ዩቶፕያ ቴክኖሎጂ በአውቶሞቲቭ፣ በታዳሽ ኃይል ቴክኖሎጂ፣ በማኑፋክቸሪንግ፣ በግብርና ምርት ፕሮሰሲንግና ኤክስፖርት በማድረግ፣ እንዲሁም በአይሲቲ ዘርፍ ላይ በመሰማራት በተለያዩ ዓለም አቀፍ የንግድ ከተሞች ላይ የኢትዮጵያን ምርት በማስተዋወቅ ሲሠራ የቆየ ማኅበር ነው፡፡ ማኅበሩ በአሁኑ ወቅት በነዳጅ የሚሠሩ ተሽከርካሪዎችን በኤሌክትሪክ በሚሠሩ ተሽከርካሪዎች ለመተካት የሚያበረታታ ‹‹ዩቶፕያ ግሪን ሞቢሊቲ›› (Utopia Green Mobility) የተሰኘና ሌሎች አዳዲስ ፕሮጀክት ላይ እየሠራ ሲሆን፣ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ወደ አገር በማስገባት ለኅብረተሰቡ ከማቅረብና ተደራሽ ከማድረግ አኳያ፣ እንዲሁም አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በማስተዋወቅ ምን እየሠራ ነው የሚለውን የዩቶፕያ ቴክኖሎጂ ማኅበር መሥራችና ዋና ዳይሬክተር የሆነውን አቶ አዶኒክ ወርቁን አበበ ፍቅር አነጋግሮታል።
ሪፖርተር፡- ዩቶፕያ ቴክኖሎጂ መቼ ተመሠረተ?
አቶ አዶኒክ፡- ዩቶፕያ ቴክኖሎጂ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ድርጅት የተመሠረተው የዛሬ አምስት ዓመታት ላይ ነበር። ይሁን እንጂ ላለፉት 15 ዓመታት ሐበሻ ዊክሊ ፕሮሞሽን ከተባለ እህት ኩባንያችን ጋር የኢትዮጵያን ምርት ባህልና መልካም ገጽታ በመላው ዓለም በማስተዋወቅ፣ እንዲሁም ለኅብረተሰቡ አገልግሎት በመስጠት አስተዋጽኦ ሲያደርግ የቆየ ነው፡፡ ዩቶፕያ ቴክኖሎጂ ለደንበኞቹና ለአካባቢ ምቹ፣ አስተማማኝና ዘላቂ የልማት መፍትሔዎችን በማስተዋወቅ ላይ ሲሆን በአውቶሞቲቭ፣ በታዳሽ ኃይል ቴክኖሎጂ፣ በማኑፋክቸሪንግ፣ በግብርና ምርት ፕሮሰሲንግና ኤክስፖርት፣ እንዲሁም በአይሲቲ ዘርፎች የተሠማራና በሙያው ልምድ ባላቸው ባለሙያዋች የተመሠረተ የቴክኖሎጂ ኩባንያ ነው።
ሪፖርተር፡- ወደ ውጭ የምትልኳቸው ምርቶች ምንድን ናቸው?
አቶ አዶኒክ፦ ድርጅታችን ባለው ዓለም አቀፍ ተሞክሮና ባካበተው ልምድ፣ እንዲሁም በተለያዩ የዓለማችን የንግድ ከተሞች በዘረጋነው ኔትዎርክ የኢትዮጵያን ምርት በማስተዋወቅና ኤክስፖርት በማድረግ የበኩላችንን አስተዋፅኦ እያበረከትን ሲሆን፣ ‹‹ዮቶፕያ ቡና›› (Utopia Coffee) በሚል ብራንድ ጥራት ያላቸው ቡናዎችና የግብርና ውጤቶችን በመላው ዓለም እየላከ ይገኛል፡፡
ሪፖርተር፡- ዩቶፕያ ግሪን ሞቢሊቲ ምን አዲስ ነገር ይዞ መጥቷል?
አቶ አዶኒክ፡- ዩቶፕያ ግሪን ሞቢሊቲ ለአካባቢ አየር ንብረት ተስማሚ፣ እንዲሁም ለነዳጅ የሚወጣውን የውጭ ምንዛሪ የሚያስቀር ፕሮጀክት ሲሆን በውስጡ አራት ንዑስ ዘርፎችን አካቷል፡፡ የመጀመሪያው በታዳሽ ኃይል የሚሠሩ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን የመገጣጠም የማቅረብና የመጠገን አገልግሎትን የሚሰጥ “ዩቶፕያ አውቶሞቲቭ” የተሰኘ ሲሆን፣ “ዩቶፕያ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ቻርጂንግ ስቴሽን ሁለተኛው ዘርፍ ነው፡፡ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን የባትሪ ሙሌት ጣቢያዎችን ከታዳሽ ኃይል ቴክኖሎጂ ጋር መገንባትን ያካተተ ነው፡፡ በሌላ በኩል የተለያዩ ዘመናዊ ሞዴል ተሽከርካሪዎችን በተመጣጣኝ ዋጋ የማቅረብ ሥራ “ዩቶፕያ ኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ሽያጭ ታክሲ ሲሆን፣ የመጨረሻው ደግሞ ዩቶፕያ ግሪን ፈንድ የተሰኘ ነው፡፡ ይህም ደንበኞች የተለያዩ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ባለቤት እንዲሆኑ ተመጣጣኝና ምቹ የፋይናንሲንግ አገልግሎትን ማመቻቸት ነው፡፡
ሪፖርተር፦ አዳዲስና ዘመናዊ ተሽከርካሪዎችን የሚያመርቱ ኩባንያዎች እንዳሉ ይታወቃል፡፡ እናንተ ከየትኞቹ አምራቾች ነው የምታስገቡት?
አቶ አዶኒያስ፦ በዓለም ብዙ አምራቾች አሉ፡፡ ከተመሠረተ 100 ዓመት ካስቆጠረው ኤምጂ ሞተር ከተሰኘ የእንግሊዝ የአውቶሞቢል ብራንድ ጋር ምርቱን በኢትዮጵያ ለመገጣጠም እንዲሁም ብቸኛ አስመጪና አከፋፋይ ለመሆን ስምምነት ፈጽመናል፡፡ በተጨማሪም የቢዋይዲ (BYD) የቮልስዋገን (VW) እና ኔታ (NETA) የተሰኙ በከፍተኛ ጥራት የተሠሩ ዋጋቸው ተመጣጣኝ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ለግልና ለታክሲ አገልግሎት በማቅረብ ላይ እንገኛለን፡፡
ሪፖርተር፡- የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ለመግዛት ወደ ድርጅታችሁ የሚመጡ ደንበኞች ምን ምን አገልግሎትን ያገኛሉ?
አቶ አዶኒክ፡- ደንበኞች ለሚወስዷቸው ተሽከርካሪዎች እስከ አምስት ዓመት የሚቆይ የረዥም ጊዜ አስተማማኝ ዋስትና፣ ቻርጅ ማድረጊያውን ጨምሮ ፈጣን የቻርጂንግ አገልግሎት እንዲሁም የተሟላ ጥገናና መለዋወጫ አመቻችቷል፡፡
ሪፖርተር፦ ብዙ ሰዎች በኤሌክትሪክ የሚሠሩ ተሽከርካሪዎች ባትሪያቸው ቶሎ ይሞታል፣ እንዲሁም የመለዋወጫ ዕቃ የለም በማለት ከወዲሁ ፍራቻ ያድርባቸዋል። እነዚህን ሥጋቶች እናንተ እንዴት አያችሁት?
አቶ አዶኒያስ፦ በእርግጥ ይህ አመለካከት እየቀነሰ የመጣ ይመስላል። አሁኑ ላይ አንዳንድ ሰዎች እንደ ችግር የሚያነሱት ቻርጅ ማድረጊያ ማጣት ነው። ይህንን በቤታቸውና በሌሎች አማራጮች ቻርጅ ማድረግ ለሚችሉ ሰዎች የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ተመራጭ ነው፡፡ ስለባትሪ አንዳንድ ሚዛናዊ ያልሆኑ አስተያየቶች አሉ፡፡ በእርግጥ የዓመቱ ሁለት በመቶ ሊቀንሱ ይችላሉ፡፡ ይህ ማለት ደግሞ በጣም ትንሽ መሆኑን ያሳያል፡፡ ለምሳሌ 500 ኪሎ ሜትር የሚጓዝ ተሽከርካሪ በዓመት ሁለት በመቶ ባትሪ ይቀንሳል ማለት በዓመት በጣም ትንሽ ነው፡፡ ብዙ ሰዎች ከአምስትና ከስድስት ዓመት በኋላ ባትሪው ያልቃል ብለው ነው የሚሠጉት፡፡ እውነታው ግን ሌላ ነው፡፡ በስምንትና በአሥር ዓመት አገልግሎት የተወሰነ ቢቀንስ ነው፡፡ በሌላ በኩል ባትሪው ከተሽከርካሪው ዋጋ ጋር እኩል ነው፡፡ በጣም ውድ ነው የሚባል አመለካከትም አለ፡፡ ይህም ትክክል አይደለም፡፡ በተለይ ቴክኖሎጂ እየተሻሻለ ሲመጣ የባትሪው ዋጋ በጣም እየቀነሰ መጥቶ አሁን ላይ ዋጋው በመቶ ሺዎች በሚቆጠር ብር ገብቷል፡፡ ሌላው ብዙዎችን ሥጋት ላይ የጣለው የጥገናና የመለዋወጫ ጉዳይ ሲሆን በእኛ በኩል ለምንሸጣቸው ተሸከርካሪዎች የጥገናና የመለዋወቻ ዕቃዎችን እናቀርባለን፡፡
ሪፖርተር፡- ችግሩን ለመፍታት ምን አማራጮችን አይታችኋል?
አቶ አዶኒክ፡- የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች መሙያ ጣቢያን ታዳሽ ኃይል ከሚባሉት የሶላርና የንፋስ ኃይል ጋር ለመተግበር፣ እንዲሁም የባትሪ ማከማቻና የሶላር ኃይል ቴክኖሎጂ ፋብሪካዎችን ለማቋቋም ከኢትዮጵያ አዕምሯዊ ንብረት ባለሥልጣን ከአምስት ዓመት በፊት ዕውቅና ወስደን ፕሮጀክቱን በመተግበር ላይ እንገኛለን፡፡
ሪፖርተር፡- ለደንበኞቻችሁ አገልግሎትን ለመስጠት ምን ዓይነት የቴክኖሎጂ አሠራር ዘርግታችኋል?
አቶ አዶኒክ፡- ዩቶፕያ ግሪን ፈንድ የተሽከርካሪ የግዥ ሒደት ሙሉ በሙሉ ደኅንነቱ በተጠበቀ የዲጂታል መተግበሪያ የሚተዳደርበትን ዳይናሚክ ሲስተም ከአገር ውስጥና ከአገር ውጭ ባሉ ባለሙያዎች በትብብር ተዘጋጅቷል፡፡
ሪፖርተር፡- የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ከነዳጅ ተሽከርካሪ ጋር ሲተያይ የሚያቀላቸው ነገሮች አሉ?
አቶ አዶኒያስ፦ አገራችን ለምትከተለው አረንጓዴ መር ዲጂታል ኢኮኖሚ ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያበረክት ሲሆን፣ ታላቁ የህዳሴ ግድብ ፕሮጀክት እንደ ኢምፖርት ሰብስቲትዩት ለመጠቀምና የኢነርጂ ፍላጎታችንን አካባቢ በካይ ከሆነው ነዳጅ በዋጋ ዝቅተኛ ታዳሽ ኤሌክትሪክ ኃይል ለመቀየር ትልቅ ዕድል ይፈጥራል። እንዲሁም ለነዳጅ የሚወጣውን ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ያስቀራል፡፡ በተጨማሪም ለኅብረተሰቡ ከፍተኛ የሥራ ዕድል ከመፍጠሩ ባሻገር ያለውን የትራንስፖርት እጥረት ይቀርፋል፡፡