድ አያዋጣቸውም፣ ለኮንትሮባንድ አይጠቅምም። ስለዚህ የትግራይ ሕዝብ ስለዴሞክራሲም ስለልማትም እንድናወራ ሰላሙ መረጋገጥ ስላለበት፣ ለዚህ የሚሆን አንድነት ሊኖር ይገባል የሚል እምነት አለኝ፤›› የሚል ማብራሪያ ሰጥተዋል።
ባለፈው ሳምንት ከታዩ ጉዳዮች መካከል የትግራይ ክልል የትምህርት ቢሮ የ12ኛ ክፍል ተፈታኞች የሚፈተኑትን ፈተና ለብቻዬ አውጥቼ እፈትናለሁ ማለቱን አስመልክቶም አቶ ጌታቸው ምላሽ ሰጥተዋል።
‹በዚህም ተማሪዎች አገራዊ የዩኒቨርሲቲ መግቢያ ፈተና መውሰድ በሚገባቸው ሰዓት የራሴን ፈተና አወጣለሁ የሚል ድንቁርና ዕብሪት ይሰማል። የራስ ፈተና ወዴት ለመውሰድ ነው? የኤርትራ መንግሥት በሰላሳ ዓመት ያደረገውንና የቀሰመውን ልምድ እነዚህ ሰዎች በአጭር ጊዜ ውስጥ ወስደው ምናልባትም ሁሉንም አንድ ሚሊተሪ ካምፕ ውስጥ ለማስገባት ፍላጎት ኖሯቸው ቢሆን እንጂ፤›› ብለዋል።
ከወቅታዊ ጉዳዮች ጋር በተያያዘ በሰጡት ማብራሪያ የግዳጅ አፈሳና ወጣቶች ላይ እየተፈጠረ ያለውን ጫና አስመልክቶም በንግግራቸው ዳሰሳ አድርገዋል።
በክልሉ አሁን ያለው አመራር አፈሳ እያከናወነ እንደሚገኝና በተለያዩ ሪፖርቶች እየተጠቆሙበት ነው ያሉትን ጉዳይም፣ ‹‹ልጆቻቸውን አይሰውም የሚባለው ቀልድ እንዳይመስላችሁ፡፡ ሁሉም አሁን የተጣላን መስሎ ግን የልጆቼን ጉዳይ ጨርስልኝ ነው የሚለው፡፡ የፌዴራል ጉዳይ ጨርስልኝ ነው የሚለው፣ ልጆቹ እንዲሄዱለት ይፈልጋል። የደሃ ልጆች ግን እንዲሞቱ እየታገሉ ናቸው፣ አሁን እየታፈሱም ጭምር፤›› ሲሉ አስረድተዋል።
የግዳጅ አፈሳ በማድረግ ሕወሓት ጦርነት አሸንፋለሁ ብሎ ያስባል በሚል ከተለያዩ አካላት የሚነሳውን ነጥብ ሲያስረዱ፣ ‹‹አሁን በአፈሳ ላይ የተመሠረተ ውጊያ ለድል አያበቃም የሚሉ ሰዎች አሉ። እነዚህ ሰዎች ድል አይደለም የሚፈልጉት፣ ጦርነቱን ማራዘም ነው የሚፈልጉት። ጦርነት ማሸነፍ አይደለም የሚፈልጉት፣ የሚፈልጉት የሥልጣን ጊዜያቸውን ማራዘም ብቻ ነው፡፡ የትግራይ ወጣት በጦርነት፣ በስደት፣ በአንድም በሌላ መንገድ ካለቀ በኋላ ትግራይ ማለት እንዳይኖር ነው፣ አሁን ጉዳዩ የህልውና ጉዳይ ነው የምንለው በዚህና በመሳሰሉት ምክንያቶች ነው፤›› ብለዋል፡፡