የትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደርን በአብላጫ ድምፅ በበላይነት የተቆጣጠረው ሕዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ሕወሓት) ለሁለት ከፍለው እየተወዛገቡ ያሉትን አመራሮች በማግባባት፣ ፖለቲካዊ ድርድር እንዲያደርጉ የማስቻል ዓላማን ያነገበ አደራዳሪ ቡድን ተዋቅሮ የዝግጅት ሥራዎችን ጀመረ፡፡
የትግራይ ሕዝብ ዲፕሎማሲ፣ የገርዓልታ የፖሊሲ ጥናትና ሥልጠና ኢንስቲትዩት፣ የትግራይ የንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት፣ የትግራይ የሲቪል ማኅበረሰብ ተቋማት ኅብረትን ጨምሮ ሰባት የተለያዩ ተቋማት የተውጣጡና የሃይማኖት አባቶችን ያካተተው ቡድን ለሁለት ተከፍሎ እየተወዛገበ የሚገኘውን በሊቀመንበሩ ደብረ ጽዮን ገብረ ሚካኤል (ዶ/ር) እና በጊዜያዊ አስተዳደሩ ፕሬዚዳንት አቶ ጌታቸው ረዳ የሚመራውን ክንፍ በማደራደር ለማስማማት እንቅስቃሴዎችን መጀመሩን የሪፖርተር ምንጮች አስረድተዋል።
በአደራዳሪ ቡድን ውስጥ ከተካተቱት በሕወሓትና በፌዴራል መንግሥት መካከል በተፈጸመው የፕሪቶሪያ ስምምነት ሕወሓትን በወከለው ቡድን በኩል ከተደራዳሪዎች አንዱ የነበሩት ወንድሙ አሳምነው (አምባሳደር)፣ የመቀሌ ዩኒቨርሲቲ የመጀመሪያ ፕሬዚዳንት ምትኩ ኃይሌ (ፕሮፌሰር)፣ እንዲሁም በትግራይ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን የመቀሌ ሊቀ ጳጳስ አባ ጥዑም በርሄ እንደሚገኙበት ለማረጋገጥ ተችሏል።
ጉዳዩን አስመልክቶ ሪፖርተር ያነጋገራቸው ወንድሙ (አምባሳደር)፣ ቡድኑ መቋቋሙንና ለማደራደር የሚያስችሉትን የዝግጅት ሥራዎች እያከናወነ እንደሆነ አረጋግጠዋል፡፡
የቡድኑ መግለጫ በመግቢያው ባለፈው አንድ ዓመት ወደ አደባባይ የወጣው የፖለቲካ ልዩነት፣ የሕወሓት አመራሮችን እያወዛገበና እየተስፋፋ በሕዝቡ ሰላምና ደኅንነት ላይ አደጋ ወደ መሆን መሸጋገር መጀመሩን አስታውቋል፡፡
የትግራይ ሠራዊት አመራሮች፣ የሃይማኖት ተቋማት፣ የሲቪክና የንግድ ተቋማትና ማኅበራት የተፈጠረውን ችግር በቀጥታ ወይም በሦስተኛ ወገን በኩል ለመፍታት ያደረጉት ያላሳለሰ ጥረት እንዳልተሳካም ይገልጻል።
የመግለጫው ሰነድ፣ ‹‹በዚህ ወቅት አመራራችን በድርጅቱ እጅ ተወስኖ የነበረውን እሰጥ አገባ ወደ መንግሥታዊ ሥልጣን ሽኩቻ ተሸጋግሮ፣ የትግራይ ሕዝብ ሰላምና ደኅንነት ወደ ከፋ አደጋ ላይ ወድቋል፤›› ይላል፡፡
‹‹በዚህ ጊዜ እየታየ ያለው የመጠፋፋት መንፈስና ተግባር ካላቆመ ወደ የማይመለስበት የህልውና አደጋ ሊደርስ እንደሚችል ግልጽ ነው፤›› በማለት ነበር እየተጋጋለ የመጣውን የሕወሓት ውዝግብ መግለጫው ያብራራው፡፡
‹‹በፖለቲካ አመራሮች መካከል ተፈጥሮ ያለውን አለመግባባት ለመፍታት ስናደርገው የነበረውን ጥረት ከሚመለከታቸው ሁሉም ተዋንያን ጋር በጋራ በመሆን አጠናክረን ለመቀጠል እንደወሰንን እያሳወቅን፣ የፖለቲካ አመራሮች የትግራይን ጥቅም ለማስቀደም፣ ፖለቲካዊ ልዩነታቸውን ሰላማዊና ሥልጡን በሆነ መንገድ ለመፍታት ዝግጁ እንዲሆኑ፤›› በማለት ቡድኑ በመግለጫው ጥሪ አቅርቧል።
መሬት ላይ ያለውን ችግር ለመቅረፍና የትግራይን ቀጣይ አቅጣጫ የመወሰን ጉዳይ የፖለቲካ ኃይሎች ጋር ብቻ መቅረት የለበትም ከሚል ሐሳብ በመነሳት፣ በችግሮች ላይ የተመሠረተ የትግራይ ቀጣይ አቅጣጫ ምን መምሰል እንዳለበት መክሮና ፈትሾ ሁሉን አቃፊ የፖለቲካ ሥርዓት ለማበጀት የሚያስችል ሐሳብ የሚቀርብበት፣ ሁሉም የማኅበረሰብ ክፍል ማለትም የሲቪክ ማኅበረሰብ፣ የንግድ፣ የፖለቲካ ድርጅቶችና የትግራይ ሠራዊት የሚሳተፉበት አጠቃላይ የትግራይ ስብሰባ በአጭር ጊዜ ውስጥ ለመጥራት መወሰኑንም ገልጿል።
የቡድኑ መግለጫ፣ ‹‹የትግራይ ሠራዊት የተፈጠረውን የፖለቲካ ትኩሳትና ፍጥነት በማቀዝቀዝ፣ ፖለቲካዊ አለመግባባት በፖለቲካዊ መንገድ፣ በሰላማዊና ሕጋዊ በሆነ አግባብ ለመፍታት የሚያስችል ጠቃሚ የመፍትሔ አቅጣጫ ተግባራዊ መደረግ የሚቻልበት አማራጭ መሆኑን እናምናለን፤›› የሚል ሐሳብም አካቷል። የትግራይ ኃይሎች በአሁኑ ወቅት ክልሉ የገባበት የተወሳሰበ ፖለቲካዊ ችግር በፍጥነት መፍትሔ አግኝቶ፣ የትግራይ ፖለቲካ ወደ ነበረበት እንዲመለስ ማድረግ መቻሉ ላይ ያላቸውን እምነትም አፅንኦት ሰጥቶበታል፡፡
ለሁለት የተከፈለውን የሕወሓት አመራር አደራድሮ ለማስማማት እየሠራ ያለው ቡድን፣ በደብረ ጽዮን (ዶ/ር) የሚመራው ክንፍ ድርጅታዊ ጠቅላላ ጉባዔውን ማካሄዱን ተከትሎ የተፈጠረውን ውጥረት በመታዘብ የተዋቀረ መሆኑን ሪፖርተር ከምንጮች መረዳት ችሏል።