በጌታነህ አማረ
ኢትዮጵያ ማለት ታላቅ አገር ቀደምት የሰው ዘር መገኛና የሥልጣኔ ባለቤት የሆነች አገር እንደነበረች ታሪክ ሲያወሳን ይኖራል። በዚያውም ልክ ይህች ታላቅ ነበረች የምትባል አገር አሁን ላይ በድህነት፣ በጦርነት፣ በግጭትና በስደት እየተሰቃየች የምትገኝ አገር አንድ ቀን ተመልሳ ታላቅና በዓለም ላይ ስሟ ከፍ ያለና የገነነ ችግር እንደምትሆን የብዙዎች ጥባቆት ነው፡፡ ይህ እንደሚሆን ደግሞ መተማመኛ የሚሆኑ ብዙ ነገሮች አሉ። ከእነዚህም ውስጥ ዋና ዋና የሚባሉት።
በተትረፈረፈ የተፈጥሮ ሀብት የበለፀገች መሆኗ ይህም ሲባል ሰፊ የሆነ መታረስ የሚችል መሬት፣ ሰፊ የሆነ ለደን ልማት መሆን የሚችል መሬት፣ ሰፊ የማዕድን ሀብት፣ ሰፊ የውኃ ሀብት፣ ሰፊ ለቱሪስት መስህብ መሆን የሚችል የመሬት አቀማመጥ፣ ብዛት ያላቸው ጥንተ ጽሑፎች፣ ምቹና ተስማሚ የሆነ የአየር ንብረትና ሌሎችም አማኝ፣ አዛኝ፣ መሥራት የሚችልና አትንኩኝ ባይ ሰፊ ሕዝብ፣ ይህ ሁሉ እያለ ታዲያ ዋና ችግር የሚባለው ምንድነው ሲባል? መልሱ አንዱ ድህነትና ኋላ ቀርነት ሲሆን ሌላኛው ደግሞ ብዝኃነትን የማስተናገድ ችግር ነው፡፡ ስለዚህ እነዚህን ችግሮች ለመቅረፍ ምን ይደረግ? ለሚለው ጥያቄ መልስ መስጠት ተገቢ ይሆናል። በመጀመሪያ ድህነትን ለማጥፋት መደረግ ያለበት የተፈጥሮ ሀብትንና የሰው ኃይልን አቀናጀቶ በመሥራት ድህነትንና ኋላ ቀርነትን ማስወገድ ነው። ይህን ለማድረግ ደግሞ አስተማማኝና ከዘመኑ ጋር አብሮ መሄድ የሚችል የኢኮኖሚ፣ የፖለቲካና የማኅበራዊ ሥርዓት መገንባትና መጠቀም የግድ ይላል። በተጨባጭ ይህን ለማድረግ ቀላሉና ዋነኛ መሆን ያለበት ነገር የኢኮኖሚ ሥርዓቱን መቀየር ነው የዚህ ሥርዓት መቀየር፣ ለፖለቲካና ማኅበራዊ ሥርዓት መቀየር ከፍተኛ ድጋፍ ሊሆን ይችላል የሚል ግምት ሊኖር ይገባል። የኢኮኖሚውን ሥርዓት ለመቀየር ደግሞ ለተሞክሮ ይሆን ዘንድ በዋነኛነት የኋላ የዓለምን የኢኮኖሚ ሥርዓት ታሪክን ማየትና ማጥናት የግድ ይላል። እንግዲህ የኋላ የኢኮኖሚ ታሪክን እንይ ብንል በጣም ብዙ ታሪክ ያለው ከመሆኑ የተነሳ በዚህ ጽሑፍ ብቻ መግለጽ ስለማይቻል በጣም መሠረታዊና አንኳር የተባሉትን አንሰተን ለማየትና በአሁኑ ሰዓት በኢትዮጵያና ብሎም በመላው ዓለም እየገጠሙ ላሉ የኢኮኖሚ ችግሮች መፍትሔ ምን ይሁን? የሚለውን ለማየት እንሞክር።
እንግዲህ በግልጽ እንደሚታወቀው አሁን ለደረስንበት የኢኮኖሚ ሥርዓት ወሳኝና መሠረት የሆነው የኢኮኖሚ አባት እየተባለ በሚጠራው የኢኮኖሚና የፖለቲካ ፈላስፍ በአዳም ስሚዝ የቀረበው (Adam smith (1723 እስከ 1790)) የነፃ ኢኮኖሚ ጽንሰ ሐሳብ (Clasical Economic School Of Thought) ነው። ይህ የኢኮኖሚ ጽንሰ ሐሳብ በዋናነት ትኩረት ያደረገው የሥራ ክፍፍል፣ ምርታማነትና ነፃ ገበያ ኢኮኖሚ (Divission of Lebour Prodactivity and Free Market) ላይ ነው። የዚህ ኢኮኖሚ ጽንሰ ሐሳብ ይከራከር የነበረው ሰዎች በነፃነት እንዲሠሩ ይፈቀድላቸው ሁሉም ነገር ለገበያ ይተው የሚል ሆኖ ነገር ግን በገዥና በሻጭ መሀል የሚደረግን የንግድ ልውውጥ ጥሰት፣ መንግሥት ሕግ የማስከበርና ምቹ መደላድልን መፍጠር ይሁን የሚል ነው። ይህ ጽንሰ ሐሳብ በጊዜ ሒደት በተለይም እ.ኤ.አ. በ1930 በዓለም ላይ የገጠመውን የኢኮኖሚ ቀውስ መታደግ ግን የተሳነው ነበር። በዚህም መሠረት ይህ የኢኮኖሚ ጽንሰ ሐሳብ ለገጠመው ችግር ፈተናውን ማለፍ ባለመቻሉ ችግሩን መፍታት ይችላል ተብሎ የታሰበ ጽንሰ ሐሳብ በጆን ሜይ ኬንስ (John Maynard Keynes Jun 05, 1883-April 21,1946) አማካይነት ተወለደ፡፡ የዚህም ጽንሰ ሐሳብ ዋና ትኩረት ገንዘብ፣ ወለድና ሥራ (Money, Intrest and Employment) ላይ ያደረገ ሲሆን፣ በነፃ ገበያ ውስጥ መንግሥት በገንዘብና በፊሲካል ፖሊሲ (Monetary and Fisical Policy) አማካይነት ጣልቃ እየገባ ኢኮኖሚው ላይ ቁጥጥር ያድርግ የሚል ነው። በዚህም መሠረት ይህ ጽንሰ ሐሳብ በኒዮ ክላሲካል ኢኮኖሚ ትምህርት ቤት (Neoclasical Economic School of Thought) አስተምህሮ ሆኖ ቀጠለ። ነገር ግን ይህ ጽንሰ ሐሳብ ለኢኮኖሚ መሠረታዊ ጽንሰ ሐሳብ ቢሆንም በራሱ ቆሞ ለኢኮኖሚ ችግር መፍቻ ዋስትና ሆኖ መቀጠል ግን አልቻለም፡፡
እንደሚታወቀው ከዚያን ጊዜ በኋላ የሁለተኛው ዓለም ጦርነት ተጀምሮ ያለቀበት ጊዜም ነበር። በመሆኑም ከጦርነቱ ፍጻሜ በኋላ አገሮች ትኩረት ያደረጉት በጦርነቱ ምክንያት ከደረሰባቸው ጉዳት ማገገምና ኢኮኖሚያቸውን ወደ ማሻሻሉ ነበር፡፡ በዚህ ረገድ ጃፓን ቀዳሚውን ሥፍራ እንደያዘችና በፍጥነት እንዳደገች ሲነገርላት በቀጣይም ታይገር ኢኮኖሚ በመባል የሚታወቁት በተለይም የእስያ አገሮች በ1970ዎቹ አካባቢ ተንቀሳቅሰው ኢኮኖሚያቸውን በፍጥነት ያሳደጉ ሲሆን፣ ዘግይታ እንቅስቃሴ ያሳየችው ቻይና ደግሞ ከ1982 ዓ.ም. ጀምሮ በፋጥነት በማደግ ዛሬ ላይ በዓለም በሁለተኛ ደረጃነት ተቀምጣ የግዙፍ ኢኮኖሚ አንቀሳቃሽ ባለቤት ስትሆን፣ በቀጣይ ደግሞ የአንደኛ ደረጃነትን ቦታ እንደምትይዝ ታላቅ ግምት የተሰጣት አገር ሆናለች፡፡ ነገር ግን አውሮፓና አሜሪካ ምንም እንኳን በጦርነቱ ከባድ ጉዳት ቢደርስባቸውም፣ ከጦርነቱ በፊት ጠንካራ መሠረት ያለው ኢኮኖሚ የገነቡ በመሆናቸው ምክንያት ያለውን ኢኮኖሚ አጠናክረው በመቀጠል አሁን እስካለንበት ጊዜ ድረስ ጠንካራ ኢኮኖሚ ይዘው የዘለቁ አገሮች ሆነዋል።
በሌላ በኩል ደሃ ሆነው እንደሌሎቹ በወቅቱ በመጠኑ ተንቀሳቅሰው አሁን የተሻለ የኢኮኖሚ ዕድገት ላይ የደረሱ አገሮች ያሉ ሲሆን፣ ነገር ግን በዚያን ጊዜ አጋጣሚውን አግኝተው በደንብ ተንቀሳቅሰው ለማደግ ያልሞከሩ አገሮች እዚያው 1980 ዓ.ም. ከነበሩበት ድህነት መውጣት አቅቷቸው በመዳከር ላይ ይገኛሉ። በዚህ ሒደት ውስጥ አገሮች ኢኮኖሚያቸውን ሲያሳድጉ የተለያዩ እርዮት ዓለምን በማራመድ ነው። ከዚህም ውስጥ ኮሙዩኒዝም፣ ሶሻሊዝም፣ ፍሪ ማርኬት ካፒታሊዝም፣ ዴቨሎፕመንታል ስቴትና ሌሎችንም በመጠቀም ነው፡፡ ነገር ግን ይህን ሁሉ ሲጠቀሙ እንደ ዋና መሠረት ያደረጉት የኒዮ ክላሲካል ኢኮኖሚ ጽንሰ ሐሳብን ነው። ያለዚህ ኢኮኖሚ ጽንሰ ሐሳብ የፈለጉትን እርዮት ዓለም ቢጠቀሙ የአንድ አገር ኢኮኖሚ ህልውና አይኖረውም እሱም ደግሞ በራሱ ለኢኮኖሚ ችግር ዋስትና ስለማይሰጥ ያለ ተጨማሪ ኢኮኖሚ ርዕዮት ዓለም ድጋፍ ጥቅም መስጠት እየተሳነው መጥቷል፡፡ ለዚህም እ.ኤ.አ. በ1970 እና በ2008 ለደረሰው የዓለም ኢኮኖሚ ቀውስ ምላሽ ባለመስጠቱ ኢኮኖሚው በቤላውት (Bailout) ከቀውስ ሲወጣ ፍሪ ማርኬት ካፒታሊዝም ያበቃለት መሆኑን እነ ፕሮፌሰር ጆሴፍ ስቲግሊትዝ (Professor Joseph Stiglitz) እና ሌሎች የኢኮኖሚ ምሁራን ሲናገሩ ይሰማል። በ2008 በደረሰው የዓለም ኢኮኖሚ ቀውስ የተበሳጨው ሳቶሺ ናካሞቶ (ቅፅል ስም) የሶፍትዌር ባለሙያ ሳይሆን እንዳልቀረ የሚገመተው ለዓለም ኢኮኖሚ ችግር መፍትሔ ይሆናል ያለውን የምናብ የመገበያያ ገንዘብ ያስተዋወቀ ሲሆን፣ በአሁኑ ጊዜ በስፋት ሥራ ላይ እየዋለ ቢገኝም በእኔ በኩል ግን የኢኮኖሚ ችግሮችን ፈቶ ቀጣይነት ይኖረዋል የሚል እምነት የለኝም (ስለዚህ ጉዳይ የሚያብራራ ጽሑፍ በታኅሳስ 23 ቀን 2017 ዓ.ም. በዚሁ ጋዜጣ ላይ የተጻፈ መሆኑን ላስታውስ እወዳለሁ)፡፡
በሌላ በኩል እ.ኤ.አ. ከ2019 የኮቪድ-19 ወረርሽኝ በኋላ ለተከሰተው የዓለም ኢኮኖሚ ቀውስ መፍትሔ ይሆናል ያልኩትን የኢኮኖሚ ጽንሰ ሐሳብ ያመነጨሁ ሲሆን፣ የዚህም ኢኮኖሚ ጽንሰ ሐሳብ መነሻ ያደረገው የኒኦ ክላሲካል አስተምህሮ ትምህርት ቤት መካተት ሲኖርበት ያልተካተተው ሐሳብ ነው፡፡ ነገር ግን በዚያን ጊዜ ተካቶ ቢሆን ኖሮ የዓለም ኢኮኖሚ በተለያየ ጊዜ ችግር አይገጥመውም ነበር ብዬ እንድደመድም አስችሎኛል። ይህንን የኢኮኖሚ ጽንሰ ሐሳብ ለመፈጸመም ፍላጎት ይኖረው እንደሆን ለኢትዮጵያ መንግሥት ከንዴም ሁለቴ፣ ከሁለቴም ለሦስተኛ ጊዜ ጥያቄ ያቀረብኩለት ቢሆንም ለፍላጎቱ ያለው ምላሽ ምን እንደሆነ ማወቅ ያልቻልኩ ሲሆን ጽንሰ ሐሳቡ ግን በእሱ በኩል የኢኮኖሚ ሪፎርም እንዲካሄድ ሞራል ሆኖ እንዳገዘው ተሰምቶኛል፡፡ ይህ የኢኮኖሚ ጽንሰ ሐሳብ አንድን አገር ከድህነት በፍጥነት የማውጣት ከፍተኛ ኃይል ያለው፣ በተለይም የኢትዮጵያን ትንሳዔ ለማረጋገጥ ብቸኛና ዓይነተኛ መሣሪያ እንደሆነ እንዳምን አድርጎኛል።
በእርግጥ በአሁኑ ጊዜ ኢትዮጵያ ከፍተኛ የተባለለትን የኢኮኖሚ ሪፎርም በማካሄድ ላይ ትገኛለች፡፡ ይህ መሆን ያለበትና ተገቢም ነው። ነገር ግን በዓለም ላይ አጠቃላይ ያለው የኢኮኖሚ ችግር መሠረታዊ የሆነ መፍትሔ ያስፈልገዋል። እንግዲህ በዓለም ላይ ሁለት ዓይነት አገሮች አሉ እነሱም በኢኮኖሚ ያደጉና ያላደጉ አገሮች ናቸው። ያደጉ አገሮች የቀደመው ጊዜ የሰጣቸውን ዕድልና በወቅቱ የነበረውን የኢኮኖሚ ጽንሰ ሐሳብ ተጠቅመው ያደጉ ሲሆን፣ ያላደጉ አገሮች ግን ያ ጊዜ በተለያየ አጋጣሚ አልፏቸዋል። ይህም በመሆኑ ምክንያት በአሁኑ ወቅት ከድህነት ለመውጣት ዳገት ሆኖባቸዋል። ከድህነት ለመውጣት በተለያየ ጊዜ የሚጠቀሙበት ተሽከርካሪ (ሪፎርም) ዳገቱን ሊያወጣቸው አልቻለም። ይህን ለማስረዳት አንድ ምሳሌ ልጠቀም፡፡ አንድ ሰው የሆነ ቦታ ለመድረስ ዳገታማ ቦታን መውጣት ቢኖርበትና ያንን ለመውጣት ብስክሌት ቢጠቀም፣ ብስክሌቱ ማርሽ ያለው ሊሆን ይገባል። ስለዚህ ያንን ዳገት ለመውጣት የግድ ማርሹን መጨመር አለበት፣ ማርሽ ለመጨመር ደግሞ ማርሹ እንደ ልብ መታዘዝ አለበት። ቀስ ብሎ ለመጓዝ ማርሹን የመጀመሪያው ማርሽ ላይ፣ ፈጠን ለማረግ ሁለተኛው ላይ፣ ከዚያ ለመፋጠን ሦስተኛ ላይ፣ በጣም ለመፍጠን ደግሞ አራተኛ ማርሽ ላይ ማድረግ ያስፈልጋል። ይህ ከሆነ ዳገቱን ወቶ ሜዳማ ቦታ ላይ በቀላሉ መድረስ ይችላል። ነገር ግን ይህን ለማድረግ ጊሩ በትክክል መሥራት አለበት፡፡ ብስክሌቱን በደንብ ለመንዳት ከዜሮ ማርሽ ወደ አንደኛ ማርሽ ጨምሮ ፔዳሉን በእግሩ ሲመታው የሳይክሉ ፍጥነት ይጨምራል። ነገር ግን ጊሩና ሰንሰለቱ በአግባቡ የማይዛመዱ ከሆነ ብስክሌቱን የሚነዳው ሰው ሲነዳ የገጠመው ሰንሰለት ስለሚወልቅ በእግሩ ፔዳሉን የቱንም ያህል ቢያሽከረክረው ወይም ቢመታው በሰውየው ኃይል መሄድ አይችልም። ይልቁንም ለመንዳት ሲሞክር ቦታው ዳገት ከሆነ ወደ ኋላ ተጎትቶ ይወድቃል ቁልቁለት ከሆነ ደግሞ ወደፊት ተደፍቶ ይወድቃል፡፡
በተመሳሳይ ያላደጉ አገሮች ለማደግ ሲሞክሩ የሚገጥማቸው ችግር ይሄ ነው። ኢኮኖሚውን ለማሳደግ የሚመቱት ፔዳል የኢኮኖሚ ሴክተሩንና የኢኮኖሚ ፖሊሲውን አገናኝቶ ወደፊት እንዲሄድ አያደርገውም። ፔዳሉን የሚመታው በሰው ኃይል ይመሰላል፣ ፔዳሉ መሣሪያ ወይም ቴክኖሎጂ ነው፡፡ ይህ ቴክኖሎጂ እንዳልነው በእግር የሚመታ ሊሆን ይችላል፣ ነዳጅ ሊሆን ይችላል፡፡ ኤሌክትሪክ ሊሆን ይችላል፣ ወይም ደግሞ ዳገታማና ቁልቁለታማ ቦታ ላይ በራሱ የሚሄድ ይሆናል። ጊር የምንለው የኢኮኖሚ ሴክተሩ ማለታችን ነው፡፡ ግብርና፣ ማኑፋክቸሪንግ፣ ማዕድን፣ ቱሪዝም፣ አይሲቲ፣ ኮንስትራክሽን፣ አገልግሎትና ሌሎችም ማለት ነው። ሰንሰለት የምንለው ደግሞ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ያላደጉ አገሮች የኢኮኖሚ ሴክተሩን (ጊር ብለን የምንጠራውን) ተስማምቶ ማንቀሳቀስ የሚችል የኢኮኖሚ ፖሊሲ (ሰንሰለት ወይም ችንጋ) ባለመኖሩ ምክንያት ከድህነት አረንቋ መውጣት አልቻሉም፡፡ በየጊዜው የነበሩትን የኢኮኖሚ ፖሊሲ ወይም ሰንሰለት በመጠቀምና ሪፎርም በማድረግ ኢኮኖሚውን ለማሳደግ ይሞክራሉ፡፡
ነገር ግን ብዙም ሳይጓዙ ሰንሰለቱ ይወልቅና ፔዳሉ ብቻውን ይሽከረከራል ማለት ነው። ይህ ማለት በሌላ አነጋገር የሰው ልጅ ይለፋል፣ ጠብ የሚል ነገር ግን አይኖርም፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ በአሁኑ ጊዜ በዋናነት እየተወሰዱ ያሉ ሪፎርሞችን እንደ ምሳሌ ወስደን ለማየት እንሞክር፡፡ ተቋም ግንባታ፣ ጥብቅ የገንዘብ ፖሊሲ፣ ጥብቅ የፊሲካል ፖሊሲ፣ የማዕከላዊ ባንክ የወለድ ፖሊሲ፣ ፍሎቲንግ ኤክስቸንጅ ሬትና ሌሎችም ይገኙበታል። በዝርዝር ለማየት እንሞክር፡፡
1.ተቋም ግንባታ፡- ለአንድ አገር ኢኮኖሚ ዕድገት በጣም ወሳኝ መሆኑ ፈጽሞ ሊካድ ባይችልም፣ ጥሩ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ከሌለ ግን ውጤት ሊያመጣ አይችልም፡፡ ይኸውም በብስክሌት ፔዳል ነዳጅ ወይም ኤሌክትሪክ ኃይል ይመሰላል፡፡ ጊሩና ሰንሰለቱ ካልተገናኘ የሚያወጣው ኃይል ይባክናል እንጅ ውጤት አያመጣም፡፡
2,ጥብቅ የገንዘብ ፖሊሲ፡- ይህ የገንዘብ ፖሊሲ ወደ ገበያ የሚለቀቅ ገንዘብን መያዝና የተረጨውን የገንዘብ መጠን መሰብሰብ ማለት ነው። ይህ የገንዘብ ፖሊሲ መተግበር ዓላማው የዋጋ ንረትን መቀነስ ነው። በእርግጥም እንደሚባለው ይህ የገንዘብ ፖሊሲ የዋጋ ንረትን የመቀነስ አቅም ሲኖረው፣ በሌላ በኩል ደግሞ የኢኮኖሚ ዕድገትን ይቀንሳል፣ የሥራ አጥ ቁጥርን ይጨምራል። አብዛኛውን ጊዜ የአገሮች መሪዎችና ፖሊሲ አውጭዎች የሚከተሉት ፖሊሲ ቢሆንም፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ግን በየጊዜው በሚያደርጉት ንግግር ይህ ዕሳቤ ለሌሎች አገሮች ሊሠራ ይችል ይሆናል እንጂ፣ ለኢትዮጵያ እንደማይሠራ ይገልጻሉ፡፡ ይሁንና የኢኮኖሚ ምሁራን እዚህ ሐሳብ ላይ ሙጥኝ ብለው ይህን ዕሳቤ የሚነካባቸውን ሰው ዱላ ቀረሽ መከላከል በማድረግ አይነኬነታቸውን ቢቀጥሉም፣ ይህ ዕሳቤ ግን የሚቀረው የማሳመን ሥራ ቢሆንም ውድቅ የሆነና ያበቃለት ነው።
ነገር ግን አብዛኞቹ የአገሮች መሪዎች ልማታቸውን ለማሳደግ ኢኮኖሚውን አስፈቶ የዜጎችን ሕግና የተቋማትን ገቢ ጨምሮ ፍትሐዊ የሆነ ግብር ከመሰብሰብና ከሌሎች ምንጮች ከሚያገኙት ይልቅ፣ ፍትሐዊ ያልሆነ ግብር መሰብሰብ፣ ገንዘብ ማተምና ብድር መበደር ይቀላቸዋል፡፡ በዚያው ልክ ፖሊሲ አውጭዎችም ኢኮኖሚው ገንዘብ እያስፈለገው ገንዘብ በመከልከል የዋጋ ንረትን መቀነስ ይፈልጋሉ፡፡ በመሠረቱ የገንዘብ አቅርቦት መብዛት የዋጋ ንረትን የሚጨምር ቢሆንም፣ አንዳንድ ጊዜ ግን ኢኮኖሚው ገንዘብ እያስፈለገው የገንዘብ አቅርቦት ላይ ገደብ ሲደረግ ይታያል፡፡ ምሳሌ ኢትዮጵያ ውስጥ በቅርቡ የተወሰደውን ጥብቅ የገንዘብ ፖሊሲ ዕርምጃ እንውሰድ። ኢትዮጵያ በጣም ትላልቅና ግዙፍ የሆኑ ሜጋ ፕሮጀክቶች ያስፈልጓታል፡፡ በቀደሙት ዓመታትም እነዚህን ፕሮጀክቶች ለመፈጸም ሙከራዎች የተደረጉ ቢሆንም፣ በቂ የማክሮ ኢኮኖሚ ቁጥጥር ባለመደረጉ ምክንያት በዋጋ ንረት እምሽክ ተደርገው በመበላታቸውና መንግሥትን ለከፍተኛ ለአገርና ለውጭ ብድር ጫና በማጋለጣቸው ለማስቀጠል አይነኬ ፕሮጀክቶች ሆነው ቀጥለዋል፡፡
ከእነዚህም ውስጥ የመንግሥት የቤት ልማት ፕሮጀክት፣ የባቡር፣ የማዳበሪያ፣ የስኳር፣ የመስኖና የግድብ፣ እንዲሁም ሌሎች ፕሮጀክቶች ይገኙበታል። እናም ታዲያ ኢትዮጵያ ከላይ የተጠቀሱት ሜጋና ሌሎች ፕሮጀክቶችን ጨምሮ ብዙ የመሠረተ ልማት፣ የመስኖ፣ የማዕድን፣ የኃይል፣ የኢንቨስትመንትና ሌሎች ስፍር ቁጥር የሌላቸው ፕሮጀክቶች እያስፈለጓት ለዋጋ ንረት ተብሎ የገንዘብ አቅርቦትን የመገደብ ዕሳቤ አዲስ ባመነጨሁት የኢኮኖሚ ፖሊሲ ውድቅ የሚደረግ ይሆናል።
3.ጥብቅ የፊሲካል ፖሊሲ፡- የዚህ ፖሊሲ ዋና ዓላማ ወጪ መቀነስና ገቢ ማብዛት ማለት ነው። እንደዚህ ዓይነት የመንግሥት ወጪ ቁጠባ መሠረታዊ የሚባሉ የመንግሥት ወጪዎች ላይ አላስፈላጊ የሆነ ገደብ በመጣል መሠራት ያለባቸው ሥራዎች እንዳይሠሩ ያደርጋሉ። የመንግሥትን ገቢ በማብዛት በድርጅቶችና በዜጎች ላይ የሚጣሉ ከፍተኛ የግብር ተመኖች የዜጎችን ገቢ ከመቀነሳቸውም ባሻገር የግል ቁጠባን፣ ኢንቨስትመንትና ምርታማነት ከመቀነስ ባሻገር ግብር ከፋዩ ከመክፈል ይልቅ ወደ መሸሹና ወደ ግብር ሥወራ ተግባር ሊያመራ ይችላል።
- የማዕከላዊ ባንክ የወለድ ምጣኔ ተመን፡– በአሁኑ ጊዜ የዋጋ ንረት ምጣኔን ለማስተካከል አቅም እያነሰው የመጣ መሣሪያ በመሆኑ፣ ሚናው ከጊዜ ወደ ጊዜ እየቀነሰና እየተዳከመ በመምጣት ላይ ይገኛል።
- ፍሎቲንግ ኤክስቼንጅ ሬት፡- የተረጋጋ የውጭ ምንዛሪን ለማስፈን እንደ ቁልፍ መሣሪያ የሚያገለግለው አጠቃላይ የዋጋ ንረትን መቆጣጠር ነው።
ታዲያ ይህ የማክሮ ኢኮኖሚ ፖሊሲ የሁሉንም ፖሊሲዎች ተግባር በአንዴ በመከወን (All in One) ወይም የኢኮኖሚ ጊር የሚባለው ላይ በመግጠም፣ የፈለጉትን ያህል ማርሽ በመጨመር ሲፈልጉ በእግር፣ ሲፈልጉ በነዳጅ ኃይል ወይም ደግሞ የኤሌክትሪክ ኃይል በመጠቀም ፔዳሉን ቢመቱት በጊሩና በችንጋው ትስስር ምክንያት ህልቆ መሳፍርት የሌላቸው ምርት፣ አገልግሎት፣ የተረጋጋ የዋጋ ንረት፣ የተረጋጋ የውጭ ምንዛሪ ተመንና ሌሎችም ይፈልቃሉ። የእነዚህም ውጤት ደግሞ ለሰው ልጅ ደስታን፣ ነፃነትን፣ ሰላምን፣ ፍቅርን፣ መተሳሰብን፣ ወንድማማችነትንና አንድነትን፣ አገር ወዳድነትንና ሌሎች ብዙ መልካም ነገሮችን ያመጣል። ይህንንም የኢትዮጵያ ትንሳዔ ብለን ልንጠራው እንችላለን። ታዲያ ይህን ለማከናወን ምን ያስፈልጋል? እንደሚታወቀው ኢትዮጵያውያን ብዙ ያልተፈቱ ችግሮችና ያልተመለሱ ጥያቄዎች አሉ፡፡ ለእነዚህ ጥያቄዎች ምላሽ ለማግኘት ዜጎች የተለያዩ ዘዴዎችን እየተጠቀሙ ነው፡፡
ከእነዚህም ውስጥ ፈጣሪን መማፀን (ፀሎት)፣ ሰላማዊ ትግል፣ የትጥቅ ትግል፣ መንግሥትን ላይ ከፍተኛ ወቀሳ ማቅረብና ሌሎችንም ማድረግ ሲሆን፣ መንግሥትም በበኩሉ ጥያቄዎችን በሚፈለገው ልክ መመለስ ስለተሳነው በምላሹ የኃይልና የሰላም አማራጮችን በመጠቀም ምላሽ በመስጠት ላይ ይገኛል።
የሆነው ሆኖ ግን በዚህ መንገድ የሚፈቱ ችግሮች ይኖራሉ አይኖሩም ለሚለው መልስ ለአንባቢያን ልተውና እኔ ትክክለኛ የምለውን መንገድ ልጠቁም። ጥያቄ ጠያቂም ሆነ ምላሽ ሰጪ ጥያቄውንም ሆነ ምላሹን ለጊዜው ያዝ (Hold or Scape) አድርገውና ከድኅረ ዘመናዊነት (Post Modernity Thinking) ዕሳቤ መለስ በማለት፣ ከ1980 ዓ.ም. በፊት ወደ ነበረበት የዘመናዊነት ዕሳቤ (Modernity Thinking) በመመለስ የጋራ ዓላማ (Comen Objective) በሚለው ዕሳቤ ድህነትንና ኋላቀርነትን በጋራ ማጥፋት ተገቢነት ያለቅ ተግባር ነው። ከዚያ ስንመለስ ጥያቄዎቹን ፈልገን አናገኛቸውም፡፡ የምናገኘው የመቃብር ድንጋይ ፈንቅላ የተነሳችውን ኢትዮጵያን ነው፡፡ ይህን ማድረግ ከተሳነን ግን ብጥስጣሽ ሰንሰለት የተገጠመለት በእግር፣ በነዳጅ፣ በኤሌክትሪክ፣ ወይም ደግሞ በሰው ሠራሽ አስተውሎት የሚነዳ ሳይክል ወደ መዳረሻው አይወስደንም፡፡ ያደግን የበለፀግን ሊመስል ይችላል። መለኪያ የምንላቸው የዋጋ ንረት ምጣኔ፣ የነፍስ ወከፍ ገቢ፣ የጂዲፒ ምጣኔ፣ የሒዩማን ዴቨሎፕመንት ኢንዴክስና ሌሎችም ግን እውነታውን ላይመሰክሩ ይችላሉ፡፡ ቢመሰክሩም ዜጎች ከሚኖሩት እውነታ ጋር በማወዳደር እውነታነቱን ጥርጣሬ ውስጥ ያስገቡታል።
ለማጠቃለል ያህል የሚከተለውን ማለት ወደድኩ፡፡ ኢትዮጵያ አሁን ያለችው ውስብስብ ችግር ውስጥ ነው፡፡ ይህ ውስብስብ ችግር ደግሞ የተፈጠረው በማኅበራዊ፣ በኢኮኖሚና በፖለቲካ ፖሊሲዎች ድክመት ነው፡፡ አሁን በሥራ ላይ ያሉት የኢኮኖሚ ፖሊሲዎች የኢኮኖሚ ሴክተሩን ይዘውት ሊጓዙ አልቻሉም፡፡ በዚህም ምክንያት መንግሥት ያግዙኛል ብሎ የሚያስባቸውን የኢኮኖሚ ፖሊሲዎች፣ መመርያዎች፣ አዋጆች፣ ትዕዛዞችና ሌሎችንም በመጠቀም ላይ ይገኛል፡፡ እነዚህ ደግሞ ለዜጋው ብዙም ምቾት የሰጡት መስለው ያልታዩ ከመሆናቸውም ባሻገር፣ የኢትዮጵያን ትንሳዔ በትክክል ማረጋገጥ ይችሉ ይሆን ብሎ ለማሰብ ይከብዳል፡፡ ይህን እንድል ያስገደደኝ ነገር ደግሞ በዚህ ዘመን ላይ ያሉት የኢኮኖሚ ፖሊሲዎች ኃይል የሌላቸውና የኢትዮጵያን ትንሳዔ ለማስነሳት ያላቸው አቅም ውሱን መሆኑን በመረዳቴ ነው፡፡
ነገር ግን አዲስና ኃይል ያለው የኢኮኖሚ ፖሊሲን ስንጠቀም እንዴት የኢትዮጵያን ትንሳዔ ማስነሳት እንደሚችል እንመልከት፡፡
- ፔዳል (ጊሩ እንዲሽከረከር የሚረዳ መዘውር) ኤሌክትሪክ አስተላላፊ ገመድ/ፒስተን/ ዲጂታል ኃይል (በአጭሩ ይህ ማለት ተቋም ወይም ድርጅት ማለት ነው)፣
- እግር (የሰው ጉልበትና ዕውቀት /የነዳጅ ኃይል) የኤሌክትሪክ ኃይል/ዘመኑ የደረሰበት ቴክኖሎጂ /ሰው ሠራሽ አስተውሎት (AI) (ሥራ የሚሠራ ማለት ነው)፣
- ጊር (የኢኮኖሚ ሴክተር) ይህ ማለት የሰው ልጅ የሚሰማራበት የሥራ መስክ ነው፣
- ቺንጋ (የኢኮኖሚ ፖሊሲ) ይህ ማለት የኮቪድ-19 ወረርሽኝን ተከትሎ የመጣው አዲሱና ዘመናዊው የኢኮኖሚ ፖሊሲ ማለት ነው፡፡
እነዚህ ከላይ ያሉት መስተጋብር ፈጥረው በተሳካ ሁኔታ ሲንቀሳቀሱና ኢኮኖሚውን ሲያሠሩት (ኦፐሬት) ሲያደርጉት፣ ደስ የሚልና ስኬት የተሞላበት የአቀበት ጉዞን የሚፈጥሩ ሲሆን የፖለቲካና የማኅበራዊ ችግሮችም አዚህ ጋር መፍትሔ ያገኛሉ፡፡
ደስ የሚለውና የተሳካው ጉዞ ደግሞ ሜዳው ላይ ያደርሰናል ሜዳው ደግሞ ሰላም፣ ዕድገትና ብልፅግና ያለበት ቦታ ነው፡፡ ይህም ቦታ ዩቶፒያ ሲባል ለኢትዮጵያ ደግሞ የትንሳዔዋ መገለጫ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ድህነትና ኋላቀርነት ታሪክ እንዲህ በአራት ነጥብ ለመዝጋት ሁላችንም ኃላፊነታችን ልንወጣ ይገባል፡፡ ከዚያም ዓለም ላይ ያሉ ችግሮችን ለመፈታት ደግሞ ሌላ አዲስ ምዕራፍ እንከፍታለን (ቀጣይ ቴክኒካዊ የሆኑ ነገሮች ለማቅረብና ለመከወን ለመንግሥት የቀረበ የፍላጎት ማሳያ ምላሽ እየተጠበቀ ይገኛል)፡፡ ሐሳቡ ይህን ከመሰለ፣ ይህን ዓይነት የኢኮኖሚ ኦፕሬሽን የሚመራ ሰው ደግሞ ፈጣሪ በቸርነቱ በውስጡ አድሮ እንደሚከውንልን በማመን ለሚሠራውም ሥራ ስሙ ለዘለዓለም በታሪክ መዝገብ ላይ ተጽፎ የሚኖር ይሆናል፡፡
ይህ ሐሳብ ነው፡፡ የሁሉም ነገር መነሻውም ደግሞ ጽንሰ ሐሳብ ነው፡፡ በእኔ በኩል ይህ ሐሳብ የኢትዮጵያን ትንሳዔ ማረጋገጥ አንደሚችል ሙሉ እምነት ያለኝ ሲሆን ሐሳቡን የሚፈጽመው ደግሞ እግዚአብሔር ነውና እሱ ይረዳናል፡፡
አዘጋጁ፡ ጸሐፊው የባንክና የኢኮኖሚ ባለሙያ ሲሆኑ፣ ጽሑፉ የእሳቸውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እየገለጽን በኢሜይል አድራሻቸው [email protected] ማግኘት ይቻላል፡፡