- በብሔራዊ ባንክ የተቀመጠውን ዝቅተኛ የካፒታል መሥፈርትም ማሟላት ችሏል

አንበሳ ባንክ በ2017 የሒሳብ ዓመት ከታክስ በኋላ 1.4 ቢሊዮን ብር በላይ ትርፍ ማግኘቱንና የተከፈለ ካፒታሉንም ከአምስት ቢሊዮን ብር በላይ ማድረሱን አስታወቀ፡፡
ባንኩ ባለፈው ቅዳሜ ባካሄደው ጠቅላላ ጉባዔ ላይ የሥራ አፈጻጸም ሪፖርቱን ያቀረበ ሲሆን፣ በሪፖርቱ መሠረት ባንኩ በሒሳብ ዓመቱ ከታክስ በኋላ 1.4 ቢሊዮን ብር አትርፏል፡፡ ባንኩ ከታክስ በፊት ያስመዘገበው ትርፍ 1.8 ቢሊዮን ብር የነበረ ሲሆን፣ ይህም ከቀዳሚው ዓመት የ94 በመቶ ብልጫ አለው፡፡ ከታክስ በኋላ የተመዘገበውም ትርፍ በተመሳሳይ ዕድገት የተመዘገበበት በመሆኑ አንድ ሺሕ ብር ዋጋ ላለው ለባንኩ አንድ አክሲዮን 420 ብር የትርፍ ድርሻ አስገኝቷል። ይህም የትርፍ ድርሻ ከቀዳሚው ዓመት የ139 ብር ብልጫ እንዳለው ተጠቁሟል።
አንበሳ ባንክ በሰሜኑ ጦርነት ምክንያት ከፍተኛ ጉዳት ከደረሰባቸው ጥቂት ባንኮች መካከል አንዱ የነበረ ሲሆን፣ ይህም የባንኩ አጠቃላይ አፈጻጸም ላይ ተፅዕኖ አሳድሮ እንደነበር ይታወሳል፡፡ የተፅዕኖው አንዱ መገለጫም የባንኩ ትርፍ እንዲቀንስ ማድረጉ ነበር፡፡
በ2013 የሒሳብ ዓመት የባንኩ ዓመታዊ ትርፍ 414 ሚሊዮን ብር ደርሶ የነበረ ቢሆንም ጦርነቱ በፈጠረበት ተፅዕኖ በ2014 የሒሳብ ዓመት የትርፍ መጠኑ ወደ 311 ሚሊዮን ብር ወርዶ ነበር፡፡ የትርፍ መጠኑ ከመቀነሱ ባሻገር የባንኩ የተበላሸ ብድር መጠንም ከፍተኛ ደረጃ አሻቅቦ በባንኩ እንቅስቃሴ ላይ ትልቅ ጫና መፍጠሩ አይዘነጋም፡፡ ከ2015 የሒሳብ ዓመት በኋላ ግን ዓመታዊ የትርፍ ምጣኔውን እያሳደገ መምጣት ችሏል፡፡ በዚህም መሠረት በ2015 የሒሳብ ዓመት ከታክስ በፊት 747 ሚሊዮን ብር ያተረፈ ሲሆን፣ በ2016 የሒሳብ ዓመት ደግሞ ዓመታዊ ትርፉን ወደ 941 ሚሊዮን ብር በማሳደግ ከነበረበት ችግር ማገገም መጀመሩን አሳይቷል። የ2017 የሒሳብ ዓመት አፈጻጸሙም ከነበሩበት ችግሮች ተላቆ የተሻለ ትርፍ ማስመዝገብ የቻለበት ነው።
የባንኩ የዳይሬክተሮች ቦርድ ሊቀመንበር አቶ ዓለም አስፋው ባንኩ በ2017 የሒሳብ ዓመት ከታክስ በፊት ያገኘው 1.8 ቢሊዮን ብር ትርፍ ከቀዳሚው ዓመት ጋር ሲነፃፀር በእጥፍ ብልጫ ያለው መሆኑንና ይህም የባንኩን ጥንካሬ አጉልቶ የሚያሳይ ከመሆኑም በላይ ለቀጣይ የላቀ ስኬት መንደርደሪያ የሚሆን ነው ብለዋል፡፡
ባንኩ በተጠናቀቀው የሒሳብ ዓመት የሰጠው የብድር ስድስት ቢሊዮን ብር ሲሆን ይህም ከቀዳሚው ዓመት የ19 በመቶ ብልጫ እንዳለው የቀረበው ሪፖርት ይጠቁማል። የባንኩ አጠቃላይ የብድር ክምችትም በ2017 መጨረሻ ላይ 36.2 ቢሊዮን ብር ደርሷል።
በሒሳብ ዓመቱ እንደ ትልቅ ስኬት የታየው ሌላው አፈጻጸም የተመላሽ ብድር አሰባሰቡ ሲሆን፣ በሒሳብ ዓመቱ 5.2 ቢሊዮን ተመላሽ ብድር መሰብሰብ ችሏል፡፡ ነገር ግን ባንኩ አሁንም ብድር በማስመለስ ላይ ጠንክሮ መሥራት እንደሚገባው ጠቅላላ ጉባዔው አሳስቧል፡፡
From The Reporter Magazine
የቦርድ ሊቀመንበሩ እንደተናገሩት የታመመ ብድርን በተመመለከተ አዎንታዊ ለውጦች እየታዩ ቢሆንም በብሔራዊ ባንክ ወዳስቀመጠው ዝቅተኛ የተበላሸ ብድር ምጣኔ ለማውረድ የባንኩ ቦርድና ማኔጅመንት እየሠሩበት ነው፡፡
በሀብት ማሰባሰብ ረገድም ባንኩ በሒሳብ ዓመቱ 8.3 ቢሊዮን ብር ተቀማጭ ገንዘብ በማሰባሰብ አጠቃላይ የተቀማጭ ገንዘብ ክምችቱን 44 ቢሊዮን ብር ማድረስ ችሏል፡፡ ይህ የተቀማጭ ገንዘብ አፈጻጸም ከቀዳሚው ዓመት የ23 በመቶ ዕድገት አለው፡፡ የባንኩን ደንበኞች ቁጥርም በ24 በመቶ ማሳደጉን የሚጠቁመው የባንኩ መረጃ ይህም በሒሳብ ዓመቱ መጨረሻ ላይ የባንኩን ደንበኞች ቁጥር 2.4 ሚሊዮን ደርሷል፡፡
አንበሳ ባንክ እስከ 2017 የሒሳብ ዓመት ድረስ አጠቃላይ የተከፈለ ካፒታል መጠኑ 3.7 ቢሊዮን ብር ነው፡፡ ይህ የካፒታል መጠን ግን መስከረም 30 ቀን 2018 ዓ.ም. ላይ ከአምስት ቢሊዮን ብር መሻገር መቻሉ በጠቅላላ ጉባዔው ላይ ተገልጿል፡፡ የቦርድ ሊቀመንበሩ በዚህ ጉዳይ ላይ በሰጡት ተጨማሪ ማብራሪያ ‹‹ይህ ሪፖርት በሚቀርብበት ሰዓት ባለአክሲዮኖቻችን በሚያስገርም ሁኔታ የባንኩን የተከፈለ ካፒታል መጠን ከአምስት ቢሊዮን ብር በላይ በማድረስ በብሔራዊ ባንክ የተቀመጠውን ዝቅተኛ የካፒታል መሥፈርት ማሟላት ችለናል፤›› ብለዋል፡፡
From The Reporter Magazine
ካፒታሉን በማሳደግ ረገድ ተጨባጭ ዕርምጃዎች በመወሰዳቸው የተገኘ ውጤት መሆኑን የገለጹት የቦርድ ሊቀመንበሩ አሁን ባንኩ የደረሰበት የተከፈለ ካፒታል መጠን ከዝቅተኛው መሥፈርትም በላይ መድረሱን አክለዋል፡፡ ባንኮች የተከፈለ ካፒታላቸውን አምስት ቢሊዮን ብር እንዲያዳርሱ የተቀመጠው የጊዜ ገደብ ከመድረሱ በፊት አንበሳ ባንክ ካፒታሉን ለማሟላት ካስቻሉት መካከል የፈረሰው የግዕዝ ባንክ ባለአክሲዮኖች አንበሳ ባንክን መቀላቀል በመቻላቸው እንደሆነ ታውቋል፡፡
አቶ ዓለም ባቀረቡት ሪፖርታቸው ይህንኑ ሐሳብ የሚያጠናክር ነው፡፡ በመሥራቾች ስምምነት የምሥረታ ሒደቱ እንዲቋረጥ የተደረገው የግዕዝ ባንክ አክሲዮን ማኅበር ባለአክሲዮኖችና አስተባባሪዎች ገንዘባቸውን ወደ አንበሳ ባንክ ለማስተላለፍ ላሳለፉት ድንቅ ውሳኔና ላደረጉት ተነሳሽነት ምሥጋና አቅርበው፣ ይህ የግዕዝ ባንክ ባለአክሲዮኖች ውሳኔ የአንበሳ ባንክን የተከፈለ ካፒታል ለማሳደግ ወሳኝ አስተዋጽኦ እንደበረከተም ተናግረዋል፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን የግዕዝ ባንክ ባለአክሲዮኖች ባንካቸውን መቀላቀላቸው የደንበኞች ቁርጥን ለመጨመርና የተወዳዳሪነት አቅማቸውንም ለማሳደግ እንደሚያግዝ ጠቅሰው የአክሲዮን ዝውውሩም በኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ይሁንታና ዕገዛ የተፈጸመ ስለመሆኑ በዚሁ ሪፖርታቸው ላይ አመልክተዋል፡፡
የፈረሰው ግዕዝ ባንክ ባለአክሲዮኖች አንበሳ ባንክን የተቀላቀሉት በቀረበላቸው ሁለት ምርጫዎች ሲሆን እሱም ያላቸውን አክሲዮን ይዘው አንበሳ ባንክን መቀላቀል ወይም ያወጡትን አክሲዮን ገንዘብ እዲወስዱ የሚል እንደነበር ያገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡ አብዛኛዎቹ ባለአክሲዮኖችን አንበሳ ባንክን ለመቀላቀል በመምረጣቸው ባላቸው አክሲዮን ልክ የአንበሳ ባንክ ባለአክሲዮን መሆን ችለዋል፡፡ በቅዳሜው የአንበሳ ባንክ ጠቅላላ ጉባዔም የነዚህ ባለአክሲዮኖች አንበሳ የተቀላቀሉበት አክሲዮኖቻቸው እንዲፀድቅላቸው ተደርጓል፡፡ አብዛኛዎቹ የግዕዝ ባለአክሲዮኖች አንበሳ ባንክን የተቀላቀሉት ከ700 ሚሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያላቸውን አክሲዮኖች ይዘው ነው፡፡ ባለአክሲዮኖችን የሆኑትም በየግላቸው ነው፡፡
አንበሳ ባንክ በሒሳብ ዓመቱ መጨረሻ ላይ አጠቃላይ የሀብት መጠኑ 54 ቢሊዮን ብር መድረሱን የገለጹት የአንበሳ ባንክ ፕሬዚዳንት አቶ ዳንኤል ተከስተ ይህ የሀብት መጠን ከቀዳሚው ዓመት 25 በመቶ ብልጫ አለው፡፡
የባንካቸው ካፒታልና የብሔራዊ ባንክ መጠባበቂያ 28 በመቶ ዕድገት በማሳየት 6.5 ቢሊዮን ብር መድረሱንም ጠቅሰዋል፡፡
አንበሳ ባንክ በሒሳብ ዓመቱ ያስመዘገበው ውጤት ባለአክሲዮኖች የተወሰደ ቢሆንም በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ቅሬታ የቀረበበትም ነበር፡፡
በቅዳሜው ጠቅላላ ጉባዔ ላይ አነጋጋሪ ጉዳይ ሆነው ከቀረቡት መካከል ወደ አራት የሚሆኑ ግለሰቦች ያለአግባብ አክሲዮን እንዲሸጥላቸው ሆኗል የሚለው ቅሬታ መቅረቡ ነው፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን አክሲዮን ሲሸጥላቸው ከባንኩ ብድር እንዲያገኙ ተደርጓል ጭምር የሚል ክስ የቀረበበት ነበር፡፡
ሌላው በጠቅላላ ጉባዔው ላይ የተነሳው ቅሬታ ወደ 400 ሚሊዮን ብር ዋጋ ያለው አክሲዮን ሽያጭ ሲደረግ ቀድሞ ለነባር ባለአክሲዮኖች ዕድል ሊሰጥ ይገባ ነበር፡፡ እንዲህ ያሉ ቅሬታዎች ያሉዋቸው ባለአክሲዮኖች ቅሬታቸውን ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ጭምር እስከማቅረብ መድረሳቸው ተነግሯል፡፡ እንዲህ ያሉ ቅሬታዎችና ክሶች ላይ ምላሽ የሰጠው የባንኩ ዳይሬክተሮች ቦርድ ተፈጸመ የተባለው ጉዳይ ፈጽሞ አመለከሰቱን ነው፡፡ አክሲዮኖቹ ለውጭ አክሲዮን ገዥዎች ከመሸጣቸው ቀደም ብሎ ዕድሉ የተሸጡት መጀመሪያ ለነባር ባለአክሲዮኖችን እንዲሰጥ ተደርጓል፡፡ ጥያቄም የቀረበላቸው ቢሆንም ምላሽ ማግኘት ባለመቻሉ ዕድሉ ለሌሎች ሊሰጥ ስለመቻሉ የሚያመለክት ማብራሪያ መስጠቱንና ይህ እንደ ስህተት መታየት የለበትም የሚል አንድምታ ያለው ምላሽ ሰጥተዋል ተብሏል፡፡
አክሲዮን እንዲገዙ የተደረጉት ከባንኩ ተበድረው ነው በሚለው ቅሬታ ላይም ይህ ያመሆኑንና ይህንንም ማረጋገጥ እንደሚቻል በመግለጽ የቀበረውን ክስ አጣጥለውታል፡፡ ጉዳዩን ብሔራዊ ባንክ የያዘው በመሆኑም በቀላሉ እውነታው ሊረጋገጥ እንደሚችልም ለጠቅላላ ጉባዔው ምላሽ ተሰጥቷል፡፡
አንበሳ ባንክ በተለያዩ የአገሪቱ ከተሞች በሒሳብ ዓመቱ ተጨማሪ 35 አዳዲስ ቅርንጫፎችን የከፈተ ሲሆን፣ ጠቅላላ የቅርንጫፎቹን ቁጥር 341 አድርሷል፡፡