ሪፖርተር – Ethiopian Reporter – #1 reliable news source in Ethiopia
[ክቡር ሚኒስትሩ ከአማካሪያቸው ጋር የሥራ መልቀቂያ ስላቀረቡት ባለሥልጣን እየተወያዩ ነው]
- ያደረጉትን ተመልክተሃል አይደል?
- ማን?
- የሥራ መልቀቂያ ያቀረቡት ባለሥልጣን፡፡
- የትኛው?
- ገዥው ናቸዋ።
- እ… መልቀቂያ ማቅረባቸውን ነው የሰማሁት።
- ያቀረቡት መልቀቂያ ላይ ውሳኔ ሳይሰጥ ያደረጉትን አልሰማህም?
- ምን አደረጉ?
- በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ላይ ሥራ መልቀቃቸውን በይፋ አሳወቁ።
- የሥራ መልቀቂያቸው ተቀባይነት ማግኘቱ ሳይገለጽላቸው በፊት?
- አዎ።
- በፍጹም ትክክል አላደረጉም።
- አዎ… ከእሳቸው የሚጠበቅ ተግባር አይደለም።
- እና ምን አደረጉ? ደወሉላቸው?
- አልደወልኩም።
- እና?
- በቀጥታ እንዲጻፍላቸው ተወሰነ።
- ምን?
- ከኃላፊነት መነሳታቸውን የሚገልጽ ደብዳቤ።
- ግን ይኼ ጠቃሚ ነው ክቡር ሚኒስትር?
- እንዴት?
- ሰውዬው ከኃላፊነት ቢለቁም በአጋሮቻችን ዘንድ ተደማጭነት አላቸው።
- እና ቢኖራቸውስ?
- ያላቸውን ተሰሚነት ተጠቅመው ነገሮችን ይቆላልፉብናል ብዬ ነው።
- ምንድነው የሚቆላልፉብን?
- ክቡር ሚኒስትር የጠየቅነው የውጭ ዕዳ ሽግሽግ ገና አልተጠናቀቀም፣ በተጨማሪም…
- በተጨማሪ ምን?
- ከሚደግፈን የገንዘብ ተቋምም ጋር ባላቸው ግንኙነትም ቀጣይ ፈንዶች እንዳይለቀቁ ሊያደርጉ ይችላሉ።
- እና ምን ይደረግ ነው የምትለው?
- ግጭት እንዳልተፈጠረ አድርገን ብንሸኛቸው አይሻልም ክቡር ሚኒስትር?
- ራሳቸው እኮ ናቸው ግጭቱን የጀመሩት፡፡
- ቢሆንም ክቡር ሚኒስትር…
- ቢሆንም ምን?
- ምንም እንዳልተፈጠረ ኬክ ቆርሰን ብንሸኛቸው አይሻልም?
- ሌሎች አመራሮችም እንደዚያ ነው ያሉት።
- ልክ ናቸው፣ ኬክ ቆርሰን በሰላም ብንሸኛቸው ይሻላል።
- ባልስማማበትም ያልከውን አድርገናል።
- ኬክ ተቆርሶ ሽኝት ተደረገላቸው?
- አዎ።
- መቼ?
- ትናንት።
- ታዲያ እኔን ለምን ጠየቁኝ ክቡር ሚኒስትር?
- በወቅቱ ስላልነበርክ እንዲያው የተለየ ሐሳብ ይኖረው ይሆን ብዬ ነው።
- ሐሳባችን ተመሳሳይ መሆኑ አስገርሞኛል፣ ሽኝቱን ያደረጋችሁት ለእሳቸው ብቻ ነው?
- ታዲያ ሌላ ማን አለ?
- ሌላኛውን የተሰናበቱ ሹመኛም አንድ ላይ ሸኝታችሁ ይሆናል ብዬ ነው።
- ማንን ማለትህ ነው?
- ሰሞኑን በአምባሳደርነት ገለል የተደረጉትን ማለቴ ነው።
- እሳቸውማ ኬኩን አግኝተዋል።
- መቼ?
- ያኔውኑ ነዋ።
- እንዴት አልሰማሁም?
- ምኑን?
- ለእሳቸውም ኬክ ተቆርሶ መሸኘታቸውን፡፡
- ሰጠናቸው ያልኩህ እኮ የሚቆረሰውን ኬክ አይደለም።
- እ…?
- ሹመቱን ነው።
- እሱን ነው እንዴ?
- ለእሳቸው እሱ ኬክ አይደለም እንዴ?
- ከኬክም በላይ ነው።
- [በቅርቡ ካቢኔውን የተቀላቀሉት ሚኒስትር ቀደም ብሎ ካቢኔውን ከተቀላቀለ የተቃዋሚ ፓርቲ ተወካይ ሚኒስትር ጋር እያወጉ ነው]
- ይህንን ኃላፊነት ከመቀበሌ በፊት ላገኝህ በጣም ፈልጌ ነበር፡፡
- ምነው ለምን?
- ልምድህን እንድታካፍለኝ ነዋ።
- የምን ልምድ?
- በገዥው ፓርቲ የተቋቋመ ካቢኔ ውስጥ ተቃዋሚ ፓርቲን ወክሎ ማገልገል እንዴት እንደሚቻል ለመረዳት።
- አይ መሥጋት የለብህም።
- እንዴት?
- ምክንያቱም የተለየ ልምድ የሚጠይቅ አይደለም።
- አይከብድም?
- ምንም የሚከብድ ነገር የለውም።
- የምትቃወማቸው ነገሮች ሲኖሩ ምንም አይሉህም?
- ለምን እቃወማለሁ?
- እንዴት?
- የምቃወመው ነገር የለማ።
- የተቃዋሚ ፓርቲ አመራር አይደለህ እንዴ?
- እሱማ ነኝ።
- ታዲያ እንዴት የምትቃወመው ነገር አይኖርም?
- አሁን የምቃወመው መንግሥትን ወይም ገዥውን ፓርቲ አይደለም።
- እና ማንን ነው የምትቃወመው?
- ተቃዋሚዎችን።
- አሃ… እንደዚያ ነው?
- እንደዚያ ባይሆንማ ይህን ያህል ጊዜ እንዴት ይቻላል?
- ምኑ?
- የካቢኔ አባል ሆኖ መቀጠሉ።
- እንደዚያ ነው?
- አዎ። አንተም እንደዚያ ነው ማድረግ ያለብህ።
- እና ታዲያ እኔ ማንን ልቃወም እችላለሁ?
- ያው የጀመርከውን ነዋ?
- ማንን?
- ጊዜያዊ አስተዳደሩን!
The post [ክቡር ሚኒስትሩ ከአማካሪያቸው ጋር የሥራ መልቀቂያ ስላቀረቡት ባለሥልጣን እየተወያዩ ነው] first appear on ሪፖርተር – Ethiopian Reporter – #1 reliable news source in Ethiopia and is written by በጋዜጣው ሪፓርተር